ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Sunday, December 26, 2021

የትግራይ ሕዝብ ከ3 ሺህ ዓመታት በላይ የሚያውቀው እና አብሮት የኖረውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ለ40 ዓመታት በሚያውቀው ህወሓት እንደማይቀየር የሚያስመሰክርበት ጊዜ አሁን ነው።


እውነት የት ነው ያለችው? የውሸት ፕሮፓጋንዳስ የትኛው ነው? ብሎ መመርመር ከሁሉም የትግራይ ተወላጅ የሚፈለግበት ጊዜ ላይ ነን። ይህ ጊዜ የትግራይ ተወላጆች ከመጪው ትውልድ ቀጣይ ሕይወት አንፃርም እውነቱን መርምረው ወሳኝ ወደሆነው ሀገር የማቅናት ሥራ የሚመጡበት ጊዜ አሁን ነው። 

እውነት ኢትዮጵያ ነች።ኢትዮጵያ ማለት ደግሞ ሁላችንም ነን።ኢትዮጵያን የማይል ትግራይን ይጠቅማል ብሎ ማሰብ ሞኝነት ነው።ህወሓት የትግራይን ሕዝብ በሦስት መንገዶች በመጠቀም የእርሱ ተገዢ እንዲሆን አድርጎታል።እነኝህ ሦስቱ መንገዶች - ስጋት በመንዛት፣ በማስፈራራት እና በመደለል ናቸው።

ስጋት  -

ሽብርተኛው ህወሓት በትግራይ ማኅበረሰብ መሃል ስጋት እንዲሰፍን አጥብቆ ይሰራል።ይሄውም ሌላው የኢትዮጵያ ክፍል በሙሉ በትግራይ ተወላጅ ላይ እንደተነሳ አድርጎ የውሸት ፕሮፓጋንዳ እስከ ቤተስብ ድረስ ይነዛል።ይህንን የውሸት ዘመቻ በመንዛት ህወሓት ብቻውን እንዳይቆም እና ትግርኛ ተናጋሪ በሙሉ አብሮት እንዲቆም ለማድረግ ይጥራል።ይህንን የስጋት ስሜት በመፍጠር የትግራይ ማኅበረሰብን በማስደንበር ከሕወሓት ስር እንዲወሸቅለት ለማድረግ ይሞክራል።

ማስፈራራት

ህወሓት በኢትዮጵያ ውስጥም ሆነ ከኢትዮጵያ ውጪ የሚኖረውን የትግራይ ማኅበረሰብ በቀጥታ እና በተዘዋዋሪ መልክ ሊያስፈራራው ይሞክራል።በቀጥታ አንድ ለአምስት ባደራጀው መዋቅር ውስጥ ያገተው ሕዝብ ከእገታው እንዳይወጣ በቀጥታ በራሱም ሆነ በቤተሰቡ ላይ ጥቃት እንደሚፈፀም ያስተነቅቃቸዋል። በመሆኑም ከህወሓት ውጭ የሆነ ወይንም ሕወሃትን የሚቃወም የትግራይ ተወላጅ ብቅ ሲል ማኅበራዊ የማሸማቀቅ ዘመቻ ከመክፈት ጀምሮ እስከ የግድያ ዛቻ እና ግድያ ሁሉ ይፈፅማል።ለእዚህም ጋዜጠኛ ሄርሜላ እና እናቷ ጥሩ ማሳያ ናቸው።ሄርሜላ እና ወላጅ እናቷ ላይ እየደረሰ ያለው ማስፈራራት ህወሓት በማሸበር  እውነትን የሚያግት ይመስለዋል።በማስፈራራትም ብዙዎች የትግራይ ማኅበረሰብ አባላት እውነቱን ተናግረው ማኅበረሰባቸውን ወደ ትክክለኛ መንገድ ከመምራት ይልቅ ግራ በተጋባ መንገድ መኖር በመምረጥ ለራሳቸው ጭንቀት አትርፈዋል። ከእዚህ ይልቅ የህወሓትን ማስፈራራት ሰብሮ እውነትን መናገር ነው የትግራይ ማኅበረሰብን ከጭንቀት አውጥቶ ትግራይን ከህወሓት የሽብር ቡድን ፈልቅቆ ማውጣት አስፈላጊ መሆኑን ማመን አለባቸው።

መደለል 

ሦስተኛ የሽብርተኛው ህወሓት የትግራይን ሕዝብ ለመሸበብ የሚጠቀምበት መንገድ መደለል ነው።መደለል በሁለት መንገድ ይጠቀምበታል። አንዱ በጥቅም እና የወደፊት ተስፋው ህወሓት ብቻ እንደሆነ እና ዛሬ የትግራይ ህዝብ መኖር የቻለው ህወሃት በመኖሯ ብቻ መሆኑን ለማሳመን ሲሞክር እፍረት አይሰማውም። በጥቅም መደለል በራሱ ብቻውን በጥቅም ላይ ብቻ የተመሰረተ አይደለም ከጥቅም ጋር አብሮ ማስፈራት አብሮ ውስጡ አለ። ድለላ የውሸት ተስፋም በውስጡ አለበት።ህወሃት እድሜውን ለማስረዘም የትግራይን ህዝብ የሚደልልበት ሌላው መንገድ የማያልቅ የውሸት ተስፋ መስጠት አንዱ መንገድ ነው። ሲሸነፍ እያሸነፈ እንደሆነ ህዝቡን ይደልለዋል።የትግራይን ወጣት አስፈጅቶ የህወሃት መሪዎች ልጆች ውጭ ሃገር በምቾት እየተማሩ እና እየኖሩ፣ ለትግራይ ህዝብ የሞቱት ልጆቹን ጉዳይ እንዳይጠይቅ አፍኖ በሌለ ተስፋ ውስጥ ለመክተት እና ለሌላ እልቂት ያዘጋጀዋል። 

አሁን የትግራይ ህዝብ ከሶስት ሺህ ዓመታት በላይ አብሮ ከኖረው የኢትዮጵያ ህዝብ ይልቅ የ40 ዓመታት የጎሳ ድርጅትን መስማቱን ማቆም ያለበት ጊዜ ነው።ሌላው ቀርቶ ባለፉት ሶስት ዓመታት ውስጥ ብቻ የሆነውን እውነት ተመልክቶ የኢትዮጵያን ህዝብ ከህወሃት መምረጥ የሚገባው ወሳኝ ጊዜ አሁን ነው። ባለፉት ሶስት ዓመታት በኢትዮጵያ የተከናወኑት የለውጥ ሂደቶች ከሁሉም በላይ ለትግራይ ህዝብ እጅግ መልካም መንገዶች የነበሩ ነገር ግን ህወሃት በራሱ ያመከናቸው መሆናቸውን በመምልከት የትግራይ ህዝብ ጠላት ህወሃት እንጂ የኢትዮጵያ ህዝብ አለመሆኑን በቀላሉ መረዳት ይቻላል።ለውጡ በራሱ በኢትዮጵያ ህዝብ የተነሳው በመከላከያ ላይ የተፈጸመው ጥቃት ተከትሎ መከላከያ መቀሌ ከመግባቱ በፊት የነበሩት ሁለት ዓመታት በኢትዮጵያ ህዝብም ሆነ መንግስት በኩል የነበሩት መልካም ሂደቶች ሁሉ ታሪክ ለመቼውም ቢሆን የሚያነሳው ጉዳይ ነው። መከላከያ መቀሌን ለቆ ከወጣ በኋላም የእርዳታ እህል ወደ ትግራይ እንዲገባ ከማድረግ ጀምሮ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ተገልጦ እንደነበረው አስፈላጊው የመሰረተ ልማት አገልግሎቶች እና የመብራት፣የስልክ አገልግሎቶች ሊቀጥሉ በነበረበት ሁኔታ እያለ ነው ህወሃት ወደ አማራ እና አፋር ህዝብ ላይ የዘመተው እና ለህሊና የሚከብድ ግፍ በሰላማዊው ህዝብ ላይ የፈጸመው።

የትግራይ ህዝብ ህወሃትን ከትግራይ ምድር በፍጥነት አለማስወጣቱ የሽብር ቡድኑ የትግራይን ህዝብ ከኢትዮጵያ ለመነጠል እና ለባዕዳን ለመሸጥ የመጨረሻ ሂደቱን እንዲሄድ ዕድል የሚሰጠው ነው።በመሆኑም ይህ ጊዜ በትግራይ ውስጥ ለሚኖረውም ሆነ በውጭ የሚኖረው ማኅበረሰብ ካለ ህወሓት መኖር እንደሚቻል፣ከህወሓት ጋር መኖር ሌላ መከራ ይዞ እንደሚመጣ አና ከአሁን በኃላ ያለው የህወሓት አውሬአዊ  አካሄድ ደግሞ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ለመነጠል የሚሄድበት እንደሚሆን መረዳት ይገባል።ሽብርተኛው ህወሓት በአማራ እና በአፋር ላይ የፈፀመው ግድያ፣አስገድዶ መድፈር እና ዘረፋ አንዱ እና ዋና ዓላማው የትግራይ ሕዝብን ከቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ የመለያያ ግንብ ለመፍጠር የተጠቀመበት ሰይጣናዊ መንገድ ነው።

በመሆኑም በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ለ27 ዓመታት የተፈፀመው ግፍ ሳይበቃ ባለፉት አምስት ወራት በአማራ እና አፋር ላይ  የደረሰው ጥፋት የኢትዮጵያ ሕዝብ ከትግራይ በተነሳ ወረራ መሆኑ እና የትግራይ ሕዝብ የሰጠው የተቃውሞ ምላሽ አለመኖሩ እና ህወሓትን አሁንም አቅፎ መቀመጡ ከባድ ቅሬታ ፈጥሯል።ቅሬታው ውሎ አድሮ የትግራይ ሕዝብ ከሦስት ሺህ ዓመት አብሮት የኖረውን የኢትዮጵያን ሕዝብ በ40 ዓመት እና ዘለቄታ በሌለው በኢትዮጵያ ሕዝብ መወገዱ በማይቀረው በህወሓት ሊቀይረው አይገባም።የትግራይ ሕዝብ እና ማኅበረሰብ በህወሓት ላይ አምርሮ መነሳት፣ማስወገድ እና ለተፈፀሙት ግፎች የኢትዮጵያን ሕዝብ የሚያለሳልስ ሃገራዊ የጋራ የይቅርታ እና የፈረሰውን መጠገን፣የተወሰደውን የመመለስ ተግባር ላይ ሕዝቡ በፍጥነት መመለስ አለበት።ይህ ተግባር ደግሞ ከባዶ የሚመጣ ሳይሆን ካለመጠባበቅ እያንዳንዱ የትግራይ ተወላጅ እንደ ግለሰብ እና ማኅበረሰብ በጋር ደግሞ እንደህዝብ ተነስተው ህወሃትን ከትግራይ ምድር ለመንቀል ሲነሱ ብቻ ነው።ይህ የመነሻው ጊዜ ደግሞ አሁን ነው። 

ቪድዮ =የጋዜጠኞቹ አርአያ ተስፋ ማርያም እና አበበች ካህሳይ ቆይታ በምርኮኞች ካምፕ 

ከኢቢሲ የተገኘ  



No comments: