ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, January 29, 2020

የጎሳቸውን የበላይነት ለማረጋገጥ ከሚሮጡ እና ስልታዊ የእርስ በርስ መመጋገብ ከሚያሳዩት የዓማራ፣የኦሮሞ እና የትግራይ የፅንፍ ኃይሎች ኢትዮጵያን እንታደጋት!

ኢትዮጵያውያን እጃችንን በእጃችን እንዳንቆርጥ ልንጠነቀቅ ይገባል።

ጉዳያችን/ Gudayachn
ጥር 20/2012 ዓም (ጃንዋሪ 29/2020 ዓም)

በኢትዮጵያ የፖለቲካ መስመር ዙርያ ግርግር ለመፍጠር ሲሞከር ይታያል።ግርግር ለመፍጠር የሚሞክሩት ደግሞ የዳበረ የፖለቲካ ዕውቀትም ሆነ ቅንነት የራቃቸው ሁሉ  መሆናቸው ነው አስቀያሚው መልኩ።መጪው የፖለቲካ መድረክ በብቸኝነት ለመቆጣጠር የሚደረግ ሩጫ ማዕከላዊ መንግስትን ሳይቀር ሥራ አላሰራ የሚል ጉዳይ ነው።አጀንዳዎች በየቀኑ የፈለፈላሉ፣የዋሁን ሕዝብ ለመቀስቀስ ይሞከራል።የመጨረሻ ግቡ ግን ጥቂቶች በጀርባ የሸረቡትን ሴራ ወደ መሃል አምጥቶ የእራሱን ጎሳ የበላይ የሚሆንበት መንገድ ላይ ብቻ የማውጠንጠን ብቸኛ ግብ ያለው እኩይ ሥራ ሆኖ ይታያል።የጎሳ ፖለቲከኞች  ይህንን ፖለቲካቸውን የሚጠቀሙት ለስልት እስከ ቤተ መንግስት መግቢያ ድረስ ብቻ እንጂ፣አይደለም ጎሳቸውን የራሳቸውን ቤተሰብ በስልጣን ከመጣባቸው  በጎሳቸው ስም እየፎከሩ ከማረድ የማይመለሱ ለመሆናቸው ብዙ ሺህ ጊዜ ቢነገርም የገባው ያለ አይመስልም።

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ የፖለቲካ ግርግር ለመፍጠር የሚሞክሩ ሁሉ ዋና ግባቸው የግላቸው የስልጣን  ጥም እና ሀብት የማካበት ብቻ እና ብቻ ግብ ነው። ከእዚህ ውጪ አንዳች ነገር አይፈይዱም።ለእዚህ ደግሞ ማስረጃው በዓለማችን ጎሳቸውን እና የዘር ሃረጋቸውን እየመዘዙ ዓለምን በደም የዘፈቁት የእነናዚ እና ፋሺሽትን ታሪክ መመልከት ነው።ሁሉም ሲነሱ ለስልትነት እና ወደ የሚለኩሱት  ጦርነት የሚገባ ሕዝብ ለማግኘት በጎሳ ስም ጠሩት።ቀጥለው ግን  በስሙ ወጥተው ቆልቁል ማየት ከጀመሩ በኃላ  መልሰው ያረዱት የራሳቸው ጎሳችን ያሉትን ነው።

በመጀመርያ ደረጃ በትክክለኛ  ለሕዝብ ቆምያለሁ የሚል ፖለቲካ እና ፖለቲከኛ የሚነሳው  በውስጡ ከሚፈጠር የጠነከረ ህዝብን የመውደድ ፍቅር ነው። ይህ ፍቅር እና ለሕዝብ አብዝቶ የማሰብ ሰውነት የታደለ ሰው ደግሞ ሊያስብ የሚገባው ቢያንስ እንደ አገር ከሚኖርበት አገሬ ለሚለው ሕዝብ በሙሉ ሳይለያይ ሲሆን ከፍ ሲል ደግሞ ለሰው ዘር በሙሉ ነው። የእዚህ ዓይነት ሰውነት ሳይላበሱ ለመንደሬ ቆምያለሁ ሌላውን ደግሞ በመርገጥ የበላይ ስሆን የፖለቲካ ትግሉ በድል ተደመደመ ማለት ነው ብለው የሚያስቡ ደካሞች የመጨረሻ መጨረሻ እንደሌለው አለማወቃቸው በራሱ አስገራሚ ነው።

የኢትዮጵይ የፖለቲካ ሜዳ ለማጥለቅለቅ የሚፈልጉ  የጎሳ አቀንቃኞች ሁሉ ስለ ጎሳ እኩልነት ሳይሆን የእነርሱ ጎሳ የበላይ ሲሆን ኢትዮጵያ ሰላም እንደምትሆን ይሰብኩናል። እነርሱ ልቦና ውስጥ የበቀለው  የጎሳ አስተሳሰብ እንዴት በሌላው ላይ እንደሚሰርፅ ሲያወጡ እና ሲያወርዱ መሽቶ ይነጋል።በኢትዮጵያ የአንዱ ጎሳ ሰው ተነስቶ አንዱን ሲበድል ሊታይ ይችላል።ብዙዎችም ይህ ደርሶባቸዋል። ላለፉት 27 ዓመታትም ይህ አይኑን አፍጥጦ ታይቷል።ችግሩ አለ።አሁንም በብሮክራሲ ደረጃ የፅንፍ ጎሰኞች በመግባታቸው ይታያል። ይህ ማለት ግን አጠቃላይ የአንድ ጎሳ ሕዝብ ሁሉ አስተሳሰብ አይደለም። ይህ ችግር ደግሞ የሚፈታው ለችግሩ ተቃራኒ የአብሮነት ፖለቲካ በማራመድ እንጂ ተመሳሳይ የጥላቻ ፖለቲካ በማራመድ አይፈታም። 

ብዙ ሰው  የበለጠ ተበደልኩ ባይ ነው።ብዙ ሰው ወደ መሃል መጥቶ የኢትዮጵያዊነት ፖለቲካ ውጪ መጨራረስ እንደሆነ የመረዳት አቅሙ ደክሟል። ስለሆነም የጎሳውን የበላይነት በማረጋገጥ ብቻ የኢትዮጵያን ሰላም የሚያመጣ ይመስለዋል።ከመቶ ዓመት በላይ ያሳለፈው  የፈረንሳይ አብዮት ያነሳቸው መሰረታዊ የሰው ልጅ ጥያቄዎች ውስጥ  -እኩልነት የሚለው አስተሳሰብ ተንቆ የእኔ ጎሳ የበላይ እንዲሆን መታገል አለብኝ በሚል አስተሳሰብ የዓማራ፣የኦሮሞ እና የትግራይ የጎሳ ፖለቲካ አራማጅ ፅንፈኞች  በየፊናቸው ማዕከላዊ መንግስት ውስጥ ኢትዮጵያዊነት ወደ መሃል ይምጣ እና በርሱ መመራት አለብን የሚለውን የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይን አስተሳሰብም ሆነ የኢትዮጵያ አንድነት ኃይሎች ላይ ዘመቻ መክፈት የዘመኑ ፋሽን ሆኗል። ይህንን የሚያደርጉ አካላት ያልተረዱት ጉዳያ ቢኖር የጎሳ ፖለቲካ ከእዚህ በላይ ከተለጠጠ እሳቱ ማቆምያ እንደሌለው ነው።ለነገሩ እሳቱ ሲነሳ እነርሱ ለክረምት ሽርሽር አውሮፓ እና አሜሪካ ናቸው።

 የእነኝህ የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች አስገራሚው ጉዳይ ደግሞ በኢትዮጵያ የሚፈጠር አንድ ግርግር በጋራ ለመፍጠር ስልታዊ መመጋገብ ማሳየታቸው ነው።ሁሉም ተነስተው ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይን ወይንም በኢትዮጵያ ጉዳይ የአንድነት ፖለቲካ የሚያራምዱት ላይ ዘመቻ ለመክፈት የሚፈጥሩት ግንባር ነው።በእዚህም የተለያዩ አጀንዳዎች በመፈልፈል እና ያንን በማራገብ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይን ሆነ የኢትዮጵያ አንድነት የምያገነቅኑ ኃይሎችን ሥራ እንዳይሰሩ ማወክ ነው።የማዋከቡን ሥራ ደግሞ በማድረግ ረብ የለሽ የህዝብ ጆሮ ለመሳብ ይጠቀሙበታል።በእዚህም ዋና ግባቸውን ከህዝብ ደብቀው ጉዳያቸው ፊት ለፊት የሚታየውን  ወቅታዊ አጀንዳ ላይ የእነርሱ ወገን የሚጠቅምበት የፖለቲካ አጀንዳ ሽምያ ላይ በየሚድያቸው ሲያራግቡ መዋል  ስራቸው ሆኗል።በእዚህም ህዝብን ከመንግስት ጋር ማጣላት፣በመንግስት ውስጥ የተሰገሰጉ የእነርሱ የጎሳ ፖለቲካ አራማጆችን ሽፋን መስጠት እና የኢትዮጵያ አንድነት እንዲጠበቅ እና ከጎሳ ፖለቲካ የፀዳ አስተሳሰብ የያዙትን በምያነሱት አጀንዳ እያስታከኩ  መምታት ስራቸው ሆኗል። ይህንን እኩይ ተግባር የኢትዮጵያ ሕዝብ ሊያውቀው ይገባል። ግርግር ለሌባ ይመቻል እንዲሉ ሁል ጊዜ ግርግር በመፍጠር የህዝብ ስነ ልቦና እንዳይረጋጋ ማድረግ አንዱ እና ተቀዳሚ ስራቸው ሆኗል።

ለማጠቃለል ወቅቱ የሰከነ አስተሳሰብ፣የኢትዮጵያን መጪ ዕድል ለማጨለም የሚንቀሳቀሰውን በዓማራ፣በኦሮሞ እና በትግራይ ውስጥ የሚታየውን  የእኔ ጎሳ የበላይ ይሁን መሰል እንቅስቃሴ በአንክሮ መመልከት የሚገባበት ጊዜ ነው።በመሰረቱ የጎሳ ፖለቲካ የዲሞክራሲ ፀር ነው ።የጎሳ ፖለቲካ ምክንያታዊነት የሌለው እንደ ጋሪ ፈረስ በአንድ እና ብቸኛ አስተሳሰብ በሆነው የእኔ ጎሳ ከሆነ ፃድቅ፣የእገሌ ከሆነ ኃጢአተኛ እያለ የመፈረጅ፣የማሰብ፣የመመራመር እና የምክንያታዊነት ድሃ አስተሳሰብ ነው። ይህ አስተሳሰብ በልምምጥ እና በማግባባት ብቻ የማይገፋበት ጊዜ ላይ ተደርሷል። ማምረር፣መቃወም እና መታገል ያስፈልጋል።ይህንን የምቃወመው፣የሚታገለው እና የሚጠላው ደግሞ አብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። ኢትዮጵያን ያኖራትም ይህ የአብዛኛው ሕዝብ ፖለቲካ የአንዱ በአንዱ ላይ የመጫን ሳይሆን የእኩልነት ጥያቄ ስለሆነ ነው። ይህ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ግን ግራ የተጋባ እስኪመስል ድረስ ዝምታው አስጠቅቶታል። በዓማራ፣ኦሮሞ እና ትግራይ ውስጥ የመሸጉ የጎሳቸውን የበላይነት በማረጋገጥ ኢትዮጵያን እናሳድጋለን ለሚሉ በሙሉ የምንላቸው አንድ ነገር ብቻ ነው። ይሄውም እባካችሁ ኢትዮጵያ እጇን በእጇ እንድትቆርጥ አታድርጉ።ለእኩልነት እንጂ የጎሳችሁ የበላይነት እንዲሰራ በመስበክ አታደንቁሩን። ኢትዮጵያ የሁሉም እንድትሆን የሚሰሩ ኢንጂ   የጎሳቸው የበላይነት እንዲኖር ለሚሰብኩን የትኛውም ዓይነት አደረጃጀች አዎንታዊ ምላሽ መስጠት እጅን በእጅ ከመቁረጥ አይለይም።


የጥቁር  አልማዝ በጃኖ ባንድ 





ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Saturday, January 25, 2020

''ኢሳት የኢትዮጵያ ዓይንና ጆሮ ብቻ አይደለም።ሐኪም ቤትም፣ፍትሕ ላጣውም እንደ ፍርድቤትም ሁሉ ነው ሕዝብ የሚያየው'' ኢሳት በሚሰጠው የሚድያ አገልግሎት ዙርያ ልዩ  የበዓል ዝግጅት ላይ የኢሳት ባለደረቦች  ከተናገሩት(ቪድዮ)

የኢትዮጵያ ሕዝብ ኢሳትን  የማጠናከር እና ወደ ዓለም አቀፍ ተፅኖ ፈጣሪ ሚድያነት የመቀየር ኃላፊነት የእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ነው።




ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Friday, January 24, 2020

መጪው ምርጫ፣ሃይማኖት፣ታሪክ፣ የጎሳ ፖለቲካ እና የመንግስት ቤተክርስቲያንን ለመታደግ በለገመበት ጉዳይ ዙርያ በማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቭዥን በእዚህ ሳምንት የተደረገ ልዩ ውይይት (ቪድዮ ክፍል አንድ እና ሁለት)

በእዚህ ውይይት የመጀመርያ ክፍሎች ላይ የሰላሌ የደብረ ሊባኖስ ጉዳይ የተነሳበት ጉዳይ በያዝነው የጥር ወር መጀመርያ ሳምንት ላይ የኦፈኮ የምርጫ ቅስቀሳ ሰበብ ጃዋር እና የኦሮምያ ቤተ ክህነት በሚል ለመክፈል የሚንቀሳቀሰው ዲ/ን ኃይለሚካኤል ሰላሌ እና ገብረጉራቻ ላይ  ሕዝብ ከህዝብ የሚያጋጭ ንግግር መነሻ ያደረገ ነው።
ክፍል አንድ  -ሀ 


ክፍል አንድ - ለ 

ክፍል ሁለት  


ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Thursday, January 23, 2020

ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ የሐረር ክልል አስተዳደር እና ፖሊስ ሆን ብለው ኦርቶዶክሳውያን ላይ ጥቃት እንዲፈፀም አድርገዋል በማለት ከሰሱ።ከአሁን በኃላ አንቆስልም ብለዋል። (ሙሉ መግለጫቸውን ለመከታተል ቪድዮውን ይመልከቱ)

ብፁዕ አቡነ መቃርዮስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል፣የሐረርጌ እና የሱማሌ ሃገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በዘንድሮ የጥምቀት በዓል ላይ የሐረር ክልል ፖሊስ እና የሐረር አስተዳደር ሆን ብሎ በኦርቶዶክሳውያን  ክርስቲያኖች  ላይ ለፈፀመው ተግባር እና የፀጥታ አለማስከበር ተግባር ተጠያቂ መሆኑን አስታውቀዋል።



ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Wednesday, January 22, 2020

Grand Ethiopian Renaissance Dam (GERD) Filling Scenarios: Analysis of Energy and Revenue losses

Photo - Ethiopian New dam on Nile (file)
ስንቶቻችን Ethiopian International Professional Support for Abay (EIPSA) እናውቀዋለን ? በእዚሁ ድረ ገፅ ላይ ኢትዮጵያውያን ምሁራን ዶ/ር በላቸው ተስፋ እና ዶ/ር ምንትዋብ በዛብህ (Dr. Belachew Tesfa and Dr Mintwab Bezabih) የፃፉት አዲስ አርቲክል ከእዚህ በታች ተያይዟል።
=========================================
The above titled article is taken from the Ethiopian International Professional Support for Abay (EIPSA). 
First of posting an article, Gudayachn would like to introduce you the professional support team. Here is the an introduction paragraph obtained from the Professional Support's page.
The Ethiopian International Professional Support for Abay (EIPSA) established on the 22, June 2013, in response to the timely need for an organized and independent professional Ethiopian voice surrounding the issue of the Nile River. The majority of the Nile River flow originates in Ethiopia and carried downstream by Blue Nile, while a much smaller portion comes from the White Nile. Both rivers meet in Khartoum to form the Nile. Despite its lion share contribution to the Nile River flow, Ethiopia has never benefited from its waters for a number of reasons. Therefore, the start of the construction of the Grand Ethiopian Renaissance Dam (GERD) virtually remains Ethiopia’s only effort in its attempt to make use of the Blue Nile waters.
================================
Grand Ethiopian Renaissance Dam (GERD) Filling Scenarios: Analysis of Energy and Revenue losses 
By Dr Mintwab Bezabih1 and Dr Belachew Tesfa
International Journal of Nile Basin (IJNB) Energy, Water, Environment & Economic Volume 3; Issue 5; December 2019, Page 1-11
To read the whole article, please click on the below link -
http://www.eipsa1.com/cms/articles/GrandEthiopianRenaissanceDam(GERD)FillingScenariosAnalysisOfEnergyBezabihandTesfa_Dec2019.pdf

ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Monday, January 20, 2020

የጥምቀት ብሔራዊ በዓላችንን ደስታ ለመንጠቅ የፈለጉ አልተሳካላቸውም። የስነ-ልቦና ዘመቻቸው ሙሉ በሙሉ ከሽፏል!



  • ሳትሰለፍ እና ሳትለፈልፍ ኢትዮጵያዊ የሞራል ልዕልናህን የምትሰቅልባቸው ቀላል መንገዶች በእዚህ ፅሁፍ ውስጥ ተካተዋል።ሕዝብ አንቂዎች ሃሳቡን ወስደው በግዙፍ መልክ ሊያንቀሳቅሱት ይገባል።


ጉዳያችን / Gudayachn
ጥር 11/2012 ዓም (ጃንዋሪ 20/2020 ዓም)

=============
የጥምቀት በዓል ባብዛኛው ተጠናቋል:: የቅደሰ ሚካኤል ታቦታት ግን ነገ ቃና ዘገሊላ በዓል ስለሆነ እስከ ቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ወደ መንበራቸው ይገባሉ::እነኝህ ታቦታት ደግሞ ሌላው ጋር ለማጀብ ሄዶ የነበረው ምዕመን በብዙ እጥፍ ሆኖ የሚያጅባቸው ታቦታት ናቸው።በዘንድሮው ጥምቀት ባብዛኛው በሚያስደስት መልኩ ተፈፅሟል::እንደ ሆሳዕና ያሉ ቦታዎች ችግር ለመፍጠር ሙከራ ተደርጎ ከሽፏል::ከእዚህ ተምረናል::
ሐረር ስርዓት አልበኞች ታቦታቱን ለማስቆም ሞክረዋል÷የክልሉ ፖሊስ ድርጊት ህዝብ አሳዝኗል÷ሰው ቆስሏል በእዚህ አዝነናል::ሁሉም በእምነቱ ለማይገፋባት ኢትዮጵያ የበለጠ መስራት እንደሚገባ ከምን ጊዜውም በላይ ግልጥ ሆኗል::

መንግስት በተቻለ ለጸጥታው መጠበቅ መድከሙ ይታወቃል::በክልል ደረጃ ያሉት የጸጥታም ሆነ የአመራሮች ዘገምተኛ እና የግል ፍላጎታቸውን በአመራር ስልጣናቸው ላይ ለመጫን ሲሞክሩ እና ችግር ሲፈጥሩ ታይተዋል።በአጠቃላይ መንግስት ያደረገው ዝግጅት ብቻ ሳይሆን የህዝቡ በተለይ የወጣቱ የትቀናጀ የመረጃ አሰራር ሁሉ በራሱ ይህ የጥምቀት በዓል አዲስ ምዕራፍ ከፍቷል።እያንዳንዱ የሚጠበቅበት ገብቶታል።ኃላፊነት ተሰምቶታል።ለአገሩ ሰላምም ሆነ ለሁሉም ዕምነት በእኩል አገሬ ብለው የሚኖሩባት ኢትዮጵያን ለማጠልሸት የሚፈልጉ ስርዓት አልበኞች ችግር ለመፍጠር መሞከራቸው በራሱ አስተማሪ ነው።

ጉዳዩ ስነ ልቦናዊ ጦርነት ነው 

በጥምቀት ሰሞን ከሆነው አንዱ የፕሮፌሰር መራራ ኦፌኮ ጀዋርን እና በኦሮምያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ለመከፋፈል የቤት ሥራ የተሰጠው ዲያቆን ኃይለ ሚካኤል የተባለ ግለሰብ በሰላሌ የምርጫ ቅስቀሳ በሚል ከከተራ አንድ ቀን ሲቀረው ጀዋርን ከጀርባው አቁሞ (ጀዋር በደስታ ሲፍነከነክ ይታያል)  የኦሮሞን ሕዝብ በራሱ የሚከፋፍል፣በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ግልጥ የሆነ ጦርነት አውጁአል።

በእዚሁ ንግግሩ ላይ የደብረ ሊባኖስን ገዳም ሳይቀር ቃል በቃል ጠቅሶ ''ሕዝብ ሰብሮ እንዲገባ'' መልዕክት አስተላልፏል።ከእዚህም በተጨማሪ ''ቤተክርስቲያን የፊውዳሎች  የፖለቲካ ኤምባሲ ነች'' በማለት  ሲናገር ተሰምቷል።እነኝህ የጥላ ንግግሮች የሚናቁ የጥላቻ ንግግሮች አይደሉም።ሆኖም ግን ዋና ግባቸው ስነ ልቦናዊ ጦርነት በኢትዮጵያውያን ላይ መክፈት ነው።የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ብሎም ለማጥፋት እንዲሁም ከሕዝቡ ጋር ለማጋጨት በብዙ ትውልዶች ተሞክሯል።ግን አልተቻለም።ባለመቻሉም ቅድምያ የስነ ልቦና ጦርነቱ ተመራጭ ሆኖ ለጥፋት ኃይሎች ታይቷቸዋል።በቅድምያ ግን የእዚህ አይነት የምርጫ ቅስቀሳ  እየሰሙ ዝም ያሉት የምርጫ ቦርድ፣  የማዕከላዊው መንግስት፣የኦሮምያ ክልል ባለሥልጣኖች፣ በኦፌኮ፣በጀዋር፣በዲያቆን ኃይለ ሚካኤልም ሆነ የጥላቻ ዘመቻ ባስተላለፉት የኦኤምኤን ሚድያ ላይ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ርምጃ ባለመውሰዳቸው በሕግ ያስጠይቃቸዋል።ይህ ጉዳይ ደግሞ በተከታይ በሚፈጠሩ ችግሮች ምርመራ ላይ መነሻው ወደኃላ ሲሄድ እንደ ኦፌኮ የምርጫ ዘመቻ ንግግሮች መሆናቸው ድምዳሜ ላይ ስለሚደረስ መቼም መቼም ከፍርድ ማምለጥ አይቻልም።ለእዚህ መፍትሄው በፍጥነት የማያዳግም ሕጋዊ ርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል።ርምጃው በመግለጫ ጋጋት የሚፈታ አይደለም።ተግባራዊ ሕጋዊ ርምጃ የመንግስት አካላት ማሳየት ግዴታቸው ነው።ይህ ካልሆነ አብረው ይጠየቃሉ።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን የስነ-ልቦና ዘመቻውን ግብ እና መነሻ በሚገባ ተረድቶ ዘመቻውን ሙሉ በሙሉ ማክሸፍ ነው ያለበት።የፅንፍ ኃይሎች ዋነኛ መለያቸው የበታችነት ስሜት መሰቃየታቸው ነው። ይህንን የበታችነት ስሜት ስቃይ የሚያስታግሱት ድሮ እንዲህ የሚባል ሰው እዚህ ቦታ አንድ ዛፍ ተክሎ ነበር አሉ እና የመሳሰሉ ታሪኮች እያነሱ አሁን ያለውን ሕዝብ የምያጋጩበት ታሪኮች በመተረክ ነው።በእዚህ አሁን ያለውን ሕዝብ ስነ-ልቦና ያሸበሩ እንደሆነ ያስባሉ።ያልተገነዘቡት ነገር ግን ይህ አካሄድ ሁለት ነገር ይዞ እንደሚመጣ ነው።አንድ፣ከምር የዛፉ ተካይ ታሪክ ሕዝብ ዛሬ አይጠቅም ብሎ ያሰበውን ታሪክ ይዞ የወጣ ቀን የፈሩት የበታችነት ስሜት በከፋ መልኩ እንደሚከሰት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ህዝቡ በበለጠ እርስ በርሱ እንዲከባበር እና የመርዘኞች አካሄድ አደጋ ከማምጣቱ በፊት እነርሱን ለማሳፈር እንደሚነሳ ነው።

ኢትዮጵያውያን ወደፊትም ሞራላዊ እና ስነልቦናዊ ልዕልናችሁን ስቀሉባቸው!

የዘንድሮ 2012 ዓም  የጥምቀት በዓል በብዙ የኢትዮጵያ ክፍሎች የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ከምንጊዜውም በላይ ደምቆ ወጥቶ በነፃነት ተከብሯል።ከጅጅጋ እስከ አርባንምጭ፣ከጋምቤላ እስከ መቀሌ፣ከሞያሌ እስከ ጉጂ ዞን፣ከሐዋሳ እስከ አሶሳ፣ከጎንደር እስከ ከሚሴ፣ከአዲስ አበባ እስከ ባሌ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ከታቦታቱ ጋር በድምቀት ታይቶ ተከብሯል።ይህ በእንዲህ እያለ የስነ ልቦና ጦርነቱን ለማድረግ ከፅንፈኛ ኃይሎች ድርጎ የለመዱ በአንዳንድ ቦታዎች በተለይ በአብዛኛው የኦሮምያ ክልል የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ሲያስወርዱ፣ሪባን ጭምር እንዳትይዙ በሚል ችግር ፈጥረዋል።ድርጊቱ የጥቂቶች ብቻ ሳይሆን በመንግስት የፀጥታ መዋቅር ውስጥ ያሉ ሁሉ የድርጊቱ ተሳታፊ ሆነዋል።ይህ በህጋዊ መልኩ ሲታይ የመንግስት ግልጥ ክስረት ያሳያል።በመጀመርያ ደረጃ ጉዳዩን በተራ የአስተሳሰብ ልክ ብናስበው  ግለሰብ በራሱ የፈለገውን  የቀለም ሕብር የመያዝ መብት አለው። ቤተክርስቲያን እንደ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ የተለየ መብት አላት።ለግለሰብ መከልከል የማትችለውን መብት ለተቁአም ልትከለክል አትችልም።የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ደግሞ የክርስቲያን ወይንም የሙስሊም አልያም የአይሁድ ዕምነት መለያ አይደለም።የክርስትናም፣የእስልምናም ሆነ የአይሁድ አባት በኖህ ዘመን ከሰማይ የተሰጠ በሁሉም የሰው ዘር እና በእግዚአብሔር መካከል የተገኘ ቃል ኪዳንን መነሻ ያደረገ ነው።ይህ ማንንም ሊያጣላ አይችልም።

በተግባር የሞራል ልዕልናው እንዲህ ይሰቀላል

በመቀጠል የልዕልናውን ደረጃ መስቀል ተገቢ ነው።እንዴት? ለሚለው 
የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ምንም ምልክት የሌለበት ሱቅ ምንም ዓይነት ግብይይት ባለማድረግ፣የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላም የሌለው ማንኛውም ምግብ ቤት ሳትቃወመው ከራስህ ጋር ተነጋግረህ ፈፅሞ ግብቶ አለመመገብ፣የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በትንሹም ቢሆን ሻጥ ያደረገች የጉልት ቸርቻሪም ብትሆን ደጋግሜ በመግዛት ስፈልግ የፈለኩትን ያህል ገንዘብ በመጨመር፣የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላም የማይታይበት የቴሌቭዥንም ሆነ የፖስተር ማስታወቂያ መንግስታውም  ቢሆን ፈፅሞ እንደማልቀበለው እና ባለመግዛት፣የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የማይታይበት ማናቸውም መጠጥም ሆነ የስነ ጥበብ ዝግጅት፣ልብስም ሆነ ማስቲካ ሳይቀር  አለመግዛት።ሳትሰለፍ እና ሳትለፈልፍ ኢትዮጵያዊ የሞራል ልዕልናህን የምትሰቅልባቸው ቀላል መንገዶች ከላይ የጠቀሱት እንደመነሻ ተነስተዋል።ወደፊትም በበለጠ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በገነት እና በሲኦል ሳይቀር ቅዱሳኑም ሆኑ ርኩሳኑ መናፍስት እስክገርማቸው ድረስ አብዝተህ አሰራጨው።ማንም ከፈለገ ከሲኦል ወይንም ከገነት ውጪ ዓለም ካለ ወደዚያ  የመሄድ መብቱን እናከብርለታለን።


ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

ከሁለት ሚልዮን በላይ እንግዳ የታደመበት  የ2012 ዓም ጥምቀት በዓል አከባበር  በጎደር የቀጥታ ሙሉ ስርጭት ቪድዮ

ከዓማራ መገናኛ ብዙሃን የተወሰደ


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Sunday, January 19, 2020

Saturday, January 18, 2020

በኢትዮጵያ የ2012 ዓም የጥምቀት በዓል አከባበር ዝግጅት ብዙ ነገሮች አመላካች ሆኗል።ዝግጅቱ በኦሮምያ ፣ሆሳዕና ፣አርባምንጭ፣አዲስ አበባ፣ ጎንደር ምን ይመስላል? (ፎቶዎች ይመልከቱ)

ጉዳያችን ዜና /Gudayachn News
ጥር 9/2012 ዓም (ጃንዋሪ 18/2020 ዓም)

በኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል ከእሁድ ጥር 10 ጀምሮ እስከ ጥር 12 ድረስ ይከበራል።በዓሉ በኢትዮጵያ የተለያዩ ክልሎች የተላያዩ መልክ ይዟል።የበዓሉ አከባበር በራሱ የብዙ ነገሮች አመላካች ሆኗል።

- በኦሮምያ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ከሪባን ጀምሮ ተከልክሎ ሕግ የሚያስከብር ጠፍቷል።ሻሸመኔ ዋና ማሳያ ሆናለች።በኦሮምያ ያሉ የክልሉ ተወላጆች የክልሉ የፀጥታ ኃይል ከፍተኛ በደል እየፈፀመባቸው ነው የሚናገሩት።በውጭ አገር ኢትዮጵያውያን የቤተ ክርስቲያኒቱን ዓርማ መስቀል ያልተከለከሉትን በአገራችን ተከለከልን የሚል ምሬት ይሰማል።ጉዳዩ በኦሮምያ የሕግ መጥፋት አመላካች ሆኗል።አብዲሳ አጋ፣ጃጋማ ኬሎ እና ብዙ ሚልዮኖች የሞቱላት የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ዛሬ በኦሮምያ ጥምቀት በዓል ላይ እንዳይታይ መደረጉ የክልሉ አስተዳደር ከፅንፍ ኃይሎች ጋር እየሰራ ለመሆኑን ማሳያ ነው የሚሉ በርካታ የኦሮምያ ክልል ነዋሪዎች አሉ።

- ሰሜን ሸዋ ፍቼ ዛሬ ረፋዱ ላይ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ መስቀል የተከለከሉ ወጣቶች ተፋጠዋል።በጣልያን ሰማዕትነት የተቀበሉት የአቡነ ጴጥሮስ አገር ፍቼ ሰንደቅ ዓላማ መስቀል ተከልክላ ከተማው ውጥረት ላይ ነች የሚለው ዜና በራሱ የክልሉ አደገኛ አካሄድ አመላካች ነው።

- በሆሳዕና ህዝቡ ለረጅም ጊዜ የጥምቀት በዓል ማክበርያ ቦታ ጠይቆ የከተማው አስተዳደር ከልክሎት እስከ ደቡብ ክልል ድረስ አቤት ብሎ  ክልሉ 20ሺህ ካሬ ፈቅዶ ለሆሳዕና ከተማ ምክርቤት ደብዳቤ ከፃፈ ሳምንት ቢሆነውም እስከ ትናንት ምሽት ድረስ ኮሚቴው  ቢጠብቅም የከተማው ምክርቤት ጉዳዩን በመከልከሉ የአገረ ስብከቱ ዘንድሮ በሆሳእና ጥምቀት አለመኖሩን በሃዘን ገልጦ ደብዳቤ አውጥቷል።ጉዳዩ ከፍተኛ ውጥረት ፈጥሯል።በመላው ኢትዮጵያ የሚኖሩ  በየትኛውም ቦታ ጥምቀት የሚያከብሩ ሆሳዕናን እንዲያስቡ በማኅበራዊ ሚድያ ጥሪ እየተላለፈ ነው።

-  በጎንደር ከሰላሳ ሺህ በላይ የውጭ ሀገር ዜጎች ጨምሮ እስከ ሁለት ሚልዮን ሕዝብ ለበዓሉ እንደምታደም ተገልጧል።በተለይ የጎብኚው ቁጥር እስከ ሁለት ሚልዮን እንደሚደርስ የዘገበው የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የከተማዋን  ባለስልጣናት ጠቅሶ ነው።

- በአርባምንጭ፣አዲስ አበባ እና ጋምቤላን ጨምሮ በዓሉ በደመቀ ሁኔታ ሊከበር ከፍተኛ ዝግጅት ላይ ነው።
ከእዚህ በታች ያሉት ፎቶዎች ለታሪክ የሚቀመጡ ናቸው።


ሻሸመኔ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ያለው ሪባን ተከልክሎ ህዝቡ ይህንን እንዲሰቅል ተገዷል።
የሆሳዕና ምእመናን የጥምቀት በዓል ማክበርያ ቦታ ተከልክለው በሃዘን ተቀምጠው።

 አዲስ አበባ ጎዳናዎች እንዲህ ደምቀዋል ቻይናውያን ሳይቀሩ 
 አርባምንጭ በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ 
 አዲስ አበባ ተክለሃይማኖት አካባቢ 
 ጋምቤላ ዛሬ 
 ጋሞዎች ጥምቀት ለማክበር ጎንደር ቀርበዋል። 
 ጋሞዎች ለጥምቀት በዓል  ወደ ጎንደር ሲገቡ 
 የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የሚልዮኖች ሰማዕታት ውጤት ጎንደር ላይ እንዲህ በእናቶች ተስማለች።
 ጎንደር ለጥምቀት በዓል ዝግጅት ሙስሊም ወገኖቻችን ከክርስቲያኖች ጎን አብረው ሥራ ላይ 

 አዲስ አበባ ተክለሃይማኖት አደባብይ ላይ የተሰራው የታቦት ማደርያ በወጣቶች የተሰራ 
  አዲስ አበባ ተክለሃይማኖት አደባብይ ላይ የተሰራው የታቦት ማደርያ በወጣቶች የተሰራው በምሽት ይህን ይመስላል።
 አዲስ አበባ ተክለሃይማኖት አደባብይ ላይ የተሰራው የታቦት ማደርያ በወጣቶች በሥራ ላይ እያለ 


ጉዳያችን GUDAYACHN

 www.gudayachn.com

Thursday, January 16, 2020

የሰሞኑ የዋሽንግተኑ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ድርድር በጥሩ ሁኔታ መፈፀሙን የሶስቱም አገሮች ልዑካን አስታወቁ።Ethiopia,Egypt and Sudan officials say they have reached a preliminary agreement on Ethiopian Renaissance Dam negotiation in Washington D.C

ሰባ በመቶ የተጠናቀቀው የታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ  

ጉዳያችን ዜና /Gudayachn News
ጥር 7/2012 ዓም (ጃንዋሪ 16/2020 ዓም)

በዋሽንግተን ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በታላቁ ህዳሴ ግድብ ዙርያ በኢትዮጵያ፣ግብፅ እና ሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች እና የውሃ ሚኒስትሮች መካከል ሲደረግ የነበረው ድርድር በጥሩ ሁኔታ ማለቁን የሶስቱም አገሮች ልዑካን በሰጡት የጋራ መግለጫ አስታውቀዋል።በድርድሩ ላይ የአሜሪካ የገንዘብ ሚኒስትር ስቴቨን ምንቺን እና የዓለም ባንክ ፕሬዝዳንት ዴቪድ ማልፓስ ተገኝተዋል።

የግድቡ ሥራ 70% መጠናቀቁ የተነገረው የታላቁ የአባይ ግድብ አወዛግቦ የነበረው ግብፆች ባነሱት የውሃው የመሙላት ጊዜ ላይ እና የድርቅ ወቅት በሚለው ትርጉም ላይ ነበር።በእዚህ መሰረት በአሁኑ ስምምነት ኢትዮጵያ በጠየቀችው መሰረት የግድቡ መሙያ ጊዜ ድረጃ በደረጃ የሚፈፀም ሆኖ በዋናው የኢትዮጵያ የዝናብ ወቅት ማለትም ከሐምሌ እስከ ነሐሴ ሆኖ እንደአስፈላጊነቱ መስከረምን ሊሻገር እንደሚችል ተስማምተዋል። የድርቅ ወቅት የሚለውን ትርጉም እና በእነኝህ ወቅት የሚወሰዱት ርምጃዎች በተመለከተ ሶስቱም አገሮች በሰጡት መግለጫ የድርቅ ወቅት  በተመለከተ በሶስቱም አገሮች በጋራ የሚወሰድ የጋራ ኃላፊነት እንደሚሆን እና የድርቅ ጊዜውን እንዴት እንደሚይዙት  እና እንደሚወጡት በጋራ ገምግመው እርምጃ የሚወሰድ እንደሆነ ነው የተነገረው።ይህንን አስመልክቶ የሶስቱ አገራት ልዑካን በሰጡት መግለጫ ላይ -

''ተደጋጋሚ ድርቅን እና ጊዚያዊ ድርቅን በተመለከተ አያይዙን ሶስቱም አገሮች በጋራ ኃላፊነት ይወስዳሉ'' 
''There is a shared responsibility of the three countries in managing drought and prolonged drought,''

የጋራ መግለጫው እንደገለጠው ይህ የአሁኑ መግባባት ግድቡን በተመለከተ የመጨረሻ ስምምነት ሳይሆን በቀሪ ነጥቦች ላይ ውይይቱ ዋሽንግተን ላይ ጃንዋሪ 28-29/2020 ዓም እኤአ እንደሚቀጥል ተነግሯል።

በሌላ በኩል የውሃ፣መስኖ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢ/ር ስለሺ በቀለ በትውተር ገፃቸው በእንግሊዝኛ ባሰፈሩት ፅሁፍ 

''የታላቁ የህዳሴ ግድብ በተመለከተ አስፈላጊ እና ወሳኝ ውጤት አግኝተናል።ከጎናችን የቆማችሁ ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች በሙሉ እናመሰግናለን።በድርድሩ ያገኘነውን ውጤት ወደ ሕጋዊ ሰነድ እና መመርያዎች ይቀየራሉ'' ብለዋል።


ጉዳያችን GUDAYACHN

 www.gudayachn.com

Monday, January 13, 2020

ጉዳያችንን በቀላሉ በቴሌግራም ይቀላቀሉ።

በርካታ አጫጭር ዜናዎች፣ማስታወቂያዎች በኖርዌይ፣ስቃንዲንቭያ፣በአገር ቤት እና በሌላው ዓለም የተከናወኑ ጉዳዮች ያገኛሉ።
Add Gudayachn on Telegram.

ይህንን ይጫኑ = t.me/gudayachn 

ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Saturday, January 11, 2020

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በኤኤንሲ 108ኛ ዓመት ክብረ በዓል ላይ በደቡብ አፍሪካ ያደረጉት ንግግር Ethiopian Prime Minister Abiy Ahmed's speech on 108th anniversary of African National Congress (ANC)

 January 11/2020  
Video = South African Broadcasting Corporation (SABC) News


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

በኢትዮጵያ በደንቢ ዶሎና ጋምቤላ መሃል የታገቱት 13 ሴት እና 4 ወንድ የደንቢ ዶሎ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች ጉዳይ ብሔራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ትኩረት ተነፍጎታል።


ጉዳያችን /Gudayachn
ጥር 2/2012 ዓም (ጃንዋሪ 11/2020 ዓም) 

  • በምዕራብ ወለጋ፣ መንግስት ከሸማቂዎች  ጋር ግልጥ ጦርነት ላይ ነው። መንግስት በእዚሁ አካባቢ በሚያደርገው ሽፍቶችን የማጥራት ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል።በቅርቡ ሁሉም ነገር ወደነበረበት ሰላማዊ ሁኔታ ይመለሳል። ለእዚህም በሽፍቶቹ የተጎዳው ሕዝብ ከፍተኛ ትብብር እያደረገልን ነው - አቶ ታዬ ደንዳበኦሮምያ የብልፅግና ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ

ከሳምንታት በፊት በምዕራብ ኢትዮጵያ በኦሮምያ ክልል የምትገኘው የደንቢ ዶሎ ዩንቨርስቲ ተማሪዎች በዩንቨርስቲው በተነሳ ግጭት ሳቢያ ተማሪው በራሱ ወደ ትውልድ ቀዬው ለመሄድ ሲነሳ የተወሰኑ የዓማራ ክልል ተማሪዎች ወደ አዲስ አበባ የሚወስደው መንገድ በመዘጋቱ በጋምቤላ በኩል አድርገው ለመምጣት በትራንስፖርት ተሳፍረው ጉዞ ይጀምራሉ።ሆኖም ያሰቡት ሳይደርሱ ደምቢ ዶሎ እና ጋምቤላ መካከል 'ሱድ' የምትባል ቦታ ሲደርሱ ጎረምሶች መኪናውን አስቁመው 18 ተማሪዎችን ማለትም 14 ሴቶች እና 4 ወንዶችን አግተው ወደ ጫካ ይገባሉ።ከእነኝህ ውስጥ ተማሪ አስምራ ሹሜ የተባለችው ወጣት በድንገት አምልጣ በብዙ ፈተና እና መከራ በአሁኑ ጊዜ አዲስ ዘመን ከተማ ከቤተሰቦቿ ጋር ተቀላቅላለች።

ተማሪ አስምራ ሹሜ ለቢቢሲ በሰጠችው ቃል እንዲህ ብላለች -

''አካባቢው ጥቅጥቅ ያለ ጫካ በመሆኑ በእርሱ ውስጥ ይዘውን ገቡ። ይዘውን ሲሄዱ በአካባቢው የነበሩ ሰዎች ከማየት ውጭ ለማስጣል የሞከረ አልነበረም።እየጮህን ነው ይዘውን የሄዱት። የጫካውን ግማሽ እንደተራመድን የተወሰኑት ሴቶች መራመድ አቃታቸውና ወደቁ። ታዲያ እነርሱን 'ተነሱ፤ አትነሱ' እያሉ ለማንሳት ሲሞክሩ ነበር እኔ ከአይናቸው የተሰወርኩት።በጫካው ውስጥ ለሁለት ቀናት ያህል ካደርኩ በኋላ፤ በሦስተኛው ቀን ወደ ዋናው የመኪና መስመር መውጣት ቻልኩ። ግራ ተጋባሁ፤ ስልኬን ስለወሰዱት ስልክ መደወል አልቻልኩም፤ ምንም ማድረግ አልቻልኩም ነበር።እንደምንም ብዬ ወደ መስመር ስወጣ አንድ አማርኛ በትንሹም ቢሆን መናገር የሚችሉ አባት አገኘሁ። እርሳቸው እንዳዩኝ 'የእኔስ ልጆች እንዲህ አይደል የሚሆኑት' ብለው በማዘን ኮታቸውን አለበሱኝ።
'ከታየሁ እኔም እገደላለሁ' ብለው ደብቀው አስቀመጡኝ። 'የት ነው መሄድ የምትፈልጊው' አሉኝ። 'ደምቢ ዶሎ ለፌደራል ፖሊሶች ስጡኝ' አልኳቸው። ከዚያም መኪና ለምነው አሳፍረው ላኩኝ። መረጃውንም ለፌደራል ፖሊሶቹ ተናግሬያለሁ። ፌደራል ፖሊሶቹ 'ቦታው እንኳን ለተማሪ ለወታደርም አስጊ ነው፤ እንከታታላለን' አሉኝ።
ከታገቱት መካከል አንዷ ጓደኛዬ መጀመሪያ አካባቢ ስልክ እየሰጧት ትደውልልኝ ነበር። ለማውራት ብዙም ነፃነት ባይኖራትም 'በጣም እያሰቃዩን ነው፤ ምግብም ሲያሻቸው ይሰጡናል፤ ሲፈልጉ ደግሞ ይከልክሉናል' ስትል ነግራኛለች። የምትደውልበትን ስልክ 'የእነርሱ ነው ያዥው' ብላኝ ነበር። ከዛን ቀን በኋላ ግን አይሰራም፤ እነርሱም ደውለው አያውቁም፤ እኛም አግኝተናቸው አናውቅም።ይመለከታቸዋል ለተባሉ አካላት፤ ለአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን፣ ለአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት፣ ለፀጥታ እና ደህንነት መረጃውን ሰጥቻለሁ፤ ጠይቄያለሁ። 'እንከታተላለን' ነው ያሉኝ።ከዚያ መምጣቴን የሚያውቁ የተማሪዎቹ ወላጆችም ያለሁበት ድረስ እየመጡ ያለቅሳሉ፤ እኔ ግን 'መንግሥት ይዟቸዋል፤ አሁን ይመጣሉ' እያልኩ ከማረጋጋት ውጭ የማደርገው ጠፍቶኛል።"
ቢቢሲ የታገቱት ተማሪዎች ወላጆችን አነጋግሮ እንደገለጠው የአንዷ ወላጅ ልጃቸው ከታገተች ከሰሙ ከአራት ሳምንታት በላይ መሆኑን እንደገልጡ ዘግቧል።ይህ በእንዲህ እያለ ጉዳዩን አስመልክቶ የኦሮምያ የፀጥታ ባለስልጣናት በቂ ምላሽ እንዳልሰጡ ነው የተሰማው። ከአንዲት ተማሪ የስልክ ንግግር በመነሳት የአጋቾቹ ዋና ፍላጎት አስመልክቶ ቢቢሲ እንደዘገበው አጋቾቹ  ሕዝብ ልጆቻችንን ብሎ መንግስትን ሲያስጨንቅ መንግስት ከእኛ ጋር እንዲደራደር ያስገድደዋል የሚል ስሌት እንዳላቸው ይጠቅሳል።ጉዳዩ ግን ብሄራዊም ሆነ ዓለም አቀፋዊ ትኩረት ይሻል።የእገታ ጉዳይ የሽብር ተግባር ነው።ሽብር ደግሞ የአገር ውስጥ  ሳይሆን አካባቢያዊም፣ዓለም አቀፋዊም የጋራ ችግር ነው። 
በሌላ በኩል በምዕራብ ወለጋ፣ መንግስት ሕዝቡን ሲዘርፉ እና ሲያሰቃዩ ከነበሩ  ሸማቂዎች ጋር ጋር ግልጥ ጦርነት ላይ እንዳለ በኦሮምያ የብልፅግና ፓርቲ ሕዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ አቶ ታዬ ደንዳ ለቪኦኤ ትናንት ጥር 1/2012 ዓም  ገልጠዋል።እንደ እርሳቸው ገለጣ በምዕራብ ወለጋ መንግስት በሸማቂዎች ላይ እርምጃ እየወሰደ ያለው ሁሉም የሰላማዊ መንገድ ከተሞከረ በኃላ መሆኑን ካብራሩ በኃላ እስከዛሬ ሰላማዊውን ሕዝብ ሲጎዱ ምንም ያላለ ዛሬ በሽፍታ ላይ እርምጃ ሲወሰድ የሚናገር አንዳንድ ማኅበራዊ ሚድያ ዘገባዎች  ትክክል አይደሉም ብለዋል።አቶ ታዬ ደንዳ በእዚሁ ማብራርያ መንግስት በእዚሁ አካባቢ በሚያደርገው ሽፍቶችን የማጥራት ሥራ ተጠናክሮ እንደቀጠለና በቅርቡ ሁሉም ነገር  ወደነበረበት ሰላማዊ ሁኔታ ይመለሳል ለእዚህም በሽፍቶቹ የተጎዳው ሕዝብ ከፍተኛ ትብብር እያደረገልን ነው ብለዋል። 
ዘግይቶ የደረሰን ዜና 
ታግተው የነበሩ 21 የደምቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች መለቀቃቸውን የጠቅላይ ሚኒስቴር ጽ/ቤት አስታወቀ
********************
በደንቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ግጭት መከሰቱን ተከትሎ ወደ ቤተሰቦቻቸው በመሄድ ላይ የነበሩ ተማሪዎች ጫካ ውስጥ ታግተው መቆየታቸውን የጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ለኢቲቪ ተናግረዋል።
ታግተው ከነበሩ ተማሪዎች ውስጥ 13 ሴትና 8 ወንድ በድምሩ 21 ተማሪዎች በሰላማዊ ሁኔታ መለቀቃቸውን አቶ ንጉሱ አስታውቀዋል።
ይሁን እንጂ አሁንም ቀሪ 6 ተማሪዎች በእገታ ላይ መሆናቸውን በአካባቢው የተሰማራው የፀጥታ ኃይል መረጃ መስጠቱን ተናግረዋል ።
ምንጭ = የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Friday, January 3, 2020

ኢቢሲ ከብርሃን ባንክ ጋር ፈጠረ የተባለው ስምምነት መንግስትን የሚያሳማ እና በባንኮች መካከል ያለውን ጤናማ ውድድር የሚያበላሽ እንግዳ ስምምነት ነው።

የኢትዮጵያ ራድዮ እና ቴሌቭዥን ዋና መስርያ ቤት 

ጉዳያችን / Gudayachn
ታህሳስ 24/2012 ዓም (ጃንዋሪ 3/2020 ዓም)
===============
ዛሬ ዓርብ ታሕሳስ 24/2012 ዓም የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ዜና ላይ ኢቢሲ (የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮርፖሬሽን) ከብርሃን  ባንክ ጋር  ስምምነት ፈጠሩ የሚለው ዜና ሲጀምር እንዲህ በማለት ይጀምራል -
'' የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን እና ብርሃን ባንክ የጠበቀ ግንኙነት በመፍጠር አብረው ሲሰሩ ቆይተዋል'' ካለ በኃላ ዜናው በመቀጠል ''የጠበቀ ግንኙነቱን ለማጠናከር የመግባብያ ስምምነት ተፈራርመዋል'' ይላል ዜናው። ዜናው ላይ የብርሃን ባንክ ባለስልጣናት እና የኢቢሲ ኃላፊዎች ሳቅ በሳቅ ሆነው ስለምን እንደተዋዋሉ ሳይነግሩን ተስማሙ የሚለው ደጋግሞ ሲነገር በዜናው ላይ ይታያል።

የኢቢሲ ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር  ንጉሴ  ምትኩ በእዚሁ በስምምነቱ  ዜና  ላይ ብርሃን ባንክን ሲገልጡ ''ባጭር ጊዜ ተመስርቶ ስኬታማ እንደሆነ እኔም በነበረኝ ምልከታ ምስክር ለመሆን ችያለሁ ብዬ አስባለሁ'' ብለው ሲናገሩ  ዜናው ያሳያል።በሌላ በኩል የብርሃን ባንክ ማርኬቲንግ ሥራ አስኪያጅ አቶ ቢንያም መስፍን ''ከኢቢሲ ጋር ያደረግነው ስምምነት የብርሃን ባንክን ቪዝብሊቲ ከፍ የሚያደርግ ነው'' ብለዋል።

ስህተት 1 
ነፃ የውድድር ሜዳ ላይ የመንግስት ጣልቃ ገብነት ያሳያል 

የባንክ ኢንዱስትሪው በኢትዮያ ከአስራ አምስት ያላነሱ ባንኮች የያዘ እና ውድድር ላይ የሚገኝ ነው።የግሎቹ ባንኮች እርስ በርስ ከፍተኛ ውድድር ላይ ናቸው።ለመንግስትም ተገቢውን ግብር ያስገባሉ።መንግስት ደግሞ በተቀበለው ግብር መልሶ የማኅበራዊ እና የመሰረተ ልማት አገልግሎት ይሰጣቸዋል።መንግስት ለሁሉም ባንኮች እኩል አገልግሎት ሊሰጥ ነው የሚገባው። መንግስት ማለት አንዱ እጁ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ነው። ኢቢሲ በተናጥል ከአንድ የግል ባንክ ጋር የዕድሜ ልክ የመስለ ስምምነት አደረገ ተብሎ መቅርቡ መንግስት በባንኮች ውድድር ውስጥ አንዱን ደግፎ የመቆም ያህል ያስቆጥረዋል።በዛሬው የስምምነት ዜና መግቢያ ላይ ኢቲቪ የብርሃን ባንክ እና ኢቲቪ አብረው ሲሰሩ ቆይተዋል የሚል ዓረፍተ ነገር ተጠቅሟል።ምንድነው አብረው ሲሰሩ የቆዩት? በምን መስፈርት? ድንገት ተዋደዱ? የህዝብ ሀብት የሆነ ድርጅት እንደፈለገ ከፈለገው የግል ድርጅት ያውም ከፍተኛ ውድድር በሚታይበት ቁልፉ የምጣኔ ሀብት አንቀሳቃሽ ከሆነ ከአንዱ ተወዳዳሪ ባንክ ጋር  በተናጥል አብሬ እየሰራሁ ነበር ሲል ምን ማለቱ ነው?ይህን እኔ አይደለሁም የምጠይቀው የውድድር ሕጉ እራሱ የሚጠይቀው ሞራላዊ ጥያቄ ነው።


ስህተት 2 
የመንግስት ሚድያ ሥራ አስኪያጅ ከተወዳዳሪ ባንኮች ውስጥ የሚያደንቀውና የማያደንቀውን ባንክ ሚድያውን ወክሎ መናገር የለበትም 

መንግስታዊ ድርጅቶች  ያውም ቁልፍ የሆነው ሁሉንም እኩል እንዲያገለግል የሚጠበቅበት የመንግስት ልሳን ኢቢሲ ሥራ አስኪያጅ ስለ አንዱ የግል ባንክ በምልከታ በሚል ከግል ባንኮች ውስጥ አንዱን ነጥለው ከላይ እንደተጠቀሰው ''ስኬታማ'' ነው የሚል ቃል መናገር የለባቸውም።እዚህ ላይ የብርሃን ባንክ ስኬታማ ነው አይደለም የሚል ክርክር እየገባሁ አይደለም።ኢቢሲ ማለት ያለበት በዘገባው ሚዛናዊ ዘገባ አቅርቦ ወይንም የባንኩ ባለስልጣን ያሉትን ጠቅሶ ማለት ይችላል።በምልከታ ግን ስኬታማ ነው ስለዚህ ስምምነት አደረግን ማለት ተገቢ አይደለም።በሁሉም ባንኮች ግብር የሚተዳዳር   ኢቢሲ አንዱን ነጥሎ በምልከታ ስኬታማ እንዴት ሊለው ይችላል? ይህ በራሱ የመንግስት ሚድያን ተጠቅሞ  ያልተከፈለ ማስታወቂያ ነው።የግል ስሜት እና ግንኙነት ሌላ ነገር ነው።የህዝብ ንብረትን እኩል ለሁሉም ተወዳዳሪ ባንኮች  ክፍት ማድረግ ሌላ ነገር ነው።


ስህተት 3
የመንግስት ሚድያ የአንዱ ባንክ የመታየት አቅም ከሌላው ጎልቶ እንዲወጣ የመስራት መብት የለውም 

ከዜናው ለመረዳት እንደሚቻለው ብርሃን ባንክ በእዚህ ስምምነት ተጠቅሞ እንደ የማርኬቲንግ ሥራ አስኪያጁ ገለጣ ባንኩ የበለጠ ''ቪዚብልቲውን'' (ጎልቶ የመታየት አቅሙን) ከፍ እንደሚያደርግ ተገልጧል።በመጀመርያ ደረጃ  ኢቢሲ በምን መስፈርት ተጠቅሞ ነው  ከሌሎች ባንኮች በተለየ ከብርሃን ጋር የተዋዋለው? በሥራ አስኪያጁ ምልከታ? ወይንስ በቦርድ አባላቱ ውሳኔ? ግልጥ አይደለም።መንግስታዊ የመገናኛ አውታር ያውም በመንግስታዊነቱም ሆነ በግዙፍነቱ ትልቁ ኢቢሲ ስምምነት ከማድረጉ በፊት ሌሎች ባንኮችን አወዳድሯል? ወይንስ ጨረታ አውጥቷል? ደግሞስ የሕዝብ ንብረት የሆነው  ኢቢሲ የህዝብ ሀብት የሆኑት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር እንዴት ይህንን ውል አላደረገም።ምናልባት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር  ይህንን ስምምነት ቢያደርግ መንግስታዊ ወይንም የህዝብ ሀብት ከመሆኑ አንፃር ይህ ጥያቄ አይነሳም ነበር። ብርሃን ባንክም ከግል ሚድያ ጋር ይህንን ስምምነት ቢያደርግ ጥያቄው አይነሳም።ምናልባት የግል ሚድያው ሥራ አስኪያጅ  ብርሃን ባንክን በምልከታዬ (ኦዲት ሪፖርቱን ሳይጠቅሱ) ስኬታማ ነው እያሉ ቢናገሩ ኖሮ ቅሬታ አያስነሳም ነበር። የህዝብ ሀብት ኢቢሲ የግል ስምምነት በሚመስል መልኩ ከተወዳዳሪ ባንኮች አንዱን ''ቪዚብልቲው'' ከፍ እንዲል ሊሰራ ነው የሚል ቀልድ መሰል  ንግግር  ባልሰማን ነበር።

ለማጠቃለል 

ከላይ ለማስረዳት እንደተሞክረው የባንኮች የውድድር ሜዳ ላይ መንግስታዊ ሚድያ ያውም ግዙፉ ሚድያ በምንም መስፈርት አንዱን ባንክ ነጥሎ አብሬው እሮጣለሁ ተወዳዳሪዎቹን እንዲቀድም እረዳዋለሁ መሰል ሥራ ውስጥ እንዲገባ የንግድ ሕጉም፣የመንግስት አሰራርም ሆነ ሞራላዊ ሁኔታዎች አይፈቅዱለትም።ቢያንስ ይህ ስምምነት ሲደረግ ኢቢሲ የሄደበት ለሁሉም ባንኮችም ሆነ ሚድያ ግልጥ የሆነ ሂደት ካለ ያሳይ።ከእዚህ ውጪ ግን ምንም አይነት አሰራር ያለ አይመስለኝም። በውድድር ዓለም ውስጥ የመንግስት ድርጅቶች በተለይ ቁልፍ የሆኑት ለምሳሌ መንግስታዊ ሚድያ (ሁሉንም ኢትዮጵያ የመሸፈን አቅም ስላላቸው)፣ የውሃ እና ፍሳሽ፣መብራት፣ቴሌ የመሳሰሉት በውድድር ዓለም ባሉ የግል ድርጅቶች ውስጥ ገብተው ካለምንም  ሕጋዊ ሂደት አንዱን እጅ ይዘው ከፍ ሊያደርጉ፣ሌላውን ደግሞ ችላ ሊሉ አይችሉም። እነኝህ መንግስታዊ አካላት ለሁሉም እኩል የማገልገል ግዴታ አለባቸው።ምክንያት - ከሁሉም በሚሰበሰብ ቀረጥ የሚተዳደሩ ናቸው እና መንግስትን ያሳሙታል።ይህንን ሁኔታ ከንግድ ሕጉ አንፃር እና ከመንግስታዊ ድርጅቶች መመርያ አንፃር ሌሎች አጣቅሰው ብዙ ሊሉበት እንደሚችል እገምታለሁ።


የመጨረሻው መጨረሻ ግን ለብዙ ዓመት በማኅበራዊ ሚድያ የጠየኩት EBC በእንግሊዝኛ ብቻ ሳይሆን በቴሌቭዥን ላይ ስፅፍ በአገሪቱ ፊደል ''ኢቢሲ'' ብሎ ይፃፍ የሚለውን ጥያቄ ለአንድ ሺኛ ጊዜ እጠይቃለሁ።ይህ ለመላው ዓለም የኢትዮጵያን መልክ የሚያሳይ ከልጆች ሳይቀር አዕምሮ የማይጠፋ ያደርገዋል።ፊደል እንደሌለን የእንግሊዝኛ ፊደል ብቻ ማድረግ ያለማወቅ ደረጃ ነው።በአማርኛ እያወሩ ኢቢሲ ብሎ አለመፃፍ ጤነኛ አስተሳሰብ አይደለም።አንድ ቀንም ይህ ጉዳይ የማኅበራዊ ሚድያ ዘመቻ የሚከፈትበት ጉዳይ መሆን አለበት።




ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Wednesday, January 1, 2020

መንግስት በግልፅ ተነጋግሮ ካላረመው ኢትዮጵያ ከባድ የፀጥታ አደጋ ያሰጋታል

ጉዳያችን GUDAYACHN   
ታሕሳስ 22/2012 ዓም (ጃንዋሪ 1/2019 ዓም)

'ሳይቃጠል በቅጠል' የምትለው የኢትዮጵያውያን አባባል ትልቅ ትምህርት አላት።ቅጠል እራሱ ተቀጣጣይ ነው።እሳት ሲቀጣጠል በቅጠል ላጥፋው ብትል አትችልም።ምክንያቱም እሳቱ እራሱ ሊያጠፋው የመጣውን ቅጠል ይበላዋል።ሳይቃጠል ገና በትንሽ ጭስ ላይ እያለ ግን በቅጠል ብትመታው ያለው ፍንጥርጣሪ እሳት ተበታትኖ ይጠፋና ትልቅ የእሳት አደጋ ሳያስከትል እና ነፋስ እያግለበለበ ሳያቀጣጥለው የመጥፋት ዕድል አለው። 

የኢትዮጵያ ወቅታዊው ፖለቲካ በቅንነት ኢትዮጵያን ወደተሻለ መንገድ ለማሻገር የሚተጉ የመኖራቸውን ያህል የተለመደውን የሴራ ፖለቲካ እያውጠነጠኑ ያደፈጡ ኃይሎችም አሉ።የሴራ ፖለቲካው ደግሞ በራሱ በመንግስት የቢሮክራሲ መዋቅር ውስጥ የተተበተበ እና በጎሳ መር ድርጅቶች ላይ ሁሉ ማድራቱ ነው አደጋው።ስለሆነም በኢትዮጵያ ወሳኝ በሆኑ መንግስታዊ ድርጅቶች ላይ ሁሉ የቅርፅ እና የዓይነት መልክ እያመጣ ኢትዮጵያዊ ቃናውን እያሳጣው እንዳይሄድ እያንዳንዱን መዋቅር መልሶ መላልሶ መፈተሽ እና አላስኬድ ያለውን አሰራር እና ፖሊሲ ሁሉ መከለስ ያስፈልጋል።

አሁን ላለው የኢትዮጵያ በር ላይ የፀጥታ አደጋ ውስጥ የሚጠቀሰው አንዱ የክልሎች ልዩ ኃይል ጉዳይ ነው።አንዲት አገር አገር የሚያሰኛት እንደ አገር የጋራ ተቋማት ሲኖሯት ነው።በተለይ ቁልፍ የሆኑት መንግስታዊ  ተቋማት ለምሳሌ የጦር ኃይል እና የፀጥታ ኃይሉ በአገሪቱ ካሉት ክፍሎች ለአንዱ ባላዳላ መልክ ሁሉንም ባማከለ እና የገንዘብ ምንጩም በአገሪቱ የጋራ ሀብት የሚተዳደር ካልሆነ እጅግ አደገኛ ሁኔታ እየተፈጠረ እንደሆነ አመላካች ነው።

በኢትዮጵያ ከ1967 ዓም ወዲህ ባሳለፍናቸው ሁለት የአምባገነን መንግሥታት ታሪክ ለአምባገነንነት ዋና ምሰሶ ሆነው ያገለገሉት በተለይ ለፖለቲካ ስልጣኑ ሶስቱ ምሰሶዎች ናቸው።እነርሱም የወታደራዊ፣ደህንነት እና የኢኮኖሚ አውታር ናቸው። ከእነኝህ ውስጥ የወታደራዊውን ጉዳይ ብንመለከት በደርግ ዘመን ከጎሳ የፀዳ ወታደራዊ ኃይል ቢኖረውም በውስጡ ግን የስልጣን ወንበሩን የሚያስጠብቁ ''ቅልብ ጦር'' የሚባል በኮ/ል መንግስቱ የሚታዘዙ አስፈሪ የሰራዊት ኃይል ነበሩ።ይህ ጦር ከሌላው የኢትዮጵያ ጦር የተለየ ሆኖ እንዲወጣ ሲደረግ ዋና ዓላማው የሚቃወሙትን ሁሉ በኃይል ለመስበር ነው። በዘመነ ህወሓት-ኢህአዴግም ''አግአዚ'' የሚባል ጦር ነበር።ይህ የጦር ኃይል ከቅልብ ጦር የሚለየው በአንድ ጎሳ የተፈረጀ እና እንደተባለውም ለይስሙላ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የመጡ አባላት ቢኖሩትም ከስያሜው ጀምሮ  እስከ ማዕከላዊ ማዘዣው ድረስ ከአንድ ጎሳ ጋር የተመደበ ይልቁንም ይህ ሰራዊት የሚሰራው የጭካኔ ሥራ ሁሉ ከጎሳው ተግባር ጋር እየተገናኘ የሄደበት ታሪክ የተስተናገደበት ሁኔታ ነበር።

የአሁኑ አስፈሪ ሁኔታ ምንድነው?

ያለፈ የታሪክ ስህተት ለአሁኑ አስተማሪ ነው።ደርግን የቅልብ ጦር ጭካኔ ስልጣኑን አልጠበቀለትም።ህወሓትም የአጋዚ ጦር አላዳናትም።የሁለቱም ጦር አባላት የት እንዳሉ አይታወቅም።ምናልባት የአጋዚ ጦር አሁንም አለ ይሆናል።ነገር ግን እያረጀ ከመሄድ እና ወደ የግል ህይወቱ ከመግባት በቀር የሚያመጣው ነገር የለም።ከእነኝህ ሁሉ ተምሮ ዛሬን ማስተካከል ተገቢ ነው። 

በኢትዮጵያ በክልሎች ያለው የልዩ ኃይል ብዛት፣የስልጠናው ዓይነት እና እየታጠቀ ያለው የጦር መሳርያ አይነት ሁሉ ስንመለከት እና በፍጥነት መታረም ካልቻለ ከደርግም ሆነ ከህወሓት የባሰ አደጋ ለኢትዮጵያ አያስከትልም ማለት ሞኝነት ነው። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ሃሳብ የሚሰጡ ሰዎች አንዳንዴ የሚገርሙኝ ትልቁን አደጋ ላይ ሲጮሁ እና መንግስት እንዲታረም ሲጮሁ አለመታየታቸው ነው። በትንሹ ጉዳይ ደግሞ ከሚገባው በላይ አጋኖ በማቅረብ ለመጠላለፍያነት ሲደክሙበት ይታያሉ። ከእዚህ የክልሎች ኃይል እያፈረጠሙ መሄድ በላይ ለኢትዮጵያ ውስጣዊ የፀጥታ ችግር የከፋ ጉዳይ ምን አለ? 

በተለየ ሁኔታ በአሁኑ ሰዓት የክልል ልዩ ኃይል ጡንቻ ማፈርጠም በእየክልሉ እንደቀጠለ ነው።በቅርቡ  ካልተሳሳትኩ በሰላም ሚኒስቴር አቅራቢነት የተወካዮች ምክር ቤት የክልል ልዩ ኃይል ትጥቅ የሚፈቱበትን ሁኔታ ላይ መነጋገሩ ተነግሮ ነበር።ሆኖም ጉዳዩ መልሶ የት እንደደረሰ አልተሰማም። በትግራይ ቁጥሩ የማይታወቅ የክልል ልዩ ኃይል እና ሚሊሻ አለ።በዓማራም በተመሳሳይ መልክ እንዲሁ ክልሉ በመንግስት ጦር ሳይሆን በልዩ ኃይል እና ሚሊሻ ነው ፀጥታውን የሚያስከብረው።በኦሮምያም እንዲሁ የክልሉ ልዩ ኃይል አሁን በከፍተኛ በጀት እየተደጎመ የ28ኛ እና 29ኛ ዙር ሰልጣኞችን አሰልጥኖ ማስመረቁ ሰሞኑን ተነግሯል።

የክልል የጦር ኃይል በተመለከተ ሁሉም ክልል ወደራሱ የአገር መልክ እየሄደ ያለ ይመስል እንደ ቀዝቃዛው ጦርነት የስልጠና እሽቅድምድም ላይ ያለም ይመስላል። በመጀመርያ ደረጃ የክልል ልዩ ኃይል ስልጠና ከዋናው የኢትዮጵያ ጦር ኃይል የስልጠና እና የትጥቅ ደረጃ ጋር እንዲገዳደር ተደርጎ መሰልጠኑ ምን ዓይነት አገራዊ ርዕይ ነው? የክልል ልዩ ኃይል የስልጠና ዓይነቱ ጣርያ የት ላይ ይቆማል? ለምሳሌ ወደፊት ታንከኛ፣አየር ኃይል እያሉ ላለማሰልጠናቸው ምን ዋስትና አለ? ሰሞኑን በኦሮምያ የታየው የክልሉ ልዩ ኃይል ከኢትዮጵያ የምድር ጦር ኃይል እኩል የሰለጠነ እንደሆነ ከእንቅስቃሴው መመልከት ይቻላል።በተለያዩ አስተሳሰቦች በምትናጠው የኦሮምያ ክልል ውስጥ የብሔራዊ ጦሩ ሚና ምን ሊሆን ነው? ብሎ አለመጠየቅ ምን ዓይነት የፖለቲካ እብደት ነው? ቀድሞ ክልሎች ትንንሽ የፀጥታ ጉዳዮችን እንዲፈቱ ከበድ ያለ ሲያጋጥማቸው በቶሎ ማዕከላዊ መንግስት የፌድራል ጦር ኃይል እንዲልክ እንዲጠይቁ ተደርገው ነበር የተሰሩት።አሁን ግን የስልጠናው ገደብም ሆነ የሚይዙት የጦር መሳርያ አይነት መጠን የሚታወቅ አይመስልም። 

ሰሞኑን በተመረቁት የኦሮምያ ልዩ ኃይል ስልጠና ምረቃት ላይ በአዋሽ ቢሾለ በመገኘት የመረቁት የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ሲናገሩ  "የልዩ ኃይሉ ተልዕኮዎች መካከል አንዱ የተገኘውን ድል ማስቀጠል ነው" ብለዋል።ምክትል ፕሬዝደንቱ በተጨማሪም የልዩ ኃይሉ ተልዕኮ የክልሉን ሰላም እና ጸጥታ ከማስጠበቅ በተጨማሪ የኦሮሞ ህዝብ ጥቅም እና መብት ማረጋገጥ የተጣለበት ሃላፊነት ነው ብለዋል። ልዩ ኃይሉ የአንድ ብሔርን ጥቅም እና መብት ማስጠበቅ የተጣለበት ኃላፊነት የሚለው አባባል እንደአገር የማሰብ የጋራ ርዕይ አይደለም።ይሄው ሰራዊት ግን ነገ በአዲስ አበባ ውስጥ ግባ ሲባል ለአዲስ አበቤ መብት ሳይሆን ለጎሳው መብት ለማስከበር እንደሆነ አቶ ሽመልስ ዛሬ ላይ ቆመው በግልጥ እየነገሩን ነው። ይህ ሁኔታ ነው የጎሳ ግጭት የሚያመጣው።የእኔ የሚለው ሰራዊት ያጣ ሕዝብ ወደ ጎሳው ልዩ ኃይል እንዲያማትር ሊያደርገው ነው።መንግስት ማለት ሁሉን በእኩል የሚዳኝ እንጂ የአንዱ አባት የሌላው እንጀራ አባት ሊሆን አይገባም።

ባጠቃላይ ከእዚህ በፊት የኦሮምያ ልዩ ኃይል በሱማሌ ክልል ላይ፣የሱማሌ ልዩ ኃይል በኦሮምያ ክልል ላይ እንዲሁም የኦሮምያ ልዩ ኃይል በሰሜን ሸዋ የዓማራ አዋሳኝ ክልሎች ላይ ያደረሱት ግጭት እና የሰው ሕይወት መጥፋት ይታወቃል። ይህ የክልል ልዩ ኃይል የኢትዮጵያ መጪ ዘመን አደጋ ነው።መንግስት ቁልፍ ከሆኑ አካላት ውስጥ አንዱ የሆነውን የወታደራዊ እና የደህንነት  አካሉን በአግባቡ በማዕከላዊነት መያዝ ይገባዋል። ፌዴራሊዝም አሰራር አለው።ክልሎች የፀጥታ ኃይል ይኖራቸዋል ቢባል የምድር ጦር ያህል ሰራዊት ያሰለጥናሉ ማለት ፈፅሞ ሊሆን አይችልም። መጪው ምርጫ ስርዓት ሊይዝ የሚችለው ክልሎች ያላቸው የልዩ ኃይል በሙሉ ፈርሶ ወደ አንድ ብሔራዊ ዕዝ ሲገባ እና በክልሎች የሚኖረው የፀጥታ ኃይል በፖሊስ አደረጃጀች ደረጃ ከተቀመጠ ብቻ ነው።ይህ ካልሆነ እያንዳንዱ ክልል የልዩ ኃይሉን በምድር ጦር ደረጃ የማሰልጠን እሽቅድምድም ውስጥ የማይገባበት ምንም ሁኔታ የለም። ከሰሞኑ የኦሮምያ ልዩ ኃይል ስልጠና የተመለከቱ የሱማሌ፣የዓማራ፣የአዲሷ ሲዳማ፣ቤንሻንጉል ወዘተ ክልሎች ሁሉ የልዩ ኃይል ስልጠና በጀት መጨመር ላይ ይሮጣሉ።ይህ ደግሞ ልማቱን ያቀጭጫል።ነገሩ ሲገፋ ነገ የውጭ ኃይሎች በጎን በልማት ስም እየገቡ የአንዳንድ ክልሎች ልዩ ኃይል ስልጠና በጀት ማዕከላዊ መንግስት ባላወቀው መንገድ አይደጉምም ማለት አይቻልም።ክልሎች የወታደራዊ ኃይላቸው ጉልበት ሲፈረጥም ደግሞ የሌሎች ክልሎች ወሰን ጋር ግፍያ ውስጥ ይገባሉ። መዘዙ ብዙ ነው።እየተሄደ ያለው ሁሉ የማዕከላዊ መንግስትን አቅም እያደከሙ በግርግር የክልሎች ጉልበት እንዲጠነክር የሚያደርግ ሂደት ነው። ይህ ማለት የጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ የማዕከላዊ ስልጣን እየተሸረሸረ በጎጥ ድርጅቶች የኢትዮጵያ መጪ ዕድል የመወሰን አደጋ አለው ማለት ነው።ጠቅላይ ሚኒስትሩም መንግስት ከልቡ ከምርጫው በፊት አንድ አይነት ወሳኝ እርምጃ መውሰድ አለበት።   

                                        በቅርቡ የተመረቀው የኦሮምያ ልዩ ኃይል በከፊል (ፎቶ =ፋና)
ጉዳያችን / Gudayachn
 www.gudayachn.com

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።