ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, June 30, 2014

ሰበር ዜና - ግንቦት 7 ንቅናቄ የየመንን መንግስት እና ኢህአዴግ/ወያኔን አስጠነቀቀ።ለኢህአዲግ/ወያኔ በሰጠው ማስጠንቀቂያ የድርጅቱ ዋና ፀሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ''አካል፣ መንፈስ እና ሕይወት ላይ ለሚደርሰው ጥቃት ሁሉ በማንኛውም መንገድ በማንኛውም ቦታ የምንበቀል መሆኑንና ብዙ የወያኔ ሹማምንት ዋጋ የሚከፍሉበት እንደሚሆን እንዲያውቁት እናስጠነቅቃለን'' ይላል መግለጫው።



የግንቦት 7 ንቅናቄ የአቶ አንዳርጋቸውን በየመን የፀጥታ ኃይሎች መታገት አስመልክቶ ያወጣው መግለጫ ከእዚህ በታች ያንብቡ።

አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በየመን ባለሥልጣናት እገታ ላይ መሆኑን በማስመልከት የወጣ መግለጫ
ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም
የግንቦት 7፣ የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ዋና ፀሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ሰኔ 16 ቀን 2006 ዓም ለሥራ ጉዳይ በየመኒያ አየር መንገድ አይሮፕላን ተጉዞ በትራንዚት ሰንዓ ከተማ እያለ በየመን መንግሥት ፀጥታ ኃይሎች በሕገወጥ መንገድ ታግቷል። አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የመን የጉዞው መዳረሻ አልነበረም፤ ከየመን ጋርም የሚያገናኘው ምንም ጉዳይ አልነበረውም። የየመን መንግሥት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን አግቶ ለአንድ ሰዓት እንኳን ለማቆየት ምንም ምክንያት የለውም። በዚህም ምክንያት ያለአግባብ የታገተብን የንቅናቄያችንን አመራር በአስቸኳይ እንዲፈታ በተለያዩ መንገዶች ላለፈው አንድ ሣምንት ያደረግነው ጥረት እስካሁን አልተሳካም። እንዲያውም የየመን ባለስልጣናት አምባገኑን ወያኔ ለመርዳት ባለው ፍላጎት ሳቢያ መሪያችንን አሳልፎ ሊሰጠው ይችላል የሚል ከፍተኛ ስጋት አድሮብናል።
አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ በሀገራችን በኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ፣ ነፃነትና ዲሞክራሲ እንዲሰፍን ጊዜውን፣ እውቀቱንና ጉልበቱን ብቻ ሳይሆን ሕይወቱን አሳልፎ ለመስጠት የተዘጋጀ፤ ዝግጁነቱንም በተግባር ያሳየ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጅ ነው። የየመን መንግሥት ከዘረኛውና ፋሽስታዊው ወያኔ ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ታጋይ መሪያችን ላይ እየፀመ ያለውን ደባ የጉዳዩ ባለቤት የሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲያውቅ የንቅናቄዓችን ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ወስኗል።
ትግላችን መስዋትነት እንደሚያስከፍል እናውቃለን። ከዚህ በፊትም ብዙ ጓዶቻችን መስዋዕትነት ከፍለዋል፤ ወደፊትም ብዙ መስዋዕትነት መከፈሉ የማይቀር ጉዳይ ነው። አሁን በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ላይ የደረሰውና ወደፊትም ሊደርስ የሚችለው ጉዳት ምሬታችን በማብዛት፣ ቁጣችንና ዝግጁነታችን ከማጠንከር በስተቀር ቅንጣት ታክል እንኳን ወደ ኋላ እንድናፈገፍግ እንደማያደርገን ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ለአባሎቻችንና ለደጋፊዎቻችን ሁሉ መግለጽ እንወዳለን።
መንግሥታት ይመጣሉ፣ ይሄዳሉ። ኢትዮጵያና የመን ግን ጎረቤታሞች ሆነው መቆየታቸው የማይቀር ነው። የየመን መንግሥት የወያኔ እድሜ አጭር መሆኑ የተገነዘበ አይመስልም። በዚህም ምክንያት የየመን መንግሥት የሁለቱን አገሮች ሕዝቦች የቆየ ወዳጅነት የሚያደፈርስ እርምጃ ወስዷል። የየመን መንግሥት የየመንን የወደፊት የረዥም ጊዜ ጥቅም እንዲያሰላና ያገተብንን መሪ በአስቸኳይ እንዲፈታ እንመክራለን። ይህ ሳይሆን ቀርቶ በመሪያችን ላይ ጉዳት ቢደርስ ወይም ለወያኔ አሳልፎ ቢሰጥ የመን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር የማይሽር ቂም ውስጥ የምትገባ መሆኑን የየመን መንግሥት አውቆ በጥብቅ እንዲያስብበት እናስጠነቅቃለን።
በየመን መንግሥት አልሰማ ባይነት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ለፋሽስቱ የወያኔ አገዛዝ ተላልፎ ቢሰጥ በአካሉና በሕይወቱ ለሚደርሰው ሁሉ የወያኔ ፋሽስቶችን ዋጋ የሚያስከፍል መሆኑ ከአሁኑ እናስጠነቅቃለን። በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ አካል፣ መንፈስና ሕይወት ላይ የሚደርሰው ማንኛውም ጥቃት ለነፃነታቸው ለመሰዋት ዝግጁ የሚሆኑ እልፍ አዕላፍ ታጋዮችን እንደሚፈጥር ጥርጥር የለንም። በአቶ አንዳርጋቸው ጽጌ አካል፣ መንፈስ እና ሕይወት ላይ ለሚደርሰው ጥቃት ሁሉ በማንኛውም መንገድ በማንኛውም ቦታ የምንበቀል መሆኑንና ብዙ የወያኔ ሹማምንት ዋጋ የሚከፍሉበት እንደሚሆን እንዲያውቁት እናስጠነቅቃለን ።
በመስዋዕትነት ድልን እንቀዳጃለን።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

የኢትዮጵያ የቀድሞ ዘመናዊ የጦር ሰራዊትን ታሪክ ሳንዘክር ስለ ኢትዮጵያ ማውራት አንችልም

የኢትዮጵያ ዘመናዊ የጦር ሰራዊት መሰረቱ በዳግማዊ ምንሊክ ዘመን ይጣል እንጂ በተደራጀ መልክ የተመሰረተው ከፋሽሽት ኢጣልያ መባረር በኃላ መሆኑን በርካታ ድርሳናት ያስረዱናል።ዛሬ ቀና ብለን ስለ ኢትዮጵያ መናገር የቻልነው በጥንት አባቶቻችን ተጋድሎ ብቻ አይደለም።የቀድሞ ዘመናዊ የጦር ሰራዊት ገድልም ትልቅ አስተዋፆ አለበት።ሱማልያ ''ቁርስ ድሬዳዋ ምሳ አዲስ አበባ'' በሚል መፈክር በ1969 ዓም በከፈተችብን ጦርነት ከሞቃዲሾ በምታስተላልፈው የአማርኛ ራድዮ ፕሮግራም ፎክራብን ነበር።ምስራቃዊውን የሀገራችንን ክፍል ይዛ ነበር።
በመቶ ሺህ የሚቆጠር ሚሊሻ ከመደበኛ ሰራዊት ጋር እልህ አስጨራሽ ውግያ አድርጎ ነፃነታችንን እና የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት ያስከበረው የቀድሞ ዘመናዊ የጦር ሰራዊት ነው።ኢትዮጵያውያን ብዙ ያልገቡን፣ክብር መስጠት ሲገባን ክብር ያልሰጠናቸው ክቡራን አሉን።
ክብር ለቀድሞ ዘመናዊ የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት! የኢትዮጵያ የቀድሞ ዘመናዊ የ ጦር ሰራዊትን ታሪክ ሳንዘክር ስለ ኢትዮጵያ ማውራት አንችልም።



ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG

Wednesday, June 25, 2014

የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ለሀገሩ የሚያደርገው አስተዋፆ ታላቅ አብነት-የኢትዮ-አሜሪካ የሕክምና ዶክተሮች ቡድን በአዲስ አበባ ለአፍሪካ ሞደል የሆነ ከፍተኛ ሆስፒታል በሁለት ቢልዮን ብር ወጪ ሊገነባ ነው የመሰረት ድንጋዩ በመጪው ቅዳሜ አዲስ አበባ ላይ ይጣላል

ኢትዮ-አሜሪካ የሕክምና ዶክተሮች ቡድን አባላት በከፊል 

ኢትዮ-አሜሪካ የሕክምና ዶክተሮች ቡድን በአሜሪካን ሀገር በህክምና ሙያ ላይ በተሰማሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን የተመሰረተ ቡድን ነው። ቡድኑ በድረ-ገፁ ላይ ተልዕኮውን እና ራዕዩን አስቀምጧል።
የቡድኑ ተልኮ '' በኢትዮጵያና አካባቢዋ እንዲሁም በአፍሪካ ደረጃውን የጠበቀ፣ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ሰጪዎች የተመሰከረለት እና የጤና ዕውቀት ማስመስከርያ የሆነ ሆስፒታል መገንባት ነው'' ይላል።
'' To build an economically sustainable, center of excellence hospital that will deliver internationally accredited standard of care and become the catalyst for change in how health care is delivered in the region and Africa.
ራዕዩ ደግሞ እንዲህ ይነበባል - '' እኛ ከ 200 በላይ የሆንን ትውልደ ኢትዮጵያውያን የሕክምና ባለሙያዎች ከፍተኛ ጥራት እና ደረጃ ያለው በዕውቀት እና በምርምር ላይ የተመሰረተ የሕክምና አገልግሎት ለኢትዮጵያ ሕዝብ፣ለአፍሪካ እና ለመላው ዓለም ሕዝብ መስጠት ራዕያችን ነው''' ይላል።
  • ''We are more than 200 physicians of Ethiopian origin coming together to develop and deliver high quality medical care through education and research for the people of Ethiopia, Africa and beyond.''
ቡድኑ የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ለሀገሩ የሚያደርገው አስተዋፆ መገልጫ የሆነውን እና  በታላቅ አብነት የሚጠቀሰውን ተግባር በመጪው ቅዳሜ ሰኔ 21/2006 ዓም በሁለት ቢልዮን ብር ለሚገነባውን ሆስፒታል የመሰረት ድንጋይ በመጣል ይጀምራል።
ሆስፒታሉ በዓለማችን ካሉት ምርጥ ሆስፒታሎች ተርታ የሚመደብ ሲሆን ደረጃውን ''ጆይንት ኮሚሽን ኢንተርናሽናል'' በተሰኘ የሆስፒታሎችን ደረጃ በሚያወጣ ድርጅት በሚሰጠው ሰርተፍኬት ዓለም አቀፍ ተወዳዳርነቱን የሚያስመሰክር እንደሚሆን ይጠበቃል።ሆስፒታሉ የማስተማርያ እና ከፍተኛ የሕክምና ምርምር የሚደረግበት መሆኑን እና ከ200 በላይ የሆኑትን የቡድኑ  አባላት ውስጥ የተወሰኑትን  ስፔሻሊስቶች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው አገልግሎት እንደሚሰጡ የቡድኑ አመራር  አባል  ዶ/ር ግርማ ተፈራ አስረድተዋል።
በ 2011 እ ኤ አ በ አስራ ሁለት አባላት የተጀመረው የኢትዮ-አሜሪካ የሕክምና ዶክትሮች ቡድን ዛሬ 200 አባላትን ይዟል።
የዜናው ምንጮች -
                  የቡድኑ ድረ-ገፅ  http://ethioamericandoctors.com/
                  ቪኦኤ የአማርኛ አገልግሎት ሰኔ18/2006 ዓም ዘገባ 

ጉዳያችን 
ሰኔ 18/2006 ዓም (ጁን 25/2014)

Monday, June 23, 2014

ማኅበረ ቅዱሳን በጥቂት ሳምንታት ውስጥ በኦሮምኛ ቋንቋ አዲስ የድረ - ገጽ አገልግሎት ሊጀምር ነው ከዚህ ቀደም ተቋርጦ የነበረው የእንግሊዝኛ ድረ-ገጽም በቅርቡ ይጀምራል።


ከእዚህ በታች የሚገኘው ፅሁፍ የተወሰደው ከማኅበሩ ድረ-ገፅ http://eotcmk.org/site/-mainmenu-18/1495-2014-06-21-08-20-51 ላይ ነው ።
''በማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል የኦሮምኛ ድረ ገጽ አገልግሎት በቅርቡ እንደሚጀምር የዋና ክፍሉ ሓላፊ ዲያቆን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ ገለጹ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፤ ቀኖና እና ትውፊት የጠበቁ ትምህርቶችን በኦሮምኛ ቋንቋ በተለያዩ የመገናኛ ብዙኀን ዘዴዎች ለምእመናን ለማሰራጨት እቅድ ከያዘ መቆየቱን የገለጹት ዲያቆን ዶ/ር መርሻ፤ የድረ ገጽ አገልግሎቱ ቅድሚያ ተሰጥቶት ለምእመናን ተደራሽ እንደሚሆን አስታውቀዋል፡፡

በዚህም መሠረት “በጥቂት ሳምንታት ውስጥ የኦሮምኛ ድረ ገጽ አገልግሎት መስጠት የሚጀምር ሲሆን፤ ወደፊት የኅትመትና የብሮድካስት ዝግጅቶችን ለምእመናን ለማዳረስ ማኅበሩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ተግባራዊ ያደርጋል” ብለዋል፡፡

የኦሮምኛ ዝግጅት ንዑስ ክፍል አስተባባሪ ዲ/ን መዝገቡ ከፍያለው ለኦሮምኛ ድረ ገጽ መከፈት ምክንያት ናቸው ያሏቸውን ሲገልጹ “በኦሮሚያ ክልል ምእመናን ስለ እምነታቸው በቋንቋቸው መማር አለመቻላቸው፤ በቋንቋው የተዘጋጁ ሃይማኖታዊ የኅትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ውጤቶች አለመኖር እና ምእመናን በሌሎች የእምነት ተቋማት መወሰዳቸው ነው” በማለት ጠቅሰዋል፡፡

እነዚህን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመፍታት እና ያሉትን ምእመናን ለማጽናት፤ የጠፉትንም ለመመለስ እንዲቻል ከዐውደ ምሕረት ስብከት በተጨማሪ በመገናኛ ብዙኀን ዘዴዎች ወደ ምእመናን ለመድረስ አዲስ የተዘጋጀው ማኅበራዊ ድረ ገጹ አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ ታምኖበታል፡፡

በድረ ገጹም ትምህርተ ሃይማኖት፤ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፤ ነገረ ቅዱሳን፤ ስብከት፤ ለጥያቄዎች ምላሽ /ከምእመናን ለሚጠየቁ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት/፤ መዝሙር እና ኪነጥበብ ወዘተ. . . የተካተቱበት ሥራዎች እንደሚቀርቡ ዲ/ መዝገቡ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የድረ ገጹ አድራሻ፡- www.eotcmk.org/afaanoromo


በተያያዘ ዜና ከዚህ ቀደም ተቋርጦ የነበረው የእንግሊዝኛ ድረ ገጽ በቅርቡ የሚጀምር ሲሆን፤ የድረ ገጹ አድራሻ፡- www.eotcmk.org/site-en መጎብኘት ይቻላል፡፡''


Saturday, June 21, 2014

የግብፅ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤ/ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎድሮስ ሁለተኛ በኖርዌይ የሶስት ቀናት ጉብኝት አደረጉ።ኖርዌይን በመጎብኘት የመጀመርያ የኮፕት ፓትርያሪክ ናቸው (የጉዳያችን ልዩ ጥንቅር -ፎቶዎች ይዘናል (Gudayachn Exclusive)



የግብፅ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤ/ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎድሮስ ሁለተኛ በኖርዌይ ከ ሰኔ 12-14/2006 ዓም ባደረጉት ጉብኝት ከፍተኛ አቀባበል በኖርዌይ መንግስት የተደረገላቸው ሲሆን ከኖርዌይ ንጉስ ሃራልድ፣ከጠቅላይ ሚንስትር ወ/ሮ አርና ሱልበርግ እና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ብረንደ ጋር ተወያይተዋል።

የፓትርያርኩ ጉብኝት  በግብፅ ባለው ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ጉዳይ ላይ ለመወያየት የኖርዌይ ቤተክርስቲያን ባደረገችላቸው ጥሪ ምክንያት መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።በመካከለኛው ምስራቅ ውስጥ ካሉት አብያተክርስቲያናት በርካታ ምዕመናንን ያላት የግብፅ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያን በብዙ ወከባ እና ፈተና ላይ መሆኗን የኖርዌይ መንግስት እና የሃይማኖት ድርጅቶች እንደሚረዱ በተወካዮቻቸው አማካይነት ለፓትርያርኩ እና ለልዑካኑ ገልፀዋል።

በአፀፋው ፓትርያርኩ በግብፅ ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ማስረዳታቸው እና በተለይ አርብ ሰኔ 13/2006 ዓም በኖርዌይ ከሚገኙ የተለያዩ የክርስቲያናዊ ድርጅቶች ጋር ልዩ ውይይት አድርገዋል።በፓትርያርኩ ለውይይት የቀረበው የመውያያ አርዕስት ''በወቅታዊው የግብፅ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ ሁኔታዎች ውስጥ የኮፕቲክ ቤተክርስቲያን የገጠሟት ተግዳሮቶች'' (''Dilemmas and challenges for the Coptic church in the current political and religious situation in Egypt'') የሚል ሲሆን ፅሁፉ የግብፅ ክርስቲያኖችን መፃኢ ፈተና እና ከዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ እና ከኖርዌይ የሚጠበቀውን ድጋፍ ያመላከተ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል። ፓትርያርክ ቴዎድሮስ ሁለተኛ ከሁለት ዓመት በፊት ህዳር ወር ላይ በተደረገ ሲመት ከእዚህ ዓለም በሞት የተለዩትን አቡነ ሺኖዳን ተክተው የተሾሙ መሆናቸው ይታወቃል።

ከእዚህ በታች ፓትርያርክ ቴዎድሮስ ሁለተኛ በኖርዌይ ባደረጉት ጉብኝት በኦስሎ ''ዱም ሺርኬ'' ቅዳሜ ሰኔ 14/2006 ዓም ባደረጉት የፀሎተ-ቅዳሴ ስነ-ስርዓት በጉዳያችን ጡመራ የተነሱ ፎቶውዎችን ነው። 








ጉዳያችን 

ሰኔ 14/2006 ዓም 
(ጁን 21/2014)

Thursday, June 19, 2014

ሰበር ዜና- ምዕራብ ወለጋ ከጊምቢ እና ቄሌም (እንፍሌ ወረዳ አሽ ቀበሌ) በሺህ የሚቆጠር የአማርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን ተፈናቀሉ።

ፎቶ ከፋይል 


በሺህ የሚቆጠር የአማርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን ከምዕራብ ወለጋ ጊምቢ እና ቄሌም በኃይል አካባቢውን እንዲለቁ ከመደረጉ በላይ  ድብደባ እና ግድያ እንደተፈፀመባቸው ቪኦኤ የአማርኛው አገልግሎት ሰኔ 12/2006 ዓም ምሽት ባስተላለፈው ዘገባ ገለፀ።
ዘገባው የተፈናቃዮችን ምስክርነት እንዳስደመጠው ድብደባው እና ግድያው በከተማው ሕዝብ እና ፖሊስ የታገዘ መሆኑን እና ህይወታቸውን ያተረፉት በኮርኒስ እና ጫካ በመደበቅ መሆኑን ሲገልጡ፣አንድ ምስክርነታቸውን ለቪኦኤ የሰጡ ተፈናቃይ አክለው እንደገለፁት ከጊምቢ ከተማ ብቻ ከሶስት ሺህ በላይ የአማርኛ ተናጋሪ ኢትዮጵያውያን መፈናቀላቸውን ተናግረዋል።ሌላው ምስክርነት ሰጪ ደግሞ ቁጥሩን ከስምንት ሺህ ሕዝብ በላይ አድርሶታል።
አምስት ልጆች የነበራቸው መሆናቸውን የተናገሩት ሌላ ተፈናቃይ የነበራቸው መደብር መዘረፉን እና ካለምንም ሀብት መቅረታቸውን፣ጉዳዩን አቤት ለማለት ወደ ባለስልጣናት ቢሄዱም ሰሚ ማጣታቸውን አስታውቀዋል።
የቪኦኤ ጋዜጠኛ ጉዳዩን አስመልክቶ ቀደም ብሎ የአካባቢው የፀጥታ ጉዳይ ኃላፊ የተባሉ እሳቸው ግን የኦሕዴድ ድርጅት ጉዳይ ኃላፊ ነኝ ያሉ አቶ አወቀ የተባሉ የክልሉ ባለሥልጣን ስለጉዳዩ ሲናገሩ ''ያባረረ የለም' ሲሉ ተደምጠዋል።
የኦሮምያ ክልል የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳይ ኃላፊ ወ/ሮ ራቢያ ኢሳ  ''ሰዎቹ የሄዱት ፈርተው ነው'' ካሉ በኃላ ''ቁጥራቸው ''መቶ አይሞሉም '' ማለታቸው ግርምትን ፈጥሯል።የቪኦኤ ጋዜጠኛ አቶ ሰለሞን በመቀጠል '' ቁጥሩ አይደለም ወሳኙ አንድም ሰው ቢሆን ለምን ተፈናቀለ? ደግሞስ ምን ያስፈራቸዋል? ያብራሩልኝ '' ብሎ ለጠየቃቸው ወ/ሮ ራቢያ አጥጋቢ መልስ መስጠት ሳይችሉ ቀርተዋል።
የኢህአዲግ/ወያኔ የጎሳ ፖለቲካ ሕዝቡን በአካል መለብለብ ከጀመረ ሰነበተ።ሺዎች የእዚህኛው ሌሎች የእዝያኛው ናችሁ እየተባሉ ተፈናቅለዋል።በተለይ አማርኛ ተናጋሪ የሆኑ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ከጉርዳፈርዳ፣ከበንሻጉል፣ከኢልባቦር  እና ከወለጋ አሰቃቂ ግድያ እና ድብደባ እየተፈፀመባቸው ለዘመናት ያፈሩትን ንብረት እየተነጠቁ መባረራቸውን ያመለከቱ ዘገባዎች ሲወጡ የነበረ መሆኑ ይታወቃል።
VOA- Voice of America Amharic service ቪኦኤ አማርኛ አገልግሎት የድምፅ ዘገባ ለመስማት ይህንን ይጫኑ 

ጉዳያችን
ሰኔ 12/2006 ዓም (ጁን 20/2014)



Wednesday, June 18, 2014

የመካከለኛው ምስራቅ ሃይማኖታዊ እና ስልታዊ አቀማመጥን መሰረት ያደረጉ ታሪካዊ ግጭቶች ወደ አፍሪካ በተለይ ወደ አፍሪካ ቀንድ እንዳይዛመቱ ስጋቱ አይሏል።(የጉዳያችን ማስታወሻ)

የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር  አቪግዶር ሊበርማን¨

¨እስራኤል በአፍሪካ የነበራትን  ቦታ ማስመለስ ትፈልጋለች። የ አፍሪካ መሪዎች ከፅንፈኛ እስልምና እንቅስቃሴ ጋር የሚደረገውን ትግል ይቀላቀሉን።¨ የእስራኤል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር  አቪግዶር ሊበርማን
ያለፉት ሁለት ዓመታት ለመካከለኛው ምስራቅ የምጥ አመታት ነበሩ።ሶርያ ማባርያ በሌላው ጦርነት ውስጥ ተነክራለች።ኢራቅ ¨ከድጡ ወደ ማጡ¨ እንዲሉ ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ያላቸው ነውጠኛ እንቅስቃሴ የያዙ ቡድኖች (አይ ኤስ አይ ኤስ-ISIS) ዛሬ ዋናውን የነዳጅ ማምረቻ ቦታ ይዘዋል።በጉዳዩ ላይ ኢራን ሥጋቷን ብቻ ሳይሆን የጦር ኃይሏን ከኢራቅ መንግስት ጎን ላማሰለፍ ዝግጁ መሆኗን ገልፃለች።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የምስራቅ አፍሪካ እና የአፍሪካ ቀንድ የፀጥታ ሁኔታዎች ከጊዜ ወደጊዜ አሳሳቢነታቸው እየባሰ መምጣቱ እየተስተዋለ ነው።የሱማሊያው አልሸባብ ከመዳከም ባለፈ በተከታታይ የአፍሪካ ሕብረት ሰራዊት ዘመቻ ሊጠፋ አልቻለም።ይልቁንም በኬንያ በሚፈፅማቸው የሽብር ጥቃቶች ከ አርባ አምስት ሰዎች በላይ መሞታቸው የያዝነው ሳምንት ዜና ነበር።ሁኔታዎቹ ለጊዜው አይቀጣጠሉ እንጂ በአፍሪካ ቀንድ ሃገራት ተመሳሳይ አደጋዎች አንዣበዋል።
ሱዳን የውስጥ ችግሯን ለመፍታት ጥረት ስታደርግ ብትታይም የጦር መሳርያ   ግዥዋን ግን ቀጥላበታለች።የደቡብ ሱዳን ግጭት እንደቀጠለ ነው።ኢትዮጵያን በጎሳ ፖለቲካ የሚመራው ኢህአዲግ/ወያኔ ከእስልምና ተከታዮች ጋር የገባው ውዝግብ መድረሻው ገና አልታወቀም።ኤርትራ ቆላው ክፍል አልፎ አልፎ የሚሰሙ የፅንፈኛ እስልምና አራማጆች እንቅስቃሴ በመሳርያ ኃይል የተደገፈ እንቅስቃሴ የመኖሩ ከመሰማቱ በላይ የወታደራዊ መፈንቅል እንቅስቃሴ ከተደረገ ገና አንድ ዓመት ማስቆጠሩ ነው።የእንቅስቃሴው መሪዎች በአቶ ኢሳያስ ፈላጭ ቆራጭ አመራር የተማረሩ ብቻ ሳይሆኑ የፅንፈኛ እስልምና አራማጆች እንደተገኙበት የሚገልፁ ዘገባዎች ተደምጠዋል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ነው እንግዲህ እስራኤል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯን ልካ የአፍሪካ ሃገራትን ለመጎብኘት የተነሳችው። ጉዳዩ ከተራ ጉብኝት ጋር የተያያዘ አይመስልም።ይልቁንም ከፀጥታ ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ውሎችን ማድረግዋ ጉዳዮቹን የበለጠ የማወሳሰብ እና ከመካከለኛው ምስራቅ ሃገራት ችግር ጋር የማዛመዱ ዕድል ከፍተኛ ነው።
እስራኤል በራሷ በአፍካ ቀንድ መገኘት ከአልቃይዳ የአፍሪካን ቀንድ ለማመስ መንቀሳቀስ ጋር ተዳምሮ ጉዳዩን እሳትና ጭድ እንዳያደርገው ነው ስጋቱ። የእስራኤሉ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ሰሞኑን አዲስ አበባ ሲገቡ የተከተላቸው የልዑካን ቡድን አባላት ብዛት ከ50 በላይ ነበሩ።

ጉዳያችን
ሰኔ 12/2006 ዓም  (ጁን 19/2006) 

Friday, June 6, 2014

በማንነት ጥያቄ እና አጠቃላይ የወደፊት የኢትዮጵያ አቅጣጫ ላይ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ውይይት በኦስሎ (ቪድዮ ክፍል 2)

ቪድዮ ክፍል 2
በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ግንቦት 16/2006 ዓም (ሜይ 24/2014) በማንነት ጥያቄ እና አጠቃላይ የወደፊት የኢትዮጵያ አቅጣጫ ላይ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ውይይት ''በባትሬት'' ኦስሎ ውስጥ ተደርጎ ነበር።ውይይቱ የተለያዩ አመለካከት ያላቸው ሁለት ግለሰቦች በወቅቱ ሁኔታዎች ላይ ካቀረቡ በኃላ ውይይቶች ተደርገዋል።በውይይቱ ላይ አቶ ግደይ ዘርአፅዮንን (የህወሃት ሰባቱ መስራቾች አንዱ) እና ዶ/ር ሙሉዓለምን ጨምሮ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ተገኝተው ነበር።

የአመለካከቶቹ አቅራቢዎች

1/ አቶ ገረመው በኦሮሞ ብሔር ማንነት ጋር በተያያዘ የተለያዩ ስራዎች ሰርተዋል።
2/ አቶ ጌታቸው በቀለ የእዚህ የጉዳያችን ጡመራ አዘጋጅ ነው።
በማንነት ጥያቄ እና አጠቃላይ የወደፊት የኢትዮጵያ አቅጣጫ ላይ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ውይይት በኦስሎ (ቪድዮ ክፍል 2)



ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG

Wednesday, June 4, 2014

በማንነት ጥያቄ እና አጠቃላይ የወደፊት የኢትዮጵያ አቅጣጫ ላይ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ውይይት በኦስሎ (ቪድዮ ክፍል 1)

በማንነት ጥያቄ እና አጠቃላይ የወደፊት የኢትዮጵያ አቅጣጫ ላይ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ውይይት በኦስሎ (ቪድዮ ክፍል 1)
በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ግንቦት 16/2006 ዓም (ሜይ 24/2014) በማንነት ጥያቄ እና አጠቃላይ የወደፊት የኢትዮጵያ አቅጣጫ ላይ ባሉ ነባራዊ ሁኔታዎች ላይ ያተኮረ ውይይት ''በባትሬት'' ኦስሎ ውስጥ ተደርጎ ነበር።ውይይቱ የተለያዩ አመለካከት ያላቸው ሁለት ግለሰቦች በወቅቱ ሁኔታዎች ላይ ካቀረቡ በኃላ ውይይቶች ተደርገዋል።በውይይቱ ላይ አቶ ግደይ ዘርአፅዮንን (የህወሃት ሰባቱ መስራቾች አንዱ) እና ዶ/ር ሙሉዓለምን ጨምሮ ሌሎች ኢትዮጵያውያን ተገኝተው ነበር።

የአመለካከቶቹ አቅራቢዎች

1/ አቶ ገረመው በኦሮሞ ብሔር ማንነት ጋር በተያያዘ የተለያዩ ስራዎች ሰርተዋል።

2/ አቶ ጌታቸው በቀለ የእዚህ የጉዳያችን ጡመራ አዘጋጅ ነው።

ክፍል 1



ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG

Monday, June 2, 2014

ሁለት አዳዲስ የራድዮ መርሃግብር ስርጭቶች በኢንተርኔት አገልግሎታቸውን ጀመሩ።ይበርቱልን!

ሚልዮኖች እንደመሆናችን በተለያዩ አቀራረቦች እና  ስልቶች የሀገራችን ምሁራን ሊያንፁን ይገባል።ያደጉትን ሀገሮች ትተን የአፍሪካ ሃገራትን ለምሳሌ እንደ ዑጋንዳ ያሉ ሀገሮች በዋና ከተማቸው ብቻ ከሃምሳ በላይ ኤፌ ኤም ራድዮኖች አሉ።ሕዝብ እንደምርጫው ይሰማል እራሱን ያይበታል።መገናኛ ብዙሃኗ በአፈና መንግስት በታገተባት ሀገራችን ኢትዮጵያማ ምን ያህል እንደሚቀረን ከእዚህ መረዳት ይቻላል።ኢትዮጵያ ወጣቶቿ እየደረሱላት ነው።ሁለት አዳዲስ የራድዮ መርሃግብሮች ወደ መስመር ገብተዋል።የመገናኛ ብዙሃን በተለያየ አቀራረብ እና ፈጠራዎች በተለይ በዲያስያስፖራው እንዲሁም በተለያዩ መንገዶች ለሚሰማው የሃገርቤት ነዋሪ የራሳቸውን በጎ ተፅኖ መፍጠራቸው ሳይታለም የተፈታ ነው።እናም እናበረታታቸው።አይዟችሁ ምን እናግዝ? እንበላቸው።እኛ መናገር ቢያቅተን የሚናገሩልንን ሃሳብ የሚያመነጩትን ማበረታታት ተገቢ ነው።

ባሳለፍነው ሳምንት ውስጥ ቀደም ብለው ለነበሩ ኢትዮጵያውያን የብሮድካስት ስርጭቶች ተጨማሪ እገዛ የሚያደርጉ ግን ደግሞ አስፈላጊ የሆኑ አዳዲስ የራድዮ መርሃግብር ስርጭቶች ተጀምረዋል።

የመጀመርያው ''ዋዜማ'' የተሰኘ ራድዮ ሲሆን ስለ ዋዜማ / About Wazema በሚለው አርዕስት ስር እንዲህ ይላል -


“ዋዜማ ሬዲዮ” በስደት ባሉ ጥቂት ኢትዮጵያውያን የተቋቋመ ሳምንታዊ የፖድካስት ሬዲዮ ስርጭት ነው። ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያውያንን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ ልንጨዋወት መክረናል። እግረመንገዳችንን ጎረቤቶቻችንን የሚመለከቱ ጉዳዮች ስናነሳ ብንገኝም የእንግዳ ተቀባይነት ወጋችን ሆኖብን ነው።
አዘጋጆቹ መስፍን ነጋሽ፣ ደረሰ ጌታቸው፣ አርጋው አሽኔ እና መዝቡ ኃይሉ ነን። ብቻችንን ግን አይደለም፣ አብረውን የሚጓዙ መደበኛ ተሳታፊዎችም ይኖሩናል።
ዝግጅቶቻችን አገራችን እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሽግግር ለማድረግ እንድትችል የሚመኙ ናቸው። ዓላማችን ማንኛውም የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ወይም ሌላ አይነት ቡድን የማይቆጣጠረው አንድ ተጨማሪ የውይይት መድርክ መፍጠር ነው።
ዋዜማ ሬዲዮ!

''ዋዜማ'' ራድዮ ከፖለቲካዊ ጉዳዮች በተጨማሪ ማኅበራዊ እና ኪነጥበባዊ ዝግጅቶችም ተካተውበታል።
ድረ-ገፁን ከእዚህ በታች ያለውን በመንካት ማዳመጥ ይችላሉ http://www.wazemaradio.com 

ሁለተኛው በተለይ በኖርዌይ እና አካባቢ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እንቅስቃሴ ላይ የሚያተኩር ነገር ግን ለመላው ዓለም በኢንተርኔት የሚዳረሰው ''የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ'' በተሰኘ በኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ለማምጣት የሚሰሩ ግለሰቦችንም ሆነ ድርጅቶች በተለያየ መንገድ የሚደግፍ ድርጅት የተጀመረ ነው።


በድረ-ገፁ ላይ  ''የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ'' እንዲህ የሚል አረፍተ ነገር አለ -
''ሰላም ጤና ይስጥልኝ መላው የስርጭታችን ታዳሚዎች ዛሬ ወረሃ ግንቦት 23ኛ ቀን ላይ እንገኛለን የዴሴሶን ራዲዮ የሙከራ ፐሮግራም ለመጀመሪያ ግዜ ለአድማጭ የሚደርስበት ቀን ነው ::ክብራትና ክቡራን ኢትዮጲያውያን ወገኖቻችን ለዘመናት ያጣነውን ስላምና እኩልነት ለማስመለስ የሚታገለው ዴሞክራሲያዊ ለውጥ ድጋፍ ድርጅት በኖርዌይ የራዲዮ ስርጭቱን ለአየር ማዋል የቻልበት የመጀመሪያ ቀን ላይ በመድረሳችን በመላ ኖርዌይ ለሚገኙ አባላትና ለደጋፊዎቻችን የደስታ መልእክታችን ይደረሳችሁ::
ዝግጅቶቻችን ዘወትር ቅዳሜ ለአድማጭ ይደርሳል በቅርቡ ቆሚ ዝግጅቶቻችንን እናቀርብላችኋለን ይጠብቁን !!''
''የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌይ'' ራድዮ ድረ-ገፅ http://www.dceson.no/news/2014/05/31/dceson-radio-opening-program-may-31-05/ ነው።

ከላይ የተጠቀሱት ራድዮኖች ለኢትዮጵያውያን በጎ መንገዶችን ማመላከት ብቻ ሳይሆን ቀደም ብለው ለነበሩ የብሮድካስት አገልግሎቶችም ሆነ በኢትዮጵያዊነት ዙርያ የተሻለ ለሚያልሙ ሁሉ አጋዥ፣መንገድ አመላካች፣እና አዳዲስ ሃሳቦች አመንጪ እንደሚሆኑ ይታሰባል።ይበርቱልን!

ጉዳያችን 
ግንቦት 25/2006 ዓም (ጁን 02/2014)


ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።