ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, September 30, 2013

በኢትዮጵያ ከሰማይ የወረደው መስቀል ጉዳይ..በሶርያ ሰሞኑን የተሰራው ተአምር... (የቪድዮ ትምህርት ዲ/ን ዳንኤል ክብረት)

በእዚህ በያዝነው ወር መስከረም 18/2006 ዓም (september 28/2013 ዓም እ.አ.አቆጣጠር) የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ከሰማይ ወረደ ተብሎ ስለተነገረው መስቀል መሰረት አድርጎ እንዲህ ዘግቦ ነበር-
''በአቃቂ ቃሊቲ ገላን ጉራ ፈለገ ግዮን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን፣ ባለፈው ነሐሴ ወር መጨረሻ ከሰማይ ወረደ ስለተባለው መስቀል፣ ቅዱስ ሲኖዶስ መርምሮ ውሳኔ  እንደሚያስተላልፍ በአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የፓትርያርኩ ረዳትና የጅማ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ አስታወቁ፤ ሕዝቡ የቅ/ሲኖዶሱን ውሳኔ በትዕግሥት እንዲጠባበቅ ብፁዕነታቸው አሳስበዋል....''

ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ከሰማይ የወረደው መስቀል ጋር በተያያዘ  በአጠቃላይ ስለ ተአምራት እንዲሁም በቅርቡ በሶርያ ሀገር በሀገሪቱ ቴሌቭዥንም ጭምር  ከተናኘው ሌላ ተአምር ጋር አያይዞ በአዲስ ዓለም ማርያም  ሰሞኑን ያስተማረው ትምህርት ወቅታዊ ግንዛቤ ይሰጣል።ይመልከቱት።




ጉዳያችን GUDAYACHNgetachewb221@gmail.com

Saturday, September 28, 2013

እኛ ኢትዮጵያውያን ምን ነካን? (የጉዳያችን ጡመራ ልዩ ማሳሰቢያ)



መስከረም 19/2006 ዓም (ሴፕቴምበር 29/2013 ዓም) ''ዓለም አቀፍ የቡና ቀን'' ይከበራል።በዓሉ በዓለም ዙርያ የአከባበሩ ስነ-ስርዓት እየደመቀ መጥቷል። በ1983 ዓም እ.አ.አቆጣጠር በጃፓን ለመጀመርያ ጊዜ መከበር እንደተጀመረ የተነገረለት ''ዓለም አቀፍ የቡና ቀን'' በመጀመርያዎቹ ተከታታይ አመታት ብዙም ትኩረት አላገኘም ነበር።ሆኖም ግን ከ2005 ዓም እ.አ.አቆጣጠር ወዲህ ግን በተለይ በአሜሪካ ከፍተኛ ትኩረት እየተሰጠው ነው።

ለምሳሌ ዛሬ መስከረም 19/2006 ዓም (ሴፕቴምበር 29/2013 ዓም) በአሜሪካ የሚገኙ የቡና መጠጫ ካፌዎች በነፃ ቡና ለደንበኞቻቸው በማቅረብ በአሉን ያከብራሉ። ግዙፉ የቡና አጠጪ ድርጅት ስታርባክስ (Starbucks)  በዓሉን እንዴት እንደሚያከብር ሲገልፅ በድህረገፁ ላይ ከእዚህ በታች የምትመለከቱትን የኢትዮጵያን የቡና ጀበና ፎቶ ጋር የሚከተለውን ከትቦ ነው።
''እሁድ ብሔራዊ የቡና ቀን ነው።ኑ! በአሉን በነፃ በምናቀምስዎ  በአዲሱ የኢትዮጵያ ቡና ያክብሩ።'' ይላል ከጀበናው በታች ያለው ፅሁፍ ትርጉም ደግሞ እንዲህ ይነበባል- ''እሁድ መስከረም 29 በስታርባክስ መሸጫዎች ቡና ከተገኘባት ሀገር ከኢትዮጵያ  የመጣውን አዲሱን  ቡና ቀምሰው ያጣጥሙ።'' ይላል።
''Come into a participating Starbucks store this Sunday, September 29 for a taste of our new Ethiopian coffee and discover flavors from the birthplace of coffee.''


ስታር ባክስ ለመስከረም 29/2013 ዓም ዓለም አቀፍ የቡና ቀንን በድህረ ገፁ እና በማስታወቂያ ሰሌዳ ያስተዋወቀበት ፖስተር  (http://www.starbucks.com)


በእዚህ የቡና ዓለም አቀፍ በዓል ቀን ስታርባክስ ብቻ ሳይሆን የሚሳተፈው ለምሳሌበአሜሪካዋ ግዛት በአትላንታ ብቻ

 - ካሪቡ ኮፊ (Caribou Coffee) በበዓሉ ቀን ሙሉ ለሚመጣው ሰው  ሁሉ በትንሽ የቡና ስኒ በነፃ ስያጠጡ ይውላሉ፣

 - ዱኪን ዶኑትስ (Dunkin' Donuts) ትኩስ እና ቀዝቃዛ ቡና  በልዩ ሳሎን ደንበኞቹን በነፃ ያጠጣል፣

 - ማክዶናልድ (McDonalds)  የተቆላ ቡና በተመረጡ ቦታዎች በነፃ ያቀርባል፣

 - ስታርባክስ (Starbucks) በኢትዮጵያ የቡና መጠጫ ስኒዎች ልዩ ጣዕም ያለው የኢትዮጵያ ቡና ለደንበኞቹ ሁሉ ያቀርባል።

ከሁሉ ጉዳዩን አሳሳቢ የሚያደርገው በዓሉን የተቀረው ዓለም እንዲህ ሲያከብረው እኛ ማክበሩ ባይሳካልን ስለበዓሉ አንዳች አለመተንፈሱ ነው አስደንጋጩ ጉዳይ። የኢትዮጵያ ቆንስላዎች ምንድነው የሚሰሩት? የእዚህ አይነቱን ሃገራዊ ጉዳይ ብሔራዊ ሀብት ማፍርያ አድርገው ማቅረብ ካልቻሉ ሌላ ስራቸው ምን ሊሆን ነው?ቡና በዓለም ላይ ለመጀመርያ ጊዜ የተገኘው ከኢትዮጵያ መሆኑን ከውክፕድያ እስከ ታዋቂው ስታርባክስ ድህረገፆች የሚያስነብቡን እውነታ ነው።

ቡና ማለት አሁን ላለው ዓለም በተለይ ለምዕራቡ ዓለም የእያንዳንዱ ሰው የደምስር ያህል አስፈላጊው መሆኑን መንገር ማጋነን አይደለም።መኪና ካለነዳጅ እንደማይሰራ ሁሉ የምዕራቡ ዓለም ሕዝብ ከፕሬዝዳንት እና ጠቅላይ ሚኒስትር እስከ ቢልየነር፣ከሶፍትዌር ጠቢብ እስከ የጠፈር ተመራማሪ ቢያንስ በቀን አንድ ሲኒ ቡና ካልቀመሰ ስራው ሁሉ መበላሸቱ ነው።ይህ በትንሹ የተቀመጠ ስሌት ነው።በሰኔ ወር 2005 ዓም በወጣ የስታትስቲክስ ዘገባ  ከአሜሪካ ሕዝብ  54 በመቶው በላይ የቡና ሱሰኛ መሆኑን መዘገቡ እና አሜሪካ ቡና ከውጭ ለማስገባት በዓመት የምታወጣው የገንዘብ መጠን ከ 4 ቢልዮን ዶላር የማያንስ መሆኑን የሚገልፀው ጥናት በራሱ የቡናን ተፅኖ የመፍጠር አቅሙን በአግባቡ የሚያመላክት ነው። http://www.statisticbrain.com/coffee-drinking-statistics/



ኢትዮጵያውያን ምን ነካን?



ቡና ከኢትዮጵያ የመገኘቱ ያማያሻማ ማስረጃ የመጠቀሱን ያህል፣የኢትዮጵያ ቡና ቃና እና ጣዕም ልዩ እና የተወደደ የመሆኑን ያህል እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ልዩ የቡና አፈላል ባህል ባለቤት መሆኑ ሀገራችንን በጎ ጎን የምናስተዋውቅበት ልዩ ወርቃማ ዕድል ነው።ለእዚህ ደግሞ አይነተኛ አጋጣሚው  የእዚህ አይነቱ የዓለምአቀፍ የቡና ቀን ነው።ኢትዮጵያ ይህንን ቀን በልዩ ዝግጅት ለምሳሌ


  •   ልዩ የሆነ የቡና ማፍላት ስርዓት ከመስቀል አደባባይ በማዘጋጀት እና በቀጥታ እንደ ስታርባክስ ያሉ ድርጅቶች ስፖንሰር እንዲያደርጉት እና ከፍተኛ የሚድያ ሽፋን በውጭ ሀገርም ደረጃ በማሰጠት ታዋቂ ማድረግ እና ሃገርን በማስተዋወቅ፣


  •  ቡና ከኢትዮጵያ መገኘቱ ላይ አፅንኦት ሰጥቶ ይህንን የሚያስተዋውቅ ጥናታዊ ፊልም ፣ዎርክ ሾፕ፣ወዘተ በማካሄድ ጉዳዩን በየዓመቱ ማንሳት እና ለቀረው ዓለም ማስተዋወቅ፣


  •  የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለአንዲት ስኒ የምትሆን ትንሽ ተቆልታ የተፈጨች ቡና (ቡና ከኢትዮጵያ መገኘቱን የሚገልፅ ፅሁፍ ለጥፎ) በላስቲክ አሽጎ ለደንበኞቹ በመስጠት ቢያስተዋውቅ።የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓመት እስከ አንድ ሚልዮን ደንበኞች የማመላለሱን አቅም ስንመለከት በአንድ ዓመት ለስንት የዓለማችን ሰዎች ማስታወቅያው እንደሚዳረስ መገመት ይቻላል።


  •  በመጨረሻም ባለ ሁሉም ኮኮብ ሆቴሎች ከውጭ ለሚመጡ ደንበኞቻቸው ከሆቴሉ መግቢያ ላይ የቡና ማፍላት ስነ-ስርዓት እንዲኖራቸው እና ለደንበኞች ለቅምሻ ያህል በትንሹ ማቅመስ እንዲችሉ ማድረግ እና የቡናውን ጣዕምም ሆነ የቡና መገኛ ሀገር ኢትዮጵያን እንዲያስተዋውቁ ማድረግ  የመሳሰሉት ስራዎችን ጠንክሮ መስራት ጥቅሙ ዘርፈ ብዙ ነው።እዚህ ላይ ለሆቴሎች ወጪ መሸፈኛ መንግስት  ከሚቀበላቸው የገቢግብር ውስጥ  ከ0.05 ፐርሰንት በታች ለእዚሁ ተግባር ቢቀንስላቸው እና ስራው መሰራቱን መቆጣጠር ቢችል እንደሀገር የሚያመጣው ጥቅም እጅግ ላቅ ያለ በሆነ ነበር።ይህ ሥራ ከቱሪዝም እስከ ውጭ የሚገኙ ኢምባሲዎች ትኩረት ሊሰጡት የሚገባ እና ከፍተኛ ብሔራዊ ጥቅም ያለው ትልቅ አጀንዳ ነው።አሜሪካ በእኛው ቡና እንዲህ የሕዝቧን ማህበራዊ፣ምጣኔ ሃብታዊ እና አእምሮአዊ  ደህንነትን ስትጠብቅ እኛ ለመልካም ገፅታ ግንባታ በተገቢው መልክ አለመስራታችን አሳዛኝ ነው።ለእዚህም ነው እኛ ኢትዮጵያውያን ምን ነካን? ለማለት የሚዳዳው።መልካም ዓለም አቀፍ የቡና ቀን።


አበቃሁ
ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ




Thursday, September 26, 2013

የመስቀል ደመራ በዓልን በዓለም አቀፍ ቅርስነት በዩኔስኮ የማስመዝገብ ሂደት ያለበት ሁኔታ (አጭር ዜና)

የመስቀል ደመራ በዓልን በዩኔስኮ (የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣የሳይንስ እና የባሕል ኮሚሽን) በዓለም አቀፍ ቅርስነት ለማስመዝገብ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ማመልከቻ አቅርባ እንደነበር ይታወቃል።ይህንንኑ የምዝገባ ሂደት የሚመለከተው የዩኔስኮ ልዑካን በዛሬው የአዲስ አበባ የመስቀል ደመራ በዓል ላይ ተገኝተው ነበር።በነገራችን ላይ በዓለም ላይ ካሉ ሀገሮች ውስጥ 300 ቅርሶች የመዝገቡልን ጥያቄ ለዩኔስኮ ቀርበው 240 ዎቹ ውድቅ ሲሆኑ 60 ጥያቄዎች በዩኔስኮ እየተጠኑ ነው።ከእነኚህ 60 ''የዓለም ቅርስ'' ምዝገባ ጥያቄ ውስጥ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሚከበረው የደመራ መስቀል በዓል አንዱ ሆኗል።በዛሬው የደመራ በዓል ላይ የተገኘው የዩኔስኮ ልዑካን ቡድን በዓሉን በዓለም ቅርስነት እንደሚመዘግብ ተስፋ እናደርጋለን።

በመሰረቱ የመስቀል ደመራ በዓል ማክበር ከሚገባቸው ሃገራት ውስጥ አውሮፓውያን ዋነኞቹ ሊሆን ይገባቸው ነበር (http://gudayachn.blogspot.no/2013/09/blog-post_22.html)።ለዘመናት  ተቀብሮ የነበረው የክርስቶስ መስቀል በሮሙ ንጉስ ቆስጠንጢኖስ እናት ንግስት እሌኒ መገኘቱን ሳስብ አውሮፓ ማክበሩ ባይሳካላት በክብር ለያዘችው ኢትዮጵያ የዓለም ቅርስ ሆኖ እንዲከበር ማገዝ ይገባታል ለማለት እደፍራለሁ። ከእዚህ ጋር በተያያዘ በዓሉ የዓለም ቅርስ ሆኖ የመመዝገቡ ፋይዳ ብዙ ነው።ከፋይዳዎቹ ውስጥ የሚጠቀሰው በዓለም አቀፍ ደረጃ የማስተዋወቁ ሥራ ከመጠናከሩ በላይ የቱሪስት ፍሰት እንደሚጨምር ይታመናል።በመሆኑም ዩኔስኮ በዓሉን በዓለም አቀፍ ቅርስነት እንዲመዘግብ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች ምን ማድረግ ይችላሉ? መጤን ያለበት ጥያቄ ነው።


ዩኔስኮ አንድን ቅርስ ወይም ባህላዊ ስርዓት በዓለም ቅርስነት ለመመዝገብ ከእዚህ በታች ያሉትን አስር መስፈርቶች ቢያንስ አንዱን ማሟላት እንዳለበት መተዳደርያ ደንቡ ያዛል።በዓለም ቅርስነት ምዝገባውን የሚያፀድቀው ኮሚቴ የሚሰበሰበው በዓመት አንዴ መሆኑ ይታወቃል።
ዩኔስኮ በዓለም ቅርስነት ለመመዝገብ የሚያስቀምጣቸው አስሩ መስፈርቶች ከእዚህ በታች የተጠቀሱት ናቸው።


  1. (i)  represent a masterpiece of human creative genius;
  2. (ii)  exhibit an important interchange of human values, over a span of time or within a cultural area of the world, on developments in architec- ture or technology, monumental arts, town- planning or landscape design;
  3. (iii)  bear a unique or at least exceptional testimony to a cultural tradition or to a civilization which is living or which has disappeared;
  4. (iv)  be an outstanding example of a type of build- ing, architectural or technological ensemble or landscape which illustrates (a) significant stage(s) in human history;
  5. (v)  be an outstanding example of a traditional human settlement, land-use, or sea-use which is representative of a culture (or cultures), or human interaction with the environment espe- cially when it has become vulnerable under the impact of irreversible change;
  6. (vi)  be directly or tangibly associated with events
    or living traditions, with ideas, or with beliefs, with artistic and literary works of outstanding universal significance. (The Committee considers that this criterion should preferably be used in conjunction with other criteria);

  7. (vii)  contain superlative natural phenomena or areas of exceptional natural beauty and aesthetic importance;
  8. (viii)  be outstanding examples representing major stages of earth’s history, including the record of life, significant on-going geological processes in the development of landforms, or significant geomorphic or physiographic features;
  9. (ix)  be outstanding examples representing signifi- cant on-going ecological and biological processes in the evolution and development of terrestrial, fresh water, coastal and marine ecosystems and communities of plants and animals;
  10. (x)  contain the most important and significant natural habitats for in-situ conservation of biological diversity, including those containing threatened species of outstanding universal value from the point of view of science or conservation.
    ለአስሩ መስፈርቶች ምንጭ- http://whc.unesco.org/uploads/activities/documents/activity-567-1.pdf  

ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ  

Friday, September 20, 2013

የኢትዮጵያ የጦር ኃይል ጉዳይ እና ሁለቱ የአስተሳሰብ ጥጎች




የጦር ኃይል አንዲት ሀገር ለህልውናዋ እና እንደ ሀገር ለመቀጠልም ሆነ ላለመቀጠል ወሳኝ ከሆኑት ጉዳዮች ውስጥ ነው።ዓለም የሚመራው በሕግ እና በሥርዓት ብቻ ነው ብሎ ለማመን የሚያዳግተው ያለፉትን የዓለማችንን ሁኔታ ስንቃኝ ነው።ከኢንዱስትሪው አብዮት ወዲህ ኢትዮጵያ ዘመናዊ የጦር ኃይል መገንባት ከጀመረች ከአንድ መቶ ዓመት በላይ ሆኗታል።ይህ ማለት የአፄ ምኒሊክ የመጀመርያውን መደመብኛ ወጥቶ አደር (ወታደር) ከመሰረቱ ጊዜ ያለውን ታሳቢ ያደርጋል።በቀዳማዊ ሃይለስላሴ ዘመን ኢትዮጵያ በኢጣልያ ወረራ በተለይ ከአየር ላይ በሚጣሉ የመርዝ ጋዝ መበለጧ በንጉሱም ሆነ በተራው ኢትዮጵያዊ ዘንድ እጅግ የሚያንገበግብ እና የትምህርት እና የስልጣኔን አስፈላጊነት ከሁሉም በላይ ቀዳሚ መሆን እንዳለበት ከነፃነት በኃላ እንዲታመንበት ያደረገ ጉዳይ ነበር።''በምድር የመጣው መች አቃተን በሰማይ በማናውቀው መንገድ መጣብን እንጂ'' የምትለው አባባል ከአዝማሪ እስከ ንጉሡ ድረስ የምትነገር አባባል እንደነበረች በወቅቱ የተከተቡ ፅሁፎች በተለያየ መንገድ ገልፀውታል።

የኢትዮጵያ ባህር ኃይል 

የቀዳማዊ ሃይለስላሴ መንግስት ካደራጃቸው የጦር ክፍሎች ውስጥ በብቃቱ እና ከፍተኛ የተማረ የሰው ኃይል በመያዝ የአየር ኃይል እና የባህር ኃይል ሰራዊት ላቅ ያለ ስፍራ ነበራቸው።በተለይ የአየር ኃይላችን በመጀመርያ በእንግሊዞች ቀጥሎ በአሜሪካኖች በኃላ ላይ በስዊድን  ያገኘው ስልጠና እና የባህር ኃይል ደግሞ ከኖርዌይ መንግሥታት በተደረጉ የስልጠና ድጋፎች በልምድም በችሎታም ብቃት ያለው የሰው ኃይል ለማፍራት ችለዋል።የቀዳማዊ ሃይለስላሴ ዘመን አንዱ በጎ አጋጣሚው በእነኚህ ስልጠናዎች የተገኘው የሰው ኃይል በተከታታይ ጦርነት በመሳተፍ የሰው ኃይሉን አለማመናመኑ ነበር።

ቀዳማዊ አፄ ሃይለስላሴ ከቀድሞዋ ዩጎዝላቭ መሪ ጆስፕ ብሮዝ ቲቶ ጋር የባህር ኃይል ሲጎበኙ

በዘመነ ደርግ ከተመለከትን የኢትዮጵያ የጦር ኃይል በብቃት የሚታማ ደረጃ አልነበረም።ከምዕራባውያን ይገኝ የነበረው የመሳርያ እና የስልጠና ድጋፍ ወደ ምስራቅ አውሮፓ እና ወደ ቀድሞዋ ሶቭየት ህብረት መዞሩ አንዱ አይነተኛ ለውጥ ሆነ። በዘመነ ደርግ የነበረው አንድ በጎ ነገር ከውስጡ የወጡ የሰራዊቱን ሕይወት የሚያውቁ የበታች መኮንኖች ስልጣን ላይ መምጣታቸው ብቻ ሲሆን ነገር ግን ለሰራዊቱ ምን አዲስ ነገር መጣ? ለሚለው ጥያቄ በእዚች ትንሽ ፅሁፍ ለማንሳት አልፈልግም።
ኮ/ል መንግስቱ ሃይለማርያም ለሰራዊቱ ንግግር ሲያደርጉ

ሆኖም ግን በዘመነ ደርግ  ሰራዊቱ የነበሩበት ችግሮች ሶስት እንደነበሩ ማንሳት ይቻላል።እነርሱም

1/ የሰራዊቱ መኮንኖች በባህር ኃይልም ሆነ በአየር ኃይል የነበሩት ከፍተኛ ልምድ እና የትምህርት ዝግጅት ያላቸው ቢኖሩበትም ከፍተኛውን የመንግስት ስልጣን የያዙት የደርግ አባላት በመስመር መኮንነት እና በዝቅተኛ የትምህርት ዝግጅት ላይ በመሆናቸው ውሳኔዎች በትክክለኛ የወታደራዊ ሳይንስ ላይ እንዳይመሰረቱ ማድረጉ፣

2/ ከፍተኛ ልምድ እና የትምህርት ዝግጅት ያላቸው መኮንኖችም ሆኑ የሰራዊቱ አባላት ከደርግ ጋር በነበረው ቅራኔ (ለምሳሌ የግንቦት ስምንቱን በኮሎኔል መንግስቱ ሃይለማርያም ላይ የተቃጣውን የመፈንቅለ መንግስት መጥቀስ ይቻላል) እንዲዳከም መደረጉ፣

3/ በሰሜናዊ ኢትዮጵያ የነበረው የተራዘመ ጦርነት ሰራዊቱ ያለውን አቅም በሙሉ በእዚህ ውግያ ላይ ለ አስራሰባት ዓመት እንዲያሳልፍ ማድረጉ የሚሉት የሚጠቀሱ ናቸው።

በ 1983 ዓም ኢህአዲግ-ወያኔ አዲስ አበባ ሲገባ የቀደመውን ሰራዊት በጠላትነት ከመፈረጅ ባለፈ የብዙዎች የጡረታ እና የሕክምና ወጪአቸው ተዘጋ።የሰራዊቱ አባላት በየመንገዱ ተመፅዋች ሆኑ።ከሁሉም የሚያሳዝነው ደግሞ ከሁለት ትውልድ በላይ በጦር ካምፖች አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ባሎቻቸው እና አባቶቻቸውን በጦርነቱ ያጡ እናቶች እና ሕፃናት ካለምንም ካሳ መኖርያ ቤታቸውን እንዲለቁ እየተደረጉ በአዲሱ ሰራዊት ቤተሰቦች ተተኩ።በእዚህም ሳብያ ዘመድ ያላስጠጋቸው የጎዳና ተዳዳሪ ሆኑ።ይህ ሁሉ ከሆነ ከሰባት ዓመት በኃላ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ሲነሳ የቀድሞ ሰራዊት አባላትን በመብራት የመፈለግ ሥራ ኢህአዲግ-ወያኔ ተያያዘው።በእስር ቤት የታጎሩ መኮንኖች ''ኑና አማክሩን'' ተብለው ከጥቅማጥቅም ጋር ተጠሩ።በሱዳን እና ኬንያ ሀገር ጥለው ከብዙ ፈተና በኃላ አሜሪካ እና ካናዳ የገቡ የቀድሞ የአየር ኃይል አብራሪዎች ልዩ ልዑክ እየተላከ ተለምነው እንዲመጡ ተደረጉ።ጥቂቶች ለሀገሬ ብለው መጡ።የተቀሩት ''ስልቻ ቀልቀሎ፣ቀልቀሎ ስልቻ'' ለሀገር አስቦ አይድለም ብለው ቀሩ።
አቶ መለስ ዜናዊ እጩ መኮንኖች ሲመርቁ

ጦርነቱ በአጭር ጊዜ የአስር ሺዎችን ሕይወት ቀጥፎ እንዳበቃ ኢህአዲግ-ወያኔ እንደገና ሥራ ጀመረ።በዘመነ ኢህአዲግ-ወያኔ ጊዜ የኢትዮጵያ ሰራዊት የገጠሙት ችግሮች በደርግ ዘመን ከገጠሙት በዓይነትም በይዘትም ይለያያሉ። ችግሮቹን በሶስት ነጥብ ማጠቃለል የሚቻል ይመስለኛል።

1/ የኢህአዲግ-ወያኔ ታጋይነትን ከብቃት በፊት ማስቀደም ይህም ከወያኔ የትጥቅ ትግል ጋር የነበሩትን በችሎታም ሆነ በትምህርት ዝግጅት ምንም ያህል ብቃት ባይኖራቸው እስከ ጄኔራልነት ማዕረግ እየሰጡ ከዓለም አቀፍ የወታደራዊ ሳይንስ አሰራር በወጣ  መልክ መሄድ፣

2/ ሰራዊቱን ሕዝባዊ ለማድረግ አለመቻል።እዚህ ላይ በዋናነት የሚጠቀሰው የብሔር ተዋፅኦ ሁሉን ባማከለ አለመሆኑ ሲሆን እዚህ ላይ ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ከከፍተኛ መኮንኖች እስከ መስመር ድረስ ያሉትን ከአንድ አካባቢ በመጡ ሰዎች መሙላት እና ይህም ሃገራዊ ራዕይን በአካባቢያዊ ራዕይ እንዲተካ ያደረገ አደገኛ አዝማምያ ነው።

3/ ሰራዊቱ የቆመለት ቀዳሚው የሀገር ሉዓላዊነት ጥያቄ ከኢትዮጵያ ጥቅም አንፃር የሚወስዳቸው እርምጃዎች አለመታየታቸው።ኢትዮጵያ ከሉአላዊነት አንፃር የሚነሱ በእንጥልጥል ላይ ይሉ በርካታ ጉዳዮች አሁንም አሉ።ለምሳሌ ከሰማንያ ሚልዮን ሕዝብ በላይ በሃያ እና በሰላሳ ኪሎሜትሮች እርቀት ሆኖ ነፃ የባህር ወደብ አገልግሎት አለማግኘቱ እና ከሱዳን ጋር ያሉት የድንበር ጉዳይ በተዝረከረከ መልክ ሲታዩ እና አንዳንዴም ለሱዳን ተቆርሶ ሲሰጥ ዝም መባሉ የሚጠቀሱ ናቸው።  


ሁለቱ የአስተሳሰብ ጥጎች 

ይህንን ፅሁፍ እንድፅፍ ካነሳሳኝ ጉዳይ ሰሞኑን አራት የአየር ኃይል አባላት መንግስትን ከድተው ሄዱ የሚለው ዜና ነው።ይህ ጉዳይ ከሁለት ጥግ አንፃር ማየት ተገቢ ነው።የመጀመርያው ከላይ በተበላሸ መንገድ ላይ ያለውን የሰራዊቱን ችግር መቃወማቸው በጎ ተግባር መሆኑን ሲሆን ሌላው ጥግ ግን እንደ አትዮጵያዊ ሆነን ስናየው የእዚህ አይነቱ ውስጣዊ የፖለቲካ ችግራችን ከውጭ ሆነው ሀገሪቱን ለማዳከም ሌት ከቀን ለሚጥሩ ኃይሎች ያለው አንደምታ ምንድነው? የሚለው ነው።ሁል ጊዜ ከመጀመርያው ጥግ ብቻ ካየን ሌላውን እና የሁሉም የጋራ አደጋ የሆነውንም ጥግ እንዳይረሳ የሚል ስጋት አለኝ።ይህንን ስጋት ማንም ኢትዮጵያዊ እንደማይጠፋው አስባለሁ።የፖለቲካው ጭቅጭቅ ይዞን እንጂ ሁሉም የኢትዮጵያ ሰራዊት ነው።ጥቂቶች ከላይ ተቀምጠው አላማቸውን ሊጭኑበት ይችላሉ።እውነታው ግን ከእዚህ ይለያል ነገ ይህ ሁሉ ችግር እንደ ኩፍኝ ይወጣል።ኢትዮጵያ ግን በኢትዮጵያውነቷ ትቀጥላለች።ኢህአዲግ-ወያኔ የቀድሞውን ሰራዊት አለመቀበሉ ጥፋት ነው እያልን አሁን ያለውን ሰራዊት ኢትዮጵያዊ አይደለም ለማለት አይቻልም።

ቀደም ብዬ ከላይ ከጠቀስኩት የስጋት ጥጎች አንፃር የውስጥ ትግሉ የሀገሪቱን ሉዓላዊነት ለውጭ ኃይሎች እንዳያጋልጥ ብለው የሚሰጉ አሉ።ስለእዚህም በተለይ የመገናኛ ብዙሃን የእዚህ አይነቱን የደህንነት ጉዳይ ሲዘግቡ ጥንቃቄ የሚሹ ሁኔታዎች መኖር እንዳለባቸው ማሰብ ይገባል።በእርግጥ  ''ሕልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም'' የውጭ ኃይላት ማሰፍሰፍ አለ ተብሎ የእኩልነት እና የነፃነት ትግል ሊኖር አይገባም ማለት አይቻልም። በቅርቡ ከአየር ኃይል ለቀው ከወጡት መኮንኖች ውስጥ ሻለቃ አክሊሉ መዘነ ለኢሳት ራድዮ በተናገሩት ንግግር ግን መደምደም ይቻላል።''ኢትዮጵያ በአሁን ሰዓት በቅርብ ሆነ በእሩቅ  ከወያኔ የበለጠ እጅግ አስጊ ጠላት የላትም'' ሻለቃ አክሊሉ መዘነ።

ኢትዮጵያን እንደ ኢትዮጵያዊነቷ ለሚጠሏት

በመጨረሻም ከላይ ከሁለተኛው ጥግ ተመልክተው ለሚሰጉም ሆነ ከውጭ ሆነው ኢትዮጵያን እንደ ኢትዮጵያዊነቷ ለሚጠሏት፣ሀገሪቱን ለማጥፋት'' አጋጣሚ አገኘን'' ለሚሉ ከእዚህ በታች ያለውን መረጃ ማስቀመጡ አስፈላጊ ይመስለኛል።''Global fire power'' የተሰኘ ዓለም አቀፍ ተቅዋም በየዓመቱ የሀገሮችን የወታደራዊ አቅም እየመዘነ ደረጃ ያወጣል።በእዚሁ መሰረት የ 2013 እ ኤ አ ባወጣው ዘገባ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ከግብፅ ቀጥሎ በሁለተኛነት ደረጃ ሲያስቀምጥ ከዓለም ከሰሜን ኮርያ እና ከእስፔን በላይ በ28ኛ ደረጃ ላይ ያስቀምጣታል።ድርጅቱ ሀገሮችን የሚ መዝንበት ከአርባ በላይ መስፈርቶች አሉት።ኢትዮጵያ አስር መንግሥታት በተቀያየሩ ቁጥር ደርግ እና ኢህአዲግ- ወያኔ እንዳደረጉት ''እያፈረሱ መስራት'' በሚለው መንገድ የነበራት የማፍረስ ተግባር ማቆም አለባት።እድገት ባለን ነገር ላይ መመስረትን የግድ ይላል።ይህ  ክፉ ጠባይ ሊቆም ይገባዋል።ነገ የሚመጣው ለውጥ ዛሬ ያለንን አክብሮ የያዘ ክፉውን በክፉነት በጎውን በበጎነት የሚመዝን መሆን ይገባዋልና።

የ ''ግሎባል ፋየር ፓወር'' የ2013 የሀገሮች የመከላከያ ኃይል ደረጃ ዘገባ ከእዚህ በታች ይመልከቱ።

Countries Ranked by Military Strength (2013) by Country

Authored By Staff Writer | Last Updated: 1/2013
Our full ranked list puts the military powers of the world into full perspective.

The GFP Top 10:
 1.United States2.Russia3.China4.India5.United Kingdom6.France7.Germany8.South Korea 9.Italy10.Brazil.

The GFP ranking makes use of over 40 factors to determine each nation's Power Index ("PwrIndx") score. From this score, the finalized ranking is generated. The factors are set within our algorithm which provides a fair canvas and allows smaller, technologically advanced nations to compete with larger, lesser-developed ones. Additionally, various bonuses and penalties are added for refinement. In the end, we hope it presents an unbiased ranking and realistic outlook on the potential conventional military firepower and strength of a given country for a given year. At the very least, this list can be used to stir healthy debate amongst visitors to GFP.

There are a total of 68 countries in the GFP database. Keep in mind that the final rankings are always being fine-tuned based on new data becoming available as well as feedback. The last major update occurred on 8/1/2013.

1 United States of America PwrIndx: 0.2475
2 Russia PwrIndx: 0.2618
3 China PwrIndx: 0.3351
4 India PwrIndx: 0.4346
5 United Kingdom PwrIndx: 0.5185
6 France PwrIndx: 0.6163
7 Germany PwrIndx: 0.6491
8 South Korea PwrIndx: 0.6547
9 Italy PwrIndx: 0.6838
10 Brazil PwrIndx: 0.6912
11 Turkey PwrIndx: 0.7059
12 Pakistan PwrIndx: 0.7331
13 Israel PwrIndx: 0.7559
14 Egypt PwrIndx: 0.7569
15 Indonesia PwrIndx: 0.7614
16 Iran PwrIndx: 0.7794
17 Japan PwrIndx: 0.7918
18 Taiwan PwrIndx: 0.8632
19 Canada PwrIndx: 0.8638
20 Thailand PwrIndx: 0.8979
21 Mexico PwrIndx: 0.9144
22 Ukraine PwrIndx: 0.9167
23 Australia PwrIndx: 0.9386
24 Poland PwrIndx: 0.9518
25 Vietnam PwrIndx: 1.0676
26 Sweden PwrIndx: 1.0841
27 Saudi Arabia PwrIndx: 1.1038
28 Ethiopia PwrIndx: 1.1725
29 North Korea PwrIndx: 1.1754
30 Spain PwrIndx: 1.1847
31 Philippines PwrIndx: 1.1871
32 Switzerland PwrIndx: 1.2275
33 Malaysia PwrIndx: 1.2457
34 South Africa PwrIndx: 1.2582
35 Argentina PwrIndx: 1.2961
36 Nigeria PwrIndx: 1.3441
37 Austria PwrIndx: 1.3695
38 Algeria PwrIndx: 1.4107
39 Syria PwrIndx: 1.4706
40 Venezuela PwrIndx: 1.4905
41 Colombia PwrIndx: 1.5049
42 Norway PwrIndx: 1.5138
43 Yemen PwrIndx: 1.5863
44 Denmark PwrIndx: 1.6116
45 Finland PwrIndx: 1.6121
46 Kenya PwrIndx: 1.6237
47 Singapore PwrIndx: 1.6284
48 Afghanistan PwrIndx: 1.6381
49 Greece PwrIndx: 1.6527
50 Romania PwrIndx: 1.6555
51 Chile PwrIndx: 1.7081
52 Belgium PwrIndx: 1.7266
53 Croatia PwrIndx: 1.7413
54 Serbia PwrIndx: 1.7501
55 Portugal PwrIndx: 1.7627
56 Jordan PwrIndx: 1.7775
57 United Arab Emirates PwrIndx: 1.8131
58 Iraq PwrIndx: 1.8133
59 Libya PwrIndx: 1.8428
60 Georgia PwrIndx: 1.8539
61 Mongolia PwrIndx: 2.0267
62 Paraguay PwrIndx: 2.1201
63 Kuwait PwrIndx: 2.1239
64 Nepal PwrIndx: 2.1578
65 Qatar PwrIndx: 2.4842
66 Lebanon PwrIndx: 2.5049
67 Uruguay PwrIndx: 2.5453
68 Panama PwrIndx: 3.0508

SOURCE- http://www.globalfirepower.com/countries-listing.asp


Monday, September 16, 2013

የኤርትራ ጉዳይ በሶስት ትውልዶች ውስጥ(ልዩ የጉዳያችን ጡመራ ሪፖርታዥ)


የኤርትራው ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ አፈወርቅ እንደቀልድ እና እንደ እልህ የጀመሩት ''ኤርትራ ኢትዮጵያዊ አይደለችም'' ብሎም ''የኤርትራ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው'' አጀንዳን የሻብያ አጀንዳ እንዲሆን ካስደረጉ በኃላ ከእሳቸው በፊት የነበረው ትውልድ ባይቀበላቸውም የእሳቸውን ትውልድ ''የኤርትራ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው'' የሚለውን ገለፃ ለመንገር አላንገራገሩም።አቶ ኢሳያስ በአንድ ጎናቸው ተንቤን ትግራይ ቢወለዱም ያነሷት ጉዳይ ግን ኢትዮጵያን ለማዳከም ለዘመናት ከሚያልሙ አንዳንድ የአረብ ሀገራትም ሆነ ጎረቤት ሱዳንን የሚያማልል ብሎም ዳጎስ ያለ ድጎማ የሚያስገኝ የወቅቱ አዋጪ ''የገበያ ማስታወቅያ'' መሆኑን የተረዱት ይመስላሉ።

ቀዳማዊ አፄ ሃይለስላሴ ዩንቨርስቲ በነፃ ትምህርት ዕድል ይማሩ የነበሩት አቶ ኢሳያስ አፈወርቅ ''የኤርትራ ነፃነት ግንባር'' (ELF) ከመቀላቀላቸው በፊት በቻይና የፖለቲካ እና የወታደራዊ ስልጠና ለመውሰድ ተጉዘው እንደነበር ተወስቷል።አቶ ኢሳያስ እና ድርጅታቸው ከሰላሳ አመት ውግያ በኃላ ''ሁሉ ነገር ተፈፀመ!'' ብለው ተናግረው ሳይጨርሱ ሌላ ጦርነት ''በባድሜ መሬት ሰበብ'' እውነታው ግን የምጣኔ ሀብት የበላይነት ለመያዝ ከሕወሓትጋር በነበረ ግፍያ አዲስ ጦርነት ውስጥ ገብተው አስር ሺዎች ሲረግፉ አብረው ከአቶ መለስ ጋር ተዋናይ ሆነው ታዩ።ያ ''የቅኝ ግዛት ጥያቄ'' ያሉት ጉዳይ አስመራን ከያዙ በኃላም ጥያቄው ተወሳሰበባቸው።

አቶ ኢሳያስ እና ድርጅታቸው ሻብያ ስልጣን ከያዘ ሃያ ሁለት ዓመታትን አስቆጠረ።በእነኝህ ሃያ ሁለት ዓመታት ውስጥ የኤርትራ ተወላጆችሲነገራቸው የነበረው ''የአፍሪካ ታይዋን ትሆናለች'' ትንታኔ ሐሰት መሆኑን ተረዱት።ይልቁን ከአስመራ ዩንቨርስቲ ጀምሮ እስከ ቀድሞ በውሱን አቅም ይሰሩ የነበሩ ድርጅቶችን የገበያ ተወዳዳሪነት አቅም ተዳከመ።በአስር ሺዎች በሱዳን፣በኢትዮጵያ፣በየመን አድርገው ተሰደዱ።ኤርትራ ከዲፕሎማሲ እስከ አካባቢ ሃገራት ድረስ እንድትገለል አደረጉ።የአቶ ኢሳያስ ''የዓለም እይታ ፍልስፍና'' የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ሆነ።እሳቸው አሜሪካንን የሚያዩበት እይታ የግል አስተያየት መሆኑ ቀረና የመንግስት ቃል አቀባይ የሚናገረው ''መዝሙረ-ኤርትራ'' ሆኖት አረፈው።አምባገነንነት አስደናቂው እና አዝናኝ ገፅታው ይሄው ነው።መሪው ሲያስነጥሰው ሁሉም ለመሳል ጉሮሮውን ይጠራርጋል።

''የኤርትራ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው'' የሚለው የአቶ ኢሳያስ ትውልድ ጥያቄ ዛሬም ፈተና ላይ ነው።

አቶ ኢሳያስ እና ትውልዳቸው የወቅቱ ገበያን ስሌት ያደረገው ''የኤርትራ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው'' አሁን በተነሳው ትውልድ የሚሞገትበት ጊዜ እሩቅ የሚመሰለው ካለ በሃሳቡ የመቀጠል መብቱን አከብራለሁ።ለእኔ ግን ይህ ጥያቄ በእራሱ የሚሞገትበት ጊዜ እንደሚመጣ አስባለሁ።የማኅበራዊ ትምህርት ሳይንስ ለምሳሌ የፖለቲካ ሳይንስ እንደ ኬሚስትሪ እና ባዮሎጂ በቤተ-ሙከራ(ላብራቶሪ) ጥናት ውጤቱን ከወዲሁ ለመወሰን አይቻልም።የሚቻለው ነገር ካለፉት፣አሁን ካለው እና መጪውን ከመተለም አንፃር በምክንያታዊ አቀራረብ ከወዲሁ ሁኔታዎችን መመልከት ነው።ከእዚህ አንፃር የኤርትራ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች ሶስተኛው ትውልድ ላይ የወደቀ የእዚህ የሶስተኛው ትውልድ ጥያቄም በእርሱ ታሪካዊ ሂደት የሚፈነዳበት ሁኔታ ይኖራል።የሶስቱ በኤርትራ ጉዳይ የተሳተፉ ትውልዶች ጥያቄዎች እንደዘመናቱ ''የፖለቲካ ገበያ አዋጭነት'' እንደ አቶ ኢሳያስ ያሉ ተዋናዮች ተጫውተውበታል።ጥያቄው የሶስተኛውንም ትውልድ ጥያቄ አሁንም ''የፖለቲካ ገበያውን'' ተመልክተው ጥያቄውን በመሞረድ የአቶ ኢሳያስ ቡድን ሊመራው ይችላል ወይ? የሚለው ጥያቄ ፈታኝ ነው።መልሱ አይመስልም ነው።

ሶስቱ በኤርትራ ጉዳይ ላይ የነበሩ ትውልዶች

 1/ የመጀመርያው ትውልድ


የመጀመርያው ከአቶ ኢሳያስ በፊት የነበሩት የጣልያን እና የእንግሊዝን ቅኝ ግዛት ግፍ የሚያውቁቱ ሲሆኑ ይህ ትውልድ ከ 1900 ጀምሮ እስከ 1960ዎቹ የነበረ ትውልድ ነው።በእዚህ ዘመን ውስጥ ኤርትራ መከራ ፍዳ በቅኝ ገዢዎች ማየቷን በአይን የተመለከቱ፣የምስራቅ አፍሪካን ብቻ ሳይሆን እንደህልም የሚያልሟት እና የሚወዷት ኢትዮጵያ ክፉ እንዳይነካት እንደ አይን ብሌን  የሚሳሱላት ትውልድ ነበሩ።ይህ ትውልድ በግድም ይሁን በውድ በጣልያን የባንዳ ሰራዊት ውስጥ ገብቶ እስከ ሊብያ እና ኢትዮጵያ የዘመተ ቢሆንም ''ኢትዮጵያ ሀገሬን ቅኝ ገዢ አይዛትም'' ብሎ እንደ አብርሃም ደቦጭ እና ሞገስ አስገዶምን አፍርቶ ግራዝያንን ያቆሰለ ትውልድ ነው።የኢጣልያ ስብከት  አላማው እና ግቡን ስለተረዳ ኢትዮጵያ እናት ሀገሬ አይደለችም የሚል አስተሳሰብ ማሰብ በራሱ አለማወቅ ብቻ ሳይሆን እራስን መካድ መሆኑን ጠንቅቆ የተረዳ ትውልድ ነው።

ጣልያን ኤርትራን በያዘችበት ጊዜ በአስመራ ከተማ ውስጥ 
- ለነጮች የተከለሉ ምግብ ቤቶች እንደ አሸን መብዛታቸውን ፣
- ከምሽቱ 11 ጀምሮ አንድም ኤርትራዊ በአስመራ ጎዳና እንዳይዘዋወር (ጣልያን እና ነጮች ብቻ የተፈቀደ ስለነበር) መታገዱን፣
- በአውቶቡስ ውስጥ ሲሄድ ኤርትራውያን ከነጮች ጋር እንዳይቀላቀሉ በመጋረጃ እንዲከለል ተደርጎ እንደ ዕቃ ይሄድ የነበረ መሆኑን፣
- እስላሙ እና ክርስቲያኑ እንዲጋደል የእስላም ቤት ከውጭ የቀይ ምልክት የክርስቲያን ቤት በነጭ ቀለም እንዲቀለም  መድረጉን ወዘተ ያውቃል።
መላከ ሰላም ዲመጥሮስ ገ/ማርያም (ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትዋሃድ እጅጉን ከገፉት የመጀመርያው ትውልድ የኤርትራ ተወላጅ) 

ይህ ትውልድ የቀንም ሆነ የማታ ሕልሙ እናት ሃገሩ ኢትዮጵያን ማየት ነበር።ለእዚህም ነበር ብዙ ሺዎች በሁመራ -ጎንደር እያደረጉ ወደ ኢትዮጵያ የመጡት እና በንግድም ሆነ በከፍተኛ የመንግስት ስልጣን ሳይቀር ቦታ እያገኙ የመጡት።ይህ ትውልድ ነበር ''ኢትዮጵያ ወይንም ሞት!'' ብሎ ''የሀገር ፍቅር ማኅበር'' መስርቶ የንጉሡ ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ ሆኑ ንጉሡ ሲያመነቱበት የነበረውን የተባበሩት መንግስታትን የፌድሬሽን ጥምረት ውሳኔ ከክህደት ቆጥሮ ንጉሱን መቆምያ መቀመጫ አሳጥቶ ወደ ውህደት የመራው።አምባሳደር ዘውዴ ረታ ስለነበረው ትውልድ ሲናገሩ ''ኢትዮጵያ ኤርትራ እንድትዋሃድ ለማድረግ ሞከረች ከሚለው ይልቅ ኤርትራውያን ውህደቱን አለመፈፀም በእራሱ ትልቅ ክህደት እንደተፈፀመ ከመቁጠራቸውም በላይ ኤርትራውያን በእራሳቸው ጥያቄ ውህደቱን ከመነሻው እስከመጨረሻው ድረስ በሁለት እግሩ አስኬዱት ማለት ይቀላል።እኔ በወቅቱ ምስክር ስለነበርኩ'' ያሉት።

ሁለተኛው ትውልድ


አቶ ኢሳያስ አፈወርቅ

ይህ ትውልድ ከ 1960ዎቹ እስከ 1990 ያለው ትውልድ ነው።ይህ ወቅት የሶሻልስቱ አብዮት፣ወታደራዊ ደርግ፣የኢትዮጵያ የለውጥ ማዕበል በተለያዩ ኃይሎች እጅ በመከፋፈሉ እና እንደ ድርጅትም ''ሻብያ'' ጎልቶ ከመውጣቱ አንፃር የኤርትራ ጉዳይ በተወሰኑ መሳርያ በያዙ ኃይሎች እጅ ወደቀ።ሌላው ቀርቶ የቆላው የኤርትራ ሕዝብ ጥያቄ የሚሰማው ከማጣቱም በላይ ተወካዮቹ ወደ ደርግ መጥተው አቤት ለማለት ተገደዱ።የእዚህ ትውልድ ጥያቄ ከቀይሽብር መከራ ጋር ተዳምሮ ''ነፃነት!ነፃነት!መብት!'' የሚሉትን ጥያቄዎች ሁሉ ከመለየት እና የእራስን መንግስት ከማቆም ጋር ተዛመደ።አምባገነንነትን መዋጋት የእራስ ሀገር ከመመስረት ጋር ያለው ተዛምዶ እና ቅራኔን የሚፈታ ጠፋ።የወቅቱ የብሔር ብሄረሰቦች ጥያቄ ማሰርያ ውሉ ጠፍቶ መገንጠልን መድረሻው ሲያደርገው የሚጠይቅ ጠፋ።ጉዳዩ ያሳሰባቸው የመጀመርያው ትውልድ አባላት የሚሰማቸው ጠፋ።ይልቁንም በዘመነ ደርግ  የተከበሩ የደጋው ሃማሴን እና  የኤርትራ ቆላ ተወላጅ  አባቶች በተለይ  ''የሀገር ፍቅር ማኅበር'' አባላት እና መስራቾችም ጭምር 'የኤርትራ እና የኢትዮጵያን አንድ ሕዝብ መሆን አትናገሩ' ተብለው ድብደባ፣ዛቻ አንዳንዶቹም እስካሁን በሻብያ ወኪሎች እንደሆነ በሚታሰብ መልኩ ቤታቸው መግብያ ላይ የጥይት አረር ሆኑ።

ይህንን እውነታ ወደፊት ታሪክ በሚገባ ይዘክረዋል።የሁለተኛው ትውልድ መነጋገርያ ውይይት፣መግባባት እና ሃሳብን መግለፅ ሳይሆን ''ቀና ብሎ ያየህን በጥይት አረር ድፋው'' መሰል የወረደ አስተሳሰብ ነውና ብዙዎች ደርግ እራሱ ሊታደጋቸው አለመቻሉን ሲመለከቱ ወደተለያዩ የአውሮፓ እና የአሜሪካ ሃገራት ተሰደዱ።ዘመንን ዘመን ተካውና የአቶ ኢሳያስ ትውልድ በ 1983 ዓም ከሰላሳ ዓመት ጦርነት በኃላ አስመራ ሲገባ ሁኔታው አዲስ ምዕራፍ ያዘ።

ትንሽ ቆይቶ ግን ነገሮች ተቀየሩ።በመጀመርያ በኤርትራ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን፣ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣እና ኤርትራውያንን ያገቡ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የያዙትን ንብረት ትተው ወደ ኢትዮጵያ እንዲሄዱ ተደረጉ።በመጀመርያ ጊዜ የነበረው አወጣጥ በተለይ ህወሃትም በወዳጅነት ላይ ስለነበር የተፈናቃዮቹን መከራ የሚያደምጥ ጠፍቶ በአዲስ አበባ የሚታተሙ የግል ጋዜጦች ብቻ የምስኪን ስደተኞች ችግር ለኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያስተጋቡ ብቸኛ ጠበቃዎች ሆኑ። ውሎ አድሮ ግን ሻብያ እራሱ ከህወሓት ጋር አዲስ ፍጥጫ ውስጥ ገባ።በለስ ቀንቷቸው አዲስ አበባ የገቡቱ ተፈናቃዮች በሳሪስ ቃሊቲ አካባቢ በድንክዋን ሆነው ቀይ መስቀል ይጎበኛቸው ገባ።ይህ በሆነ በሰባተኛው ዓመት ብዙም ስለ ጀት ማብረር ችሎታ የሌላቸው የአቶ ኢሳያስ አይሮፕላን አብራሪዎች ትግራይ ውስጥ ትምህርት ቤቶችን በቦንብ ደበደቡ።ሕፃናት በትምህርት ገብታ ላይ ሳሉ ተቀጠፉ።

ከጥቂት ወራት በኃላ የበቀል እርምጃው ቀጠለከሰባ ሺህ በላይ የሚሆኑ ቀኝ እና ግራ እጃቸውን ያልለዩ ሕፃናትን ጨምሮ በኢትዮጵያ ይኖሩ የነበሩ ትውልደ ኤርትራውያንን ህወሓት በማባረሩ ኢትዮጵያውያንን አሳዘነ።ብዙዎቹ ለዘመናት ያፈሩትን ንብረት በአንዲት ጀንበር ሲነጠቁ አነቡ።ከቤት ወጥተው የማያውቁ ልጆች በአውቶቡስ እየተጫኑ በትግራይ በኩል ደቡብ ኤርትራ ላይ ተወረወሩ።ምናልባት የሁለተኛው ትውልድ (የአቶ ኢሳያስ ትውልድ) የመጀመርያው ትውልድ ሲናገረገው የነበረውን ሁሉ ማሰብ የጀመረው በእዚህ ወቅት ይሆናል።የሆነው ሆኖ ይህ ወቅት ''መንግሥታት'' ተብለው የሚጠሩ ሁለት አካላት አስመራ እና አዲስ አበባ ላይ ሆነው በከረመ የመለያየት ፖለቲካቸው ሕዝብን ስያሰድዱት ተስተዋሉ።የሁለተኛው ትውልድ አባዜ በእዚህ አላበቃም በሻብያ እና በህወሓት መካከል የነበረውን የቆየ ቁርሾ ''ወደ ሀገር አጀንዳነት'' ተቀየረ እና ሁለቱም የህዝብን ስሜት እየኮረኮሩ በባድማ መሬት ስም ውግያ ገጠሙ።በውግያው የኢትዮጵያ ሰራዊት ገፍቶ  አስመራ ሊገባ ሰዓታት ቀሩት።በውቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት ቃል አቀባይ የነበሩት ወይዘሮ ሶሎሜ በአሜሪካዊ እንግሊዝኛ በተቃኘ ንግግራቸው ለቢቢሲ ''ፎከስ ኦን አፍሪካ'' ፕሮግራም ''we gave them our lesson'' ''ዋጋቸውን ሰጠናቸው'' አሉ።ይህ ሁሉ ሲሆን ግን በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በሁለቱም ወገን የአፈር ሲሳይ ሆነው ነበር።

ሶስተኛው ትውልድ


በኤርትራ ጉዳይ የሶስተኛው ትውልድ ታሪክ የሚጀምረው ከ 1992ቱ የባድሜ ውግያ በኃላ ነው። ኢትዮጵያ እናቴ! ያለው የመጀመርያው ትውልድ አለፈ። ''የኤርትራ ጉዳይ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው'' ያለውም ሁለተኛው ትውልድ ብሎት ብሎት ደከመው። በመጀመርያ ኤርትራን በሀገርነት በማወጅ (በኤርትራ በኩል) እንዲያውጅ በማገዝ (በአቶ መለስ በኩል) ተፈፅሟል።ሺዎች ኢትዮጵያ ነክ ናችሁ ተብለው ከኤርትራ ተባረዋል።ሌሎች ሺዎች ኤርትራ ነክ ናችሁ ተብለው ከኢትዮጵያ ተግዘዋል።በድንበር ሰበብ ብዙ አስር ሺዎች አልቀዋል።ሁለተኛው ትውልድ ደከመው።ከእዚህ ሁሉ በኃላ የመጀመርያው ትውልድ የመከረውን የፍቅር ጥሪ እያሰበ ሳለ ሶስተኛው ትውልድ ተነሳ።
ድምፃዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) ከባለቤቱ ጋር 

ሶስተኛው ትውልድ በተለይ ሁለተኛው ትውልድን የሚያደንቀው በጠበንጃ አያያዙ ካልሆነ በቀር ልማት እና እድገትን ሲያመጣ ማየት አልቻለም።ይልቁን ይህ ትውልድ በመረጃ ዘመን እንደመኖሩ ታሪክ ሲነገረው በደቂቃዎች ውስጥ የተባለው ትክክል መሆኑን ለማረጋገጥ ስለሚችል በአራዳ አነጋገር ''የማይሸወድ'' ሆነ።ከሁሉም በላይ አቶ ኢሳያስ ቀደም ብለው ያነሱት ''የኤርትራ ጉዳይ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው'' አባባል ውላ አድራ በእዚህ በሶስተኛው ትውልድ ከባድ ፈተና ገጠማት።
  • ''ኤርትራ ቅኝ ግዛት ተይዛ የነበረው በኢጣልያ እና በሞግዝቷ እንግሊዝ ነው እንጂ በኢትዮጵያ መች ሆኖ ያውቃል?'' የሶስተኛው ትውልድ ጥያቄ ቀጠለ...
  • ''በደል እና ጭቆና ቢኖርም ይህ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ላይ የመጣ መከራ አይደለም ወይ?''
  • ''የኃይለስላሴ አስተዳደርም ሆነ የደርግ ቀይሽብር በአስመራ ላይ በተለየ ተደረገ ወይስ ሁሉም ኢትዮጵያዊ የቀመሰው ገፈት ነበር?''
  • ''ይህ የሚያሳየው የአቶ ኢሳያስ ትግል መሆን የነበረበት ከደርግ አምባገነንነት እና ከንጉሡ ፍፁም ዘውዳዊ ስርዓት ለመላቀቅ ብሎም ስልጣንን ከማዕከላዊ መንግስት ለመንጠቅ መሆን የለበትም ነበር ወይ?'' ወዘተ ጥያቄዎች አቶ ኢሳያስ እንዲመልሱለት ሶስተኛው ትውልድ የሚጠይቃቸው ናቸው።

ሶስተኛው ትውልድ ድንበር ከድንበር ቢዘጋበት በመከራ ላይ ሆኖ በስደት ሲገናኝ የሁለተኛውን ትውልድ ሥራ ማብሰልሰሉ አልቀረም።ጊዜ፣ቦታ እና አጋጣሚ ሲገጥመው ግን የአቶ ኢሳያስ ''የቅኝ ግዛት ጥያቄ'' ብለው የሰሩት ዶሴን ይዘት እራሳቸውን አቶ ኢሳያስን ይጠይቅበታል።
የሶስተኛው ትውልድ ጥያቄ አልቆመም..
  •  ''ከኢጣልያን የዘር መድሎ የተላበሰ አገዛዝ ከእንግሊዝ ከሞግዝትነት ባለፈ ሌላ ቅኝ ገዢ ለመሆን ታደርገው ከነበረው ዝግጅት ኤርትራ የዳነቸው ከኢትዮጵያ ጋር በፌድሬሽን ከተቀላቀለች በኃላ አይደለም ወይ?''
  • '' አስመራ በነፃነት ከ 11 ሰዓት በኃላ መሄድ የተቻለው፣የፈለጉበት ምግቤት (የነጮች የጥቁሮች)ሳይባል መመገብ የተቻለው ከፌድሬሽን በኃላ አይደለም ወይ?''
  •  ''በአስመራ መንገድ ላይ በእግር ለመሄድ 'ነጮች በሚሄዱበት መንገድ ላይ መሄድ አይቻልም' ተብሎ ለጥቁር በተከለለ መንገድ ላይ ብቻ ይሄድ የነበረው ኤርትራዊ በነፃነት በሁሉም የእግር መንገድ ላይ በዜግነቱ ኮርቶ መሄድ የቻለው ከፌድሬሽን በኃላ አደለም ወይ?''
  • ኢጣልያ ለኤርትራ ተወላጆች ትምህርት እስከ አራተኛ ክፍል ብቻ እንዲሆን መወሰኗ ያቆመው እና ኤርትራውያን የትምህርት ዕድል እስከፈለጉት ክፍል ድረስ መግፋት የቻሉት ከፌድሬሽን በኃላ አይደለም ወይ?
  • ''ለመሆኑ  በኤርትራ የተወለደው ኢትዮጵያ ከተወለደው በምን ተለያየ?  በንግግር? ወይንስ በመልክ? በአመጋገብ?ወይንስ በሃይማኖት በምን ተለያይቶ ነው የዲሞክራሲ፣የመብት እና የስልጣን ጥያቄ ''የቅኝ ግዛት ጥያቄ'' የተባለው? የሶስተኛው ትውልድ ጥያቄ ይቀጥላል።


አበቃሁ
ጌታችው በቀለ
ኦስሎ  

Friday, September 13, 2013

ትኩስ ዜና ስለ ዘመን ተሻጋሪው አየርመንገዳችን


ኢትዮጵያ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ከገነባቻቸው ተቋማት ውስጥ በውጤታማነቱ የሚጠቀሰው አንዱ እና ጉልሁ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው።የኢትዮጵያ አየር መንገድ በየዘመኑ ሀገራችን ከሚገጥማት ፖለቲካዊ ፈተናዎችን የሚወጣበት የእራሱ የሆነ ''የጥሩ ነጋዴ ክህሎት'' ማዳበሩን የሚናገሩ አሉ።ለእዚህ አይነቱ ክህሎት ያላበሰው አይነተኛ ምክንያት ደግሞ  የረጅም ጊዜ ልምድ ያዳበሩ ሰራተኞቹ ድርጅቱን በጡረታ አልያም ለሌላ ድርጅት በተሻለ ደሞዝ ትተው ቢሄዱምካሉበት ሀገር ሆነው ማኔጅመንቱን በምክር ከማገልገላቸውም በላይ የእኔነት ስሜት (belongingness) በሌሎች ላይ በማሳደር የሚፈጥሩት በጎ ተፅኖ ተጠቃሽ ነው።


የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኞች ከድርጅቱ በጡረታም ሆነ የተሻለ ሥራ አግኝተው ከወጡም በኃላ ጠንካራ በሆኑት ማኅበራቱ ለምሳሌ በገንዘብ ቁጠባ እና ብድር ማኅበር፣በጡረተኞች ማህበር፣የአብራሪዎች ማኅበር በመሳስሉት መንገድ ድርጅቱ የሚያገኝበት መንገድ አለው።ይህም እንደ አንዳንድ መስርያቤቶች ሰራተኞች ጡረታ ሲወጡ ድርጅቱን በሩቅ ተመልካች እንዳይሆኑ ባለማድረጉ ለአብነት ተጠቃሽ ነው።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በያዝነው ሳምንት መጀመርያ ላይ መሰረቱን አሜሪካ፣ካሊፎርንያ  ያደረገው Airline Passenger Experience Association (APEX) በተሰኘ ድርጅት ተሸላሚ ሆኗል።

ይሄው በመላው አለም በአየር መንገድ ለሚጠቀሙ መንገደኞች ምቾት የሚሰራው ድርጅት  በአለም ዙርያ በአየር መንገድ ለሚጠቀሙ መንገደኞች በቀጥታ በሚጠይቀው መጠይቅ በሚልዮን የሚቆጠሩ  መንገደኞች የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምርጫቸው መሆኑን እንደገለፁለት አሳውቆ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ''የ 2013 በአፍሪካ በደንበኞች የበለጠ ተመራጭነት'' ሽልማት አሸናፊ መሆኑን ገልጧል።ዜናውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ  እና ''All africa.com'' መስከረም 2/2006 ዓም በድህረ ገፃቸው ላይ ዘግበውታል።

በሌላ በኩል  ''ሰላምታ'' የተሰኘው የኢትዮጵያ አየርመንገድ መፅሄት በዓለም ላይ ካሉት የበረራ መፅሄቶች ውስጥ ከአምስቱ ምርጦች ውስጥ መደመሩ እና ለሽልማት መብቃቱ ሌላው ተጨማሪ  የዜናው አካል ነበር።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከብዙ ድርጅቶች ብዙ ሽልማቶችን ተቀብሏል።እንደዚህ በቀጥታ በሚልዮን የሚቆጠሩ ደንበኞች ሲመርጡት መመረጡን ደግሞ ገለልተኛ የሆነ ድርጅት ሲያረጋግጥ ሀገርኛ ደስታ ነው።ለዘመን ተሻጋሪው አየር መንገዳችን መልካም አዲስ ዘመን።

ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ 

Tuesday, September 10, 2013

የ2005 ዓም የጉዳያችን ጡመራ ሁለት ምርጦች


የእኔ የ2005ዓም ምርጤ ማነው? ብዬ አሰብኩ።

ዘንድሮ ማንን አደነቅሁ? ብዬ እራሴ ለእራሴ ጠየቅሁት? ለአመታት ያጣነውን የሙያውን ስብዕና እያላበሱ ያሉ ሁለት ክቡራኔን አገኘሁ።የጋዜጠኛ ሙያ ስብዕናን።

ዳኛው እኔው መራጩ እራሴው። ምን ቀረ?
በ 2005 ዓም ብዙ መልካም የሰሩ ሰዎች ይኖራሉ። እኔ ግን ስለ እነኚህ ኢትዮጵያውያን ''የአመቱ ሰው'' ብላቸው ማን ከልካይ አለብኝ?

ማንነህ እና ነው አንተ የአመቱ ምርጥህን የምትመርጠው? ማለት አይቻልም።በጡመራ መድረክ(ብሎግ) ሁሉም ሰው ሃሳቡን በነፃ እንዲገልፅ የፈቀደው ህገ-ቴክኖሎጂ የእዚህ አይነቱን ጥያቄ አያስተናግድምና።

በ 2005 ዓም ብዙ ነገር አድንቄ ይሆናል።ሀገራቸውን ከልብ ከሚወዱ ውስጥ በሩቁ የተመለከትኩትን ግን እንዳደንቅ ይፈቀድልኝ።

ደግነቱ አያውቁኝ አላውቃቸው።የቴሌቭዥን መስኮት አገናኘን እንጂ።እኔ በመመልከት እነርሱ በማቅረብ። ሌላ የምሸልማቸው የለኝም።ያለችኝ ትንሿ የጡመራ መድረክ (ጉዳያችን ጡመራ) ነች።

እነኚህ ሁለት ምርጦቼ ስለሚከተሉት ሶስት ነገሮች የአመቱ ምርጥ ጋዜጠኞች መባል አለባቸው እላለሁ።

  •  ጋዜጠኝነትን ኢትዮጵያዊ ጨዋነት፣ትሕትናን እና ድፍረትን በአንድነት አላብሰውታል፣
  •  የሃገር መውደድ ከፊታቸው ይነበባል። የእውነት መደበቅ ደግሞ  ሲያበሳጫቸው ያስታውቅባቸዋል፣
  • በሚያቀርቡት ጥያቄ ሃብታምን በሀብቱ አያፍሩትም፣ጉልበተኛውን ስለጉልበቱ አይራሩለትም ተመልካች አዕምሮ ውስጥ ሊኖር ቢችል ያሉትን ጥያቄ ያቀርባሉ።

የኢሳት ጋዜጠኞች ሲሳይ አጌና  እና ደረጄ ደስታ የ 2005 ዓም ምርጥ የጋዜጠኝነት ብቃት በማሳየት ምርጦቼ ናቸው።

ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ


ጋዜጠኛ ደረጄ ደስታ                                           




              ጋዜጠኛ   ሲሳይ አጌና



























Friday, September 6, 2013

ከሰላሳ ሺህ ቃላት በላይ የያዘ ኖርዌይኛ-በአማርኛ አዲስ መዝገበ ቃላት በገበያ ላይ ዋለ

አምስት መቶ ስልሳ ገፅ የያዘ ኖርዌይኛ በአማርኛ  መዝገበ ቃላት በአይነቱ ልዩ በሁለት ኢትዮጵያውያን ተዘጋጅቶ እና በኖርዌይ ትምህርት ሚኒስቴር ታትሞ በመፃህፍት መደብሮች በገበያ ላይ መዋሉን ለማወቅ ተችሏል።በኖርዌይ የብዙ ሀገሮች መዝገበ ቃላት (የሱማልኛን ጨምሮ) በኖርዌይኛ ተተርጉሞ መኖሩ ሲታወቅ የኢትዮጵያ ግን በእየመፃሕፍት መደብሮች አልፎ አልፎ ከሚታዩት  በቃላት ብዛታቸውም ሆነ በይዘታቸው እጅግ ትንንሾች እና የተወሰኑ ቃላትን ብቻ የያዙ ጥቂት የአማርኛ እና የትግሪኛ መዝገበ ቃላት ብቻ በመኖራቸው በብዙዎች ዘንድ ደረጃውን የጠበቀ የመዝገበ ቃላት አስፈላጊነት ጉዳይ ሲወሳ ነበር። 

ይህ ከሰላሳ ሺህ በላይ ቃላት መያዙ የተነገረለት መዝገበ ቃላት የተዘጋጀው በሁለት ኢትዮጵያውያን ማለትም በአቶ እንግዳ እሸት ታደሰ እና  በተባባሪያቸው አቶ አበበ ተፈራ ሲሆን እንደ አቶ እንግዳ እሸት ገለፃ መዝገበ ቃላቱን ለማዘጋጀት እና ደረጃውን የጠበቀ አድርጎ ለማውጣት  ሃያ አመታት እንደደከሙበት ለማወቅ ተችሏል። 

ኢትዮጵያውያን በሚኖሩበት ሀገር ሊሰሯቸው ከሚገባቸው ተግባራት ውስጥ ዋነኞቹ እንደዚህ አይነት ትውልድ ተሻጋሪ እና ለሀገር የሚጠቅሙ ስራዎች መሆን እንደሚገባ የኢትዮጵያውያኑን ሥራ በአብነት መጥቀስ ይቻላል።

በመጨረሻም መፅሐፉን በመስመር ላይ ( on line) ለማዘዝም ሆነ በአካል ወደ መደብር ሄደው  ለመጠየቅ የመፅሐፉን ኮድ (ISBN number 978-82-450-1360-3) መያዝ ጊዜ ይቆጥባል።



ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ 


Thursday, September 5, 2013

Wednesday, September 4, 2013

የሶርያ ጉዳይ (አጭር ማስታወሻ)


President Barack Obama meets with Members of Congress to discuss Syria in the Cabinet Room of the White House, Sept. 3, 2013. (Official White House Photo by Pete Souza)
ፕሬዝዳንት ኦባማ በዋይትሐውስ የካቢኔ መሰብሰብያ አዳራሽ ውስጥ ከምክርቤት አባላት ጋር ሲወያዩ (ማክሰኞ ነሐሴ 28/2005 ዓም ፎቶ በፔተ ሳኡዛ )

አሜሪካ በተናጥል በሶርያ ላይ ጥቃት የመፈፀሟ ግምት እያደገ ነው።ከምክርቤቱ ስብሰባ በኃላም ጉዳዩን በቀላሉ ማጣጣል አልተቻለም።ፈረንሳይ ጥቃቱን ብትደግፍም ብቻዬን ግን አይሆንም ብላለች።ቢያንስ የአሜሪካ ከጎኗ መቆም አስፈላጊ ነው እያለች ነው።የሶርያው በሽር አል-አሳድ ወደመጨረሻ ደረጃ ላይ ሲደርሱ ያለ የሌለ ኃይላቸውን (በተለይ በአለም በኬሚካል የጦር መሳርያ ምርት ቀደምት የሆነችውን ሀገራቸውን) በእስራኤል ላይ ሊያሳዩ ይችላሉ ተብሎ ተፍርቷል።እስራኤል ለዜጎቿ የፊት መሸፈኛ ጭንብል ማደል ከጀመረች ሳምንታት ተቆጥረዋል። ኦባማ ፈለጉት አልፈለጉትም አሜሪካ እያለች  የአይሁዳውቷ ሀገር ጥቃት ማየት የማይችሉበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል።

የእንግሊዝ ፓርላማ በጉዳዩ ላይ አሉታዊ ድምፅ ቢሰጥም ከመስከረም 5 እስከ 6/2013 እኤአ በሩስያ ዋና ከተማ ቅዱስ ፔተርስፐርግ (St. Petersburg) ከተማ የሚደረገው የቡድን 20 ሀገሮች ስብሰባ ላይ የአሜሪካ እና የሩስያ ፍጥጫ በሶርያ ጉዳይ ላይ ጎልቶ የመውጣት ዕድል እንዳለው ይገመታል።ከእዚህ በተለየ ግን አሜሪካ እንደተገመተው ጥቃት ከፈፀመች እና ጦርነቱ በአጭሩ ከማለቅ ይልቅ የአካባቢውን ሀገሮች በረጅም ጊዜ ወገን እንዲይዙ ወደመምራት ከሄደ ለአፍሪካ ቀንድም የራሱ የሆነ አጀንዳ ይዞ ሊመጣ ይችላል።

ጦርነቱን በአሜሪካ ዘመቻ ቢጀመር በአጭር ጊዜ ላለመጠናቀቁ አንዱ እና አይነተኛ አመላካች ጉዳይ በአሜሪካ በትጥቅ እና ስንቅ የተደገፉት  የባሽር ተቀናቃኞች እራሳቸው የዘመቻ-አሜሪካንን መጀመር ፈፅመው እንደማይቀበሉ እያሳወቁ መሆኑ ነው።ለሁሉም ግን ጉዳዩ ከአንድመቶ አስር ሺህ በላይ ሶርያውያን ከሞቱ በኃላ የአሜሪካ የዘመቻ ጉሰማ አለምአቀፉ ሕብረተሰብን ለማፅናናት ይሁን ወይንስ  ከምር አይሁዳውቷን ሀገር  ለመከላከል መሆኑ ከሰሞኑ የሚታዩ ክስተቶች ግልፅ ያደርጉልናል።

በነገራችን ላይ ኢትዮጵያ የአፍሪካ እና የመካከለኛው ምስራቅ ድልድይ አንደመሆኗ እሳቱ እሩቅ ነው በሚል ቅኝት ብቻ ማለፍ አይቻልም። እንደዛ ከታሰበ በኩሬ ውስጥ ሆና እሳት ሲነሳ የሳቀችው እንቁራሪትን መርሳት ነው። ይችው እንቁራሪት ማዶ በሚነደው እሳት ስትስቅ በመጨረሻ እሳቱን ለማጥፋት ውሃ ሲቀዱ ከባሊው ውስጥ ጨምረዋት ወደ እሳቱ እንደከተቷት ማሰብ ይገባል።ለማለት የፈለኩት ጉዳዩ  በቀጥታ ባይነካንም ጦርነቱ ከረዘመ ግን የእራሱ የሆነ አዲስ አጀንዳ እና የኃይል አሰላለፍ ይዞ አይመጣም ማለት አይቻልም ነው።እዚህ ላይ ነፍሳቸውን ይማረው እና ደራሲ እና ጋዜጠኛ ማሞ ውድነህን ማሰብ ይገባል።ጋሽ ማሞ በተለይ ከመካከለኛው ምስራቅ ጋር የተያያዙ ታሪኮችን በትርጉም ባስነበቡን መፃህፍቶቻቸው ለምሳሌ ''የካይሮ ጆሮ ጠቢ''፣ የእኛ ሰው በደማስቆ'' መግቢያ ላይ መፅሃፎቹን ለመተርጎም ምን እንዳነሳሳቸው የሚያሰምሩበት ነጥብ አንድ እና አንድ ነው። ይሄውም መካከለኛው ምስራቅ ውስጥ የሚነሱ ጉዳዮች በሙሉ ኢትዮጵያን በታሪክም ሆነ በወቅታዊ ክስተቶች ሁሉ ይነካታል የሚል ነው።

መልካም አዲስ አመት

ጌታቸው
ኦስሎ

Tuesday, September 3, 2013

የህፃኑ ጥሪ - (እስክንድር ነጋን እና ሌሎች በግፍ የታሠሩ የህሊና እሥረኞችን ለማሰብ የተጻፈ! ግጥም በአንዱአለም በቀለ 2005ዓም)



በረንዳ ቢወጣ - እጉዋዳ ቢገባ፣
ቢጣራ ቢጣራ - አስሬ ቢል ባባ፣
እናቱን ቢያስጨንቅ - ፊቱ ተጥቦ በ'ንባ፣
ውስጧ ቢተራመስ - የሷም ሆድ ቢባባ፣
መልስ ግን የላትም - ታውቀዋለችና፣
ለጊዜው አይመጣም ...
እውነትን ፍለጋ - ትግል ላይ ነው ባባ።


ውጣ ችላው እንጂ - እሷስ ምን ታድርገው፣
ቀን ዘሞባት እንጂ - እሷስ መቼ ፈቅዳው፣
ምን ብላ ትዋሸው - እነደምን ታባብለው፣
ያን ቆሻሻ ታሪክ - ምን ብላ ትንገረው!፣
......................እንዴት ትተርከው!፣
ቢሆንም ታሪክ ነው - ይወቀው ይረዳው፣
ፈርድ የሚሰጥበት - የነገ ሥራው ነው፣
......................ብላ እያየችው፣
"ባክህ ማሙሽዬ - ነገሩ እንዲህ ነው፣
ቆየ 'ኮ ከረመ - ቤታችን ወህኒ ነው፣
አንተን የወለድኩህ - እትብትህም ያለው፣
ባታውቀውም ቅሉ - እስር ቤት እኮ ነው!፣
አባትህም ባባ - እዛችው ቦታ ነው፣
ርቆ አልሄደም - እዛው እቤቱ ነው፣
ከሞቀ ኑሮው - አብርሮ ያመጣው፣
የሃገሩ ነገር - የወገን ፍቅር ነው፣
...............እናም እዚሁ ነው፣
እዚሁ ሀገሩ - እዚሁ እስር ቤት ነው፤
ታገስ ማሙሽዬ - ታሪኩ ብዙ ነው፤
በአምላክ ቸርነት - በነፃ ተፈጥረው፣
እንዳንተው ማሙሽን - ጨቅላቸውን ትተው፣
ታስረው የሚኖሩ - ብዙ አባቶች ናቸው፤
ኦልባና ና አንዱዓለም - ፍትህ የራቃቸው፣
በቀለ ና ውብሸት - እውነት የጠማቸው፣
መቁጠር የሚታክት - ብዙ ዜጎች ናቸው፤
ይገባሃል ማሙሽ - ሁሉም እስር ቤት ነው!፤
አይዞህ ማሙሽዬ - አባትህ ጎበዝ ነው፣
ለኛም ለእነሱም - ለሁላችን ሲል ነው፤
ከኔ በፊት ሀገር - ወገኔ ብሎ ነው፣
እኔንም አንተንም - ታስሮ ሊያስፈታ ነው፤
ሀገርን ከ'ስር ቤት - እስር ቤትን ካገር...
......................ታስሮ ሊለይ ነው።
ደግሞም ማሙሽዬ - ሌላም ሚስጥር አለው፣
ምናልባት አባትህ - ቢመረጥ እኮ ነው!፣
ከሌላው ለይቶ - ምሳሌ ሊያረገው፣
እሱን ሻማ አርጎት - ለሌላ ሊያበራው፣
በሱ ወህኒ መውረድ - ሌላውን ሊያስፈታው፣
ለዛም 'ኮ ይሆናል - ጨለማ የጣለው!፣
እንዴ ማሙሽዬ.......................!
የፈጣሪ ሥራ - ረቂቅ እኮ ነው!፣
እቺን የኛ ዓለም - ከጥፋት ያዳነው፣
የኛን ክፉ ሥራ - በደሙ ያጠበው፣
ያ የዓለም ጌታ - ሁሉን ያደረገው፣
እከብቶች ማደሪያ - በረት ተወልዶ ነው!።
የጥቁርን ውርደት - መንግሎ የጣለው፣
ማንዴላ ሃገሩን - ባ'ለም ከፍ ያረገው፣
ሃያ ሰባት ዓመት - ታሥሮ ተገርፎ ነው!።''

ብላ ስታወራው - ይሰቀጥጣታል፣
ይሄ ጨቅላ ህጻን - እንዴት ይገባዋል!፣
ሃገርን ከእሥር ቤት....................
እሥር ቤትን ካገር - እንዴት የለየዋል?፣
ቢሆንም ግን ቅሉ - ማሙሽ ያስተውላል፣
አባቱን ሊያይ ሲሄድ - ፖሊስ ይቆጣዋል፣
ከእቅፉ እንዳይቆይ - በብረት ተከቧል፣
ባባ ወጥቶ አይመጣ - በግረ ሙቅ ታሥሯል፣
እንዴት አያስጨንቅ..................!
ሁሉም ታሥሮ እያየ - ምኑን ይለየዋል!፣
ያባት ፍቅር ሳያይ - ሃገር እንዴት ያውቃል!?
በምን መመዘኛ..........................
ሃገር ተረካቢ - ተተኪ ይባላል?፣
እሥር ቤት ነው ሃገር - ምኑን ይረከባል!፣
እንኳን ለዚህ ጨቅላ - እኛም ቸግሮናል፣
እንኳን ለመናገር - መስማት ወንጀል ሆኗል፣
በገዛ ጣታችን - መጻፍ ያስጠይቃል፣
ዓይናችንም ላየው - አንቀጽ የጠቀሳል፣
በነፃ ተፈጥረን - ሆኖ አለመታደል፣
ዳግመኛ ነጻነት - ከሰው ይለመናል!፤
እንቆቅልሽ ነገር - እርግጥ ነው ይጨንቃል፣
ለዚህ ህፃን ጨቅላ - ለምን ይተረካል?!
ማሙሽ ግን ብልህ ነው - ተችሮት ማስተዋል፣
ሁሉንም ታዝቧል - ጠልቆ ተረድቶታል፣
መዝለል መቦረቁን - የልጅ ወጉን ትቷል፣
ይወጣል ይገባል - እናቱን ያያታል፣
እንደሰውነቱ - እውነት ይፈልጋል፣
ችላ ባትመልስም - ማሙሽ ይጠይቃል፣

''ማማ ምን ይሻላል?
እኔም ባባን ሳክል - ፖሊስ ይወስደኛል?፣
ጨለማ ክፍል ውስጥ - ይቆልፉብኛል?፣
ሰው እነዳላናግር - ይከለክሉኛል?፣
ቆይ ደሞ ማማዬ'' - ይላል ይቀጥላል፣
''ለወገኑ ሲል ነው - ያሰሩት ብለሻል፣
ይሄ ሁሉ ሥቃይ - ላገር ነው ብለሻል፣
እሱ እንዲህ ሲሆን - ወገኑ ግን የታል!?
ስሚኝ ባክሽ እናት.......................!
እንደዚህ ናት ሃገር - እኔም የማድግባት?፣''
ግን ለምን ወለድሽኝ - ምን ይሰራልኛል፣
ይላል ይገረማል - እናቱን ያያታል፣

መልስ ያጣ ጥያቄ - ምን መልስ ይኖራታል!፣
እናት ታለቅሳለች - እሱም ይጠይቃል፣
ህፃኑ ይጣራል - የአባት የወገን ያገር ያለህ ይላል፣
ላባቱ ያልሆነ - ሀገር ያስፈራዋል፣
ያቅበጠብጠዋል - ይጣራል ይጮሃል!፣
የተኛችሁ ንቁ - የነቃችሁ በረቱ አንድ ሁኑ ይለናል፣
ማሙሽ እውነቱን ነው - በጣም ያስጨንቃል፣
መውለድ እስኪያስፈራ - መጪው ያሳስበል፣
ሀገር ለማቆየት - ተተኪ ለማብቀል፣
ከዚም ጫፍ ከዚያም ጫፍ - አርቆ ማስተዋል፣
ከራስ በዘለለ - ማሰብ ያስፈልጋል፣
ደጋግሞ ደጋግሞ - መጨነቅ ይገባል፣
የህፃኑ ጥሪ - - - -ምላሽ ይፈልጋል።


Sunday, September 1, 2013

ሕጉ ለሕግ አክባሪው ከለላ ካልሰጠ ሕግ አለማክበር ሆይ ምንኛ ታላቅ ነሽ! (አጭር ማስታወሻ)


 የሕግ ከለላን እና በሕገመንግሥቱ የተቀመጠውን ሕግ ተማምነው የሰላማዊ ሰልፍ የጠየቁ የሰማያዊ ፓርቲ አባላት ለእሁድ ነሐሴ 26 ሰልፍ በዝግጅት ላይ ሳሉ ቅዳሜ ነሐሴ 25 ምሽት  በፅህፈት ቤታቸው ላይ በተደረገው ድንገተኛ የፌድራል ፖሊስ የማሸበር ተግባር ተደብድበዋል፣ተሰድበዋል ግማሾቹ ለከፍተኛ የአካል ጉዳት ተዳርገዋል።

 የተቀመጠው ሕግ የሚሰራው የአይን ቀለም እና ምላስ እየለየ መሆኑ ተነግሯቸዋል።በድብደባው ወቅት ተሰድበዋል፣ተረግጠዋል። በኢትዮጵያ ሕግ ስር በህጋዊነት የተመዘገበ የፖለቲካ ፓርቲ ቀርቶ የንግድ ፍቃድ አውጥታ የምትሰራ ለትንሿ ኪዮስክም ተገቢ ክብር መስጠትለታደለ መንግስት የሚከውናት ትንሿ ተግባር ነበረች። ማክበር ደግሞ ለመከበር ይጠቅማል። የወያኔ ታጣቂዎች ግን ከእነርሱ አስተሳሰብ በተለየ የሚያስበውን ግለሰብም ሆነ ድርጅት በጠላትነት ፈርጀው ሃገሩ የእነርሱ የአምባገነንነት ላንቃ ማላቀቅያ ሲያደርጉት ማየት አለመታደል ነው።አንዳንዶች እጅግ ከበዛ ፍርሃታቸው እና ለስርዓቱ ካላቸው አፈር የላሰ ታማኝነት የተነሳ በሰማያዊ ፓርቲ አባላት ላይ የተፈፀመው የማሸበር ተግባር ''እንዳስደሰታቸው ሲናገሩ'' አፋቸውን ትንሽም ወለም አይላቸውም። የሰማያዊ ፓርቲ የመሰሉ ፍትህ፣ስርዓት እና የሕግ ልዕልና ይኑር የሚሉ ፓርቲዎችም ሆኑ ግለሰቦች የሚታገሉት ለእነዚህ የስርዓቱ ታማኞችም ጭምር ለነገ ዋስትና እየታገሉ መሆናቸውን አለመረዳታቸው የግንዛቤ ውሱንነትን ያመላክታል።

እርግጥ ነው ይህ ክስተት ላለፉት 22 አመታት ሲከናወን የነበረ መሆኑ ዛሬ እንደ አዲስ ሊወሳ ላይችል ይችላል።ጉዳዩን ለማውገዝም ሆነ ወያኔ የሚማርበትን ሁነኛ መንገድ መፍጠር የግድ የሰማያዊ ፓርቲ አባል መሆን ወይንም ፓርቲውን በቅርብ ማወቅ አይጠይቅም።የእዚህ አይነቱን  የእብሪት ተግባር  የመግታት ተግባር የእዚህ ትውልድ ዕዳ ለመሆኑ ግን ቅንጣት  ታክል መጠራጠር አይገባም።

የሃገራችሁ መፃኢ ዕድል አሳስቧችሁ የሰማያዊ ፓርቲ አባል የሆናችሁም ሆናችሁ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን የታተራችሁ ሁሉ ክብር ሊቸራችሁ ይገባል።ዘመን ስም ሊለጥፍ ይችላል። በፋሽሽት ጣልያን ዘመን ለኢትዮጵያ ነፃነት በዱር በገደሉ የሚጋዳሉ አርበኞችን ፋሺሽት ''ወንበዴዎች'' ይባሉ ነበር።በዘመነ ደርግ ዲሞክራሲ ያሉ ''የኢምፐራሊዝም'' አቀንቃኞች ይባሉ ነበር።እናንተም  ለሕግ፣ለሞራል እና ለሥርዓት እንደምትገዙ በመግለፅ ጥያቄያችሁን አቀረባችሁ።መልሱ ግን በግፍ መደብደብ ሆነ።ካለስማችሁ ስም ተሰጣችሁ። የእዚህ ጊዜ ነው ታድያ ሕጉ ለሕግ አክባሪው ከለላ ካልሰጠ ሕግ አለማክበር ሆይ  ምንኛ ታላቅ ነሽ! ማለት ተገቢ የሚሆነው።





ጉዳያችን GUDAYACHNgetachewb221@gmail.com

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።