ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, July 30, 2018

በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ የለውጥ ሂደት ደግፈው ሕዝባዊ ስብሰባ አደረጉ። የአቋም መግለጫም አውጥተዋል።(ጉዳያችን ዜና)

በኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ድጋፍ ሰጪ ድርጅት እና የኢትዮጵያውያን የጋራ መድረክ ያዘጋጁት ስብሰባ በከፊል።

ጉዳያችን/Gudayachn
ሐምሌ 24/2010 ዓም (ጁላይ 31/2018 ዓም)

ሐምሌ 21፣2010 ዓም የኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ አሁን በኢትዮያ የሚደረገውን የለውጥ ሂደት በመደገፍ በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በኦስሎ ከተማ ''ኦልፋንገን 3'' በሚገኘው አዳራሽ የፍቅር፣የአንድነት እና የመደመር ቀን በሚል መሪ ቃል  በኢትዮጵያውያን የጋራ መድረክ እና የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ በጥምረት በጠሩት ሕዝባዊ ስብሰባ  ላይ አሁን በኢትዮጵያ እየተረገ ያለውን ዲሞክራሲያዊ የለውጥ ሂደት እንደሚደግፉ በጋራ መግለጫ በማውጣት ጭምር ውሳኔ አሳልፈዋል።ከላይ በተጠቀሰው ቀን ከቀትር በኃላ 9 ሰዓት ላይ የተጀመረው ስብሰባ ''በአባይ ሚድያ'' ቀጥታ የቪድዮ ስርጭት ለመላው ዓለም  ተከታታዮች እንዲታይ  ሽፋን ማግኘቱን ጉዳያችን በስፍራው ተገኝታ ለመረዳት ችላለች።  

በስብሰባው ላይ የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ (ኮሚኒቲ) ሰብሳቢ አቶ ፍቅሩ ሁሴን እና ከፖለቲካ ድርጅት የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራር እና የኖርዌይ ቻፕተር ተጠሪ ዶ/ር ሙሉ ዓለም ተገኝተዋል።የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ሰብሳቢ ኮሚኒቲው አሁን ያለውን የኢትዮጵያ ለውጥ እንደ ኢትዮያዊ ሲቪክ ድርጅት እንደሚከታተሉ እና  በአዎንታዊ መልክ እንደሚመለከቱት ከገለጡ ባኃላ በቅርቡ በኢትዮጵያ በነበሩበት ወቅት የተመለከቱት የሕዝብ ደስተኛ ስሜት ከእዚህ በፊት ያልተመለከቱት መሆኑን ምስክርነታቸውን ከመስጠታቸውም በላይ ወደፊት ከኮምንቲው አመራር ጋር ተመካክረው በጋራ በሚደርሱበት ውሳኔ መሰረት የሚጠበቅባቸውን ሁሉ  ለማከናወን ዝግጁነታቸውን ለተሰብሳቢዎቹ አረጋግጠዋል።

የአርበኞች ግንቦት 7 አመራር እና የኖርዌይ ቻፕተር ተጠሪ ዶ/ር ሙሉ ዓለም የአርበኞች ግንቦት 7 ሊቀመንበር ከጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ጋር ሁለት ዙር ውይይት እንደተደረገ እና በቅርቡ ድርጅቱ በውይይቱ ውጤት ላይ ተንተርሶ መግለጫ እንደሚሰጥ አስታውቀዋል።

ቀድም ብሎም የዲሞክራቲካዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ሰጪ ድርጅት  ሰብሳቢ አቶ ይበልጣል ጋሹ የድርጅቱን ቀደም ብሎ ዲሞክራሲ በኢትዮጵያ እንዲሰፍን ያደረገውን ትግል አብራርተው  አሁን ያለውን የለውጥ ሂደት የዲሞክራቲክ ለውጥ ድጋፍ በኢትዮጵያ እንደሚደግፈው ገልጧል።በመቀጠል የኢትዮጵያውያን የጋራ መድረክ ሰብሳቢ አቶ ጌታቸው በቀለ በአሁኑ ወቅት  ለውጥ በኢትዮጵያ አለ ወይንስ የለም? በሚል ርዕስ ለሃያ ደቂቃዎች የፈጀ የለውጡን ሂደት ፣የለውጥ መኖር፣ ሁለተናዊ ተፅኖውን  እና የውጭው ማኅበረሰብ የሚጠበቅበትን ተግባራት ዙርያ የመነሻ ፅሁፍ አቀርቦ በተሰብሳቢዎች ውይይት ተደርጎበታል።

በእዚሁ ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አንድ ዶላር ለወገን ጥሪ ላይ ውይይት ከተደረገ በኃላ ወደ ተግባራዊነቱ ለመግባት ኃላፊነቱን ለኢትዮጵያውያን ማኅበረሰብ (ኮምዩንቲ) ኃላፊነቱ የተሰጠው ሲሆን  የጋራ መግለጫም  ወጥቷል። በስብሰባው ማጠቃለያ ላይ የወጣው የስብሰባው የጋራ መግለጫ ከእዚህ በታች ይመልከቱ።


በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን የመደመርና የፍቅር ቀን በሚል በሀገራችን ኢትዮጵያ የተጀመረውን ለውጥ በመደገፍ የተሰጠ የአቋም መግለጫ! 

ሀገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት 27 ዓመታት ለፍትህ፣ለነፃነት፣ለአንድነት የከፈሉት ዋጋ በቃላት ብቻ የሚገለጥ አይደለም። የተከፈለው ዋጋም ፍሬ አፍርቶ አሁን ሀገራችን በለውጥ ሂደት ላይ ትገኛለች። ይህ የለውጥ ተስፍ እንዲመጣ ብዙዎች የህይወት ዋጋ ከፍለውበታል። የአካልና የመንፈስ ስብራት ደርሶባቸዋል። 


እኛ በኖርዌይ የምንኖር ኢትዮጵያዊያን አቅማችን በፈቀደው መልኩ አገራችን ኢትዮጵያ ከአረመኔያዊ ዘር ገነን አገዛዝ ነጻ ወጥታ፣ ሰባዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ሙሉ በሙሉ ተከብረው፣ ዜጎች በእኩልነት የሚኖሩባት ሀገር በመገንባት የተረጋጋችና ዲሞክራሲያዊት አገር ትሆን የበኩላችንን አስትዋጾ በድርጅትም በግለሰብ ደረጃ አስትዋጾ ስናበረክት ቆይተናል። ጠቅላይ ሚኔስተር ዶ/ር አብይ አህመድና የለውጡ ቡድን ብዙዎች መስዋዕትነትን የከፈሉበትን ዓላማ ከግብ እንዲደርስና የተጀመረው ለውጥ እንዲመጣ ከፍተኛ ሚና ስላበረከቱልን በስብሰባው ላይ የተገኘን ኢትዮጵያዊያን በታላቅ ደስታ ልባዊ አክብሮትና ምስጋና አቅርበናል። ስለሆነም በዚህ ዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ሰጭ ድርጅት በኖርዌይና በኢትዮጵያውያን የጋራ መድረክ በተዘጋጀው ስብሰባ ላይ የተገኘን እኛ በኖርዌይ የምንኖር ኢትዮጵያውያን የተጀመረው የለውጥ ሂደት ለዓመታት ስንታገልለት የነበረ ፅኑ ዓላማችን በመሆኑ በማነኛውም መልኩ ለውጡን ከዳር ለማድረስና የጠነከረ መሰረት እንዲይዝ ለማድረግ የበኩላችንን አስትዋፅኦ ለማበርከት በአንድ ድምፅ ተስማምተናል። 


በዚህም መሰረት የስብሰባው ተሳታፊዎች በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ ተስማምተን የአቋም መግለጫ አውጥተናል። 


1ኛ/ አሁን በሀገራችን የተጀመረው የመደመር እና የፍቅር ሂደት በፍትሃዊና ስር ነቀል እርቅ እንዲሆን፤ 


2ኛ/ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ለዘለቄታዊ ለውጥ ለሚደረግ ጥሪ ሁለተናዊ ድጋፍ መስጠት በሚገባን ሁሉ የበኩላችንን አስተዋፅኦ ለማድረግ ከመቼውም በበለጠ ዝግጁዎች ነን፣ 


3ኛ/ አሁን የተጀመረውን ለውጥ ለማደናቀፍ የሚደረግ ማናቸውንም ሙከራ በጥብቅ እንቃወማለን፣እናወግዛለን፤ 


4ኛ/ ከዚህ በፊት የነበርን የፖለቲካ፣የአመለካከት፣ የብሄርና ሌሎች ልዩነቶችን በማጥበብ በፍቅርና የጋራ ሀገራችንን ለመገንባት ተስማምተናል፤ 


5ኛ/ ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ የለውጥና ሰላም ሐዋርያ ስለሆኑ የኖቬል ተሸላሚ እንዲሆኑ ቅስቀሳ እናደርጋለን፤ 


6ኛ/ ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ አህመድ ላለፉት ሶስት ወራት የወሰዱት የለውጥ እርምጃ የምንደግፍ መሆናችንን እየገለጥን ለወደፊትም ሃገርን የመገንባት ሂደት ላይ ሁሉ መንግስታዊና ማኅበራዊ ተቋማት በሙሉ ነፃነት እንዲሰሩ ለሚደረገው ጥረት የበኩላችንን አስተዋፅኦ እናደርጋለን፤ 7ኛ/ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በቀን ከሚያወጡት አንድ ዶላር ለሀገራቸው አስተዋፅኦ እንዲያደርጉ ባደረጉት ጥሪ መሰረት በኖርዌይ የምንኖር ኢትዮጵያውያንም የበኩላችንን ለማድረግ በዛሬው ስብሰባችን በኖርዌይ የኢትዮጵያ ማህበር በኩል የገንዘብ ማሰባሰብ ተግባር እንዲከናወን እና እኛም ሃገራዊ ግዳጃችንን በፍቅር፣ በሰላም፣ በመደመርና በይቅርታ ለመወጣት ተስማምተናል፤ 


ጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ! 


ሐምሌ 28/2018 እኤአ ኦስሎ፣ ኖርዌይ 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Friday, July 27, 2018

የኢንጅነር ስመኘው በቀለ ሞት ተከትሎ ለኢትዮጵያ መንግስት እና ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር የቀረቡ አራት ጥያቄዎች (ጉዳያችን)

የኢትዮጵያ ዓባይ ግድብ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ኢንጅነር ስመኘው በቀለ 
===============================
ጉዳያችን/Gudayachn
ሐምሌ 20/2010 ዓም (ጁላይ 27/2018 ዓም)

የኢትዮጵያ ዓባይ ግድብ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና ኢንጅነር ስመኘው ትናንት ሐምሌ 19/2010 ዓም በመስቀል አደባባይ በመኪናቸው ውስጥ እያሉ በጥይት ተገድለው ተገኝተዋል።ድርጊቱ እጅግ አሳዛኝ ነው።ወንጀለኞቹ አደባባይ መጋለጣቸው አይቀርም። አሁን ያለችው ኢትዮጵያ ደግሞ ማንንም በተንኮል የምትከስ አለመሆኗ ምርመራው ተጣርቶ በመንግስት በኩል የሚቀርበውን ውጤት ሕዝብ በሙሉ መተማመን የሚቀበለው ውጤት ነው።
ዛሬ ሐምሌ 20/2010 ዓም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ዋሽንግተን ላይ ለተሰበሰቡ የኢትዮጵያውያን ሙስሊም ማሕበረሰብ አባላት ባደረጉት ንግግር : - 

"ለሀገሩ እየሰራ የነበረው ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ትናንት ተገድሏል። ግድያው በማን እንደተፈፀመ ምርመራው ገና እየተጣራ ነው። ሽፍታ በጫካ ውስጥ ዝርፊያና ግድያ መፈፀሙ የተለመደ ነው።ነገር ገን በጠራራ ፀሀይ መሀል ከተማ ላይ የሚፈፀምባት ሀገር ከመምራት በላይ የሚያሳፍር ነገር የለም።ሰይጣን ሲጀመርም ነበር፣እስከ መጨረሻውም ይኖራል።ክፉ ነገር ስንመለከት ሰው ነን እና ማዘናችን አይቀርም ፣ ሆኖም ግን ጥርሳችንን ነክሰን እንሻገራለን እናሸንፋለን።" ብለዋል።


የቀብር ስነ ስርዓታቸው በመጪው እሁድ ቅድስት ስላሴ ቤተ ክርስቲያን በመንግስታዊ የጀግና ስነ ስርዓት የሚፈፀመው ኢንጅነር ስመኘው ቀብር ላይ በርካታ ሕዝብ እንደሚገኝ ይጠበቃል።  

በመጨረሻም  ጉዳያችን መንግስትን የሚከተሉትን ጥያቄዎች ትጠይቃለች። እነርሱም : - 


1ኛ) ያለፈ የግድቡ የስራ ሂደት ላይ የነበሩበት የአፈፃፀም ችግሮች እና መልካም ጎኖች እንዲሁም  የወደፊቱ እቅድ ማብራርያ በመገናኛ ብዙሃን እንዲሰጥ፣ 


2ኛ) መንግስት በቀብራቸው ቀን የግድቡን ስያሜ በኢንጅነር ስመኘው በቀለ ስም እንዲሰይምልን፣

3ኛ) የግድቡ መግቢያ ላይ ''ለኢትዮጵያ እድገት መስዋዕት የሆኑ'' በሚል አንድ ሐውልት እንዲያቆምላቸው እና 

4ኛ) በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በግድቡ ዙርያ  በገንዘብም ሆነ በሙያ ያላቸው ተሳትፎ እንዲያድግ ሁኔታዎች እንዲመቻቹ ።

ድምፃዊ ፀጋዬ እሸቱ ''ይዋል ይደር እንጂ ቀን ይመሰክራል''


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Thursday, July 26, 2018

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሲኖዶስ አንድነት የዕርቅ ጉባኤ ዝርዝር ውሳኔ እና የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ አህመድ የቪድዮ ንግግር።

ጉዳያችን/Gudayachn
ሐምሌ 19/2010 ዓም (ጁላይ 26/2018 ዓም)
በሁለቱም ሲኖዶስ ለዑካን በተፈጸመው እርቅ የተደረስበትን ስምምነት ቃል በቃል እንደሚከተለው ይቀርባል።
1. ስለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ
በሀገራችን ኢትዮጵያ በ1983 ዓ.ም. በተፈጠረው የመንግሥት ለውጥ የተነሣ አንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ለሁለት ተከፍላ በሁለት ፓትርያርኮች የሚመሩ አንድ ሲኖዶስ ለሁለት ሲኖዶሶች መፈጠራቸው ግልጽ ነው። በዚህም የተነሣ አራተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ከሁለት አሥርት ዓመታት በላይ በስደት ዓለም መቆየታቸው ይታወቃል። ስለሆነም የሁለቱን ቅዱሳን ፓትርያርኮች ቀጣይ ሁኔታ በተመለከተ በሁለቱም ቅዱስ ሲኖዶሶች የተወከሉት የሰላም ልዑካን ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ሰላም በአደረጉት የጋራ ስብሰባ በሰፊው ከተወያዩ በኋላ እንደሚከተለው በአንድ ድምጽ ወስነዋል።
ሀ/ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ በፓትያርክነት ክብርና ደረጃ ወደ ቅድስት አገር ኢትዮጵያ እንዲመለሱ /እንዲገቡ፤
ለ/ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ወደ አገር ቤት ኢትዮጵያ ሲመለሱ በክብር የሚያርፉበትን የመኖሪያ ቦታ በተመለከተ ደረጃውን የጠበቀ በመንበረ ፓትርያርክ ግቢ ውስጥ ቦታ ተዘጋጅቶና የሚያስፈልጋቸው ሁሉ ተሟልቶ በክብር እንዲቀመጡ፤
ሐ/ የሥራ አፈጻጽምን በተመለከተ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ጸሎት እና ቡራኬ በማድረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ፤
1.1/ ስለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤
ሀ/ በሕገ ቤተ ክርቲያን መሠረት የአስተዳድር ሥራውን በመሥራት ቅድስት ቤተ ክርስቲንን እንዲመሩ፤
ለ/ ጸሎት እና ቡራኬ በማድረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ፤
1.2/ የሁለቱም ቅዱሳን ፓትርያርክ አባቶቻችን ስም በቅደም ተከተል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአለችበት ዓለም ሁሉ ዘወትር በጸሎት እንዲነሣ፤
1.3/ ሁለቱ ቅዱሳን ፓትርያርኮች በሕይወተ ሥጋ እስከ አሉ ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በእኩልነት የአባትነት ክብራቸውን ጠብቃ እንድትይዝ፤
1.4/ይህ ስምምነት ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ የአገር ቤትና የውጭ አገር ሲኖዶስ የሚለው ስም ቀርቶ አንዲት ቤተ ክርስቲያንና አንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ እንዲሆን፤
2. ስለ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት
ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት የተነሳ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፈተና ላይ ወድቃለች። ይህም ይታወቅ ዘንድ ሁለተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ተላልፈው ለሞት ከተሰጡበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ የቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥሰት እንደ ተፈጸመ በልዑካኑ ታምኖብታል። ስለሆነም ለአለፉት ዘመናት የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መብትና ክብር በመጠበቅና በማስጠበቅ በውጭም ሆነ በውስጥ በአገር ቤት የሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ ኃላፊነቱን መወጣት ባለመቻሉና ከጊዜው ጋር አብሮ በመሄዱ ስለተፈጸመው ጥፋትና ለዘመናት በቤተ ክርስቲያኒቱ መለያየት የተነሣ በጥልቅ ኃዘን ልባችው የተሰበረውን የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ልጆች ያለፉትንም ሆነ ዛሬ ላይ ያሉትን በጋራ ይቅርታ እንዲጠይቅ የልዑካኑ ጉባዔ በአንድ ድምጽ ተስማምቶ ወስኖአል።
ስለሆነም ከሁለቱም ሲኖዶስ ውህደት በኋላ ያለፈው የቀኖና ጥሰት ስህተት ለወደፊቱ እንዳይደገም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሉዓላዊነት ተጠብቆና ጸንቶ እንዲኖር ለማድረግ ሕገ ቤተ ክርስቲያንንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት ያደረገ ደንብ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባዔ እንዲዘጋጅ የልዑካኑ ጉባዔ በአንድ ድምጽ ተስማምቶ ወስኖአል።
3. ስለነባር ሊቃነ ጳጳሳት
ከልዩነት በፊት የተሾሙ ነባር ሊቃነ ጳጳሳትን በተመለከተ በሁለቱ ሲኖዶስ የተላለፈው ቃለ ውግዘት በጋራ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተፈቶ ስማቸውና ክብራቸው ተጠብቆ በውጭ ሀገርም ሆነ በሀገር ቤት በሀገረ ስብከት እንዲመደቡና እንዲያገለግሉ ጉባኤው በአንድ ድምጽ ተስማምቶአል።
4. ከልዩነት በኋላ ስለተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳት፤ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት
ከልዩነት በኋላ በሁለቱም ወገኖች የተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳትን፤ ጳጳሳትንና ኤጲስቆጶሳትን በተመለከተ ፦ ስማቸውን እንደያዙ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቀበላቸውና በውጭ ዓለምም ሆነ በሀገር ቤት በሀገረ ስብከት ተመድበው እንዲያገለግሉ ጉባዔው በአንድ ድምጽ ተስማምቶአል። ስም አጠራራቸውንም አስመልክቶ እንደ ሹመት ቅደም ተከተላቸው ቀዳማይ፤ካልዓይ፤ሣልሳይ... ወዘተ እየተባሉ እንዲጠሩ ጉባዔው በአንድ ድምጽ ወስኖአል።
5. ስለቃለ ውግዘት
በተፈጠረው ችግር ምክንያት በሁለቱም ሲኖዶስ ቃለ ውግዘት እንደ ተላለፈ ይታወቃል። ስለሆነም ከዚህ ስምምነት በኋላ ቃለ ውግዘቱ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ እንዲነሣ የሰላም ልዑካኑ በአንድ ድምጽ ወስኖአል።

6. በውጭ ዓለም በስደት የምትገኘውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓላማ ያገናዘበ መዋቅራዊ አስተዳድርን ስለማዘጋጀት
እንደሚታወቀው በዘመናችን በየትኛውም ዓለም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ በአሉበት ሁሉ ተስፋፍታ ትገኛለች። ይሁን እንጂ በውጭ ዓለም የምትገኝ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከእናት ቤተ ክርስቲያን ጋር አንድነቷን፤ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንንና ክብሯን ጠብቃ መኖር እንዳለባት ጉባዔው አምኖበታል።
ስለሆነም የየሀገሩን ሕገ መንግሥት መሠረት ያደረገ የቃለ አዋዲውና የሕገ ቤተ ክርስቲያን ገዥነት የሚረጋገጥበት መመሪያ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲያዘጋጅ ልዑካኑ በአንድ ድምጽ ወስኗል። እንዲሁም በውጭ ዓለም የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንና በመዋቅራዊ አስተዳድር መሠረት ከአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ በመቀበል በአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ እንድትመራም ወስኖአል።
በተጨማሪም በሁለቱ ሲኖዶስ መካከል የተደረገውን የዕርቀ ሰላም ስምምነት ተግባራዊ ለማድረግና የሁለቱንም ሲኖዶስ ውሕደት ፍጹም ለማድረግ እንዲሁም በስደት የሚገኙ ብፁዓን አባቶች ወደ እናት አገራቸው ተመልሰው፥ የቀደመውን ሰላምና አንድነት አጽንተው፥ ሁሉም በአንድ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚተዳደሩበትን ቅድመ ሁኔታ የሁለቱም ቅዱስ ሲኖዶስ ተወካይ ልዑካን እንዲያዘጋጁና እንዲከታተሉ የሁለቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ተወካይ ልዑክ በአንድ ድምጽ ወስኗል።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐብይ አህመድ ከስኖዶሳዊ ዕርቅ ውሳኔ በኃላ ያደረጉት ንግግር

ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Tuesday, July 24, 2018

«ሃይማኖት አረጀ ቢሉ» ግጥም በገጣሚት አፎምያ ሚካኤል (ቪድዮ)

ወ/ሮ አፎምያ ሚካኤል ኦስሎ፣ኖርዌይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ መካነ ቅዱሳን ቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ምዕመን ነች።



ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Sunday, July 22, 2018

ለሃያ አራት ዓመታት በትግራይ በእስር ላይ የሚገኙት የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን ሊቅ ሴት ልጅ አባቷ እንዲፈቱ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ድምፁን እንዲሰማ ለፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ግልፅ ደብዳቤ በጠበቃዋ በኩል ላከች ።Ethiopian daughter sent an official letter to French President.(Gudayachn Exclusive)


ደብዳቤው የተፃፈላቸው የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ማርኮን 

ጉዳያችን/Gudayachn
ሐምሌ 16/2010 ዓም (ጁላይ 23/2018 ዓም)
  • በመላው ዓለም ያሉ ኢትዮጵያውያን ደብዳቤውን ወደ እንግሊዝኛ በመቀየርም ጭምር ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ  በተለይ ለሰብዓዊ መብት ድርጅቶች እና ጋዜጠኞች እንዲያደርሱ ይለመናሉ።
ላለፉት ሃያ አራት ዓመታት በትግራይ እስር ቤት ታስረው የሚገኙት የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን ሊቅ እንደስራቸው አጉማሴ ሴት ልጅ ግልፅ ደብዳቤ አባቷ እንዲፈቱ ዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ድምፁን እንዲያሰማ ግፊት ያደርጉ ዘንድ ለፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ግልፅ ደብዳቤ ፅፋለች።ደብዳቤው በፈረንሳይኛ የተፃፈ ሲሆን አባቷ እንዴት እንደታገቱ እና ምን አይነት ፈተና ላይ እንዳሉ አብራርታ ፕሬዝዳንቱ አባቷ እንዲፈቱ ጥረት እንዲያደርጉ ተማፅናለች።
በመላው ዓለም ያሉ ኢትዮጵያውያን ደብዳቤውን ወደ እንግሊዝኛ በመቀየርም ጭምር ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ  በተለይ ለሰብዓዊ መብት ድርጅቶች እና ጋዜጠኞች እንዲያደርሱ ይለመናሉ።
A quarter century imprisoned. Ethiopian church senior scholar, ENDESIRACHEW AGUMASE's daughter sent an official letter to French president to make his effort to release her father from Tigray prison in Ethiopia. Please find full content of the letter here below.
የሊቁ እንደስራቸው አጉማሴ ሴት ልጅ ለፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት የላከችው ደብዳቤ ከእዚህ በታች ያንብቡ።

===========================================================

Madame Tirsit ENDESSERACHEW 
28, rue du Landsberg 
67100 STRASBOURG 
Tél. +33 6 95 17 41 38 
E-mail : tirsit67@gmail.com


Monsieur le Président de la République
Palais de l'Elysée
55, rue du Faubourg Saint Honoré
75008 PARIS
Strasbourg, le 19 juin 2018

LETTRE RECOMMANDÉE AVEC AVIS DE RECEPTION

Madame, Monsieur,

Je me permets de m'adresser à vous afin de solliciter votre aide dans la mesure du possible. Je ne vous cache pas si j'interviens auprès de hautes autorités, c'est parce que j'ai une lueur d'espoir pour retrouver mon père disparu depuis très longtemps. Je vous relate en un court résumé ce qui s'est passé. 

Mon père, ENDESSERACHEW Agmasie, né le 30 mai 1947 à DEBRETABOR (province de Gondar) en Éthiopie, Professeur de théologie, se trouve actuellement incarcéré dans une prison secrète en Éthiopie et ce depuis 24 ans. Le 19 juin 1994 (calendrier éthiopien 12 juillet 1986) vers 17 h 35 cinq hommes armés sont venus et l'ont enlevé alors qu'il revenait de son travail et l'ont emmené à Ras Gimb (un ancien palais à Gondar) qui était utilisé comme centre de torture souterrain par le gouvernement Éthiopien. Depuis ce jour aucune nouvelle. 

Un mois plus tard une tierce personne est venue nous voir de la part d'un gardien de la prison de Betemengist à Gondar désirant garder l'anonymat de peur de risquer sa vie et nous remettre une lettre manuscrite de mon père. Dans cette lettre il nous expliquait qu'il a été arrêté avec l'accusation de faire partie des opposants du gouvernement en l’occurrence le parti opposant ce qui est faux, mon père n'ayant jamais fait de politique. Cette accusation est due au fait que mon père a porté secours à une personne qui n'était autre que le Général Haile MELESE, lui-même opposant et activement recherché. Dans cette lettre il nous expliquait qu'il était enfermé dans un sous-sol, menotté, maltraité et torturé. À la suite de ce courrier nous il nous a encore été transmis deux autres lettres tenant les mêmes propos, puis plus rien, le gardien ayant été muté à plus de 1000 kilomètres. Depuis ce jour, plus de nouvelles, nous ne savions même pas si notre père était encore en vie, malgré nos nombreuses recherches. L'entourage et la famille de mon père a fait l'objet de nombreuses menaces, surtout envers moi-même, ce qui m'a obligé à m'enfuir d’Éthiopie pour me rendre à Dubaï et par la suite je me suis retrouvée en France où j'ai été accueillie avec le statut de réfugiée politique. 

Nous sommes restés sans nouvelles depuis 24 ans, sachant que mon père n'a jamais été jugé mais gardé en détention dans une des nombreuses prisons « secrète » où il se passe des choses les plus horribles qu'on ne peut même pas imaginer. Il y a quelques mois une personne faisant partie de l'état, a visité plusieurs de ces prisons « secrètes » et par hasard a rencontré mon père et a discuté avec lui demandant son état civil. Avec ces éléments il a fait des recherches et a envoyé une personne voir ma famille pour leur annoncer que notre père était toujours en vie. D'après les éléments recueillis cette prison serait dans la province de TIGRAI dans le nord de l’Éthiopie. Je vous supplie d'intervenir d'urgence pour obtenir la libération de mon père âgé de 71 ans pour qu'il puisse encore passer des moments restants de sa vie, le soigner et si nécessaire être jugé équitablement devant un tribunal après une si longue détention injustifiée. Je reste à votre disposition pour vous fournir encore de plus amples informations si nécessaire. Dans l'espoir que vous pourriez m'apporter de l'aide, veuillez agréer, Monsieur le Président de la République, l'expression de ma respectueuse considération.

Tirsit ENDESSERACHEW


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Tuesday, July 17, 2018

ሲኖዶስያዊው እርቅና የጠቅላይ ሚንስትሩ የአሜሪካ ጉዞ (የጉዳያችን ሪፖርት)


ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ከሊቃነ ጳጳሳት ጋር  ሰላምታ ሲለዋወጡ  
ጉዳያችን/Gudayachn 
ሐምሌ 11/2010 ዓም (ጁላይ 18፣2018 ዓም) 

በያዝነው የሐምሌ ወር 2010 ዓም በኢትዮጵያ የፖለቲካም ሆነ ማኅበራዊ ጉዳይ ላይ ሶስት ቁልፍ ጉዳዮች መልክ ይይዛሉ ተብሎ ይጠበቃል።የመጀመርያው እና ባሳለፍነው ሳምንት የተከናወነው ጉዳይ ከኤርትራ ጋር የነበረው ችግር በመሪዎቹ የተጀመረው ፖለቲካዊ ግንኙነት ታፍኖ የነበረውን የህዝብ ለሕዝብ ፍቅር አገንፍሎ መሪዎቹን እስከሚያስደነግጥ ድረስ ስሜት በሚነካ መልኩ ተፈፅሟል።የቀሩት ሁለት አበይት ተግባሮች ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ እርቅ እና የጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ወደ አሜሪካ የሚያደርጉት ጉብኝት ናቸው።

ሲኖዶሳዊው እርቅ 
ላለፉት ሃያ ስድስት አመታት ለሁለት ተከፍሎ የቆየው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወደ አንድ ለማምጣት አዲስ ዙር ንግግር በአሜሪካን መዲና ዋሽንግተን ውስጥ በመጪው ሐሙስ ሐምሌ 12 ይጀመራል። ለውይይቱም በውጭም ሆነ በሀገር ቤት ባሉት ሲኖዶሶች አንፃር ሶስት ሶስት አባቶች ተመድበዋል።ከእዚህ በተጨማሪ ላለፉት አስራ ሁለት ወራት ጥረት ሲያደርጉ የቆዩት አስታራቂ ኮሚቴ አባላትም ለስኖዶሳዊው እርቅ ዋሽንግተን  መግባት መጀመራቸውን ለማወቅ ተችሏል።
ይህ ሲኖዶሳዊ እርቅ የመጨረሻ መሆን እንዳለበት ሁሉም የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት እያሳሰቡ ነው።አሁን ወቅቱ ያለፈውን እያነሳን የምንወቅስበት አይደለም።የወደፊቱ ላይ ማተኮር ግን አስፈላጊ ነው።ይህ ማለት ያለፈው ስህተት ይሸፈን ማለት አይደለም።ትኩረት ችግሩን ፈትቶ ወደ አንድ ሲኖዶስ መምጣቱ እጅግ አንገብጋቢ ጉዳይ ነው።ለሲኖዶስ መከፈል አንዱ እና ዋናው ምክንያት የህወሓት መንግስት በቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት እና አሰራር ውስጥ ጣልቃ በመግባት በአቡነ መርቆርዮስ ላይ ያደረሰው ከመንበራቸው የመግፋት እኩይ ተግባር እንደነበር ይታወቃል።ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ ደግሞ የውጭውን ሲኖዶስ ለስኖዶሳዊ እርቅ የሚወክሉት አቡነ ኤልያስ ስዊድን ከተማ ሉንድ ውስጥ በተደረገ አውሮፓ አቀፍ ጉባኤ ላይ የ1984 ዓም የፓትርያርኩን እና የጳጳሳቱን ስደት አስመልክተው ለምእመናን እንደተናገሩት -
 ''ምእመናን! በወቅቱ (የነበረውን ስውር የመንግስት እጅ ማለታቸው ነው) ሊገድሉን እንደነበረ ታውቃላችሁ?'' ካሉ በኃላ ''ወጣቱ የችግሩን መንስኤ በሚገባ ማወቅ አለበት። እግዚአብሔር ይህንን ዶ/ር ዓብይን አመጣው።ይህ የሰው ሥራ እንዳይመስላችሁ።የእግዚአብሔር ተአምር ነው።አሁንም የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር ለመፍታት ለምናደርገው ሁሉ ምዕመናን ፀልዩልን።እኔ በምእመናን ፀሎት አምናለሁ።እግዚአብሔር የሚያውቃቸው  ሰው የማያውቃቸው የሚፀልዩ አሉ'' ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሁሉም ወገኖች በጉጉት የሚጠበቀው ሲኖዶሳዊ እርቅ ከተከናወነ በኃላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በርካታ ስራዎች ይጠብቃታል።የመጀመርያው ተግባር መዋቅሯን፣ከቤተ ክህነት ውስጥ ያለውን አሰራር፣የአጥብያዎች የቢሮ አሰራር፣የአገልጋይ አመዳደብ፣የገንዘብ አያያዝ እና በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ አጥብያዎች እና ሃገረ ስብከቶች መካከል ያሉ አሰራሮች በሙሉ ማዘመን እና ተጠያቂነትን በሚገባ ያሰፈነ ማድረግ ሁሉ አንገብጋቢ ተግባራት ናቸው።ከእዚህ በተለየ ቅዱስ ሲኖዶስ ከዘመኑ ጋር የገጠሙ የቀኖና ስርዓቶች መቀነን እና ምእመናን እንዲመሩበት ማድረግ ሌላው አስፈላጊ ጉዳይ ነው። ከእዚህ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተልዕኮ ሀገር አቀፍ፣ አፍሪካ አቀፍ እና ዓለም አቀፍ እንዲሆን መስራት ያሉባት በርካታ ተግባራት አሉ።የቤተ ክርስቲያን ሚና ለሀገራዊ ሰላም እና መረጋጋት ያላትን ሚናም ማሳደግ ሌላው እጅግ አስፈላጊ ጉዳይ ነው። 

ሐሙስ ሐምሌ 12 የሚጀመረው ሲኖዶሳዊ እርቅ በተመለከተ የእርቅ ሂደቱ ሲጀመር እና በሂደት ላይ እያለ ምዕመናን ከስሜት፣እና ከወገንተኝነት የፀዳ ስሜት ሆነው መከታተል እንጂ ቀድመው አላስፈላጊ ሃሳቦችን በማህበራዊ ሚድያ ከመግለጥ መቆጠብ ይገባቸዋል።ይህ ማሳሰብያ ሚድያዎችንም ይመለከታል።

በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ በሐምሌ ወር ሁለተኛ አጋማሽ ላይ በሚደረገው የአሜሪካ ጉዞ ውስጥ ከተካተተው መርሃ ግብር ውስጥ አንዱ በስደት የሚገኙትን የኢትዮያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስን መጎብኘት እና የስኖዶሳዊ እርቁን ተከትሎ ባለው ውጤት መሰረት ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና አስታራቂ ኮሚቴ ካህናት አባቶች እና ምዕመናን ጋር መወያየት ነው።ከእዚህ በፊት በተደረጉ ሲኖዶሳዊ እርቅ ሙከራዎች ውስጥ አንዱ እንቅፋት ሆኖ የቆየው የመንግስት ፈቃደኝነት አለማሳየት ብቻ ሳይሆን ወደ እርቅ የቀረቡ ሂደቶችን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ማደናቀፍ እንደነበረ ይታወቃል።ለምሳሌ ከአራት አመታት በፊት በዳላስ ቅዱስ ሚካኤል ተሞክሮ የነበረው ሲኖዶሳዊ እርቅ በወቅቱ በነበሩት ፕሬዝዳንት ግርማ የድጋፍ ደብዳቤ አባቶች ወደ ሀገራቸው እንዲመጡ የሚያዝ ቢሆንም በመሀከል በተለየ መልክ የህወሓት ከፍተኛ አባላት በተለይ አቦይ ስብሐት በቀጥታ ጣልቃ በመግባት እና በስደት የሚገኙትን አባቶች ቃል በቃል ''ሊሰቀሉ ይገባል'' የሚል እና ሌሎች አሳፋሪ ንግግሮች በመናገር እንዲሁም  የወቅቱ ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ የፃፉትን ደብዳቤ እንዲስቡ ተፅኖ በመፍጠር ሂደቱ እንዲደናቀፍ መደረጉ ይታወሳል። በአሁኑ ሲኖዶሳዊ እርቅ ሂደት ግን የመንግስት ድጋፍ ከፍተኛ ከመሆኑ ባለፈ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ በቀጥታ በጉዳይ በመግባት እና በማበረታታት እንዲሁም ወደ ሀገር ቤት ከስደት ለሚመለሱ አባቶች ዋስትና በመስጠት ጭምር እጅግ ከፍ ያለ አስተዋፅኦ እያደረጉ ነው።አባቶቻችንም ይህንኑ መልካም ጉዳይ ከዳር አድርሰው የቤተ ክርስቲያኒቱን  አንድነት ወደነበረበት እንደሚመልሱ ተስፋችን ከፍ ያለ ነው።ከእዚህ ሁሉ ሂደት ጋር ግን በስደት ያሉ አባቶች ወደ ሀገር ቤት ሲገቡ የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅር በጠበቀ መልኩ መሆኑ እጅግ አስፈላጊ ነው።ይህ ማለት ሀገር ቤት ከቤተ ክህነቱ የተለየ ሌላ ፅህፈት ቤት ወይንም ቢሮ መክፈት በሚል የሚመክሩ አንዳንድ በውጭ ያሉ በስደት ላሉ አባቶች የሚቆረቆሩ የሚመስሉ አካላት በሀገር ቤት ያለውን ምእመንም ሆነ ነባራዊ ሁኔታ ካለመረዳት የሚመነጭ መሆኑ መታወቅ አለበት።ይህ አካሄድ ቤተ ክርስቲያንን ለበለጠ መለያየት የሚዳርግ ከመሆኑም በላይ እንደ ሀገርም ወደ አደገኛ እና የባሰ ሁኔታ የሚመራ መሆኑ መረዳት ተገቢ ነው። 

የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ የአሜሪካ ጉዞ 


ዘንድሮ አሜሪካ ኢትዮጵያውያን ለስደት ከወጡባት ምናልባትም ላለፉት አርባ አመታት ያህል አይታ የማታውቀውን አዲስ ክስተት ታስተናግዳለች።ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ በሶስት ከተሞች የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ይጎበኛሉ።ጉብኝቶቹ በሁለት መልክ የሚደረጉ እንደሆነ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ቡርቱካን አያና የሚመራውና ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በጸሐፊነት የሚገኙበት፣የጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሜሪካ ጉብኝት አመቻች ኮሚቴ አዲስ አበባ፣ዋሽንግተን እና ሎስ አንጀለስ ላይ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።ይሄውም በሺህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የሚገኙባቸው እና ከተለያዩ የህብረተሰቡ ክፍሎች የተውጣጡ ስብስቦች ጋር የሚደረጉ ውይይቶች ናቸው።ይህ ''ግንቡን እናፈርሳለን፣ ድልድዩን እንገነባለን'' በሚል መርህ የሚደረገው ጉብኝት ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት እራሳቸውን ያገለሉ ባለሙያዎች እና ሀገር ወዳዶች እንደሚሳተፉ ሲጠበቅ በሌላ በኩል በውጭ የተወለዱ እና በማደጎነት የሄዱ ከፍተኛ ሃገራዊ ፍቅር ያላቸው ትውልደ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለመጀመርያ ጊዜ በኢትዮጵያ ጉዳይ የሚሰባሰቡበት ድንቅ የሆነ ስብስብ እንደሚሆን ይጠበቃል።
በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሜሪካንን ምድር ሲረግጡ በርካታ ቁጥር ያለው ኢትዮጵያዊ ከአየር መንገዶች ጀምሮ የሚያደርገው አቀባበል ከፍተኛ የዓለም አቀፍ ዜና አውታሮችን እንዲስብ ተደርጎ መዘጋጀቱ ለኢትዮጵያ የሚሰጠው መልካም ስም የጉብኝት አመቻች ኮሚቴ ቢያስብበት ጥሩ መሆኑን የሚናገሩ ብዙዎች ናቸው። በሌላ በኩል ድልድይ መገንባት በሀገር ቤት እና በውጭ ባለው ማኅበረሰብ መሃከል ጭምርም ስለሆነ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የሁሉንም ከተሞች ዝግጅቶች በቀጥታ ስርጭት ለኢትዮጵያ ሕዝብ እና ለመላው ዓለም ቢያዳርስ ለእዚህም የማስታወቂያ ስፖንሰሮች መሰረታቸውን አሜሪካ ካደረጉ የኢትዮጵያውያን ንግድ ድርጅቶች ማግኘት እንደሚችል ቢያስብ መልካም ይሆናል።ይህ ማለት ኢቲቪ ስንት ዓመት ሲያስከፋን እንዳልኖረ በውጭ ከሚኖረው ኢትዮጵያዊ ጋር በእዚህ ሰበብ ቢደመር ይሻለዋል።ይህ ድልድይ አንዴ ከተሰራ ኢቲቪ ቢሮውን ዋሽንግተን ላይ መክፈት እና በትርፍ ጊዜ አገልጋዮች የዲያስፖራውን ስሜት እየተከተለ የሚሰራቸውን መርሃ ግብሮች ማስፋት ሁሉ ይጠበቅበታል።

የጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሜሪካ ጉዞ መርሃ ግብር ቀን እና አድራሻ 
ሐምሌ 21(July 28) ዋሽንግተን ዲሲ
ሐምሌ 22(July 29) ሎስ አንጀለስ
ሐምሌ 23(July 30) ሜኔሶታ 
በዋሽንግተን ዲሲ
ሐምሌ 21 ቀን 2010 ዓም
July 28, 2018
አድራሻ
Walter E. Washington Convention Center
801 Mt Vernon Pl NW, Washington, DC 20001
በሎስ አንጀለስ
ሐምሌ 22 ቀን 2010 ዓም
July 29, 2018
አድራሻ
Los Angeles convention center 1201s Figueroa st.Los Angeles CA 90015
በሜኔሶታ 
ሐምሌ 23(July 30)
July 30/2018
600 N 1st Ave.
Minneapolis MN 55403
starting at 10 AM


በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ቡርቱካን አያና የሚመራውና ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በጸሐፊነት የሚገኙበት፣የጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሜሪካ ጉብኝት አመቻች ኮሚቴ
ከእዚህ በተጨማሪ በሁሉም ከተሞች የጠቅላይ ሚኒስትሩ መርሃግብር ላይ ሁሉም ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የተጋበዙ ሲሆን ለሁሉም ከተሞች መግብያ በነፃ ነው።
ለማጠቃለል ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን አስመልክተው ከተናገሩት በመጥቀስ ሪፖርቱን እደመድማለሁ።
"በውጭ ሀገር የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን ሀገራችሁን ተሸክማችሁ እንደሄዳችሁ እንረዳለን። ኢትዮጵያውያንን ከኢትዮጵያ ታወጧቸው ይሆናል እንጅ ኢትዮጵያን ከኢትዮጵያውያን ልብ ልታወጧት አትችሉም የሚባለውን ለዚህ ነው። የጋራ ሀገራችንን በጋራ ልንገነባ ይገባል። ከመወቃቀስ ወጥተን መተባበር ይገባናል። በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ የምትኖሩ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ከልብ ታርቀንና ብሔራዊ መግባባትን ፈጥረን ለጋራ ሀገራችን ልንሠራ ይገባል። ዘረኝነትና መከፋፈልን እናጥፋለን። ኢትዮጵያ በልጆቿ ታፍራና ተከብራ ትኖራለች። ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ።” ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ 

ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Tuesday, July 10, 2018

አንዳንድ በእድሜ የገፉ ኤርትራውያን ዲያስፖራዎች የአቶ ኢሳያስ ጋሬጣ ወይንስ አጋዥ? ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወደፊት ሊያተኩሩበት የሚገባው ዋናው ጉዳይ የቱ ነው?

ጉዳያችን/Gudayachn
ሐምሌ 3/2010 ዓም (ጁላይ 10/2018 ዓም)


አንዳንድ በእድሜ የገፉ ኤርትራውያን ዲያስፖራዎች የአቶ ኢሳያስ ጋሬጣ ወይንስ አጋዥ?


የኢትዮጵያ እና ኤርትራ የ1990 ዓም ግጭት መልሶ ለመፈጠሩ ምክንያቶች ላይ በጉዳዩ ዙርያ  የጠለቀ መረጃ  በነበራቸው ሰዎች  ብዙ ተብሏል።በጠራ መልኩ ደግሞ የታሪክ ፀሐፊዎች ወደፊት ያስነብቡናል ብለን ተስፋ እናደርጋለን። በእዚህ ፅሁፍ ላይ ግን የማነሳው አንዱ ጉዳይ በውጭ የሚኖሩ በእድሜ የገፉ አንዳንድ የኤርትራ ተወላጆች ከአቶ ኢሳያስ ብሰው እና ለእራሳቸው ለአቶ ኢሳያስም መገራት ያስቸገሩበት ሁኔታ እንደነበር ዛሬ ላይ ማንሳቱ ለወደፊቱም ጠቀሜታ ያለው ይመስለኛል።ዛሬ ላይ በእድሜ የገፉ የምንላቸው የዲያስፖራ ኤርትራ ተወላጆች በመጀመርያ ለጀብሃ ቀጥለው ለሻብያ ገንዘብ በማዋጣት እና በውጭ ሀገር በሚደረጉ የገቢ ማሰባሰብያ ዝግጅቶች ላይ የመሳተፍ ሚና ብቻ ያላቸው ነበሩ።ሆኖም ግን በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መካከል ያለው ትልቅ፣የታሪክ፣የትውልድ፣የሃይማኖት እና የቤተሰባዊ ግንኙነት ወደጎን አድርገው ግንኙነቱ  እንዳይጠናከር አንዳንዶች ለማጠናከር ሲሞክሩም የኤርትራን ሃገራዊነት የሚያጠፋ አደጋ አድርገው ይቆጥሩ ነበር።በእዚህም ሳብያ በእምነት ድርጅቶች ውስጥ አመራርነት እየያዙ ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን ወጣቶችን አብረው የእምነት ቦታዎቻቸው ላይ መታደማቸውን በእራሱ ሲበጠብጡት ኖረዋል።ይህ በተለይ ከኢትዮጵያ የዛሬ ሃያ ዓመት  ''ትውልደ ኤርትራውያን'' እየተባሉ በህወሓት ተባረው የወጡትን የአዲሱ ትውልድ አካላት  ቀደም ብለው በውጭ ሃገራት  በያዙት ማኅበራዊ መሠረትነት ሳብያ እነኝሁ በእድሜ የገፉ ኤርትራውያን አዲሶቹን ስደተኞች ከኢትዮጵያውያን ለመለየት ብዙ መጣራቸው ይታወሳል።ሆኖም ግን የማኅበራዊ  እና የሃይማኖት መሰረቶች ቀላል ስላልሆኑ ወጣቶቹ ፈፅመው አልተቀበሏቸው።

እነኚሁ በውጭ የሚኖሩ በእድሜ የገፉ ኤርትራውያን ትውልድ ከትውልድ ማስታረቅ ሲገባቸው ምን ያህል በሚያባብሱ ስራዎች ላይ የተጠመዱ እንደነበር በቀላሉ ለማሳየት  የአቶ ኢሳይሳን አስተዳደርም የተፈታተኑበትን አንድ ስብሰባ በማሳየት ለአብነት ላንሳ።አቶ ኢሣያስ በ1980ዎቹ መጨረሻ ገደማ በናይሮቢ ባደረጉት ጉብኝት ላይ ከላይ የተጠቀሱት አይነት ግለሰቦች በተገኙበት ስብሰባ ላይ አቶ ኢሳያስ ከኢትዮጵያውያን ጋር ግጭት የሚፈጥሩ እንዲታረሙ የሚል ሃሳብ ሲሰጡ ለብዙ ዓመት ውጭ የኖሩ ''ከመምህሩ ደቀ መዝሙሩ'' አይነቶቹ ግለሰቦች መልሰው አቶ ኢሳያስን እኛ ለስንት ዓመት ስናዋጣ የኖርን መሆናችንን ይወቁልን አይነት አስተያየት ይሰጣሉ። በእዚህ ጊዜ አቶ ኢሳያስ የመለሱላቸው መልስ ''እናንተ ገንዘብ ሰጠን ትላላችሁ ህይወቱን ለእኛ የሰጠ ኢትዮጵያዊም አለ'' በሕዝብ መሃል ግጭት መፍጠር አይገባም አይነት ቁጣ የተቀላቀለበት ንግግር ማድረጋቸውን ከአስር ዓመት በፊት ዑጋንዳ እያለሁ ስብሰባውን የታደመ ሰው የነገረኝን አስታውሳለሁ። 

እነኝሁ ወገኖች የፈጠሩት ችግር በውጭ ሀገር ብቻ ሳይሆን ሀገር ቤት ሲሄዱም ከሰባ ዓመታት በላይ አብረው የኖሩ፣አንድም ቀን ከኢትዮጵያዊነት ውጭ ሌላ ሀገር ብለው አስበው የማያውቁትን ሁሉ ሪፍረንደም ላይ ካልተሳተፉ እንደሚገለሉ በመስበክ የፈጠሩት ውዥንብር አብሮ የነበረውን መልካም ሕዝብ ሰላሙን ያናጋ ነበር።ይህ ማለት በውጭ የኖሩት በእድሜ የገፉት የኤርትራ ተወላጆች ብቸኛ ተወቃሽ ናቸው ለማለት ሳይሆን፣ አንዳንዶች ያደረጉት አሉታዊ አስተዋፅኦ ለሌላው ዲያስፖራ ትምህርት ስለሆነም ነው።በነገራችን ላይ በኤርትራም ሆነ በኢትዮጵያ የሚኖሩ የኤርትራ ተወላጆች እንደ ዲያስፖራው በእድሜ የገፉ ኤርትራውያን የሚያስቡ አይደሉም።ይህንን መልካም አካባቢያዊ ሁኔታ የበከለው በውጭ በሴራ ፖለቲካ እና በጥላቻ የተካነው በእድሜ የገፋው የኤርትራ ተወላጅም ጭምር እንደነበር ለማስታወስ ነው።ይህ ጉዳይ ዛሬ ላይ ጥቅም የለውም ብሎ የሚያስብ ሊኖር ይችላል።አዎ! አሁን ያለፈውን ጉዳይ የምናወራበት አይደለም።ሆኖም ግን ለወደፊቱም ወጣቱ ትውልድ መጠንቀቅ ያለበት የእዚህ አይነት የተሳሳተ እሳቤ ካላቸውም ጭምር  መሆኑን ማሳሰቡ ጠቃሚ ነው።በሌላ በኩል ለወደፊት በጉዳዩ ዙርያ የሚያጠኑ በውጭ የሚኖሩ በእድሜ የገፉ ኤርትራውያን ነገሮችን ከማብረድ ይልቅ የማካረር ሚና በእራሱ አንዱ ሊጠና የሚገባ መሆኑንም ለመጠቆም ነው።


ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወደፊት ሊያተኩሩበት የሚገባው ዋናው ጉዳይ የቱ ነው?


የኢትዮጵያ እና የኤርትራ መለያየት ፈፅሞ እንደማይሆን በተምኔታዊ ግምት ብቻ ሳይሆን ለ27 ዓመታት በተደረገ ሙከራ ተረጋግጧል።በማኅበራዊ እና የተፈጥሮ ሳይንስ መካከል ያለው ልዩነት ፣ የተፈጥሮ ሳይንስን በላብራቶሪ ውስጥ አስገብቶ እና ሞክሮ ውጤቱን ማወቅ ሲቻል የማኅበራዊ ሳይንስ ግን ያለፈውን ተሞክሮ በማየት እና አሁን እየሆነ ያለውን መረጃ በመሰብሰብ የሚደረስበት ድምዳሜ ነው።የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ጉዳይም የማኅበራዊ ሳይንስ ጉዳይ እንደመሆኑ ላለፉት ሃያ ሰባት አመታት ተለያይተው  መኖር እንደማይችሉ በሙከራም ጭምር አረጋግጠዋል። 

አሁን የተጀመረው መልካም ጅምር በሚገባ ለማስኬድ ከዝርዝር ግንኙነቶቹ በተጨማሪ የዜግነት ጉዳይ አንዱ መስተካከል ያለበት ነው።በኢትዮጵያም ሆነ በኤርትራ ያሉ ካለ አንዳች ገደብ የመስራት እና የመኖር ፍላጎት አላቸው።ይህንን ጉዳይ ግን ምንም አይነት ነፃ ቪዛ ቢደረግ እና ካለ ፓስፖርት መሄድ ይቻላል ቢባል መልሶ የሚይዝ ጉዳይ ለሁለቱም ሃገር ፖለቲከኞች እንደ ''ሽንፍላ'' የማይጠራው ጉዳይ የዜግነት ጉዳይ ነው።አቶ አሳያስም ሆኑ ዶ/ር አብይ ይህንን ጉዳይ አንድ አይነት ማሰርያ ማበጀት መቻል አለባቸው። አንድ ኤርትራዊ ለኢትዮጵያ የፀጥታ ስጋት እንደማይሆን፣አንድ ኢትዮጵያዊም ለኤርትራ የፀጥታ ስጋት እንደማይሆን ያለፈው ስምምነት አመላካች ነው።ከእራሱ ዜጋ ስጋት ያለበት ሀገር የለም።ምን ለማለት ነው? በምንም አይነት ሁለቱም ሀገሮች በአንድ አይነት መልክ ወደ ኮንፈድሬሽን የሚመጡበት እና ኢኮኖሚያዊ ውህደቱን በፖለቲካዊ ውህደት፣ወይንም ተወራራሽ ቅርፅ ካልሰጡት በተገደበ መልክ የሚኖር ግንኙነት ሁል ጊዜ የሁለቱንም ሀገር ዜጎች እንዳሳቀቀ የሚኖር ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ፖለቲከኞቻቸው የመከራከርያ አጀንዳ አድርገው ጊዜያቸውን እንዲያጠፉ የሚያደርግ '' ጉንጭ አልፋ'' ትንተና ውስጥ እንዲገቡ አያስፈልግም።

ባጠቃላይ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ በኢትዮጵያ እና ኤርትራ መሐከል የተቀደደው የመለያየት መጋረጃ ታሪካዊ ነው።የህዝቡንም የፍቅር ጥማት በሁለቱም መካከል የታየ ብዙዎችን ያስለቀሰ ክስተት ነው።አቶ ኢሳያስም ዘግይተውም ቢሆን ምንም አይነት ልዩነት ለማውጣት የሚቸግር መሆኑን ቆይተውም ቢሆን የተረዱት ይመስላል።አሁን ካለፈው የመማርያ እና የወደፊቱን በጥልቅ መሰረት ላይ ለመጣል እንዲሁም ትውልድ ተሻጋሪ ሥራ ለመስራት ዕድል ያላቸው መሪዎች በጥልቅ ሊመለከቱት ይገባል። ሁለቱም ሀገሮች ወደ ፖለቲካዊ ሕብረት በመምጣት የዜግነት ጉዳይ ላይ በኢትዮጵያዊ ቅኝት አንድ አይነት መልክ ማስያዝ አለባቸው።እንዴት? ለሚለው ጥያቄ አሁን ዝርዝር መልስ ለማስቀመጥ ጊዜ ይፈልጋል። ፖለቲካዊ ህብረት ማለት ግን በዋናነት የዜግነት ልዩነትን ማጥፋት እና ወደ ኢትዮጵያዊ ጎራ ገብቶ ባለቤት የመሆን ጉዳይንም ይጨምራል። አንዳንዶች ምጣኔ ሀብታዊው ግንኙነት እና ሕብረት በራሱ ወደ ፖለቲካዊው ያመራል ይላሉ።ይህ ግን በዘገምተኛ መልክ የሚሄደው የተለያየ ባህል ላላቸው ህዝቦች ነው እንጂ እንደ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ያለ ጥልቅ የባህል መመሳሰል ብቻ ሳይሆን ፍፁም አንድነት ላላው ሕዝብ አይደለም።በሁለቱ መካከል ያለው የምጣኔ ሀብት ግንኙነት በሚቀጥሉት ስድስት ወራት ውስጥ ወደነበረበት ይሄዳል።በመቀጠል የፖለቲካ እና ዜግነት ጉዳይ ወድያው አፍጥጦ ይመጣል።ያን ጊዜ ይህንን በጎ ተግባር ያንገጫግጨዋል።ስለሆነም በተለይ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ  በእዚህ በኩል ያለውን እውነታ ወደ ጎን ሊሉት አይችሉም።ይህ ማለት ኤርትራን ከሚነጥል የፖለቲካ ግንኙነት ከኢትዮጵያ ጋር ወደ የሚደምር የፖለቲካ ግንኙነት መምጣት ወሳኝ ነው።ይህ ማለት በዲሞክራሲያዊ ሂደት ኢትዮጵያውያን ስለ ኤርትራው ፖለቲካ እኩል በጋር መልክ እንዲሳተፉ፣ኤርትራውያንም እንዲሁ በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ የዲሞክራሲያዊ ሂደት እንዲሳተፉ ማድረግ እና ድህነታችንም ሆነ ሀብታምነታችን ተወራራሽ አብሮ የሚወድቅ እና የሚነሳ በእኩል ዜግነት ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ማድረግ ተገቢ ነው። እዚህ ላይ የአሰብ ወደብ እና ሌሎች ጉዳዮች በጣም ጥቃቅን ጉዳዮች አድርጌ ነው የማያቸው።ጥቃቅን የምለው ከጉዳዩ አስፈላጊነት አንፃር ሳይሆን እነኝህ ጉዳዮች ላለፉት 27 ዓመታት ተሞክሮም ኢትዮጵያ እና ኤርትራ  ካልሰሩበት ወደቡ በራሱ  የበለጠ አደጋ ይዞ እንደሚመጣ አደጋው ደግሞ ለሁሉም የሚተርፍ መሆኑ ተመስክሯል። ስለሆነም ከምጣኔ ሃብቱ ጉዳይ ጋር እኩል የዜግነት ጉዳይ እንዴት አንዱ ከሌላው የተለየ እንዳልሆነ ሆኖ በሚያሳይ እና ትውልድ አሻጋሪ በሆነ መልክ በሕግ መቀመጥ ይችላል? የሚለው ወሳኝ ጉዳይ ነው።ይህ ጉዳይ አሁን በስልጣን ላይ ያሉት ወገኖች በቶሎ ካልፈቱት ሕዝብ በጉልበቱ ወደ እዚሁ መንገድ እንደሚያመጣው ማመን ይገባል። ጥያቄው የታሪኩ አካል የመሆን እና ያለመሆን ዕድል እና ክፉ ዕጣ ነው። 


አስመራ ላይ ለዘንድሮ አዲስ ዓመት በድምቀት የሚሰማው ሙዚቃ 




ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Saturday, July 7, 2018

በክቡር ጠ/ሚንስትር ዶ/ር ዓብይ እና ኢትዮጵያዊነት አንፃር የቆመው እሳቤ።

ጉዳያችን/Gudayachn
ሐምሌ 1/2010 ዓም (ጁላይ 8/2018 ዓም)

በእዚህ ፅሁፍ ውስጥ 
- በኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ ያሉት ሁለቱ ሃሳቦች እና ኃይሎች፣
የኢትዮያ መጪ የፖለቲካ መንገድ ዋስትናው እና መፍትሄው በሚል ርዕስ ፅሁፎች እና 
የአዲስ ሙላት አዲስ ነጠላ ዜማ(ቪድዮ) ያገኛሉ።

ኢትዮጵያ የክፍለ ዘመኑ አንዱ እና አይነተኛ የለውጥ ሂደት ላይ ነች።ለውጡ አንድ እየሞተ ያለ ሐሳብ እየሸኘ አዲስ ሀሳብ እያስተዋወቀ የሚሄድ የለውጥ ሂደት ነው።እየሞተ ያለው ሐሳብ ላለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመን  ኢትዮጵያን ሲያምስ የኖረው '' ከእኔ ሃሳብ ጋር የማይስማማ ሁሉ ጠላቴ ነው እና ደምስሰው'' የሚለውን ሃሳብ ሲሆን እያስተዋወቀ ያለው ሃሳብ ደግሞ ''የእኔን ሃሳብ የማይቀበል ሁሉ ጠላት አይደለም።ችግሩን በውይይት መፍታት ይቻላል'' የሚለው ሃሳብ ነው። አዲሱ ሃሳብ በእራሱ በቂ ቦታ ለማግኘት በቀደመው ሃሳብ ላይ የተመሰረቱ ፅንሰ ሃሳቦች አራማጆች አሁንም መኖራቸው እና ወራሾችም ከአዲሱ ትውልድ ውስጥ መኖራቸው የለውጥ ሂደቱ በጥንቃቄ እንዲራመድ እና ጥንቁቅ አራማጅም የሚፈልግበት ወሳኝ ጊዜ ነው። አንዲት ሀገር በእዚህ አይነት የለውጥ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ስትሆን የተለያዩ ሃሳቦች ሰፊውን ምህዳር ለመያዝ የተለያዩ ስልቶች ከመቀየስ እስከ አላስፈላጊ መንገድ ውስጥ የመግባት አደጋዎች እንዳይኖሩ የሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል ኃላፊነቱን የመወጣቱ ፋይዳ እጅግ ወሳኝ ነው።

በኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ ያሉት ሁለቱ ሃሳቦች እና ኃይሎች

በኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ ያሉት ሃሳቦችን በሁለት ኃይሎች ከፍሎ በማየት መጠቅለል ይቻላል። የመጀመርያው ሕብረ ብሄራዊት ኢትዮጵያን የሚያቀነቅነው እና በኢትዮጵያዊነት የወል ስም ሃሳብ ስር ያለው እና  ብሔርተኝነትን ዋስትናዬ የሚለው ሃሳብ እና ኃይል ነው። 

ሕብረ ብሔራዊነት እና ኢትዮጵያዊነት

የመጀመርያው ሕብረ ብሔራዊነት እና ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅነው ኃይል ካለምንም ማጋነን በስፋቱ፣በርካታውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ከማቀፉ እና እሳቤው በራሱ ያለው የኃላ እና የወደፊት መሰረት ጥልቀት አለው። ይህ ማለት ወደ ኃላ ስንመለከት ኢትዮጵያ በኖረችበት የመንግስትነት ስሪት ታሪክ ውስጥ የፖለቲካው መሪ ተዋናይ እሳቤ ኢትዮጵያዊ እሳቤ መሆኑ ነው።የወደፊቱንም ስንመለከት እንደሀገር በጋራ ለመኖር ሌላ አማራጭ እሳቤ ለጊዜው ከኢትዮጵያዊ እሳቤ የተሻለ እንዳልተሰማ ብዙ ማስረጃ ማምጣት አይሻም።የህብረ ብሔራዊ እና ኢትዮጵያዊ እሳቤ ያለፈ እና የመጪው እሳቤ አካል ብቻ አይደለም የዘመናዊነት እሳቤ አካልም ነው።በዘመናዊው ዓለም በፈጣን ቴክኖሎጂ ምርት አሳድጎ ሰፊ ገበያ የመፍጠር እሳቤ የሚጋራው አሁንም ሰፊ የሕዝብ አንድነት እና ስምምነት ፈጥሮ የገበያ አድማስን ማስፋት ከሚለው ዘመናዊ አስተሳሰብ ጋር የሚጣጣም ነው።

ይህ የህብረ ብሔራዊነት እና ኢትዮጵያዊነት እሳቤ ላለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት ያህል እንዲጎሳቆል ያልተደረገበት ሙከራ አልነበረም።

እሳቤውን በራሱ ያለፈ እና ያረጀ ስርዓት እሳቤ ነው ብሎ ከማጥላላት እስከ የሃሳቡ ተጋሪዎችን ማሰር እና መግደል ድረስ ያልተፈፀመ የግፍ አይነት በህወሓት/ኢህአዴግ ስርዓት  አቀንቃኞች ሁሉ ሲፈፀምበት ኖሯል።ይህም ሆኖ ግን ሃሳቡ ገዢ ሃሳብ ሆኖ መኖሩን የሚገታው ኃይል አልተገኘም።ለእዚህ ምክንያቱ ደግሞ መሬት ላይ ያለው ዕውነታ ነው። ምክንያቱም በፖለቲካው ብቻ ሳይሆን በምጣኔ ሃብቱ መስክ ሁሉ ለሚገጥሙ ችግሮች መፍትሄው ምንድነው? ለሚለው ፈታኝ ጥያቄ መልሱ ሁሉ የሚያመራው ወደ አንድ ነጥብ ብቻ መሆኑ ነው። ይሄውም ሕብረ ብሄራዊት ኢትዮጵያ የሚለው መልስ ነው። ይህ በእንዲህ እያለ ነው እንግዲህ በኢህአዴግ የውስጥ ቅራኔ አይሎ የዶ/ር አብይ ቡድን ነጥሮ እንዲወጣ ዕድል የሰጠው።ይህ ቡድን ደግሞ በኢህአዴግ ውስጥ ሆኖ የኢትዮጵያን ችግር በሚገባ ለማየት የቻለ አካል ነበር እና የሕብረ ብሔራዊ ኢትዮጵያዊነት እሳቤን በአማራጭ የፖለቲካ መሪ ሃሳብ ይዞ መውጣቱ ሳይንሳዊ እና ተሞክራዊ እንጂ ድንገት ደራሽ ሃሳብ አይደለም። ዶ/ር አብይ የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን መንበር በተረከቡበት ቀን መጋቢት 24/2010 ዓም ለፓርላማ ባደረጉት ንግግር በሕዝብ ውስጥ የነበረውን የህብረ ብሔራዊ ኢትዮጵያዊነት እሳቤ መግነጢሳዊ በሆነ መልክ በሕዝብ ውስጥ የነበረውን ስሜት አንፀባረቁት።በደቂቃዎች ውስጥም ሚልዮኖች ከጎናቸው አሰለፉ።ይህ ማለት ለሕዝብ የነገሩት አዲስ እሳቤ ስለሆነ አይደለም።ይህ ቢሆን ኖሮ ሀሳባቸው ሕዝብ ዘንድ ደርሶ ድጋፍ ለማግኘት አመታትን በጠበቀ ነበር።ሆኖም ግን ሕዝብ ውስጥ ሲንተከተክ የነበረው የህብረብሔራዊ ኢትዮጵያዊነት ስሜት የመተንፈሻ ቀዳዳ ሲያገኝ ፈንቅሎ ወጣ እንጂ ስሜቱ ቢቆይ ኖሮ በአብዮት ወይንም በሌላ መልኩ ገንፍሎ መውጣቱ የማይቀር እንደነበር መረዳት ይገባል።

 ብሔርተኝነትን ዋስትናዬ የሚለው ሃሳብ እና ኃይል 
ሁለተኛው እሳቤ እና ኃይል ብሔርተኝነት ዋስትናዬ የሚለው እሳቤ ነው።የእዚህ እሳቤ ዋነኛ መነሻ እና ምክንያት ስጋት እና ስጋት ነው።ስጋቱ የሚነሳው ላለፈው ሩብ ክፍለ ዘመን በህወሓት እና አጋሩ ኢህአዴግ እንዲሁም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ተቃዋሚ ግን ብሄርተኝነትን የሙጭኝ ያሉ ኃይሎች ተከታታይ የፕሮፓጋንዳ ሥራ በአንድ ትውልድ ላይ የፈጠረው ያለመተማመን እና  የስጋት ውጤት ነው። የእዚህ እሳቤ አቀንቃኞች ሁል ጊዜ የሚሰጉት ኢትዮጵያዊነት እና ሕብረ ብሔራዊነት የእነሱን የብሔር እይታ የሚጋርድ ብቻ ሳይሆን ሊያጠፋን ይችላል በሚል ስጋት የተሞላ ነው።ይህንን ስጋት ደግሞ ከሃምሳ እና መቶ ዓመታት በፊት የነበሩ የታሪክ ትርክቶችን የተለያየ ቀለም በመቀባት በአይነት በአይነት እየመተረ የልዩነቱን ጎራ ብቻ እያጎላ ስለኖረ ከስጋት ሊወጣ ፈፅሞ አልቻለም። ሆኖም ግን አስከፊው ጉዳይ ከስጋት ለመውጣት አለመቻሉ ብቻ ሳይሆን ወደፊትም ስጋቱ የሚርቀው የራሱ የብሔር ኃይል የስልጣን እርከኑን ሲቆጣጠር ብቻ መሆኑን ያስባል።እዚህ ላይ ግን የስልጣን እርከን ተቆጣጠረ የሚባለው የቱን የፖለቲካ ኃይል ሲይዝ መሆኑን እራሱም ጥርት አድርጎ ማስቀመጥ አይችልም።ምክንያቱም የእዚህ አይነቱ የስልጣን አላማ እሳቤ በራሱ መለክያ የለውም።ሁሉንም የስልጣን እርከን ቢቆጣጠርም ተቆጣጠርኩ ብሎ እንደማይረካ ግልጥ ነው።ይህ የስጋት ፖለቲካ ዋና ጠባይ ይህ ነው።ስልጣን ላይ ሆኖም እንዳልሆነ ቆጥሮ ሌላ ግንባር ይከፍታል።በብሄርተኝነት እሳቤ ውስጥ ያሉት የህወሓት፣የኦሮሞ እና የአማራ ብሔርተኝነቶች ተጠቃሽ ናቸው።እዚህ ላይ ግን የህወሓት የብሄርተኝነት ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የገንዘብ እና የስልጣን ጥማት ያላቸው እና በልዩ ልዩ ወንጀል ውስጥ የገቡ ብሔርተኝነትን እና የትግራይን ሕዝብ እንደ ሰብዓዊ ጋሻ ለመጠቀም የሚያስበው አካል ፍፁም ብሔርተኘነት ስሜት ያለው ነው ለማለት የሚያስቸግርበት ደረጃ ደርሷል።ይህ ደግሞ ከብሄርተኝነት አልፎ ወደለየለት የፋሽሽት ኃይል ለመቀየር በማኮብኮብ ላይ ያለ ምናልባትም የተቀየረበት ደረጃ እንደሆነ በጥልቀት አጥንቶ በማስረጃ ማቅረብ ይቻላል።ከእዚህ በተለየ ግን የኦሮሞ፣አማራ እና ትግራይ ብሄርተኛ እሳቤዎች ብቸኛ ችግር መጪውን ዋስትና የማግኘት ጥማት ነው።በእዚህ ውስጥ ግን ሁሉም ውስጥ የስልጣን እና የግል ''ኤጎ'' ስሜቶች የሉም ማለት አይቻልም።ይህንን በሚገባ ለመመርመር ግን  እንደ እየቡድኖቹ አመራሮች ጠባይ በዝርዝር መመልከትን ይፈልጋል።

የኢትዮያ መጪ የፖለቲካ መንገድ ዋስትናው እና መፍትሄው

ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው በአሁኗ ኢትዮጵያ ያሉት የፖለቲካ እሳቤዎች በሁለቱ ማለትም በሕብረ ብሔራዊ እና የብሔርተኝነት እሳቤዎች ስር መሆኑን መረዳት ይቻላል።አሁን ጥያቄው የኢትዮጵያ መጪ የፖለቲካ መንገድ ዋስትናው እና መፍትሄው ምንድነው? የሚል ነው።

ከመጋቢት 24/2010 ዓም ዶ/ር ዓብይ ወደ ስልጣን የመጡበት መንገድ እና ከሁሉም በላይ ያነሱት የህብረ ብሔራዊ ኢትዮጵያዊነት እሳቤ የኢትዮጵያ እጅግ ውድ የሆነ መልካም ዕድል ነው።ይህ ማለት መጪው የለውጥ ሂደት ሕዝብ ከህዝብ ሳይጣላ፣ኢትዮጵያ የጀመረችው የልማት ሂደት ሳይቆም እና የመንግስት ስሪቷ ሳይበጠስ ስለለውጥ እና አዲስ የፖለቲካ ሂደት ለመወያየት እና ወደ ውጤት ለመድረስ ፋታ አገኘን ማለት ነው።ይህንን ዕድል የህብረ ብሔራዊውም ሆነ የብሄርተኛ አቀንቃኙ በሚገባ ሊጠቀሙበት ይገባል።ስለሆነም ለመጪው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳር ዋስትናው እና መፍትሄዎቹ የሚከተሉት ናቸው። እነርሱም

  • የህብረ ብሔራውውም ሆነ የብሔረሰብ አቀንቃኞች ዋስትናቸው የሕግ የበላይነት እና ከሴራ ፖለቲካ የራቀ የዲሞክራሲያዊ ሂደት ውጤት መሆኑን ማመን፣
  • ለሕግ የበላይነት እና የዲሞክራሲያዊ ሂደት ውጤት ስኬት ሃሳብን በጨዋነት የመግለጥ እና ሃሳብን ለሕዝብ ግምገማ በመግለጥ ማመን፣ለእዚህም እንዲረዳ የሚድያው ሚዛናዊ ሂደት ሁሉም እኩል መግባባት እና መጠበቅ መቻል፣
  • የኢትዮጵያ ብሔራዊ የጦር ሰራዊት፣የደህንነት መዋቅር እና የፍትህ ሂደት ውስጥ ምንም አይነት ቀጥተኛ እና ተዘዋዋሪ ተፅኖ አለመፍጠር። ምክንያቱም ሶስቱም አካላት ለሁሉም እኩል የሚያገለግሉ መሆናቸውን ማረጋገጥ በእራሱ አንዱ የዋስትና ምንጭ ስለሆነ፣
  • ካልሰለጠነ እና ኃላ ቀር አስተሳሰብ እና ተራ ንትርክ እንዲሁም ብሽሽቅ ወጥቶ በሰለጠነ ሃሳብን የማንሸራሸር፣የመግለጥ እና የላቀ የሃሳብ ማመንጨት ልዕልና መሸጋገር፣ 
  • በህብረ ብሔራዊ ኢትዮጵያዊነትም ሆነ በብሄርተኝነት ስም የተደራጁ ሁሉ በእየቦታው በሃሳብ የሚመሳሰሉ ግን በቁጥር የተለያዩ ድርጅቶች ከማብዛት ሁሉም በሃሳብ ወደሚመስላቸው ስብስብ በመጠቃለል ሁለት ግዙፍ የፖለቲካ ድርጅቶች ወይንም መድረኮች ፈጥረው ለምርጫ የመቅረብ ዝግጅት ማድረግ እና  
  • ለኢትዮጵያ እኩል የመጠንቀቅ፣የመቆርቆር እና ህልውና መቆምን በተግባር ሁሉም ወገን ማሳየት እንዲህም ለጋራ የሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ሁሉም ልዩነት ሳይኖራቸው የሚቆሙበት የጋራ ሃገራዊ ህገ መንግስት ላይ ማሻሻል አድርጎ ፍፁም ታዛዥነትን ከግደታ ማስገባት የሚሉ ናቸው።
ባጠቃላይ አሁን ኢትዮጵያ ያለችበት የፖለቲካ ሁኔታ እጅግ ተስፋ ሰጪ፣የትውልድ ሽግግር የሚታይበት እና ኢትዮያ ተስፈንጥራ ለመነሳት ኃይል የመስጠት አቅም ያለው ነው።በእዚህ ሁሉ ሂደት ላይ ግን በብልጣብልጥነት አንዱ ጠቅልሎ ለመያዝ የሚደረጉ ሙከራዎች እጅግ አደገኛ ብቻ ሳይሆን መልሶ ወደ አልተፈለገ  ግጭት ውስጥ የሚቀት ነው።ለእዚህ ደግሞ አደጋው ያለው በአጉል ጀብደኘንት የሴራ ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ ሂደቱን ለማሰናከል ከሚመኘው ከህወሓት በኩል ያለው የመጀመርያው አደጋ ሲሆን በመቀጠል ከአንዳንድ የብሄርተኛ አካላት ዘንድ ተመሳሳይ ምልክቶች አሉ።የእዚህ አይነቱ ሙከራ ለመጭዋ ኢትዮጵያ የማይመጥን ጊዜው ያለፈበት አንዲት ስንዝር የማያስኬድ የተሳሳተ አስተሳሰብ ነው።በእዚህ አይነት የተሳሳተ መንገድ ለሚያልሙ ደግሞ ሁለት አይነት መንገዶች መጠቀም ይቻላል።የመጀመርያው በተቻለ መጠን የተሳሳተ ሕልም ለሚያልሙ የሴራ ፖለቲከኞች በሙሉ በግልጥ ማስጠንቀቅ ያስፈልጋል።ማስጠንቀቁን አልፎ ሂደቱን ለማደናቀፍ ለሚሞክር ደግሞ የሚመጥን ምላሽ አስፈላጊ ነው።ከእዚህ ውጭ ግን በህብረ ብሔራዊውም ሆነ በበሄርተኛ እሳቤ ባለቤቶች በካከል የሚደረጉ የሃሳብ ልውውጦች አንዳንዴም  ከሰንደቅ አላማ ጀምሮ እስከ ዜግነት ድረስ የሚነሱ የሃሳብ ክርክሮች አንዳንዴም መወራረፎች ጨዋነትን ባለፈ መልኩ እስካልተቀየሩ ድረስ አደጋዎች አይደሉም።በእርግጥ ለእኛ ሀገር ፖለቲካ የእዚህ አይነት የሃሳብ ክርክሮች ካለማዳበራችን አንፃር የዓለም የመደናገጥ፣ተስፋ የመቁረጥ ስሜቶች አንዳንዶች ቢያሳዩ አይገርምም።እአየቆየ ግን ልምዱን እያዳበርን በሃሳብ ልዩነቶች መካከል መኖር አደጋ ሳይሆን እውነታውን ማየት ግን በሃሳብ የማሸነፍ አስፈላጊነትን ብቻ እንደሚያሳይ ስንረዳ ሁሉም ቀላል ይሆናል።አዎን ሁሉም ቀላል ይሆናል።መልካም መንገድ ላይ ነን።የበለጠ ደግሞ የላቀው የፍቅር፣በልዩነት አንድነት እና የመተሳሰብ ፖለቲካችን ያድጋል።ዋናው ቁምነገር እያንዳንዱ የዳር ተመልካች ከመሆን የእኔ ሚና በፖለቲካው ብቻ ሳይሆን በምጣኔ ሃብቱ እና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ሁሉ ምን ለስራ ብለን ወደ ተግባር መግባት አስፈላጊ እና ጊዜ የማይሰጠው ነው።

የአዲስ ሙላት አዲስ ነጠላ ዜማ(ቪድዮ) 
======================
አብይ አብይ ሲሉ ያው ፆሙን ነው ብዬ፣
ሰውም አብይ አለው አረ እናንተ ሆዬ።
 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Friday, July 6, 2018

ክቡር ጠ/ ሚ/ር ዶ/ር ዓብይ አህመድ ለዲያስፖራ ኢትዮጵያውያን ሀገራቸውን እና ሕዝባቸውን የሚረዱበት አዲስ የመነሻ ሃሳብ ዛሬ አቀረቡ።ሀሳባቸውን በስምንት ደቂቃ ቪድዮ ይመልከቱ።

ጉዳያችን/Gudayachn
ሰኔ 29/2010 ዓም (ጁላይ 6/2018 ዓም)

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ለዲያስፖራ ይህንን መነሻ ሃሳብ (ፕሮፖዛል) ያቀረቡት በተወካዮች ምክር ቤት የ2011 ዓም በጀት ማብራርያ ከሰጡ በኃላ በልዩ መነሻ ሀሳብነት በመጪው ዓመት ብንሰራው ብለው ያቀረቡት ዓብይ የመነሻ ሃሳብ ነው።ሃሳቡን ባቀረቡ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ የዲያስፖራው ማኅበረሰብ በማኅበራዊ ሚድያ አዎንታዊ ምላሻቸውን መስጠት ጀምረዋል።



ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Tuesday, July 3, 2018

የሆለታ ገነት የጦር አካዳሚን ስም ማን ሰወረው?

ጉዳያችን/Gudayachn
ሰኔ 26/2010 ዓም (ጁላይ 4/2018 እኤአ)

ሆለታ እና የጦር አካዳሚዋ

ከአዲስ አበባ ስላሳ አምስት ኪሎሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው የሆለታ ገነት ከተማ ከአዲስ አበባ ባልተናነሰ ታሪካዊ መነሻ አላት።በ1903 ዓም የመጀመርያው በውሃ ኃይል የሚሰራ ወፍጮ የተተከለባት ታሪካዊ ከተማ መሆኗን የታሪክ ምሁሩ ሪቻርድ ፓንክረስ ፅፈውላታል።የከተማው ስም ሆለታ (ኦለታ) ሲባል ገነት የሚለውን ስም የሰጧት ግን አፄ ምንሊክ እንደነበሩና  ከቦታው ማራኪነት የተነሳ እንደነበር ታሪኩን የሚያውቁ ይናገራሉ።አፄ ምንሊክ ቤተ መንግስታቸውን አዲስ ዓለም እና ሆለታ ላይ እንደሰሩ ይታወቃል።ቤተ መንግስታቸው ጋር ተያይዞም አሁን ማሰልጠኛው ባለበት ግቢ የኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን ትገኛለች።
ሆለታ ገነት ጦር የምትገኘው የኪዳነ ምህረት ታቦት በጦር ሰራዊቱ ታጅባ ወደ ጥምቀተ ባህር ስትሸኝ።

የሆለታ ገነት ጦር አካዳሚ በ1928 ዓም በቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ ስም በአምስት የስዊድን መኮንኖች አሰልጣኞች እገዛ ስራውን ጀመረ።ሆኖም ግን ወድያው የፋሽሽት ጣልያን ሀገራችንን መውረር የጦር ማሰልጠኛው በአግባቡ ስራውን ማከናወን አቃተው።በወቅቱ ስልጠና ይከታተሉ የነበሩ ሰልጣኞች የመጀመርያ ዘመናዊ ጦር ሰልጣኝ ስለነበሩ ብርቅ ተዋጊዎች ነበሩ።ከማሰልጠኛው ውስጥ የነበሩ ሰልጣኞችም ሆኑ ስልጠናውን ያጠናቀቁ የጥቁር አንበሳ ጦር በሚል አዲስ የአርበኞች እንቅስቃሴ በተለይ በምዕራብ ኢትዮጵያ ጀመሩ።
የጥቁር አንበሳ ጦር በፋሽሽት ጣልያን ወረራ ወቅት  በአርበኝነት የተሳተፉ የሆለታ ገነት ጦር ምሩቃን እና በውጭ የተማሩ ጥቂት ኢትዮጵያውያን የመሰረቱት ፀረ ፋሽሽት እንቅስቃሴ በጣልያን ላይ ዘመናዊ የጦር ውጊያ በማሳየት ብቻ ሳይሆን በጥንታዊ መንገድ ለሚዋጋው የኢትዮጵያ ገበሬ አርበኛ ዘመናዊ ውግያ ስልትን በማስተማር የጥቁር አንበሳ ጦር ያደረገው አስተዋፅኦ ቀላል አልነበረም።የጦር አካዳሚው ተመልሶ የተመሰረተው ጣልያን ከሀገራችን ተባርራ ንጉሰ ነገስቱ ተመልሰው ከመጡ በኃላ በ1935 ዓም ነበር።የጥቁር አንበሳ የጦር አካዳሚ ሆለታ ገነት ጦር አካዳሚ የሚል ስያሜ ያገኘው ደርግ ወደ ስልጣን ከመጣ በኃላ ነበር።

የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት ስም ማን ሰወረው?

የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት በአፍሪካ አንጋፋው በዓለማችንም ከሁለተኛ  ዓለም ጦርነት በፊት ከተመሰረቱ ጥቂት የጦር ትምህርት ቤቶች ውስጥ አንዱ ነው። ይህ ለሀገራችን የጦር ሰራዊት ታሪክ አንዱ እና አይነተኛ ቅርስም ነው።ይህ የጦር ትምህርት ቤት በዘመነ ህወሓት/ኢህአዴግ በ1990 ዓም ከሕግ ውጭ በሆነ መንገድ ለግማሽ ክፍለ ዘመን የሆለታ ገነት ጦር አካዳሚን ስም  አቶ መለስ ደምስሰው ሐየሎም አርአያ የጦር ማሰልጠኛ አሉት።ጉዳዩ በወቅቱ ከፍተኛ ተቃውሞ በተለይ ከጦር ትምህርት ቤቱ ከተመረቁ የቀድሞ ሰራዊት አባላት ቢነገርም ሰሚ አላገኘም።


ለማጠቃለል ማንንም መንግስት ለሚያደንቀው የጦር ሰው በስሙ ማሰልጠኛ መሰየም መብቱ ነው ብለን የምንናገር እንኖራለን።ሆኖም ግን ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ በአፍሪካም ሆነ በኢትዮጵያ ዝነኛ ማሰልጠኛን ታሪካዊ መሰረት በምንድ መልኩ በአንድ ሰው ስም መሰየም ፈፅሞ ተቀባይነት የለውም።የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት የህዝብ፣የሀገር ከፍ ሲል ደግሞ የአፍሪካም ነው።ቀድሞ የነበረው ስም የግለሰብ ስም አይደለም።አሁንም ስሙ በክብር ሊመለስለት ይገባል።አቶ መለስ ለሐየሎም አዲስ ማሰልጠኛ ከፍተው መሰየም መብት ነበራቸው።ከጣልያን ፋሽሽት ጀምሮ ገድል የሰራ ታላቅ አፍሪካዊ የጦር አካዳሚን ታሪካዊ ዳራ በሚያጠፋ መልኩ ስሙን መቀየራቸው ግን ወንጀል ነው። አሁንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ይህንን የስም ጉዳይ እንዲስተካከል ማድረግ አለባቸው።የሆለታ ከተማ ልጆችስ ለምንድን ነው ይህንኑ የሚጠይቅ የማኅበራዊ ሚድያ ጥያቄ የማትጀምሩት። ሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት ስምሽን ማን ሰወረው?

ጥቁር አንበሳ በድምፃዊ አብዱ ኪያር 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።