Friday, August 28, 2026

የኢትዮጵያ ወዳጅ ንጉስ ልጅ ዛሬ ከእዚህ ዓለም አረፉ። ለኖርዌይ ትልቅ የሃዘን ቀን ሆኗል።Norway's King Harald V has died at the age of 89

በዚህ አጭር ዘገባ ውስጥ የሚከተሉትን ያገኛሉ።
  • ስለ ንጉስ ሃራልድ በጥቂቱ
  • የንጉስ ሃራልድ አባት ንጉስ ኦላቭ እና ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ የት ተዋወቁ?
ንጉስ ሃራልድ አምስተኛ የኖርዌይ ንጉስ



=====================
ጉዳያችን ልዩ ሪፖርት
Gudayachn Special Report
=====================
የኖርዌይ ንጉሥ ሃራልድ አምስተኛ ባለፈው ሳምንት ልዩ የደም ሕመም ሕክምና ከተደረገላቸው በኋላ በ89 ዓመታቸው ዛሬ ማረፋቸው ታውቋል።በኦስሎ የሚገኘው ብሔራዊ ቤተ መንግሥት ዛሬ ዓርብ ነሐሴ 22፣2018 ዓም ( ነሐሴ 28/2026 ዓም እኤአ) በኦስሎ ዩንቨርስቲ ስር በሚገኘው ብሔራዊ ሆስፒታል (ሪስክ ሆስፒታል) የኖርዌይን ንጉስ ሃራልድ 5ኛ ማረፍ ከማለዳው በ06:35 የኦስሎ ሰዓት አቆጣጠር ከተገለጸ በኋላ በቤተ መንግሥቱ ጣሪያ ላይ ያለው የንጉሣዊ ባንዲራ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ ሆኗል። የንጉሱ የቀብር ስነ ስርዓት እስኪከናወን ድረስም በኖርዌይ የሐዘን ቀን የታወጀ ሲሆን፣የንጉሱን ማረፍ የሰሙት ኖርዌጃውያን ከማለዳ ጀምሮ ወደ ቤተ መንግስት በመጉረፍ  አበባና የኖርዌይን ሰንደቅ ዓላማ በማስቀመጥ ላይ ይገኛሉ።

ሃራልድ ከ14ኛው ክፍለ ዘመን ወዲህ በኖርዌይ የተወለዱ የመጀመሪያው ንጉሥ ሲሆኑ። ልጃቸው ሃኮን በ53 ዓመታቸው ንግስናውን መተካታቸውን ከኖርዌይ የመጣው ዘገባ ያመለክታል።

ንጉስ ሄራልድ 5ኛ በስልጣን ዘመናቸው የኖርዌይ ንጉሣዊ አገዛዝ ስለ ንጉሣዊው ቤተሰብ የፋይናንስና የጤና ጉዳዮች የበለጠ እኩልነትና ግልጽነት እንዲያሳይ ያደረጉ ንጉስ ናቸው ሲሉ የኖርዌይ ታሪክ ምሁርና የቲቪ2 ንጉሣዊ ዘጋቢ ኦሌ-ጆርገን ሹልስሩድ-ሃንሰን ይናገራሉ።

==========
ንጉስ ሃራልድ የተወለዱት የካቲት 21 ቀን 1937 ዓም እኤአ በኦስሎ አቅራቢያ በሚገኘው የስካጉም እስቴት ውስጥ ነው። አምባገነኑ አዶልፍ ሂትለር በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መጀመሪያ ላይ የናዚ ጀርመን ኖርዌይን ወረራ ባዘዘበት ጊዜ የሦስት ዓመቱ ልጅ ነበሩ።

የሃራልድ እናት ከልጆቻቸው ጋር ወደ ስዊድን ድንበር አቋርጠው ሸሽታ በፕሬዝዳንት ፍራንክሊን ዲ ሩዝቬልት ግብዣ ወደ አሜሪካ ተጉዘዋል።

ልዑል ሃራልድ በጦርነቱ መጨረሻ ከቤተሰባቸው ጋር ወደ ኖርዌይ ተመልሰው እና ትምህርት እና የግዴታ ወታደራዊ አገልግሎታቸውን አጠናቀዋል። በ1957 እኤአ ሃራልድ የዘውድ ልዑል ሆኑ፣ ከ1960 እስከ 1962 ዓም እኤእ በኦክስፎርድ በሚገኘው ባሊዮል ኮሌጅ ማህበራዊ ሳይንስ፣ ታሪክ እና ኢኮኖሚክስ ተምየተማሩት ንጉስ ሃራልድ 5ኛ ወደ ትዳር ሕይወታቸው የገቡበት አጋጣሚም አስገራሚ ነበር። 

ነገሩ እንዲህ ነው፡ በአንድ ግብዣ ላይ የአንድ ነጋዴ ልጅ ሶንጃ ሃራልድሰንን የተዋወቁት የዛንጊዜው ልዑል ሃራልድ፣ እሷን ለማግባት እስኪፈቀድላቸው ዘጠኝ ዓመታት መጠበቅ ነበረባቸው። በመጨረሻም ሶንጃን ማግባት ካልቻሉ ላጤ ሆኖነው እንደሚቆዩ ለአባታቸው እንደነገሯቸው፣ ንጉሥ ሃራልድ በአንድ ወቅት ለኖርዌይ የህዝብ ብሮድካስተር (ኤንአርኮ) ተናግረው ነበር።ሆኖም አባታቸው በመጨረሻ ፈቃዳቸውን ስለ ሰጡ ጥንዶቹ በኦስሎ ካቴድራል ነሐሴ 29 ቀን 1968 ዓም እኤአ ተጋቡ።

በሐምሌ 2011 እኤአ ንጉስ ሃራልድ ኖርዌይ ከባድ ፈተና በገጠማት ጊዜ ማለትም በጽንፈኛው ብሬቪክ በኦስሎ ውስጥ በመኪና ቦምብ ስምንት ሰዎችን ሲገድልና፣ በኡቶያ ደሴት ወደሚገኝ የወጣቶች ካምፕ በመሔድ  69 ወጣቶች (ባብዛኛው የአርባይድስ ፓርቲ ወጣት ክንፍ አባላት ያሉበት ብዙዎቹ በአስራዎቹ ውስጥ የነበሩቱን) ከገደለ በኋላ በኖርዌይ በደረሰው ሃዘን ንጉስ ሃራልድ ሕዝቡን ያጽናኑበት መንገድ ዛሬም ድረስ በብዙ ኖርዌጅያውያኖች ዘንድ ሲታወስ ይኖራል። ንጉሱ በእዚሁ ለሕዝብ ባደረጉት ንግግር የእንባ ሳግ ለቅሶ እየተናነቃቸው በቴሌቭዥን ባሰሙት ንግግር እንደ አባት፣ አያት፣ ባል እና ንጉሥ ለተጎጂዎቹ እና ለቤተሰቦቻቸው በቀጥታ በተላለፈ የቴሌቭዥን መልዕክታቸው ሁኔታውን ሲገልጹ ፡ "የህመማችሁን ጥልቀት መገመት እችላለሁ። የዚህች ሀገር ንጉሥ እንደመሆኔ መጠን ለእያንዳንዳችሁም እጨነቃለሁ" ብለዋል።

እኤአ በ2016 ዓም ደግሞ ንጉሱ ሃራልድ የሰው ልጅ ዘር አንድ መሆኑን እና በኃይማኖትም ላይ ልዩነት መደረግ እንደሌለበት በገለጹበት ንግግር ላይ እንዲህ ብለው ነበር፡ ''ኖርዌጂያውያን "ከአፍጋኒስታን፣ ፓኪስታን እና ፖላንድ፣ ከስዊድን፣ ከሶማሊያ እና ከሶሪያ የመጡ መሆናቸውን ማወቅ አለብን '' ብለዋል።

ንጉስ ኦላቭ እና ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ


በኢትዮጵያ እና በኖርዌይ መካከል ረዘም ያለ ታሪካዊ ግንኙነት አለ።ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ እና  የኖርዌይ ንጉሳዊ ቤተሰብ በቅርብ የተዋወቁት በሁለተኛው ዓለም ጦርነት መጀመርያ አካባቢ ለንደን ላይ ነበር።በወቅቱ ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ የጣያንን ኢትዮጵያ መውረር በወቅቱ የዓለም ማኅበር ተብሎ ለሚጠራው የዛሬው የተባበሩት መንግሥታት ለማቅረብ ለአቤቱታ እንግሊዝ ነበሩ።

የቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ጉብኝት በኦስሎ ኖርዌይ እኤአ 1954 ዓም


ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ ኖርዌይን የጎበኙት በ1954 ዓም እንደ ኤውሮፓውያን አቆጣጠር ነበር ።በመቀጠል የኖርዌይ ንጉስ ኦላቭ ኢትዮጵያን በ1959 ዓም እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ይፋዊ ጉብኝት አደረጉ።ኖርዌይ ኢትዮጵያ የባህር ኃይሏን ምፅዋ እና አሰብ ላይ ስትመሰርት በስልጠና የረዳች የመጀመርያ ሀገር ነች።

ዛሬ ለኖርዌይ ሕዝብ ታላቅ የሃዘን ቀን ነው።ለአዲስ ዓመት በልዩ የማጽናኛና የማበረታቻ ቃላት ለሕዝቡ መልዕክት የሚያስተላልፉት፣በግንቦት 17 ቀን በቤተመንግስታቸው ሰገነት ላይ ሆነው ከሕጻናት እስከ አዋቂ በሰገነቱ ስር ሲያልፍ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ሆነው ሰላምታ እየሰጡ በልዩ ፈገግታ የሚቀበሉት ንጉስ ሃራልድ አርፈዋል። ለንጉሱ ዕረፍተ ነፍስን ለቤተሰቦቻቸውና ለኖርዌይ ሕዝብ መጽናናትን እንመኛለን።
====================////==============

Friday, August 14, 2026

የኢትዮጵያ ወቅታዊ ፖለቲካ፣ የአፈጀው የአዛውንቶች ክበብ፣ ''ፅንዶ'' እና ቅምጥሎቹ ''ባንዳ'' ዩቱበሮች በአውሮፓና አሜሪካ።



+++++++++++++
ጉዳያችን ወቅታዊ ምጥን
+++++++++++++

መንደርደርያ

ኢትዮጵያ በዘመን አቆጣጠሯ ስንሔድ የሐያ አንደኛውን ክ/ዘመን የመዠመርያ ሩብ ክፍለዘመን ለማጠናቀቅ ሰባት ዓመታት ብቻ ቀርተዋታል። ያለፈው ሐያኛውን ክፍለዘመን በአጭሩ ለማስቀመጥ የነፃነት እና የሉዓላዊነት ክብሯን ለማስጠበቅ ከጣልያን ሁለተኛ ወረራ ጋር በተያያዘ ከፍተኛ መስዋዕትነት የተከፈለበት። የነፃነት ድሉን ተከትሎ የዓለምን ወቅታዊ ሁኔታ ተንተርሶ እራሷን ነጥራ ለማውጣት የታገለችበት ጊዜ ሲሆን በእዚህ ትግል ውስጥ ንጉሱ በሐገር ውስጥ ከጎጃም እስከ ትግራይ በሽፍትነት፣ከባሌ እስከ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ በተቃውሞ፣ከቤተመንግስት እስከ የመንግስት ፍንቀላ ሙከራ ተደርጎባቸዋል። በእዚህ ሁሉ መሃል ግን የቀዳማዊ ኃይለስላሴ መንግስት ለኢትዮጵያ የዘመናዊ ስልጣኔ እና ትምሕርት በር ለመክፈት ዕድሉን ያገኘ መንግስት ነበር። ከንጉሱ ቀጥሎ ኢትዮጵያ በርዕዮተ ዓለም ንትርክ ውስጥ ገብታ ብትቸገርም ለሀገሪቱ ታሪካዊ ጠላቶች ያልተመቸች ሀገር ሆና ኖራለች።

ኢትዮጵያ ለታሪካዊ ጠላቶቿ አመቺ የሆነችው በኢሕአዴግ ሕወሓት ዘመን ነው። ይሄውም በቀዳሚነት የባሕር በሯን ትታ መሪዋ አቶ መለስ የባሕር በር '' የገበያ ጉዳይ ነው '' በሚል ትርክት እየተነገራት፣ሀገሪቱ የአስተዳደር ክልሏን በብሔር ከፋፍላና ''እስከመገንጠል '' የሚለውን ሕግ በአንቀፅ 39 ላይ ሰንቅራ የምትሔድ አሳዛኝ ሀገር ሆና ኖራለች። በእዚህ ዘመን የኢትዮጵያ ተቋማት የግለሰብ ብቻ ሳይሆን የሆነ አካባቢ የግል ቤት እስኪመስል ድረስ ከመቀረጹ በላይ የመከላከያ ሰራዊቷ በዕውቀት ላይ ያልተመሰረተ ዘመኑን ያልዋጀ እና እጅግ አደገኛ ደረጃ ላይ የነበረበት ጊዜ ነበር። በእዚህ ሁሉ ሂደት ውስጥ ነው የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መንግስት ወደ ስልጣን የመጣው።

ወቅታዊው የኢትዮጵያ ፖለቲካ

አሁን ያለንበት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት ከምንግዜውም በላይ ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች መዘውር በእጅጉ ከመራቁም በላይ የማይገመት አካሄዱ እና የግቡ እርቀት እና ምጥቀት ኢትዮጵያን ለማጥፋት የተለያየ ተልዕኮ የያዙ ጠላቶቿን ግራ ያጋባ ሆኗል።
ፖለቲካው በመጀመርያ ደረጃ የጠራ አቋሙን በግልጽ አስቀምጧል ይሄውም በሀገር ውስጥ የኢትዮጵያን ሕብረብሔራዊ አንድነት ማረጋገጥ ሲሆን በውጭ የኢትዮጵያን ጥቅም በማንኛውም መንገድ አሳልፎ በማይሰጥ መልኩ ማስከበር ነው። በሀገር ውስጥ ያለው ፖለቲካ ክኢሕአዴግ የቀድሞው ሕወሃት ሰራሽ የጎሳ ፖለቲካ ጋር እየተማታ አልፎ አልፎ መንገራገጭ ቢገጥመው ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ሐዲዱን በትክክል እንደያዘ ለመረዳት ብዙ ምርምር አይጠይቅም። ለእዚህ ደግሞ ዋና መሰረቱ የአብዛኛው ሕዝብ በተለይ በለየለት ጎሳዊ ፖለቲካ የተንገላታው ወጣት ሕብረብሔራዊ አንድነትን አጥብቆ መፈለጉ እና ይህ ብቻ ኢትዮጵያን ሊያሻግር መቻሉን የማመኑ ዕውነታ ነው። 

እዚህ ላይ መሰመር ያለበት ጉዳይ የአክራሪ ብሔርተኞች የፖለቲካውን መዘውር ለመቆጣጠር ጥረት አያደርጉም ወይንም ለማድረግ አልሞከሩም ማለት አይደለም።ነገር ግን ይህ ሙከራ ባብዛኛው ከሽፏል። የቀረው የያዘው የጎጥ በሽታ እስኪለቀው በትንንሽ ማባበያ ''ሕክምና'' እየተደረገለት ነው።ይህ ሂደት ቀጥሎ ተተኪው ትውልድ በሕብረ ብሔራዊ አስተሳሰብ ተቃኝቶ የኢትዮጵያን ተቋማት በሚገባ በኢትዮጵያዊነት ማረስረስ ሲጀምር የጃጀው ኢትዮጵያን የማመስ ፖለቲካ በራሱ ተሽመድምዶ ይንኮታኮታል። አሁን በምናየው መልኩም ከኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እስከ የኢትዮጵያ ሙዜሞች፣ከትምሕርት ፖሊሲ እስከ ውጪ ፖሊሲ በዘመነ ኢህአዴግ እና የቀድሞው ሕወሃት የተጎሳቆለው ኢትዮጵያዊነት በሚገባ እየተቀነቀነ ነው። ይህ ሂደት ሃገር ይሰራል፣የተሳሳተ ትርክት ያርማል፣ ትውልድ ያጋምዳል።

ባፈጀ አስተሳሰብ የሚዳክረው የአዛውንቶች ክበብ  ''ፅንዶ'' ተልዕኮው ኢትዮጵያን ማፍረስ እንጂ መንግስት መቀየር አይደለም።

ከስሙ ስያሜ ገና ''ፅምዶ'' ይባል ''ፅንዶ'' ገና የሚጨቃጨቀው የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች የዳቦ ስም እንደ 1969 ዓም የኢሕአፓ እና መኢሶን ''እናሸንፋለን '' ይባል '' እናቸንፋለን'' የሚለው ጭቅጭቅ ያልተላቀቀ ነገር ግን ከባዕዳን የሚገኝ ድርጎ በአንድ ጣሳ ውስጥ እንዲገኝ ያደረገው የዘመናችን ግራ የተጋቡ የአዛውንቶች ክበብ ሆኖ ብቅ ብሏል። ስካር እና ምኞት፣ ማለም እና ዕውነታ የተደባለቁበት ስብስብ ነው። ስብስቡ ''የጨነቀ ዕለት'' የሚሉት ነው። መሰረተ ሀሳቡን ከማኅበራዊ ትስስር እና ከቋንቋ ጋር ሊይስተሳስረው የሚሞክርበት ዐውድ በራሱ የዕውር ድንብር አካሄድ ነው። ፅንዶ የድፍረቱ ድፍረት ከአማራ እና ሌሎች ክልሎችንም ስነ ልቦና ሰልቦ በእርሱ ኢትዮጵያን የማፍረስ አጀንዳ ስር ለማሰለፍ ሲታትር ሰዎቹ የት ነው የነበሩት ያስብላል።

ቅምጥሎቹ ባንዳ ዩቱበሮች በአውሮፓና አሜሪካ የኢትዮጵያ የስፖርት ፌስቲቫል ላይ ሽርሽር 

ይህ የአዛውንቶች ያፈጀ የጎጥ ጥምረት ወላጅ አባቱ ኢትዮጵያን ማተራመስ የምፈልጉቱ ታሪካዊ ጠላቶች ቢሆኑም በትግራይ እና በኤርትራ ሕዝብ እንዲሁም በዐማራው እና ኦሮሞው ደም እየነገዱ ኑሯቸውን በውጭ ሀገር ያደረጉት ቅምጥሎች ተግባር ግን በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ቅምጥሎቹ ከሚኖሩበት ሀገር ሶፋ ላይ ሳይወርዱ በዩቱብ የኢትዮጵያን ወጣቶች ተዋጉ እያሉ ሲለፍፉ ያመሻሉ። በቀጣይ ቀን ቅምጥሎቹ ዩቱበሮች በአሜሪካና አውሮፓ የኢትዮጵያውያን የእግርኳስ ውድድር ላይ ከልጆቻቸው ጋር ሲምነሸነሹ ማምሸታቸውን፣ ወይን እና ውስኪ መጠጣታቸውን እና ለልጆቻቸው የገዙትን መጫወቻ ከራሳቸው ጋር ካደረጉት የቴክሳስ ኮፍያ ጋር ብቅ እያሉ በአራዳ ቋንቋ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ '' ይላጡበታል '''። 

ለመሆኑ ሕሊና በእዚህ ደረጃ ተሸጦ ተቀርጥፎ ይበላል እንዴ? የአማራ ክልል ወጣት ተነሳ ሙት እያልክ ጦርነት ቀስቅሰህ እና በሚልዮን የሚቆጠር በተለይ የጎጃም ወጣት ከሦስት ዓመታት በላይ ከትምሕርት ገበታ እርቆ እና ትምሕርት እንደ ውሃ ጠምቶት እያለቀሰ፣እናት አባቱ በጥጋበኛ አጋች እየታገተ እና ገንዘብ አምጣ እየተባለ መከራውን እያየ፣ቅምጥሎቹ ባንዳ ዩቱበሮች በአውሮፓና አሜሪካ የስፖርት ፌስቲቫል ላይ ልጆቻቸው ከትምሕርት ዕረፍት ጋር ይዘው ወዝ ወዝ ሲሉ ማየት የእዚህ ዓይነት የባንዳነት እና ባሳደገች ሀገር ላይ የመጨከን ዓይን ያወጣ አውሬነት ለገንዘብ ሲሉ እንዴት ተዘፈዘፉበት ያስብላል። እነኝህ ባንዳ ዩቱበሮች የድፍረታቸው ድፍረት ትናንት የኢትዮጵያ አንድነት እያሉ ሲያወሩን በሰማንበት አንደበት ዛሬ ላይ የጎጥ ፖለቲካ እያቀነቀኑ ብቻ ሳይሆን ከጠላት ሀገር ጋር መሞዳሞድ እና ኢትዮጵያን በአደባባይ መሸጥ ከፍ ሲልም የባሕር በሯ መዘጋትን እና የመጣባትን መከራ በተድበሰበሰ የስልጣን ጥያቄ እና አዲስ አበባ ላይ ጎርፍ አየን በሚል የቱቦ መደፈን እና መዘጋት ጉዳይ እያነሱ ሊያጃጅሉን ይሞክራሉ። ለራሳችሁ የመጃጃል መብታችሁን ብናከብርም ኢትዮጵያን ለማሻሻጥ የምታደርጉትን የባንዳነት ተግባር ግን አይደለም ይህ ትውልድ መጪው ትውልድም በይቅርታ የሚዘለው ጉዳይ አይደለም። ሌላው ቀርቶ ለገዛ ልጆቻችሁም ''የባንዳ ልጆች '' ከመባል አያስጥላቸውም።

ኢትዮጵያ እና የኢትዮጵያ ሕዝብ የተኙ ለመሰሏችሁ።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ከግማሽ ክፍለዘመን በላይ ልጆቹን በጦርነት የማገዱትን የአዛውንት ክበቡን ፅንዶ፣ ያሳደገቻቸው እናታቸው ኢትዮጵያ እና ሕዝቧ የባሕር በር ተዘግቶበት እያዩ ዛሬም ለእናታቸው መውጫ በር ለመዝጋት የሚራወጡቱ እና ባንዳ ዩቱበሮችን ተግባሮቻቸውን ሁሉ በአንክሮ እየተከታተለ፣ ትዕግስቱን ከመፈታተን በላይ ከደሙ አልፎ አጥንቱን እያጋሉት መሆኑ አልገባቸውም። ይህ እንቆቅልሽ የሆነ ምድር ነው  ኢትዮጵያ፣ ይህ የተኛ ሲመስልህ እንደ አንበሳ አጓርቶ፣እንደ ግስላ የሚነሳ ሕዝብ ያለበት ሀገር ነው። ኢትዮጵያ ና የኢትዮጵያ ሕዝብ በአማራ፣በትግራይ እና በኦሮሞ ስም እያላችሁ በስሙ የነገዳችሁ ብቻ ሳትሆኑ ለባዕዳን ለመሸጥ እና ኢትዮጵያን ለማፍረስ የምታደርጉትን የአዛውንቶች ክበብ ስብስብም ሆነ በዩቱብ የባንዳነታችሁን ላንቃ የምትለቁበት ሁሉ ዕወቁት። የኢትዮጵያ ሕዝብ አልተኛም።ኢትዮጵያም አልተኛችም።እንዴት ተነስቶ ባንዳነትን እና ኢትዮጵያን ለማፍረስ የተውተረተሩትን ሁሉ እንደሚቀጣ ያውቅበታል።ከእዚህ በፊትም ሲነሳ ታውቁታላችሁ።ሀገሩ ተገማች አይደለም። ሕዝቡም እንዲሁ።
++++++++++++++/////++++++++++++++


Tuesday, August 11, 2026

የኢትዮጵያ የባሕር ኃይል አዛዥ ኮሞዶር ጌታቸው ስዩም በምፅዋ የኢትዮጵያ የባሕር በር ላይ እጅ አልሰጥም ብለው ያፈሰሱት ደም ዛሬም በባሕሩ ዳር ላይ ይጣራል።


በአስመራ የተወለዱት የኮሞዶር ጌታቸው ባለቤት፣በአዲስ አበባ የተወለዱት ልጆቻቸው ዛሬ ላይ ሆነው የሚነግሩን አለ 
ሙሉ ቪድዮውን ይከታተሉ።


Monday, August 3, 2026

በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ዛሬም ከምንጊዜውም በላይ የቅዱስ ሲኖዶስን የአፈጻጸም ጥብቅ ክትትል ትፈልጋለች።በሺህ የሚቆጠሩ ምእመናን ችግር ላይ ናቸው።


በጥንታውቷ ግሪክ ዋና ከተማ ከአቴንስ ወጣ ብሎ  ከስድስት ሺህ ካሬ በላይ ስፋት ያለው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስም የተገዛው ገዳም

=============
ጉዳያችን ልዩ ሪፖርት
=============

ኢትዮጵያና ግሪክ

ኢትዮጵያና ግሪክ ወደኋላ ከአምስት ሺህ ዓመታት በላይ ታሪክ ያላቸው ጥንታውያን አገሮች ውስጥ በቀዳሚነት ከሚቀመጡት ውስጥ ናቸው።800 ዓዓ አካባቢ የኖረው የግሪክ ባለቅኔ ሆሜር ኢትዮጵያን በጽሑፉ ከትቧታል። በግሪክ አይቲዮፕያ የጠይም ሰው መገለጫ ነው። ኢትዮጵያ እና ግሪክ የጥንቱ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን  ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ ስላላቸው ብቻ ሳይሆን በቀላሉ የማይቦረቦር ክፍለ ዘመናትን በኩራት የተሻገረ ባሕል ባለቤቶች ናቸው።ከእዚህ በዘለለ ወደ የጥንቱ የዓለም ታሪክ ስንሄድ ኢትዮጵያ በቀይባህር ላይ ባላት የበላይነት፣ግሪክ ደግሞ በሜዴትራንያን ባህር ላይ ባላት ስልታዊ ወሳኝ አቀማመጥ አንጻር ከንግድ ግንኙነት በላይ ተጽዕኖ ፈጣሪነታቸው ጉልህ ነበር።

በዘመናዊዋ ኢትዮጵያ በቀዳማዊ  አጼ ኃይለሥላሴ ዘመን ኢትዮጵያ እና ግሪክ ግንኙነት ወደ ከፍተኛ ደረጃ የተሸጋገረበት ነበር።ንጉሱ በ1947 ዓም ግሪክ ዋና ከተማ አቴንስ ሲገቡ የአቴንስ ሕዝብ በከፍተኛ ቁጥር በአደባባይ ወጥቶ ተቀብሏቸዋል። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በጸረ ፋሽሽት ትግል አኩሪ ገድል የፈጸመው የግሪክ ህዝብ በአውሮፓ ደርሶ እንደነበረው ጦርነቱ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 1945 ዓም እንደተጠናቀቀ ረሃብ ገብቶ ነበር። በእዚህ ጊዜ ታድያ አፄ ኃይለሥላሴ አቴንስ ከተማ ተገኝተው ቁጥሩ ብዙ የሆነ የቁም ከብት ገዝተው ህዝቡን በአደባባይ ስጋ አብልተዋል። ይህ ሥጋ ህዝቡን ያበሉበት ቦታ አሁን ድረስ አቢሲኒያ አደባባይ ይባላል።የእዚህ ጽሑፍ አዘጋጅም ቦታው ድረስ ሄዶ በአደባባዩ ዙርያ ያሉ ባለሱቆችን ለምን የአቢሲንያ አደባባይ ተባለ ብሎ ሲጠይቃቸው ይህንኑ ንጉሱ የሰሩት የቸርነት ሥራ አስታውሰው ነግረውታል። 

ግሪኮች በቀድማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት ጊዜ በተለይ ወደ ኢትዮጵያ እየመጡ በመኖር በንግድ፣በመምህርነት፣በግንባታ እና በተለያዩ ሙያዎች ተሰማርተው ለኢትዮጵያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል።በምሕንድስናው ዘርፍ መሃል አዲስ አበባ የሚገኘው የአራዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሕንጻ ዲዛይን እስከ የንግድ ባንክ ህንጻዎች ግሪካውያን አሻራቸውን አስቀምጠዋል። እዚህ ላይ የሱፐርማርኬት ባለቤቱ እና ከቤቴ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ተለይቶኝ አያውቅም ያሉት አቶ ባምቢስን ማስታወስ ይቻላል።ይህ ሁሉ ሆኖ በአሁኑ ጊዜ ግን ኢትዮጵያውያን እና ግሪካውያን ግንኙነት ላይ በጣም የጠለቀ ግንኙነት አይታይም።አዳዲሶቹ የሁለቱ አገሮች ትውልዶች በሚገባ መተዋወቅ እንዲችሉ የባሕል ልውውጥ እና የንግድ ግንኙነታቸውን ማሳደግ አለባቸው። እዚህ ላይ በኢትዮጵያ ይኖሮ የነበሩ ግሪካውያን የመሰረቱት የግሪክ ኢትዮጵያውያን ማኅበርን መጥቀስ ይቻላል። ማኅበሩ በየጊዜው የኢትዮጵያውያንን ባሕል እና ታሪክ በማስተዋወቅ የተጋ ማኅበር ሲሆን በአቴንስ የሚገኘውን የአቢሲንያ አደባባይ ሕጋዊ ይዞታ እንዲጠበቅ እና የቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴን ሃውልት ለማሳነጽ እንቅስቃሴ ላይ ያለ ማኅበር ነው። 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በግሪክ ሕጋዊ ዕውቅና እንዴት አገኘች?

በአቴንስ የምትገኘው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በተለይ ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ  የሰነድ ተቀባይት ችግሯን መፍትሔ ለመስጠት ሰበካ ጉባኤው በላከው ደብዳቤ በብፁዕ አቡነ ጳውሎስ በሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅና የተሰጣት ሲሆን ይኽውም የሶማቲዎ (ማኅበር) የግብር መለያ ቁጥር (Tax No) 997874156  “AΙΘΙΟΠΙΚΗΣΟΡΘΟΔΟΞΗΣ ΕΚΚΛΗΣΙΑΣ ΤΗΣ ΑΘΗΝΑΣ” በሚል ንብረት ለማፍራት፣ ገንዘብ ለማንቀሳቀስ፣ በግብርና ተያያዥ ክፍያዎች አፈጻጸም ዙሪያ ያሉ ችግሮችንም ለመፍታት በሚያስችል መልኩ ቤተክርስቲያኒቱ እውቅና አግኝታለች። ይህንን እውቅና የዛሬ አስር ዓመት ቅዱስ ሲኖዶስ በሦስት ሰዎች አሳሳች ደብዳቤ ቀድመው በመጡት አባ ወልደሚካዔል ጣውዬ ላይ ተደርበው በመጡት አባ ገብረየሱስ ጊዜ የቤተክርስቲያኒቱ ፍቃድ በክስ ምክንያት ለማወዛገብ ተሞክሮ ነበር።

ይህም ሆኖ ግን በግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስም የተመዘገበው እና በሶማትዮ ማኅበርነት የሚታወቀው አደረጃጀች ዛሬም በግሪክ መንግስት እውቅና ያለው ብቻ ሳይሆን በመተዳደርያ ደንቡም ውስጥ ኦርቶዶክሳዊ ትምሕርቶችን ከግሪክ አልፎ እስከ መካከለኛው ምስራቅ ድረስ ማስፋፋት እንደሚችል በጸደቀለት ደንብ ተገልጿል። ከእዚህ በተለየ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ደንብ እና ስርዓት መሰረት ያለው አደረጃጀች በውስጥ ደንቡ መሰረት የሚነሱ ማናቸውም የሃይማኖት ክርክሮች እና ጥያቄዎች የሚፈታው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዶግማና ቀኖና መሰረት ብቻ እና ብቻ እንደሆነ ደንቡ ያዛል።ይህም በቤተርክስቲያኒቱ ላይ ለሚነሱ የሃይማኖት ቅሰጣዎች ሁሉ ዕድል የማይሰጥ ሆኖ የተደራጀ ጠንካራ አደረጃጀት ያለው ነው።

በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ዛሬም ከምንጊዜውም በላይ የቅዱስ ሲኖዶስን የአፈጻጸም ጥብቅ ክትትል ትፈልጋለች።

ቅዱስ ሲኖዶስ በመጋቢት/2017 ዓም አቡነ ጢሞቲዎስ እና አቡነ ጴጥሮስ ያሉበት ልዩ ልዑክ ግሪክ ድረስ ልኮ የግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ጉዳይ ለማየት ተሞክሯል። ከብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት የአቴንስ ጉዞ ተከትሎ ቅዱስ ሲኖዶስ ክሕነታቸው ተይዞ የነበረው የአባ ወልደሚካኤልን ስልጣነ ክሕነት የመለሰ ሲሆን ለአቴንስ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በሕገ ቤተክርስቲያን መሰረት አዲስ አስተዳዳሪ ሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬን መድቦ፣በአሁኑ ጊዜ ምእመናን የአዲሱን አስተዳዳሪ መምጣት በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።ይህ በአሁኑ ጊዜ ቤተክርስቲያኒቱ የምትገኝበት ተጨባጭ እውነት ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በኋላ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዙርያ የሚከተሉት ሁኔታዎች ተከስተዋል እነርሱም ፡
  • አቴንስ ፖሊጎኖ የምትገኘው ለአራት አስርተ ዓመታት ምእመናን ሲገለገሉባት የነበረችው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በአጽራረ ቤተክርስቲያን በሆኑ በቤተክርስቲያን ውስጥ ፊሽካ ከመንፋት እስከ ደም ማፍሰስ ወንጀል በፈጸሙ እና አሁንም ጉዳያቸው በሕግ የተያዘ ግልሰቦች እና እራሱን ኪኖቲታ በማለት በሚጠራ የዕድር አደረጃጀት በፈጠሩት ሁከት አማካይነት ቤተክርስቲያኒቱ በግሪክ መንግስት እንድትዘጋ ሆነ።
  • ቤተክርስቲያኒቱ ከተዘጋች ወዲህ በአቴንስ የሚኖሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሚያስቀድሱበት ቦታ በተለይ በአቴንስ ከተማ ውስጥ አለመኖሩና ቤተክርስቲያኒቱን በግሪክ በሕጋዊነት እንዲያገለግሉ የተመደቡት ሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ ወደ ግሪክ በቶሎ አለመምጣት መጪው የፍልሰታ የፆም ወቅት ሳይቀር ምእመናን ተቸግረው እንደሚያሳልፉ ቅዱስ ሲኖዶስም የሚያውቀው ጉዳይ ነው።
  • ይህ በእንዲህ እያለ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በአቡነ ኤልያስ ቤተክርስቲያኒቱን ያወከውን የዕድር አደረጃጀት (ኪኖቲታን) ማዕከል ያደረገ  በሆቴል ያደረጉት ''ጉባዔ'' አይደለም ሌላ የራሱ የኪኖቲታ ስር ናችሁ የተባሉ ምእመናንን ሳይቀር ማሰባሰብ ያልቻለ ብቻ ሳይሆን በቅዱስ ሲኖዶስም ምንም እውቅና የሌለው የጉባዔው ምንነት እና ሆቴል የተመረጠበትም ምክንያት ሳይታወቅ ተድበስብሶ ይሄው ሳምንታት ነጎዱ። 
  • ቤተክርስቲያኒቱ በስሟ የተገዛውን ከስድስት ሺህ ካሬ በላይ ስፋት ያለው በአውሮፓ የመጀመርያዋ የሆነውን ገዳም በተመለከተ ምን ደረሰ፣ይህ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ንብረት ነው ብሎ የሚከታተለው ሊቀጳጳስም ሆነ ሀገረስብከት ሳይኖረው ስምንት ዓመታትን ያሳለፈበት እውነታ ዛሬም መሬት ላይ ያለ ዕውነታ ነው።
  • አቡነ ኤልያስ በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር በኩል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በግሪክ ያላቸው የኃላፊነት ደረጃ በግልጽ እንዲነገረው በአዲስ አበባ የሚገኘውን የግሪክ ኤምባሲ ቤተክሕነት ድረስ ሄዶ እና የሚመለከተውን መምርያ ተገናኝቶ እንዲገለጽለት ጠየቀ።
  • የግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር ይህንን ጥያቄ ያቀረበበት ምክንያት አቡነ ኤልያስ ተደጋጋሚ ደብዳቤ በተለይ ወደ የግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር በመላክ በግሪክ ያለውን ጉዳይ እኔ የምቆጣጠረው ነው በሚል ከጊዜያዊ አስተዳዳሪ ምደባ ጀምሮ በሚልኳቸው ደብዳቤዎች የሚኒስቴር መስርያቤቱ ግራ ስለተጋባ ነበር።
  • በእዚህ መሰረትም መስመር ኤምባሲው ወደ ቤተክሕነት ልዑክ ልኮ የአቡነ ኤልያስ የኃላፊነት መጠን በቤተክርስቲያን ሲጋበዙ መባረክ ብቻ መሆኑ ተገለጸለት።ይህ የማጣራት ሂደት በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር ከደረሰው በኋላ አቡነ ኤልያስ በግሪክ በተጋበዙበት ቦታዎች የመባረክ ተግባራትን እንጂ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በተመለከተ ማናቸውም ጉዳዮች የሚከወኑት እና የተፈጻሚነት ደብዳቤዎች የሚመጡት ከቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ መሆኑን የሃይማኖት ሚኒስቴር አረጋገጠ።
  • በእዚህም መሰረት ምንም እንኳን እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስርዓት እና ደንብ መሰረት የሃገረስብከቱ ሊቀጳጳስ ሚና ከፍተኛ ቢሆንም ከግሪክ አንጻር ግን የሃይማኖት ሚኒስቴር ባረጋገጠው የሕግ ተቃርኖ ትንተና መሰረት አቡነ ኤልያስ በአሁኑ ጊዜ በግሪክ ቤተክርስቲያን የመመስረትም ሆነ የማስቀጠል እንዲሁም በሃይማኖት ሚኒስቴር በኩል አስተዳዳሪ የመሾም መብት እንደሌላቸው በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር በኩል የታወቀ ነው።
  • ለእዚህም ነው አንዳንድ በኪኖቲታ በኩል ያሉ ምእመናን ወንድሞች እና እህቶች ቤተክርስቲያን ልንገዛ ነው፣ገንዘብ አዋጡ ስትባሉ ሁለቴ አስቡ። አሰራሩ እንደዛ አይፈቅድም ገንዘቡን ለመዝረፍ ያሰፈሰፉ ዙርያችሁን አሉ እያልን ደጋግመን የምንመክረው።
  • በግሪክ ለምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ የሚመደበው በቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ መሆኑ ለግሪክ የኃይማኖት ሚኒስቴር በድጋሚ ግልጽ ስለሆነ አሁንም ቅዱስ ሲኖዶስ የመደባቸው ሊቀ ስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ ሲመጡ ብቻ ነው ቤተክርስቲያኒቱ በግሪክ ያላት የማስፈጸም አቅም የሚከፈተው።ይህ በግሪክ ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ነው።
አሁን ቅዱስ ሲኖዶስ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አንጻር ምን ማድረግ አለበት?

ቅዱስ ሲኖዶስ አሁንም በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አንጻር የሚከተሉትን አፋጣኝ ተግባራት ቢያከናውን የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን በግሪክ እንድታብብ ወሳኝነት ይኖረዋል። እነርሱም፡
  1. የሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ የግሪክ ጉዞ በተመለከተ ቅዱስ ሲኖዶስ ልዩ ክትትል በሚከተሉት ሁለት መንገዶች መከታተል እና ማስፈጸም ይችላል።
    • በአዲስ አበባ የሚገኘው የግሪክ አምባሳደርን ቅዱስ ፓትርያሪካችን ጠርተው ቤተክርስቲያኒቱ የመደበቻቸው አባት ወደ ግሪክ ተጉዘው በፍጥነት አገልግሎት እንዲጀምሩ እንዲያደርጉ ውይይት ማድረግ እና ለግሪክ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንም ደብዳቤ በመጻፍ ቤተክርስቲያኒቱ ቅሬታዋን ማቅረብ አለባት።
    • የግሪክ ሀገረ ስብከት አንዱ የገጠማት ችግር ሀገረስብከቱን አስተባብሮ የቤተክርስቲያንን ችግር ከመፍታት ይልቅ በግል እና የሀገረስብከቱን መዋቅራዊ አቅም ባገለለ መልክ ከግለሰቦች ጋር በሚደረግ  ግንኙነት ብቻ ለመምራት የሚሞክሩት የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ አካሄድ መሆኑ ፀሐይ የሞቀው እና ሊቀጳጳሱን የሚቀርቡ ሁሉ እጅግ ያዘኑበት ጉዳይ ነው። በመሆኑም ሀገሩን እና ዘመኑን የዋጀ የሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ምደባ አሁንም በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ የምትጠብቀው አሁንም አንገብጋቢው ጉዳይ እና ቅዱስ ሲኖዶስም ከእዚህ አንጻር የጉዳዩን አንገብጋቢነት ለመረዳት መዘግየቱ አሁንም ድረስ በቅርብም ሆነ በሩቅ ያሉ የቤተክርስቲያኒቱን አባቶችም ሆነ ምእመናንን ግራ ያጋባ ጉዳይ ነው።
  2. በግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ ምደባ ጉዳይ ከቤተክርስቲያን ጉዳይነት በዘለለ የሀገር ገጽታ፣ ከእዚያም ሲያልፍ የኢትዮጵያና የግሪክ የረጅም ጊዜ ትስስር ነጸብራቅም ስለሆነ የኢትዮጵያ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የአውሮፓ ዴስክ እና በጣልያን የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲም በጥብቅ ተከታትሎ ሊያስፈጽመው የሚገባ ጉዳይ ነው።በውጪ የሚኖረው ማኅበረሰብ የራሱን ኃይማኖት በተገቢ መንገድ ማከናወን አለመቻሉ ከቤተክሕነትም አልፎ የኢትዮጵያውያን ጉዳይ ያገባኛል የሚል ማናቸውም ቢሮ ይመለከተዋል። ስለሆነም የተጠያቂነቱ አድማስ በቀላሉ የሚወሰን አይደለም።
ባጠቃላይ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ በተመለከተ ቅዱስ ሲኖዶስ በመላው ዓለም ከሚገኙ የቤተክርስቲያኒቱ ችግሮች በቀዳሚነት እና አንገብጋቢነት የሚገኝ መሆኑን ተመልክቶ ጥብቅ ክትትል አለማድረጉ ቤተክርስቲያንን በእጅጉ የሚጎዳ ብቻ ሳይሆን በእግዚአብሔርም ሆነ በሰው ፊት የሚያስጠይቅ የጊዜያችን እጅግ አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን ደግመን አሁንም እንደልጅነት ለብፁዓን አባቶቻችን ለማሳሰብ እንወዳለን።
=======================///=============

Tuesday, July 14, 2026

የክፍለዘመናችን የኢትዮጵያ የስልጣኔ ማማ መለኪያ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ጉባዔ ነገ በአዲስ አበባ ይከፈታል። ህልውናችን፣መጪው ስልጣኔያችን፣ሰላማችን እና ዕድገታችን በእዚህ ጉባዔ ውጤትና ሒደት ይወሰናል።

Foto : Fana digital

  •  የቻልን በሀሳብ እና በጸሎት፣ ያልገባን እና የተምታታብን ደግሞ እኪገባን በዝምታ በመቆየት ኢትዮጵያን እናግዛት።
=========
ጉዳያችን ልዩ
=========

ኢትዮጵያ ሐምሌ 8፣2018 ዓም ከ4 ሺህ በላይ ከመላ ሀገሪቱ የተውጣጡ ተሳታፊዎች እንደሚሳተፉና 93% የኢትዮጵያን ክፍል እንደሸፈነ የተነገረለት የሀገራዊ ምክክር ጉባዔ በአዲስ አበባ ይከፈታል።የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አመሰራረትና አደረጃጀት ኢትዮጵያ በቅርብ ዓመታት እየገነባቻቸው ያሉት የተቋሞቿ የጥራት ደረጃ አንዱ ማሳያ ሊሆን ይችላል። ተቋም የሚለካው ከተቋማዊ መዋቅሩ አንጻር ብቻ ሳይሆን ከአመሰራረቱ ግልጽነት እና ሒደት ጭምር ነው። ከእዚህ አንጻር የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የአመሰራረት ሂደትና የያዘው የሰለጠነ የሰው ኃይል ኢትዮጵያን በሚመጥን መልኩ የተቀናጀ ነው። 

ኮሚሽኑ ሰሞኑን በሸራተን አዲስ ሆቴል ለሚዲያዎች መግለጫ መስጠቱ ይታወሳል። በዚህም የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር መስፍን ዓርዓያ (ፕ/ር)፣ "ዋናው ሀገራዊ ጉባዔ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ/ም ጀምር ይካሄዳል" ሲሉ ተናግረዋል።
ይህ የመጨረሻው ዋና ጉባዔ በአዲስ አበባ ከተማ ከሦስት ሳምንታት ባልበለጠ ጊዜ እንደሚካሄድም አስታውቀዋል።
በትግራይ ክልል በሚስተዋለው የፖለቲካ አለመረጋጋት መግባት ባለመቻሉ የክልሉን አጀንዳ በአዲስ አበባ ከተማ መቀበሉን፣ በሌሎች ሁሉም ክልሎች በአካል በመንቀሳቀስ መቀበሉን ሲያስታውቅ ቆይቷል። በተያያዘ የቀረቡለት አጀንዳዎቹን ለባለድርሻ አካላት በማቅረብ ሀሳብ እየተቀበለ መሆኑን መሆኑን ከሰሞኑ ጭምር ገልጿል።
በውጭ ሀገራት ከሚገኙ ዳያስፖራዎችም አጀንዳ መቀበሉን ኮሚሽኑ ገልጿል።
ኮሚሽኑ መጀመሪያ በተሰጠው ሦስት አመታት ስራው ባለመጠናቀቁ ፓርላማው ለአንድ ዓመት ተጨማሪ ጊዜ ከሰጠው በኋላ፣ ያም ባለመብቃቱ ለሁለተኛ ጊዜ የስምንት ወራት ጊዜ ተጨምሮለት እየሰራ ይገኛል።

ኮሚሽኑ ከመላው ሀገሪቱ እና ከራሱ ከመንግስትም ጭምር አጀንዳዎችን ከተቀበለ በኋላ አጀንዳዎቹን በሚከተሉት ዋና ዋና ሃሳቦች ጠቅልሏቸዋል።

እነርሱም ፡-

👉 የሀገር ግንባታ

👉 የመንግሥት አደረጃጀትና ቅርጽ፣ የፖለቲካ ሥርዓት፣ የፖለቲካ ውክልና እና የምርጫ ሥርዓት፣ 👉 የፌዴራል ከተሞች አዲስ አበባና ድሬዳዋ ጉዳይ፣ 👉 የሃይማኖት ጉዳዮች፣ታሪካዊ ቅሬታዎች እና እርቅ 👉 የተቋማት ግንባታ፣ የሕግ የበላይነትና ሰብዓዊ መብቶች፣ 👉 ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም የአርሶ አደሮች እና አርብቶ አደሮች ጉዳዮች
👉 ሙስና እና መልካም አስተዳደር እና የሰላም ግንባታ ናቸው፡፡

ይህ ጉባዔ የኢትዮጵያ የኢትዮጵያ የስልጣኔ ማማ መለኪያ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ጉባዔ ነው

ህልውናችን፣መጪው ስልጣኔያችን፣ሰላማችን እና ዕድገታችን በእዚህ ጉባዔ ውጤትና ሒደት ይወሰናል። በእዚህ ጉባዔ ከባሕር ማዶ ተቀምጠው አቃቂር የሚያወጡ እና በገዛ እናታቸው ኢትዮጵያ የወደፊት ዕጣ ላይ የሚሳለቁ ወደ ሕሊናቸው እንዲመለሱ ይመከራሉ። በራስ ላይ መቀለድ ለጊዜው እንደ ቀላል ሕመም ሊታይ ይችላል።በአሁኑ እና በመጪው ትውልድ ላይ ለመቆመር መሞከርና በመዘባበት እንዲሁም ትውልዱ እያደረገ ያለውን ምክክር ለማጣጣል መሞከር ግን እንዲሁ በቀላል መታየት ያለበት ጉዳይ አይደለም። ትውልዱ እራሱ ተዉን! ተመካክረን ችግራችንን እንፍታበት! ብሎ ሊገስጻቸውና ከእዚያም ሲያልፍ መቅጣት መቻል አለበት።

አሁን ኢትዮጵያ እየመከረች ነው። መንግስትም የራሱን አጀንዳ እንደማንኛውም የሕብረተሰብ ክፍል አቅርቦ እኩል የሚወያይበት እና በኢትዮጵያ መጪው የፖለቲካ፣ማኅበራዊ እና ምጣኔ ሀብታዊ ጎዳና ላይ ጉልህ አስተዋጽዖ የሚኖረው ሀገራዊ ውይይት እንዲሳካ እና ለሀገራችን ጥቃቅኖቹም ሆነ ግዙፍ የልዩነት ጉዳዮች መፍትሔ እንዲሰጥ የቻልን በሀሳብ እና በጸሎት፣ ያልገባን እና የተምታታብን ደግሞ እኪገባን በዝምታ በመቆየት ኢትዮጵያን እናግዛት።

============///////==========

Tuesday, June 2, 2026

7ኛው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ግንቦት 24፣2018 ዓም በከፍተኛ የሕዝብ ተሳትፎ ተጠናቋል።

ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ በሰባተኛው ብሔራዊ ምርጫ ድምፅ ሲሰጡ።

  • ስለምርጫው ዝርዝር ጉዳይ ምን ያውቃሉ?

✓ ሰባተኛው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ 42 ፓርቲዎች እና 73 የግል ተወዳዳሪዎች ለተለያዩ ምክር ቤቶች ዕጩዎች የቀረቡበት ነው።

✓ በዚህ ምርጫ በአጠቃላይ 2,198 ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲሁም 8,736 ለክልል ምክር ቤቶች መቀመጫዎች በዕጩነት ቀርበው ተወዳድረዋል።

✓ በዚህም በምርጫው የተወዳደሩት አጠቃላይ ዕጩዎች ቁጥር 10,934 ዕጩዎች መሆናቸውን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መረጃ ያመለክታል።

✓ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለክልል ምክር ቤቶች ከፍተኛውን ዕጩዎች ያቀረቡት ሦስት ፓርቲዎች ናቸው።

✓  በዚህም ገዢው ብልጽግና 2,950 ዕጩዎችን በማቅረብ ቀዳሚ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) 1,256 እና ሦስተኛው ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት 1,032 አቅርበዋል

✓ ሌሎች ፓርቲዎች እና የግል ተወዳዳሪዎችም በተለያየ ቁጥር ለተለያዩ ምክር ቤቶች መቀመጫ ለማግኘት ዕጩዎችን በምርጫው ላይ እንዲወዳደሩ አቅርበዋል።

 ✓ በአማራ ክልል ከሚገኙ 138 የምርጫ ክልሎች መካከል በስምንቱ ምርጫ እንደማይደረግ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ቀደም ብሎ ማስታወቁ ይታወሳል።

✓ በአማራ ክልል ድምጽ የማይሰጥባቸው 8ቱ የምርጫ ክልሎች በደቡብ እና ምዕራብ ጎንደር፣ በአምባሰል እንዲሁም በደጋ ዳሞት የሚገኙ መሆናቸው ተገልጿል።

✓ በትግራይ ክልል ከሌሎች የአገሪቱ ክልሎች ጋር በአንድ ላይ ምርጫ አልተካሄደም።

 ✓ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢዋ ወ/ሮ ሜላተወርቅ ሰኞ ዕለት ድምጽ በማይሰጥባቸው ስምንት የምርጫ ክልሎች ወደፊት እንዲመርጡ እንደሚደረግ ገልጸዋል።

✓ በትግራይም 38 ወንበሮች ክልሉ በምርጫ ቦርድ በተቀመጠው የምርጫ ሒደትና ሕግ መሰረት የሚካሔድና ወንበሮቹ ክፍት ሆነው ይጠብቃሉ።

✓ ትናንት ግንቦት 24፣2018 ዓም የተደረገው ብሔራዊ ምርጫ 501 ዕጩዎችን ወደ የሕግ መወሰኛው ወይንም የተወካዮች ምክርቤት የሚያስገባና ምስክርም 25፣2019 ዓም በሚከፈተው የኢትዮጵያ ምክርቤት አዲሱ መንግስት ሥራ ይጀምራል።

✓ በእዚህ ምርጫ የኢትዮጵያን የመንግስት ስሪት ምርጫውን በማደናቀፍ ዕቅድ ተግባር የሸረቡ የቅርብና የሩቅ ቡድኖች በኢትዮጵያ ሕዝብ ጥንቁቅና የቆረጠ የምርጫ ተሳትፎ በእጅጉ ተበሳጭተዋል።

በሰባተኛው የኢትዮጵያ ምርጫ የተሳተፉ ብሔራዊና የክልል ፓርቲዎች ዝርዝር:-

ምንጭ:- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

ምንጭ:- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ







የኢትዮጵያ ወዳጅ ንጉስ ልጅ ዛሬ ከእዚህ ዓለም አረፉ። ለኖርዌይ ትልቅ የሃዘን ቀን ሆኗል።Norway's King Harald V has died at the age of 89

በዚህ አጭር ዘገባ ውስጥ የሚከተሉትን ያገኛሉ። ስለ ንጉስ ሃራልድ በጥቂቱ የንጉስ ሃራልድ አባት ንጉስ ኦላቭ እና ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ የት ተዋወቁ? ንጉስ ሃራልድ አምስተኛ የኖርዌይ ንጉስ ===================...