Monday, August 3, 2026

በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ዛሬም ከምንጊዜውም በላይ የቅዱስ ሲኖዶስን የአፈጻጸም ጥብቅ ክትትል ትፈልጋለች።በሺህ የሚቆጠሩ ምእመናን ችግር ላይ ናቸው።


በጥንታውቷ ግሪክ ዋና ከተማ ከአቴንስ ወጣ ብሎ  ከስድስት ሺህ ካሬ በላይ ስፋት ያለው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስም የተገዛው ገዳም

=============
ጉዳያችን ልዩ ሪፖርት
=============

ኢትዮጵያና ግሪክ

ኢትዮጵያና ግሪክ ወደኋላ ከአምስት ሺህ ዓመታት በላይ ታሪክ ያላቸው ጥንታውያን አገሮች ውስጥ በቀዳሚነት ከሚቀመጡት ውስጥ ናቸው።800 ዓዓ አካባቢ የኖረው የግሪክ ባለቅኔ ሆሜር ኢትዮጵያን በጽሑፉ ከትቧታል። በግሪክ አይቲዮፕያ የጠይም ሰው መገለጫ ነው። ኢትዮጵያ እና ግሪክ የጥንቱ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን  ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ ስላላቸው ብቻ ሳይሆን በቀላሉ የማይቦረቦር ክፍለ ዘመናትን በኩራት የተሻገረ ባሕል ባለቤቶች ናቸው።ከእዚህ በዘለለ ወደ የጥንቱ የዓለም ታሪክ ስንሄድ ኢትዮጵያ በቀይባህር ላይ ባላት የበላይነት፣ግሪክ ደግሞ በሜዴትራንያን ባህር ላይ ባላት ስልታዊ ወሳኝ አቀማመጥ አንጻር ከንግድ ግንኙነት በላይ ተጽዕኖ ፈጣሪነታቸው ጉልህ ነበር።

በዘመናዊዋ ኢትዮጵያ በቀዳማዊ  አጼ ኃይለሥላሴ ዘመን ኢትዮጵያ እና ግሪክ ግንኙነት ወደ ከፍተኛ ደረጃ የተሸጋገረበት ነበር።ንጉሱ በ1947 ዓም ግሪክ ዋና ከተማ አቴንስ ሲገቡ የአቴንስ ሕዝብ በከፍተኛ ቁጥር በአደባባይ ወጥቶ ተቀብሏቸዋል። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በጸረ ፋሽሽት ትግል አኩሪ ገድል የፈጸመው የግሪክ ህዝብ በአውሮፓ ደርሶ እንደነበረው ጦርነቱ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 1945 ዓም እንደተጠናቀቀ ረሃብ ገብቶ ነበር። በእዚህ ጊዜ ታድያ አፄ ኃይለሥላሴ አቴንስ ከተማ ተገኝተው ቁጥሩ ብዙ የሆነ የቁም ከብት ገዝተው ህዝቡን በአደባባይ ስጋ አብልተዋል። ይህ ሥጋ ህዝቡን ያበሉበት ቦታ አሁን ድረስ አቢሲኒያ አደባባይ ይባላል።የእዚህ ጽሑፍ አዘጋጅም ቦታው ድረስ ሄዶ በአደባባዩ ዙርያ ያሉ ባለሱቆችን ለምን የአቢሲንያ አደባባይ ተባለ ብሎ ሲጠይቃቸው ይህንኑ ንጉሱ የሰሩት የቸርነት ሥራ አስታውሰው ነግረውታል። 

ግሪኮች በቀድማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት ጊዜ በተለይ ወደ ኢትዮጵያ እየመጡ በመኖር በንግድ፣በመምህርነት፣በግንባታ እና በተለያዩ ሙያዎች ተሰማርተው ለኢትዮጵያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል።በምሕንድስናው ዘርፍ መሃል አዲስ አበባ የሚገኘው የአራዳ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሕንጻ ዲዛይን እስከ የንግድ ባንክ ህንጻዎች ግሪካውያን አሻራቸውን አስቀምጠዋል። እዚህ ላይ የሱፐርማርኬት ባለቤቱ እና ከቤቴ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ተለይቶኝ አያውቅም ያሉት አቶ ባምቢስን ማስታወስ ይቻላል።ይህ ሁሉ ሆኖ በአሁኑ ጊዜ ግን ኢትዮጵያውያን እና ግሪካውያን ግንኙነት ላይ በጣም የጠለቀ ግንኙነት አይታይም።አዳዲሶቹ የሁለቱ አገሮች ትውልዶች በሚገባ መተዋወቅ እንዲችሉ የባሕል ልውውጥ እና የንግድ ግንኙነታቸውን ማሳደግ አለባቸው። እዚህ ላይ በኢትዮጵያ ይኖሮ የነበሩ ግሪካውያን የመሰረቱት የግሪክ ኢትዮጵያውያን ማኅበርን መጥቀስ ይቻላል። ማኅበሩ በየጊዜው የኢትዮጵያውያንን ባሕል እና ታሪክ በማስተዋወቅ የተጋ ማኅበር ሲሆን በአቴንስ የሚገኘውን የአቢሲንያ አደባባይ ሕጋዊ ይዞታ እንዲጠበቅ እና የቀዳማዊ አጼ ኃይለስላሴን ሃውልት ለማሳነጽ እንቅስቃሴ ላይ ያለ ማኅበር ነው። 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በግሪክ ሕጋዊ ዕውቅና እንዴት አገኘች?

በአቴንስ የምትገኘው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በተለይ ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ  የሰነድ ተቀባይት ችግሯን መፍትሔ ለመስጠት ሰበካ ጉባኤው በላከው ደብዳቤ በብፁዕ አቡነ ጳውሎስ በሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅና የተሰጣት ሲሆን ይኽውም የሶማቲዎ (ማኅበር) የግብር መለያ ቁጥር (Tax No) 997874156  “AΙΘΙΟΠΙΚΗΣΟΡΘΟΔΟΞΗΣ ΕΚΚΛΗΣΙΑΣ ΤΗΣ ΑΘΗΝΑΣ” በሚል ንብረት ለማፍራት፣ ገንዘብ ለማንቀሳቀስ፣ በግብርና ተያያዥ ክፍያዎች አፈጻጸም ዙሪያ ያሉ ችግሮችንም ለመፍታት በሚያስችል መልኩ ቤተክርስቲያኒቱ እውቅና አግኝታለች። ይህንን እውቅና የዛሬ አስር ዓመት ቅዱስ ሲኖዶስ በሦስት ሰዎች አሳሳች ደብዳቤ ቀድመው በመጡት አባ ወልደሚካዔል ጣውዬ ላይ ተደርበው በመጡት አባ ገብረየሱስ ጊዜ የቤተክርስቲያኒቱ ፍቃድ በክስ ምክንያት ለማወዛገብ ተሞክሮ ነበር።

ይህም ሆኖ ግን በግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስም የተመዘገበው እና በሶማትዮ ማኅበርነት የሚታወቀው አደረጃጀች ዛሬም በግሪክ መንግስት እውቅና ያለው ብቻ ሳይሆን በመተዳደርያ ደንቡም ውስጥ ኦርቶዶክሳዊ ትምሕርቶችን ከግሪክ አልፎ እስከ መካከለኛው ምስራቅ ድረስ ማስፋፋት እንደሚችል በጸደቀለት ደንብ ተገልጿል። ከእዚህ በተለየ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ደንብ እና ስርዓት መሰረት ያለው አደረጃጀች በውስጥ ደንቡ መሰረት የሚነሱ ማናቸውም የሃይማኖት ክርክሮች እና ጥያቄዎች የሚፈታው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዶግማና ቀኖና መሰረት ብቻ እና ብቻ እንደሆነ ደንቡ ያዛል።ይህም በቤተርክስቲያኒቱ ላይ ለሚነሱ የሃይማኖት ቅሰጣዎች ሁሉ ዕድል የማይሰጥ ሆኖ የተደራጀ ጠንካራ አደረጃጀት ያለው ነው።

በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ዛሬም ከምንጊዜውም በላይ የቅዱስ ሲኖዶስን የአፈጻጸም ጥብቅ ክትትል ትፈልጋለች።

ቅዱስ ሲኖዶስ በመጋቢት/2017 ዓም አቡነ ጢሞቲዎስ እና አቡነ ጴጥሮስ ያሉበት ልዩ ልዑክ ግሪክ ድረስ ልኮ የግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ጉዳይ ለማየት ተሞክሯል። ከብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት የአቴንስ ጉዞ ተከትሎ ቅዱስ ሲኖዶስ ክሕነታቸው ተይዞ የነበረው የአባ ወልደሚካኤልን ስልጣነ ክሕነት የመለሰ ሲሆን ለአቴንስ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በሕገ ቤተክርስቲያን መሰረት አዲስ አስተዳዳሪ ሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬን መድቦ፣በአሁኑ ጊዜ ምእመናን የአዲሱን አስተዳዳሪ መምጣት በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ።ይህ በአሁኑ ጊዜ ቤተክርስቲያኒቱ የምትገኝበት ተጨባጭ እውነት ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በኋላ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዙርያ የሚከተሉት ሁኔታዎች ተከስተዋል እነርሱም ፡
  • አቴንስ ፖሊጎኖ የምትገኘው ለአራት አስርተ ዓመታት ምእመናን ሲገለገሉባት የነበረችው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በአጽራረ ቤተክርስቲያን በሆኑ በቤተክርስቲያን ውስጥ ፊሽካ ከመንፋት እስከ ደም ማፍሰስ ወንጀል በፈጸሙ እና አሁንም ጉዳያቸው በሕግ የተያዘ ግልሰቦች እና እራሱን ኪኖቲታ በማለት በሚጠራ የዕድር አደረጃጀት በፈጠሩት ሁከት አማካይነት ቤተክርስቲያኒቱ በግሪክ መንግስት እንድትዘጋ ሆነ።
  • ቤተክርስቲያኒቱ ከተዘጋች ወዲህ በአቴንስ የሚኖሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሚያስቀድሱበት ቦታ በተለይ በአቴንስ ከተማ ውስጥ አለመኖሩና ቤተክርስቲያኒቱን በግሪክ በሕጋዊነት እንዲያገለግሉ የተመደቡት ሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ ወደ ግሪክ በቶሎ አለመምጣት መጪው የፍልሰታ የፆም ወቅት ሳይቀር ምእመናን ተቸግረው እንደሚያሳልፉ ቅዱስ ሲኖዶስም የሚያውቀው ጉዳይ ነው።
  • ይህ በእንዲህ እያለ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በአቡነ ኤልያስ ቤተክርስቲያኒቱን ያወከውን የዕድር አደረጃጀት (ኪኖቲታን) ማዕከል ያደረገ  በሆቴል ያደረጉት ''ጉባዔ'' አይደለም ሌላ የራሱ የኪኖቲታ ስር ናችሁ የተባሉ ምእመናንን ሳይቀር ማሰባሰብ ያልቻለ ብቻ ሳይሆን በቅዱስ ሲኖዶስም ምንም እውቅና የሌለው የጉባዔው ምንነት እና ሆቴል የተመረጠበትም ምክንያት ሳይታወቅ ተድበስብሶ ይሄው ሳምንታት ነጎዱ። 
  • ቤተክርስቲያኒቱ በስሟ የተገዛውን ከስድስት ሺህ ካሬ በላይ ስፋት ያለው በአውሮፓ የመጀመርያዋ የሆነውን ገዳም በተመለከተ ምን ደረሰ፣ይህ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ንብረት ነው ብሎ የሚከታተለው ሊቀጳጳስም ሆነ ሀገረስብከት ሳይኖረው ስምንት ዓመታትን ያሳለፈበት እውነታ ዛሬም መሬት ላይ ያለ ዕውነታ ነው።
  • አቡነ ኤልያስ በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር በኩል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በግሪክ ያላቸው የኃላፊነት ደረጃ በግልጽ እንዲነገረው በአዲስ አበባ የሚገኘውን የግሪክ ኤምባሲ ቤተክሕነት ድረስ ሄዶ እና የሚመለከተውን መምርያ ተገናኝቶ እንዲገለጽለት ጠየቀ።
  • የግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር ይህንን ጥያቄ ያቀረበበት ምክንያት አቡነ ኤልያስ ተደጋጋሚ ደብዳቤ በተለይ ወደ የግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር በመላክ በግሪክ ያለውን ጉዳይ እኔ የምቆጣጠረው ነው በሚል ከጊዜያዊ አስተዳዳሪ ምደባ ጀምሮ በሚልኳቸው ደብዳቤዎች የሚኒስቴር መስርያቤቱ ግራ ስለተጋባ ነበር።
  • በእዚህ መሰረትም መስመር ኤምባሲው ወደ ቤተክሕነት ልዑክ ልኮ የአቡነ ኤልያስ የኃላፊነት መጠን በቤተክርስቲያን ሲጋበዙ መባረክ ብቻ መሆኑ ተገለጸለት።ይህ የማጣራት ሂደት በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር ከደረሰው በኋላ አቡነ ኤልያስ በግሪክ በተጋበዙበት ቦታዎች የመባረክ ተግባራትን እንጂ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በተመለከተ ማናቸውም ጉዳዮች የሚከወኑት እና የተፈጻሚነት ደብዳቤዎች የሚመጡት ከቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ መሆኑን የሃይማኖት ሚኒስቴር አረጋገጠ።
  • በእዚህም መሰረት ምንም እንኳን እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስርዓት እና ደንብ መሰረት የሃገረስብከቱ ሊቀጳጳስ ሚና ከፍተኛ ቢሆንም ከግሪክ አንጻር ግን የሃይማኖት ሚኒስቴር ባረጋገጠው የሕግ ተቃርኖ ትንተና መሰረት አቡነ ኤልያስ በአሁኑ ጊዜ በግሪክ ቤተክርስቲያን የመመስረትም ሆነ የማስቀጠል እንዲሁም በሃይማኖት ሚኒስቴር በኩል አስተዳዳሪ የመሾም መብት እንደሌላቸው በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር በኩል የታወቀ ነው።
  • ለእዚህም ነው አንዳንድ በኪኖቲታ በኩል ያሉ ምእመናን ወንድሞች እና እህቶች ቤተክርስቲያን ልንገዛ ነው፣ገንዘብ አዋጡ ስትባሉ ሁለቴ አስቡ። አሰራሩ እንደዛ አይፈቅድም ገንዘቡን ለመዝረፍ ያሰፈሰፉ ዙርያችሁን አሉ እያልን ደጋግመን የምንመክረው።
  • በግሪክ ለምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ የሚመደበው በቅዱስ ሲኖዶስ ብቻ መሆኑ ለግሪክ የኃይማኖት ሚኒስቴር በድጋሚ ግልጽ ስለሆነ አሁንም ቅዱስ ሲኖዶስ የመደባቸው ሊቀ ስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ ሲመጡ ብቻ ነው ቤተክርስቲያኒቱ በግሪክ ያላት የማስፈጸም አቅም የሚከፈተው።ይህ በግሪክ ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ነው።
አሁን ቅዱስ ሲኖዶስ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አንጻር ምን ማድረግ አለበት?

ቅዱስ ሲኖዶስ አሁንም በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አንጻር የሚከተሉትን አፋጣኝ ተግባራት ቢያከናውን የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን በግሪክ እንድታብብ ወሳኝነት ይኖረዋል። እነርሱም፡
  1. የሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ የግሪክ ጉዞ በተመለከተ ቅዱስ ሲኖዶስ ልዩ ክትትል በሚከተሉት ሁለት መንገዶች መከታተል እና ማስፈጸም ይችላል።
    • በአዲስ አበባ የሚገኘው የግሪክ አምባሳደርን ቅዱስ ፓትርያሪካችን ጠርተው ቤተክርስቲያኒቱ የመደበቻቸው አባት ወደ ግሪክ ተጉዘው በፍጥነት አገልግሎት እንዲጀምሩ እንዲያደርጉ ውይይት ማድረግ እና ለግሪክ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንም ደብዳቤ በመጻፍ ቤተክርስቲያኒቱ ቅሬታዋን ማቅረብ አለባት።
    • የግሪክ ሀገረ ስብከት አንዱ የገጠማት ችግር ሀገረስብከቱን አስተባብሮ የቤተክርስቲያንን ችግር ከመፍታት ይልቅ በግል እና የሀገረስብከቱን መዋቅራዊ አቅም ባገለለ መልክ ከግለሰቦች ጋር በሚደረግ  ግንኙነት ብቻ ለመምራት የሚሞክሩት የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ አካሄድ መሆኑ ፀሐይ የሞቀው እና ሊቀጳጳሱን የሚቀርቡ ሁሉ እጅግ ያዘኑበት ጉዳይ ነው። በመሆኑም ሀገሩን እና ዘመኑን የዋጀ የሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ምደባ አሁንም በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ የምትጠብቀው አሁንም አንገብጋቢው ጉዳይ እና ቅዱስ ሲኖዶስም ከእዚህ አንጻር የጉዳዩን አንገብጋቢነት ለመረዳት መዘግየቱ አሁንም ድረስ በቅርብም ሆነ በሩቅ ያሉ የቤተክርስቲያኒቱን አባቶችም ሆነ ምእመናንን ግራ ያጋባ ጉዳይ ነው።
  2. በግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ ምደባ ጉዳይ ከቤተክርስቲያን ጉዳይነት በዘለለ የሀገር ገጽታ፣ ከእዚያም ሲያልፍ የኢትዮጵያና የግሪክ የረጅም ጊዜ ትስስር ነጸብራቅም ስለሆነ የኢትዮጵያ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የአውሮፓ ዴስክ እና በጣልያን የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲም በጥብቅ ተከታትሎ ሊያስፈጽመው የሚገባ ጉዳይ ነው።በውጪ የሚኖረው ማኅበረሰብ የራሱን ኃይማኖት በተገቢ መንገድ ማከናወን አለመቻሉ ከቤተክሕነትም አልፎ የኢትዮጵያውያን ጉዳይ ያገባኛል የሚል ማናቸውም ቢሮ ይመለከተዋል። ስለሆነም የተጠያቂነቱ አድማስ በቀላሉ የሚወሰን አይደለም።
ባጠቃላይ በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ በተመለከተ ቅዱስ ሲኖዶስ በመላው ዓለም ከሚገኙ የቤተክርስቲያኒቱ ችግሮች በቀዳሚነት እና አንገብጋቢነት የሚገኝ መሆኑን ተመልክቶ ጥብቅ ክትትል አለማድረጉ ቤተክርስቲያንን በእጅጉ የሚጎዳ ብቻ ሳይሆን በእግዚአብሔርም ሆነ በሰው ፊት የሚያስጠይቅ የጊዜያችን እጅግ አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን ደግመን አሁንም እንደልጅነት ለብፁዓን አባቶቻችን ለማሳሰብ እንወዳለን።
=======================///=============

Tuesday, July 14, 2026

የክፍለዘመናችን የኢትዮጵያ የስልጣኔ ማማ መለኪያ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ጉባዔ ነገ በአዲስ አበባ ይከፈታል። ህልውናችን፣መጪው ስልጣኔያችን፣ሰላማችን እና ዕድገታችን በእዚህ ጉባዔ ውጤትና ሒደት ይወሰናል።

Foto : Fana digital

  •  የቻልን በሀሳብ እና በጸሎት፣ ያልገባን እና የተምታታብን ደግሞ እኪገባን በዝምታ በመቆየት ኢትዮጵያን እናግዛት።
=========
ጉዳያችን ልዩ
=========

ኢትዮጵያ ሐምሌ 8፣2018 ዓም ከ4 ሺህ በላይ ከመላ ሀገሪቱ የተውጣጡ ተሳታፊዎች እንደሚሳተፉና 93% የኢትዮጵያን ክፍል እንደሸፈነ የተነገረለት የሀገራዊ ምክክር ጉባዔ በአዲስ አበባ ይከፈታል።የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አመሰራረትና አደረጃጀት ኢትዮጵያ በቅርብ ዓመታት እየገነባቻቸው ያሉት የተቋሞቿ የጥራት ደረጃ አንዱ ማሳያ ሊሆን ይችላል። ተቋም የሚለካው ከተቋማዊ መዋቅሩ አንጻር ብቻ ሳይሆን ከአመሰራረቱ ግልጽነት እና ሒደት ጭምር ነው። ከእዚህ አንጻር የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የአመሰራረት ሂደትና የያዘው የሰለጠነ የሰው ኃይል ኢትዮጵያን በሚመጥን መልኩ የተቀናጀ ነው። 

ኮሚሽኑ ሰሞኑን በሸራተን አዲስ ሆቴል ለሚዲያዎች መግለጫ መስጠቱ ይታወሳል። በዚህም የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር መስፍን ዓርዓያ (ፕ/ር)፣ "ዋናው ሀገራዊ ጉባዔ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ/ም ጀምር ይካሄዳል" ሲሉ ተናግረዋል።
ይህ የመጨረሻው ዋና ጉባዔ በአዲስ አበባ ከተማ ከሦስት ሳምንታት ባልበለጠ ጊዜ እንደሚካሄድም አስታውቀዋል።
በትግራይ ክልል በሚስተዋለው የፖለቲካ አለመረጋጋት መግባት ባለመቻሉ የክልሉን አጀንዳ በአዲስ አበባ ከተማ መቀበሉን፣ በሌሎች ሁሉም ክልሎች በአካል በመንቀሳቀስ መቀበሉን ሲያስታውቅ ቆይቷል። በተያያዘ የቀረቡለት አጀንዳዎቹን ለባለድርሻ አካላት በማቅረብ ሀሳብ እየተቀበለ መሆኑን መሆኑን ከሰሞኑ ጭምር ገልጿል።
በውጭ ሀገራት ከሚገኙ ዳያስፖራዎችም አጀንዳ መቀበሉን ኮሚሽኑ ገልጿል።
ኮሚሽኑ መጀመሪያ በተሰጠው ሦስት አመታት ስራው ባለመጠናቀቁ ፓርላማው ለአንድ ዓመት ተጨማሪ ጊዜ ከሰጠው በኋላ፣ ያም ባለመብቃቱ ለሁለተኛ ጊዜ የስምንት ወራት ጊዜ ተጨምሮለት እየሰራ ይገኛል።

ኮሚሽኑ ከመላው ሀገሪቱ እና ከራሱ ከመንግስትም ጭምር አጀንዳዎችን ከተቀበለ በኋላ አጀንዳዎቹን በሚከተሉት ዋና ዋና ሃሳቦች ጠቅልሏቸዋል።

እነርሱም ፡-

👉 የሀገር ግንባታ

👉 የመንግሥት አደረጃጀትና ቅርጽ፣ የፖለቲካ ሥርዓት፣ የፖለቲካ ውክልና እና የምርጫ ሥርዓት፣ 👉 የፌዴራል ከተሞች አዲስ አበባና ድሬዳዋ ጉዳይ፣ 👉 የሃይማኖት ጉዳዮች፣ታሪካዊ ቅሬታዎች እና እርቅ 👉 የተቋማት ግንባታ፣ የሕግ የበላይነትና ሰብዓዊ መብቶች፣ 👉 ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም የአርሶ አደሮች እና አርብቶ አደሮች ጉዳዮች
👉 ሙስና እና መልካም አስተዳደር እና የሰላም ግንባታ ናቸው፡፡

ይህ ጉባዔ የኢትዮጵያ የኢትዮጵያ የስልጣኔ ማማ መለኪያ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ጉባዔ ነው

ህልውናችን፣መጪው ስልጣኔያችን፣ሰላማችን እና ዕድገታችን በእዚህ ጉባዔ ውጤትና ሒደት ይወሰናል። በእዚህ ጉባዔ ከባሕር ማዶ ተቀምጠው አቃቂር የሚያወጡ እና በገዛ እናታቸው ኢትዮጵያ የወደፊት ዕጣ ላይ የሚሳለቁ ወደ ሕሊናቸው እንዲመለሱ ይመከራሉ። በራስ ላይ መቀለድ ለጊዜው እንደ ቀላል ሕመም ሊታይ ይችላል።በአሁኑ እና በመጪው ትውልድ ላይ ለመቆመር መሞከርና በመዘባበት እንዲሁም ትውልዱ እያደረገ ያለውን ምክክር ለማጣጣል መሞከር ግን እንዲሁ በቀላል መታየት ያለበት ጉዳይ አይደለም። ትውልዱ እራሱ ተዉን! ተመካክረን ችግራችንን እንፍታበት! ብሎ ሊገስጻቸውና ከእዚያም ሲያልፍ መቅጣት መቻል አለበት።

አሁን ኢትዮጵያ እየመከረች ነው። መንግስትም የራሱን አጀንዳ እንደማንኛውም የሕብረተሰብ ክፍል አቅርቦ እኩል የሚወያይበት እና በኢትዮጵያ መጪው የፖለቲካ፣ማኅበራዊ እና ምጣኔ ሀብታዊ ጎዳና ላይ ጉልህ አስተዋጽዖ የሚኖረው ሀገራዊ ውይይት እንዲሳካ እና ለሀገራችን ጥቃቅኖቹም ሆነ ግዙፍ የልዩነት ጉዳዮች መፍትሔ እንዲሰጥ የቻልን በሀሳብ እና በጸሎት፣ ያልገባን እና የተምታታብን ደግሞ እኪገባን በዝምታ በመቆየት ኢትዮጵያን እናግዛት።

============///////==========

Tuesday, June 2, 2026

7ኛው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ግንቦት 24፣2018 ዓም በከፍተኛ የሕዝብ ተሳትፎ ተጠናቋል።

ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ በሰባተኛው ብሔራዊ ምርጫ ድምፅ ሲሰጡ።

  • ስለምርጫው ዝርዝር ጉዳይ ምን ያውቃሉ?

✓ ሰባተኛው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ 42 ፓርቲዎች እና 73 የግል ተወዳዳሪዎች ለተለያዩ ምክር ቤቶች ዕጩዎች የቀረቡበት ነው።

✓ በዚህ ምርጫ በአጠቃላይ 2,198 ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲሁም 8,736 ለክልል ምክር ቤቶች መቀመጫዎች በዕጩነት ቀርበው ተወዳድረዋል።

✓ በዚህም በምርጫው የተወዳደሩት አጠቃላይ ዕጩዎች ቁጥር 10,934 ዕጩዎች መሆናቸውን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መረጃ ያመለክታል።

✓ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለክልል ምክር ቤቶች ከፍተኛውን ዕጩዎች ያቀረቡት ሦስት ፓርቲዎች ናቸው።

✓  በዚህም ገዢው ብልጽግና 2,950 ዕጩዎችን በማቅረብ ቀዳሚ ሲሆን፣ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) 1,256 እና ሦስተኛው ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት 1,032 አቅርበዋል

✓ ሌሎች ፓርቲዎች እና የግል ተወዳዳሪዎችም በተለያየ ቁጥር ለተለያዩ ምክር ቤቶች መቀመጫ ለማግኘት ዕጩዎችን በምርጫው ላይ እንዲወዳደሩ አቅርበዋል።

 ✓ በአማራ ክልል ከሚገኙ 138 የምርጫ ክልሎች መካከል በስምንቱ ምርጫ እንደማይደረግ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ቀደም ብሎ ማስታወቁ ይታወሳል።

✓ በአማራ ክልል ድምጽ የማይሰጥባቸው 8ቱ የምርጫ ክልሎች በደቡብ እና ምዕራብ ጎንደር፣ በአምባሰል እንዲሁም በደጋ ዳሞት የሚገኙ መሆናቸው ተገልጿል።

✓ በትግራይ ክልል ከሌሎች የአገሪቱ ክልሎች ጋር በአንድ ላይ ምርጫ አልተካሄደም።

 ✓ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢዋ ወ/ሮ ሜላተወርቅ ሰኞ ዕለት ድምጽ በማይሰጥባቸው ስምንት የምርጫ ክልሎች ወደፊት እንዲመርጡ እንደሚደረግ ገልጸዋል።

✓ በትግራይም 38 ወንበሮች ክልሉ በምርጫ ቦርድ በተቀመጠው የምርጫ ሒደትና ሕግ መሰረት የሚካሔድና ወንበሮቹ ክፍት ሆነው ይጠብቃሉ።

✓ ትናንት ግንቦት 24፣2018 ዓም የተደረገው ብሔራዊ ምርጫ 501 ዕጩዎችን ወደ የሕግ መወሰኛው ወይንም የተወካዮች ምክርቤት የሚያስገባና ምስክርም 25፣2019 ዓም በሚከፈተው የኢትዮጵያ ምክርቤት አዲሱ መንግስት ሥራ ይጀምራል።

✓ በእዚህ ምርጫ የኢትዮጵያን የመንግስት ስሪት ምርጫውን በማደናቀፍ ዕቅድ ተግባር የሸረቡ የቅርብና የሩቅ ቡድኖች በኢትዮጵያ ሕዝብ ጥንቁቅና የቆረጠ የምርጫ ተሳትፎ በእጅጉ ተበሳጭተዋል።

በሰባተኛው የኢትዮጵያ ምርጫ የተሳተፉ ብሔራዊና የክልል ፓርቲዎች ዝርዝር:-

ምንጭ:- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

ምንጭ:- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ







Friday, May 29, 2026

ከሰባተኛው የኢትዮጵያ ምርጫ በቀጣይ የሚታዩ የሚታዩት ሦስት እውነታዎች

ኢትዮጵያ 7 ኛው የሕዝብ ተውወካዮች ምክርቤት ምርጫ ሰኞ ግንቦት 24፣2018 ዓም ታካሂዳለች።ይህንን ምርጫ አንዳንዶች ሊያቃልሉት እና በለሆሳስ ሊያልፉት ይሞክራሉ።ሌሎች ደግሞ ምርጫው ይልቅ ነው ብቅ ፉክክር አልታየበትም ይላሉ።የቀሩት ሞቅ ሞቅ አላለልንም ይላሉ።እነኝህኞቹ ተፎካካሪዎች የሆኑ የድራፍት ቤት መነጋገርያ የሆኑ ቃላት ሲቀያየሩ ካላዩ ደስ የማይላቸው ናቸው።

ይህ ምርጫ ግን የኢትዮጵያን መጻኢ መንገድ የሚያቀና ነው።ምርጫው ከ ሀምሣ ሚልዮን በላይ ሕዝብ የሚሳተፍበት ሲሆን ለመጀመርያ ጊዜ በዲጂታልም ጭምር የሚከናወን ምርጥ ነው።

በእኔ ዕይታ ይህ 7ኛው የኢትዮጵያ ምርጫ ተከትሎ ሦስት እውነታዎች ለኢትዮጵያ ያመጣሉ።

እነርሱም:-

፩) ኢትዮጵያ ከጎሳ ፖለቲካ ማዕበል ቀዝፋ ወጥታ ወደ ሕብረብሔራዊ አንድነት የምትሸጋገርበት ነው።

፪) በጎሳ ፖለቲካ የቆሰለችው ኢትዮጵያ ቁስሏ መጥገግ የሚጀምርበት ነው።

፫) በሁለት እግሯ ለመቆም የምትጥረው ኢትዮጵያ ከባሕር በር የተገለለችበትን የክህደት ካባ አውልቃ በሁለት እግሮቿ ቆማ ተጽዕኖ ፈጣሪነቷ ዳግም የሚታይበት ጅማሮ ነው።

ሃተታ አላበዛም እነኝህ ሦስት እውነታዎች ዛሬ ያልገባን የዛሬ አምስት ዓመት ይገባናል።

ባሳለፍነው ሳምንት ኢትዮጵያውያን በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት ደግፈው ተሰልፈዋል።ለሀገራችን በጎ የሚታየንን ከመውቀስ ኢትዮጵያ ያለፈችበትን፣አሁን የቆመችበትንና ለነገ ያቀደችውን መረዳቱ ጥቅም አለው።

ፎቶ ይናገራል።

































Thursday, April 30, 2026

በአቴንስ፣ግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን ላለፉት 40 ዓመታት በላይ ስትጠቀምበት የነበረውን ፖሊጎኖ የሚገኘው ቤተክርስቲያን በፖሊስ ታሸገ።የቅዱስ ሲኖዶስ አፋጣኝ ምላሽ እየተጠበቀ ነው።



የአቴንስ ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን የታሸገችበት የጉግል የእንግሊዝኛ ትርጉም እና የግሪክኛ ዋናው ኮፒ።

በግሪክ አቴንስ የምትገኘው እና ወደ ግማሽ ክ/ዘመን አገልግሎት ስትሰጥ የነበረችው እና በአቴንስ ፖሊጎኖ የምትገኘው የኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያንን ሐሙስ ሚያዝያ 22፣2018 ዓም በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር መታዘዛቸውን በገለጹ የአቴንስ ኪፕሴሊ ወረዳ ፖሊሶች መታሸጉ ታውቋል።

መንደርደርያ

በአቴንስ የምትገኘው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን በተለይ ከ1994 ዓ/ም ጀምሮ  የሰነድ ተቀባይት ችግሯን መፍትሔ ለመስጠት ሰበካ ጉባኤው በላከው ደብዳቤ በብፁዕ አቡነ ጳውሎስ በሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅና የተሰጣት ሲሆን ይኽውም የሶማቲዎ (ማኅበር) የግብር መለያ ቁጥር (Tax No) 997874156  “AΙΘΙΟΠΙΚΗΣΟΡΘΟΔΟΞΗΣ ΕΚΚΛΗΣΙΑΣ ΤΗΣ ΑΘΗΝΑΣ” በሚል ንብረት ለማፍራት፣ ገንዘብ ለማንቀሳቀስ፣ በግብርና ተያያዥ ክፍያዎች አፈጻጸም ዙሪያ ያሉ ችግሮችንም ለመፍታት በሚያስችል መልኩ ቤተክርስቲያኒቱ እውቅና አግኝታለች። ይህንን እውቅና የዛሬ አስር ዓመት ቅዱስ ሲኖዶስ በሦስት ሰዎች አሳሳች ደብዳቤ ቀድመው በመጡት አባ ወልደሚካዔል ጣውዬ ላይ ተደርበው በመጡት አባ ገብረየሱስ ጊዜ የቤተክርስቲያኒቱ ፍቃድ በክስ ምክንያት ለማወዛገብ ተሞክሮ ነበር።

ይህም ሆኖ ግን በግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስም የተመዘገበው እና በሶማትዮ ማኅበርነት የሚታወቀው አደረጃጀች ዛሬም በግሪክ መንግስት እውቅና ያለው ብቻ ሳይሆን በመተዳደርያ ደንቡም ውስጥ ኦርቶዶክሳዊ ትምሕርቶችን ከግሪክ አልፎ እስከ መካከለኛው ምስራቅ ድረስ ማስፋፋት እንደሚችል በጸደቀለት ደንብ ተገልጿል። ከእዚህ በተለየ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ደንብ እና ስርዓት መሰረት ያለው አደረጃጀች በውስጥ ደንቡ መሰረት የሚነሱ ማናቸውም የሃይማኖት ክርክሮች እና ጥያቄዎች የሚፈታው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ዶግማና ቀኖና መሰረት ብቻ እና ብቻ እንደሆነ ደንቡ ያዛል።ይህም በቤተርክስቲያኒቱ ላይ ለሚነሱ የሃይማኖት ቅሰጣዎች ሁሉ ዕድል የማይሰጥ ሆኖ የተደራጀ ጠንካራ አደረጃጀት ያለው ነው።

የአቴንስ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ለምን ታሸገች?

የአቴንስ ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን የፌስቡክ ገጽ በዛሬው ዕለት በግሪክ ፖሊስ ስለታሸገችው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን አስመልክቶ በለጠፈው ጽሑፍ ላይ እንደሚከተለው ገልጾታል፡ 

''በቅድምያ የከበረ መንፈሳዊ ሰላምታ እያቀረብን ላለፉት ከአራት አስርተ ዓመታት በላይ ኢትዮጵያውያን ሲገለገሉበት የነበረው በአቴንስ ፖሊጎኖ የምትገኘው የአቴንስ ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን ስትገለገልበት የነበረው ቤተክርስቲያን በግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር መታዘዙን በመግለጽ ፖሊስ ዛሬ ሚያዝያ 22፣2018 ዓም ማሸጉ ታውቋል። ጉዳዩን በቤተክርስቲያኒቱ ጠበቃ በኩል የፖሊስ ጣቢያው የተጠየቀ ሲሆን ፖሊስ ከግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር መታዘዙን እንደገለጠለት ለማወቅ ተችሏል።

ቤተክርስቲያኒቱ ከየካቲት 16/2018 ዓም ጀምሮ ቅዳሴ እንዳይቀደስ በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ፊሽካ በማጮህ፣ተአምረ ማርያም እንዳይነበብ፣ኪዳን እንዳይደርስ የመረበሽ ተግባር ሲፈጸም የነበረ ሲሆን፣ቅዱስ ሲኖዶስ በየትኛውም የቤተክርስቲያን አገልግሎት እንዳይገቡ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ቀሲስ አየለ እና በሀገረስብከቱ ሊቀጳጳስ አቡነ ኤልያስ ድጋፍ የሚደረግላቸው በቤተክርስቲያናችን አገልግሎት ላይ ተደጋጋሚ የመረበሽ ስራ የሰሩት ግለሰቦች የአካባቢውን ማኅበረሰብ እንዲረበሽ ማድረጋቸውና የሀገረ ስብከታችን ሊቀ ጳጳስ አቡነ ኤልያስ ከሃይማኖት ሚኒስቴር ጋር የሚያደርጉት ምእመናንን የሚከስ እና የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ከግሪክ ለመንቀል ከሚሰሩ ግለሰቦች ጋር ያደረጉት ያልተገባ ግንኙነት እንዲሁም በቅዱስ ሲኖዶስ የተመደቡት አባት ሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ በቶሎ እንዲዘገዩ የተደረጉ አሻጥሮች ሁሉ ተደምሮ ቤተክርስቲያኒቱ እንድትታሸግ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ቤተክርስቲያናችን በከፍተኛ ሃዘን ትገነዘባለች።

በመሆኑም ምእመናን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተርክስቲያን ላይ የሆነው ሁሉ አሳዛኝ ቢሆንም፣ ወደ ቤተክርስቲያን ላይ የተወረወረውን ድንጋይ መልሰን ለቤተክርስቲያን የሚጠቅም ግንብ የምንሰራበት እንጂ የምንተክዝበት ስላልሆነ እና ችግሮችን ወደ መልካም እድል በመጠቀም ምእመናን ከእዚህ በፊት ከነበራችሁ ትጋት በበለጠ ለቤተክርስቲያናችን  ማበብ በአዲስ መንፈስ የምንነሳበት መሆኑን አውቀን በእግዚአብሔር ቸርነት፣በእመቤታችን ኪዳነምሕረት አማላጅነት ለቤተክርስቲያናችን በአዲስ መንፈስ እና በጸና ልቦና እንድንነሳ ቅድስት ቤተክርስቲያን መልዕክቷን ታስተላልፋለች።''

ከላይ ከቤተክርስቲያኒቱ ፌስ ቡክ ገጽ ላይ ለመረዳት እንደሚቻለው ለቤተክርስቲያኒቱ መዘጋት ቀዳሚ ሚናውን የሚጫወቱት ጉዳያችን ከእዚህ በፊት ''የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አቴንስ ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን የሰሞኑ ከራሞት ልዩ ሪፖርታዥ'' ላይ እንደተብራራው የአማሳኙ ቡድን ከሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ባገኘው አረንጓዴ መብራት አማካይነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እንድትታሸግ ሆኗል።

የምእመናኑን እና የቤተክርስቲያኒቱን ችግር የሚፈታ የሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ያለህ!

በግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን ላይ የደረሰው እንግልት በቃላት ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም። ሀገረስብከቱ በቂ ክትትል አድርጎ ችግሩን የሚፈታለት ሊቀ ጳጳስ አላገኘም። እስካሁን ከተመደቡለት ሊቀጳጳሳት ውስጥ የመፍትሄ ሃሳብ በማመንጨት በቆዩበት አጭር ጊዜ የሞከሩት የጣልያን እና ፈረንሳይ እና አካባቢው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ሲሆኑ። አሁን መቀመጫቸውን በስዊድን ያደረጉት እና የግሪክም ሊቀጳጳስ የሆኑት አቡነ ኤልያስ ላለፉት አስር ዓመታት ውስጥ ዛሬ የታሸገችውን የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን የጎበኙት ባለፈው ዓመት አስታራቂ አባቶች ወደ አቴንስ ሲመጡ እና በቅርቡ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ትዕዛዝ እና ደብዳቤ ምክንያት በማድረግ ወደ አቴንስ ካደረጉት ያልተሳካ ጉዞ ውጪ ቤተክርስቲያኒቱን ከአስር ዓመታት በላይ ቀድሰውባት አያውቁም።

ጉዳያችን ከወር በፊት ይህንኑ አስመልክታ በጻፈችው ላይ እንዲህ ብላ ነበር፡

"እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።" (የሐዋርያት ሥራ 20:28) የሚለው ቃል ዛሬ በግሪክ በሚኖሩ ምእመናን ጆሮ ላይ የሚጮህ ድምፅ ነው። በግሪክ ምእመናን ለዓመታት አልቅሰዋል፣ገንዘባቸውን አውጥተው የገዙትን ገዳም ገዳም አድርጎ የሚባርክላቸው አባት አጥተው ተንከራተዋል፣ ለቤተክርስቲያን ያወጡት ገንዘብ በሌቦች ተወስዶ ከሌባ ጋር ሲተናነቁ ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በተጻፈ ደብዳቤ ለሰረቁት የእውቅና ደብዳቤ እየተሰጠ ባለፈው ዓመት ምእመኑን ሲያገለግሉ የኖሩት ካሕናት ስልጣነ ክሕነታቸው ''ከምእመን ያለፈ ስልጣን የሌለው ግለሰብ በጻፈልኝ ደብዳቤ መሰረት'' በሚል ለመያዝ ማስፈራርያ ተጽፏል። ቤተክርስቲያኒቱ ከግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር ጋር የሚኖራት ግንኙነት በድብቅ እና የአማሹ ቡድን በሚሰሩት ደባ የታጀለ በመሆኑ በአሁኑ ጊዜ የቤተክርስቲያኒቱ ክብር በግሪክ ቢሮዎች ውስጥ ዝቅ ያለ እንዲሆን የራሱን አስተዋጽኦ አድርጓል። ሌላው ቀርቶ አሁን በፖሊጎኖ የምትገኘው የኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን ከባለቤቷ የግሪክ ቤተክርስቲያን ጋር ያለው ግንኙነት ቤተክርስቲያኒቱን ለአማሹ ቡድን ለመስጠት በሚደረገው አድሏዊ ሕገወጥ ግንኙነት ምክንያት የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ክብር ዝቅ የሚያደርግ ግንኙነት በመደረጉ ከፍተኛ ቅሬታ እንዲፈጠር ሆኗል።በእዚህም ሳብያ የግሪክ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪም በጉዳዩ ተማረው ቅሬታ አቅርበዋል።''

መፍትሔው 

በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ችግር ለመፍታት ከቡድናዊ ስሜት የራቀ፣ለሌቦች እና ለዘራፊዎች ምንም ዓይነት መለሳለስ የማያሳይ፣ምእመናንን በፍቅር እና በትኅትና የሚያይ እና ከፍተኛ የቤተክርስቲያን አስተዳደር አቅምና ልምድ ያለው ሊቀጳጳስ በፍጥነት ለግሪክ ቅዱስ ሲኖዶስ ሊመድብ ይገባል። አሁን ያሉት ሊቀጳጳስ አቡነ ኤልያስ ከ90 ዓመታት በላይ የሆኑ እና በቤተክርስቲያን ዝርፍያ በሚታወቁ አማሾች ጋር በመወገናቸው የቤተክርስቲያኒቱን ችግር የማይፈቱበት ደረጃ ደርሰዋል። ላለፉት አምስት ዓመታት ያልፈቱት ችግር ከአሁን በኋላ ይፈቱታል ተብሎ አይታሰብም። አቡነ ኤልያስ የቤተክርስቲያን አጥፊዎች ጋር የገጠሙበት እና ሕጋዊ የሚመስል ሽፋን ለመስጠት አንዴ ''የቅዱስ ሲኖዶስ አስፈጻሚ ኮሚቴ'' ሌላ ጊዜ ሦስተኛ ወገን ቅሬታ ያላቸው እያሉ የሄዱበት ሂደት ሁሉ የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ክብር በግሪክ ዝቅ ያደረገ ብቻ ሳይሆን የሀገራቱን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ሁሉ የሚያውክ ተግባር ከግሪክ የሃይማኖት ሚኒስቴር ቢሮ ጋር የነበራቸው የቅዱስ ሲኖዶስን ትዕዛዝ ያልጠበቀ የአስተዳዳሪ ምደባ ሁሉ የታየ እጅግ አሳዛኝ ጉዳይ ነው።

በመሆኑም ለግሪክ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ችግር ለመፍታት ቅዱስ ሲኖዶስ መፍትሄ ሰጪ ሊቀጳጳስ መመደብ እና በቅዱስ ሲኖዶስ የተመደቡት ሊቀስልጣናት አባ ኪሮስ ጸጋዬ ወደ ግሪክ እንዲመጡ በቅዱስ ሲኖዶስ ከፍተኛ ግፊት ማድረግ የሚሉት ቀዳሚ ናቸው።ይህ ውሳኔ የርክበ ካሕናት ጉባዔ በፊት በአስቸኳይ እና በጊዜያዊነት መወሰን የቅዱስ ሲኖዶስ አፋጣኝ ተግባር መሆን አለበት። ምእመኑም የጠየቀው ይሄው ነው።
=============////========





Monday, April 20, 2026

በጠ/ሚ/ዐቢይና ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ላይ በውሸት ወሬ የዘመቱት ''አፈ-ጊንጦች'' በቴዲ አፍሮ ዘፈን ሊሸሸጉ ሲሞክሩ የኢትዮጵያ ሕዝብ እየሳቀባቸው ነው።

ጠ/ሚ/ዐቢይ አሕመድ እና ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በታላቁ የዓባይ ግድብ ምርቃት ቀን።

========
ጉዳያችን ምጥን
========

አፈ ጊንጥነቱ እና የውርደት ካባው

''አፈ ጊንጥነት'' የሚለውን ቃል ለነገር ሰሪዎች እንዲመጥን አድርገው በልካቸው የገለጡት ኢትዮጵያዊው ሎሬንት ጸጋዬ ገብረመድሕን መሆናቸውን ከሰሞኑ አንድ ኢትዮጵያዊ የፍልስፍና ምሑር ሲናገሩ ሰምቼ በጣም ሲገርመኝ ነበር። ኢትዮጵያን ኢትዮጵያዊነትን ለማጎስቆል የሚፈልጉ ሁሉ የለመዱት እና የሚሰነዝሩት ያላቸውን አፈ ጊንጥነት ነው።ኢትዮጵያን ያሉ የቀድሙ የኢትዮጵያ መሪዎች የቀደሙት ባንዳዎች እና ባዳዎች በአፈ ጊንጥነት ሊነድፏቸው ሞክረዋል።ሆኖም ግን ታሪክ እውነትን ያነጥራልና ከኢትዮጵያ ታሪክ ሊፍቋቸው አልቻሉም። በዘመናቸው ግን ለኢትዮጵያ የበለጠ እንዳይሰሩ እንቅፋት አልሆኑም ማለት አይደለም። አፈ ጊንጦች በየዘመኑ ነበሩ። ዛሬም አሉ።

በዘመናችን በኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑት ላይ የተለያየ የሃሰት ስሞችን እየለጠፈ ኢትዮጵያን ወደ የበለጠ መከራ መክተት ዓላማው ያደረገው ቡድን በመጀመርያ የአፈ ጊንጥነት ካራውን በማኅበራዊ ሚድያ፣ በመቀጠል ወደ የኢትዮጵያ ማኅበራዊ ዕሴቶች ውስጥ ማለትም ከኃይማኖት ተቋማት እስከ ዕድር እና የተለያዩ ማኅበራዊ አደረጃጀቶች ውስጥ እየገባ ለኢትዮጵያ በጎ ያሰቡትን ሁሉ ሲነድፍ፣ሕዝብ በማያባራ የጦርነት ቋያ እንዲገባ ሲያደርግ፣ቡድኑ ግን እራሱን በዲያስፖራ እና ሀገርቤትም በስውር እራሱን ደብቆ ሀገርና ህዝብ ሲያምስ ከረመ። ይህ የማተራመስ ካራው ግን ቀስ በቀስ እየተነቃበት ሲመጣ የውርደት ካባውን ከፍና ዝቅ እያደረገ የሚሸሸግበት ጥግ ሲፈልግ ከረመ።የሚሸሸግበት ሲያፈላልግ ምቹ ሆኖ ያገኘው ደግሞ ስመ ጥሩ የሆኑ የኢትዮጵያ የኪነጥበብ ሰዎችን ነው። ከእዚህ ውስጥ በሰሞኑ አዲስ ዜማ ይዞ ብቅ ያለውን ቲዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) ላይ ለመንጠላጠል ያለው መጋጋጥ አስገራሚ ብቻ ሳይሆን አስቂኝ ሆኗል።

በዘመናችን በአፈ ጊንጦች ኢትዮጵያዊ አጀንዳቸውን ለማጣጣል ዘመቻ ከተከፈተባቸው ውስጥ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና የማኅበራዊ ጉዳይ አማካሪ ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ይገኙበታል።


የአፈ ጊንጡ ቡድን ከላይ የተጠቀሱት ሁለት ኢትዮጵያውያን ላይ የነገር መርዞቹን ሲረጭ ከረምረም ብሏል።

አፈ ጊንጦች በጠ/ሚ/ዐቢይ ላይ የረጩት የሃሰት ወሬ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ላይ የተሰነዘሩት ሃሰተኛ የአፈ ጊንጦች ወሬ ውስጥ ፡
  • ''የብሔር እና የጎሳ ፖለቲካ አራማጅ ናቸው፣''
  • ''ከጀዋር የጽንፍ ሃሳብ ጋር አብረው ይሄዳሉ፣''
  • ''ኢትዮጵያን መከፋፈል ይፈልጋሉ፣''
  • ''የእገሌ ጎሳ ጠላት ናቸው፣''
  • ''የእገሌ ጎሳ ወዳጅ ናቸው፣''
  • ''ባሕርዳር ላይ፣ወለጋ ላይ አዲስ አበባ ላይ የተገደለው ሁሉ በእሳቸው ነው፣''
  • ሰሞኑን በኢራን የተዘጋው የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ በእሳቸው ነው ለማለት ሩብጉዳይ የቀረው አሉባልታ ወዘተ በአፈ ጊንጦች ተነዛ።
ይህንን ሁሉ አሉባልታ ዛሬ ላይ ውሸት መሆኑ ታውቆ እውነታውን ጊዜ ፈታው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሕብረ ብሔራዊነትን፣ኢትዮጵያዊነትን እና አብሮነት መመርያቸው መሆኑን በሦስት መንገዶች አረጋገጡ። አንድ ሰው በሦስት ነገር አንድን ጉዳይ ካረጋገጠ ምንም ጥያቄ አይነሳበትም። 

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በሦስት መንገዶች የአፈ ጊንጦችን አሉባልታነት አረጋግጠዋል። እነርሱም፡ 

1/ በቃል በመናገር (በሁሉም ንግግሮቻቸው)፣ 
2/ በመጽሐፍ መልክ መደመር በሚል ተከታታይ ጽሑፎቻቸው እና 
3/በተግባር የኢትዮጵያን ልማት ለሁሉም አካባቢ በተቻለ እንዲዳረስ በማድረግ እና የጋራ የፖለቲካ ዐውድ ለመፍጠር በሚያደርጉት ተግባር እና መጪ ዕቅዶች ሁሉ የአፈ ጊንጦች ወሬ ውሸት መሆኑን አረጋግጠዋል።

ይህ እውነት የማይዋጥለት ካለ እራሱን በመዳፉ ሸፍኖ የገዛ ሕሊናውን ለማታለል የሚሞክር ሰው ይመስላል።

በሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት  ላይ የተሰነዘሩ የአፈ ጊንጦች ወሬዎች

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ እና በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ጥልቅ ምርምር በማድረግ የሚታወቀውን ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት ላይ ሆን ተብለው የተነሱ የአፈ ጊንጦች ወሬዎች ውስጥ ሦስቱን የውሸት ወሬዎች በናሙናነት እዚህ ላይ እጠቅሳለሁ። 

1) ውሸት አንድ ፡ ዳንኤል ክብረት ''የትግራይ ሕዝብ መጥፋት አለበት'' አለ የሚለው የውሸት ትረካ 

ይህች የውሸት ትረካ የተጀመረችው ሕወሃት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ጦርነት ባወጀበት እና የሀገር ህልውና ጦርነት በተጀመረበት በ2014 ዓም ላይ ነበር። በእዚህ ጊዜ ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት የሕወሃት ህልውና ለሃገር አደጋ መሆኑን እና የድርጅቱ እና በታኝ አስተሳሰብ መኖር ስለማይጠቅም ከምድር ገጽ መጥፋት አለበት በሚል በአንድ የመከላከያ ሰራዊት ስብሰባ ላይ የገለጸውን አገላለጽ እነ አፈ ጊንጦች ገልብጠው ''የትግራይ ህዝብ ይጥፋ አለ'' በሚል ማውራት ጀመሩ። እውነታው ግን ለህወሃት እና በታኝ ሃሳቡ የተነገረ እንጂ ህዝብ ላይ ያነጣጠረ አልነበረም።ይህ ንግግር ዛሬም በድምፅ እና በጽሑፍ የሚገኝ ሆኖ ሳለ። አሁን ድረስ አውቀው ይህንኑ የሚያስተጋቡ አፈ ጊንጦች አሉ።

2) ውሸት ሁለት ፡ ዳንኤል ክብረት ለሀገር ታሪክ የሰራውን የጥንቱን ''ፋኖን '' እና የአማራን ሕዝብ አጥላላ የሚለው የውሸት ተረክ ነው።

ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በጻፋቸው መጽሐፎቹም ሆኑ ማብራርያዎቹ የኢትዮጵያ የነፃነት ዕሴት የሆነውን እና በተለይ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መግቢያ ላይም ሆነ ቀደም ባሉ ዘመናት ለኢትዮጵያ ኅልውና ዋስትና እና ማገር የሆነውን ''ፋኖ'' የተሰኘውን የኢትዮጵያን ነፃነት ያስከበረ ታሪካዊ አደረጃጀት አጣጥሎ አያውቅም።

የዳንኤል ክርክር በዘመናችን በአማራ ክልል የተነሳው ታጣቂ ፋኖ ሳይሆን ጃውሳ ነው። ሁለቱ በትርጉም ይለያያሉ ነው። 

ባጭሩ በዳንኤል አገላለጥ በአማራ ክልል ውስጥ ጥንት የኢትዮጵያን ነጻነት ያስጠበቀው በፋኖ ስም የሚነግደውና በአማራ ህዝብ ላይ አሁንም ድረስ በአንዳንድ ቦታዎች ህዝቡን የሚያውከውን ታጣቂ በፋኖ ስም የሚነግድ እንጂ የታሪካዊው ፋኖ ስም ይዞ መንቀሳቀስ የማይችል ነገር ግን የጃውሳ ስብስብ ነው በሚል ነበር ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በተለያዩ ጊዜዎች የገለጠው። አፈ ጊንጡ ቡድን ግን ዳንኤል ክብረት የአማራ ህዝብ ላይ የጥላቻ ንግግር የተናገረ በማስመሰል በሃሰት ያላለው እና ያልተናገረው የለም። ለሁሉም ጊዜ ይፈታዋል ነውና። በአሁኑ ጊዜ በአማራ ክልል ያለው የከተማ እና የገጠር ነዋሪ በጥንቱ ፋኖ እና በጃውሳ መካከል ያለው ልዩነት በሚገባ እንደገባው ወረድ ብሎ ህዝቡን መጠየቅ ነው።በሚልዮን የሚቆጠር የአማራ ክልል ወጣት ከትምሕርት ገበታ ለሁለት እና ለሦስት ዓመታት ያፈናቀለው፣ህዝቡን እያገተ የገንዘብ ምንጭ ያደረገው እና ዛሬም በሕዝቡ ስም እየነገደ ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር የሚሞዳሞደው ፋኖ ሳይሆን ጃውሳ መሆኑን ለማወቅ ብዙ ምርምር አይጠይቀውም።

3) ውሸት ሦስት ፡ ዳንኤል ክብረት ''በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሀገር ቤት ለምን ቅበሩን ይላሉ'' አለ በሚል የተነገረው የሃሰት ወሬ ነው።

እዚህ ላይ ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በአንድ የምሁራን ስብሰባ ላይ በኢትዮጵያ ላይ የባንዳነት ተግባር የሚፈጽሙትን በተለየ ከጠቀሰ በኋላ እነኝህ ግለሰቦች በኋላ (ኢትዮጵያን ሲያቆስሉ ቆይተው) መልሰው ለምን ለቀብር ሲሆን ኢትዮጵያን ይፈልጓታል በሚል ''ለምን ቅበሩን ያላሉ?'' በሚል ያብራራውን ዲያስፖራው በኢትዮጵያ አይቀበር አለ እያለ የአፈ ጊንጡ ቡድን እየተቀባበለ ሲናገር ከረመ። ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል የተናገረው ምንድን ነው? ብሎ የማያደምጠው እና ገባ ብሎ የንግግሩን ጭብጥ መነሻ ሳይመለከት የሚያወራውም እየተቀባበለ ''ዲያስፖራው በሀገርቤት አይቀበር'' ዳንኤል አለ አሉ እያለ በየስታርባክስ እና ቡና ቤት ማውራት ጀመረ። ሆኖም ግን በዕለቱ ዳንኤል ሲናገር ከቀብር ጉዳይ በፊት ያነሳው እና ያወራው ኢትዮጵያን በውጭ ሆነው ስለሚይቆስሉ እና ስለከዷት የባንዳና የባዳ ጉዳይ እንጂ መላው የዲያስፖራ ማኅበረሰብን እንዳልወቀሰ ግልጽ ነው። ዛሬም ድረስ እውነቱን እያወቁ ባላቸው የፖለቲካ ልዩነት እና ተራ ጥላቻ ከዚያም ሲያልፍ ላደሩበት የባንዳ ቡድን አስፈጻሚነት ሲሉ ብቻ ያልተነገረውን እንደተባለ ሲያወሩ የምንሰማቸው እነኝሁ አፈ ጊንጦች ናቸው።

ለማጠቃለል አፈ ጊንጦች የኢትዮጵያ የታሪክ አተላዎች ናቸው።የቀደሙ የኢትዮጵያ መሪዎችን በውሸት ነድፈዋል፣ለኢትዮጵያ የቆሙላት ሊቃውንቷን በወሬ ለመውጋት ሞክረዋል።አንዳንዶቹን ከመንገዳቸው አሰናክለዋል፣የቀሩትን አሁንም ድረስ ህዝብ በሚገባ እንዳይዘክራቸውና ከጀመሩት ስራ እንዳይማር በውሸት ትርክት ጋርደውበታል። አፈ ጊንጦች በባንዳነት እና የባዕዳንንን ተልዕኮ ለማስፈጸም ላይና ታች ሲሉ የኖሩ እና ዛሬም የሚሞክሩ ናቸው። የ21ኛው ክ/ዘመን ትውልድ እንደቀደስሙት አይደለም። የመረጃ እና ነገሮችን የማመዛዘን ከፍ ሲልም እውነትን የማንጠር ችግር የለበትም።ለእዚህም ነው።አፈ ጊንጦች የቱንም ያህል ቢጋጋጡ አይሳካላቸውም። ስላልተሳካላቸውም ነው መግቢያ መሸሸግያ ሲያጡና በውሸት ያወሩባቸው የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች በሥራ እየቀደሟቸው ህዝብና ሀገርን እያስደመሙ ሲያጡ በቴዲ ሙዚቃ ላይ ለመንጠልጠል የተውተረተሩት። እርሱም አልተሳካም። ምክንያት ቴዲ እራሱም አሳፈራቸው።ከኢትዮጵያዊነት ማማ ላይ አልወርድ አላቸው። እየሆነ ያለው ይሄው ነው።

=================///============







በግሪክ የምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጉዳይ ዛሬም ከምንጊዜውም በላይ የቅዱስ ሲኖዶስን የአፈጻጸም ጥብቅ ክትትል ትፈልጋለች።በሺህ የሚቆጠሩ ምእመናን ችግር ላይ ናቸው።

በጥንታውቷ ግሪክ ዋና ከተማ ከአቴንስ ወጣ ብሎ  ከስድስት ሺህ ካሬ በላይ ስፋት ያለው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስም የተገዛው ገዳም ============= ጉዳያችን ልዩ ሪፖርት ============= ኢት...