ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, January 15, 2025

የግሪክ አቴንሱ ''ኢትዮጵያዊው'' አውርቶ አዳሪው ''ዲያቆን'' እና ከጥንትም የኢትዮጵያ ጠላት የሆነው የ''አውርቶ አደር'' ማንነት



=============
የጉዳያችን ማስታወሻ
=============

ከጥንትም የኢትዮጵያ ጠላት የሆነው ''አውርቶ አደር'' ማንነት 

የኢትዮጵያ የታሪክ ስብራት ዋነኛዎቹ ምክንያቶች አውርቶ አደሮች ናቸው።ይህ አደር የሚለው የአማርኛችን ቃል ከፊት አንድ ቃል እያስከተለ ''አደር'' የሚለውን ቃል ብዙ ፍቺ ያሰጠዋል። ወቶአደር(ወታደር)፣ላብአደር፣ ሰርቶአደር፣ወዝአደር የሚሉትን ቃላት እናውቃቸዋለን። በስማቸው ያልጠራናቸው እና መጥራትም የሚገባን ''አውርቶአደር'' የሚባሉትን ነው።

ኢትዮጵያን ወደፊት ለማስፈንጠር የተጉቱ የቀደሙ የኢትዮጵያ ነገስታት፣ምሑራን፣ሃሳብ አመንጪ ዜጎችን ሁሉ አላሰራ ያለ አፉን በነጠላ ሸፍኖ አንዳች ፍሬ ነገር ሳይሰራ እያልጎመጎመ ሲያወራ ውሎ የሚያድረው አውርቶ አደር ነው። አፄ ቴዎድሮስ ከዘመናቸው ቀድመው የሚያስቡ መሪ ነበሩ።ሌላው ቀርቶ መጪው የሀገር መከላከያ በዘመናዊ መሳርያ ካልታገዘ ሃገር መጠበቅ አዳጋች መሆኑን ስላወቁ መድፍ እንዲሰራላቸው ትዕዛዝ ሲሰጡ፣አውርቶ አደር ያወራ ነበር።

ዳግማዊ ምንሊክ አውርቶ አደር ሳይሆኑ ሰርቶ አደር ነበሩ።ከዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እስከ የትራንስፖርት ስራ፣ከአካባቢ ጥበቃ እስከ ዘመናዊ ጦር ማደራጀት፣ከስልክ እና መኪና ማስመጣት እስከ አብያተክርስቲያናት ግንባታ ሰርቶ አደር ነበሩ። አውርቶ አደሩ ግን በዘመናቸው ሰላም የነሳቸው ጊዜ በቀላሉ የሚቆጠር አልነበረም። በእያንዳንዱ ስራቸው አውርቶ አደር እየገባ ለሀገራቸው የሚሰሩትን ለማደናቀፍ ሲያወራ ውሎ ሲያወራ ያድር ነበር። ዳግማዊ ምንሊክ መኪና አስመጥተው የመጀመርያው ነጂ ሲሆኑ፣ሊገዝቱ የቃጡ ነበሩ። ሲኒማ ቤት ከፍተው ለሕዝብ ሲያሳዩ አውርቶ አደር ''የሰይጣን ቤት'' ብሎ ሲያወራ ዋለ። መጪው የታያቸው ዳግማዊ ምንሊክና እቴጌ ጣይቱ የመጀመርያውን ዘመናዊ ሆቴል ጣይቱ ከፍተው ንጉሱና ንግስቲቱ እየገቡ ሰውን ለማለማመድ ሲሞክሩ አውርቶ አደሩ ሴት እንዴት ሆቴል ገብታ ትበላለች? እያለ ይሳለቅ ነበር። አውርቶ አደር በየዘመኑ ነበር። በዘመናችንም ጨምሮ።

አሁን ባለንበት ዘመን አውርቶ አደር እንደቀድሞው አፉን በኩታ ሸፍኖ የሚንሾካሾክ ወይንም ጠላና ጠጅ ቀኑን ሙሉ እየጠጣ ሲያወራ የሚውል አይደለም። የማኅበራዊ ሚድያ ላይ ተጥዶ ለኢትዮጵያም ለወገኑም አንድ ሳይሰራለት ብቻ ሳይሆን የሚሰሩትን ሲያብጠለጥል ሲሳለቅ የሚውል  በአውርቶ አደርነቱ ደግሞ ዩቱብና ሌሎች የማኅበራዊ ሚድያ ተቋማት ገንዘብ ስጡኝ እያለ ሲማጸን የሚኖር ነው።

የዘመናችን አውርቶ አደር ከተማ ጸዳ፣መብራት ተተከለ ሲባል ሰርቶ አደሩ በሰራው የሚነቅፍበትን ሲያስብ ያድራል። የአድዋ ሙዜም ሊሰራ ነው ሲባል፣ የምንሊክን ሃውልትን ሊነቅሉት ነው ይላል፣ ይሄው አውርቶ አደር።ሃውልቱም ደምቆ ያልነበረ ሙዜም ተሰርቶ ሲያልቅ ደግሞ ሙዜም ከሚሰራ ይልና ሌላ ትረካ ይጀምራል።አውርቶ አደር ስራው አውርቶ ማደር ብቻ ስለሆነ ማመስገን ብሎ ነገር አያውቅም። ሌላው ቀርቶ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ያልታደሰው የብሔራዊ ቤተመንግስ ሲታደስ፣ሸረሪት ያደራባቸው የሀገር ቅርሶች በወጉ ሲቀመጡ፣የሳይንስ ሙዜም ሲሰራ፣ግዙፍ ብሔራዊ መጻሕፍት ቤት ተሰርቶ ሲያልቅ፣የብሔራዊ መዛግብት መረጃ ማዕከል ሲሰራ፣የስቶክ ኤክስቸንጅ ማዕከል ስራ ሲጀምር፣የጎንደር አብያተ መንግስታት ታድሰው ከተማው ሲደምቅ ሳይቀር አውርቶ አደር አይኑን እያሸ ይመጣል። ያው እንደለመደው ለማውራት።

የዘመናችን አውርቶ አደሮች ምሳሌ እንጥቀስ ብንል እጅግ ብዙ ናቸው።ከአክቲቪስት ጀዋርን ብንወስድ አንዲት ጉድጓድ ውሃ ላላስቆፈረለት እና አንዲት ብርጭቆ ውሃ እንዲጠጣ ያላደረገውን የኦሮሞ ወንድሞቻችንን በአውርቶ አደርነት ነግዶ ጨርሶ አሁን በኢትዮጵያ ስም አውርቶ ለማደር እየሞከረ ነው። አውርቶ አደሮች እንዲህ ናቸው። ከአንዱ ጎራ ወደ ሌላ ለመዝለል ችግር የለባቸውም።በዩቱብ በአማራ ክልል ህዝብ የሚነግዱት አውርቶ አደሮች ለህዝቡ አንድ ቀን አንዲት ሳንቲም ልከው የአንድ ትምህርት ቤት መገልገያ የሚሆን አንዲት ቾክ አልላኩለትም። በስሙ አውርተው እያደሩ ግን በዩቱብ የልጆቻቸውን የትምሕርት ቤት ወጪ ይሸፍናሉ። የኢትዮጵያ ጉዳይ በሰርቶ አደሮች እና በአውርቶ አደሮች መሃል የሚደረግ ፍልምያ ነው። ህዝብ አውርቶ አደሮችን እየለየ ብቻ ሳይሆን እያራገፈ እና በስሜ አትነግዱ፣ከጫንቃዬ ውረዱ እያለ ነው።የኢትዮጵያ ሀገራዊም ሆነ ሃይማኖታዊ ችግር ፈጣሪዎች አውርቶ አዳሪዎች ናቸው።በእዚህ ዘመን ''አውርቶ አደሮች'' እና ''ሰርቶ አደሮች'' ተለይተዋል።

 የግሪክ አቴንሱ ''ኢትዮጵያዊው'' አውርቶ አዳሪው ''ዲያቆን'

ያልደረሰበትን ግጭት ሲተርክ የነበረ በቦታው ያለ ይመስላል።የዛሬ ዘጠኝ ዓመት የነበረ የቤተክርስቲያን ችግር ቪድዮ ለቃቅሞ በኪሱ ይዞ ይዞራል።አባቶችን ሲሳደብ የኢትዮጵያ ውሃ የጠጣ አዛውንት እና የሃይማኖት አባት ከሚከበርባት ምድር የመጣ አይመስልም።በቤተክርስቲያን ስም በከፈተው የማኅበራዊ ሚድያ አንድም ሃይማኖታዊ ነገር ሳይጽፍበት የጠላ ቤት ወሬ ብቻ ሳይሆን ፈጽመው ውሸት የሆኑ ጽሑፎች እየጻፈ፣ካህን ከካህን፣ምዕመን ከምዕመን ያጣላል። የአውርቶ አዳሪውን ''ዲያቆን''  ነገሩን የከፋ የሚያደርገው በቤተክርስቲያን መሃል ይዛሬ ዘጠኝ ዓመት የነበረ ጉዳይ እያነሳ ''ይሄኛው ቅዱስ፣ያኛው እርኩስ '' እያለ ህዝቡን ያለያያል።ሰዉ ጭቅጭቅ ሰልችቶት እርስ በርሱ እየተገናኘ ''ይሄ ሰው ግን ጤነኛ ነው?'' እያለ ያወራል። ይህ አውርቶ ማደር ለእርሱ የሙሉ ጊዜ ስራ አድርጎታል። ህዝቡ ደግሞ ሰርቶ አደር ነው።እንደእርሱ ሲያወራ አይውልም አያድርም። ለፍቶ ውሎ ሲገባ አውርቶ አደሩ የጻፈውን የውሸት ክምር የሚያይለት ይመስለዋል። ሰርቶ አደሩ ህዝብ ደግሞ የአውርቶ አደሩን ''ዲያቆን'' ነጭ ውሸት ከመሰልቸቱ የተነሳ ስለ አዕምሮው ጤንነት ተጠራጥሯል። 

አውርቶ አዳሪው ''ዲያቆን'' ሲያጥላላቸው የነበሩት እና በውሸት ህዝብ ሲያታልል የነበረባቸው ጉዳዮች አንድ በአንድ እየተተረተሩ እውነታቸው ሲሰጣበት፣ ሲያጥላላው የነበረውን ጉዳይ አብራሪ ሆኖ ብቅ ይልና ሊያብራር ሲሞክር ሰርቶ አዳሪውን በሳቅ እየገደለው ነው።ሰርቶ አዳሪው ህዝብ ጊዜ የለውም።ይሰራል።ሰርቶ ገዳም ገዝቶ ሀገሩን ያስጠራል።አውርቶ አዳሪው ''ዲያቆን'' ሰርቶ አደሩ ህዝብ ገንዘቡን አውጥቶ የገዛውን ገዳም ለማዘጋት ቁና ሙሉ ደብዳቤ በያዘው የቤተክርስቲያን ማኅተም እየጻፈ ይልክና በማኅበራዊ ሚድያው ላይ ብቅ ብሎ ገዳሙ ሊያዘጉት ነው ይልና ''እሪ!'' ይላላ። ይህ ብቻ አይደለም።ወደ ሃገርቤት ቤተ ክህነት ሳፋ ሙሉ ደብዳቤ እየጻፈ ሰርቶ አደሮቹ የቤተክርስቲያን ፈቃዳቸውን ንጠቁልኝ እያለ ይጮህና በማኀራዊ ሚድያ መጥቶ ወደ ስርዓት አልመጡም፣መጡ እያለ ያላዝናል።ይህ አውርቶ አደር ''ዲያቆን'' ህዝብ አውኳል።በውሸት አባቶችን ተሳድቧል፣ከጳጳሳት ጋር ለማጣላት ሆን ብሎ በማስረጃ ያሉ እኩይ ተግባራት ፈጽሟል። 

አውርቶ አደሩ ''ዲያቆን'' በቤተክርስቲያን የተነሱ ችግሮች እንዳይፈቱ፣ሰዎች እንዳይታረቁ ሌት ተቀን ይለፋል። ሀገረስብከት ከጳጳስ፣ጳጳስ ከካህን፣ካህን ከምዕመን ማጣላት እንደ ትልቅ ጥበብ ሲናገር እፍረት አይሰማውም። ለእዚህም በቂ ማስረጃዎች ተይዘውበታል።የመረጃ ማዛባት ላይ ሆን ብሎ እና ጉዳዬ ብሎ ሰርቶበት አሁን ከሽፎበታል። በእዚህ የማዛባት ስራው የቤተክርስቲያን ችግር እንዳይፈታ ሆን ብሎ እና አቅዶ ሰርቷል። ለምን? ምን ለማግኘት? ከእነማን ጋር አብሮ እየሰራ? የሚሉ ጥያቄዎች በቂ ምርመራ ይፈልጋሉ።እርሱ ኝ አድርጎታል።አሁንም አላቆመም።

የእዚህ ጽሑፍ አቅራቢ በህይወቱ አይደለም በድቁና ማዕረግ ያለ አንድ ቀን የሰርክ ጉባዔ የተማረ ምዕመን የእዚህን ያህል ''አካይስት'' መንገድ በራሱ ሀገር ህዝብ ላይ ሲፈጽምም ሆነ ቤተክርስቲያን ሰላም እንዳታገኝ ሲታትር ተመልክቶም ገጥሞትም አያውቅም።ይህንን ያህል የውሸት ክምር እየለጠፈ የሚዘልፋቸው አባቶች፣ምዕመናን እና ሰርተው የሚያድሩ በግሪክ ያሉ ኢትዮጵያውያን እጅግ ያዘኑበት ልክ ለመግለጽ ቃላት አይበቁም። እርሱ ግን ዛሬም በቤተክርስቲያኒቱ እየታከከ የመንደር የጠበበ አዎን የጠባባ ዓላማውን ለማራመድ በአውርቶ አደርነቱ ብቻ መቀጠልን ስራዬ ብሎታል።ስርቶ አደሩ ገዳም ገዝቶ ገና ለሌላ የበለጠ ስራ እየተጋ ነው። ቀድሞ አባቶቻችንን አላሰራ ያለው የአውርቶ አደር ውላጅ ግን ዛሬም ኢትዮጵያውያንን በአውርቶ አደር ሙያው ይሳደባል። በነገራችን ላይ ብዙ አውርቶ አደሮች የአዕምሮ ችግር የለባቸውም ብሎ ለመናገር አይቻልም።ማኅበራዊ ሚድያው ደግሞ አዕምሮ አይመረምርም። አውርቶ አደር የግድ የአዕምሮ ህክምና ለማግኘት ወደ ሃኪም ዘንድ ወይንም የስነ ልቦና ባለሙያ ማየት አለበት። አውርቶ አደር እንጀራው አይባረክም።ክፋቱ እራሱ ይበላዋል።ድቁናውን ግን መመርመር እና መልሶ ማዘግየት የሊቃነ ጳጳሳት ኃላፊነት ነው።እንጥፍጣፊ የእርቅ እና የክርስትና ሽታ የሌለው አውርቶ አደር እንዴት ''ዲያቆን'' ሆነ? የሁሉም ጥያቄ ነው።

=================////============

Friday, December 13, 2024

ኢትዮጵያ ከሞቃዲሾ ሱማልያ ጋር በአንካራ፣ቱርክ ያደረገችው ስምምነት በተመለከተ፡

በአንካራ የተደረገው የኢትዮጵያና የሱማልያ ስምምነት


  • የስምምነቱ ምንነት፣ 
  • ኢትዮጵያ የመዘዘቻቸው ካርዶች ከአስመራ እስከ ካይሮ የፈጠሩት ድንጋጤና ድንዛዜ፣
  • ኢትዮጵያ ያስከበረችው ጥቅሞቿ ምን ምንድን ናቸው? 
  • ስምምነቱ ካለፈው ይልቅ መጪውን የኢትዮጵያ አቅጣጫ ያመላክታል።
===========
ጉዳያችን ምጥን
===========

ኢትዮጵያ ከሞቃዲሾ ሱማልያ ጋር በአንካራ፣ቱርክ ያደረገችው ስምምነት ምንነት?

በያዝነው ሳምንት አጋማሽ ኢትዮጵያ እና ሱማልያ ያደረጉት ስምምነት የሚከተሉትን ነጥቦች ይዟል። እነርሱም፡
  • የኢትዮጵያ እና የሶማሊያ መሪዎች አንዳቸው የሌላኛቸውን ሉዓላዊነት፣ ነጻነት እና የግዛት አንድነት እንዲሁም በተባበሩት መንግሥታት እና በአፍሪካ ሕብረት ደንቦች ላይ የሰፈሩ ዓለም አቀፍ ሕጎችን ለማክበር ተስማምተዋል።
  • በወዳጅነት የመከባበር መንፈስ ያለፉ ልዩነቶችን እና አወዛጋቢ ጉዳዮችን ወደ ኋላ በመተው በትብብር ለጋራ ብልጽግና ወደፊት ለመሥራት ተስማምተዋል።
  • ሶማሊያ በአፍሪካ ሕብረት ተልዕኮ ስር ሆነው በአገሯ የተሰማሩትን የኢትዮጵያ ወታደሮች መስዋዕትነት ዕውቅና ትሰጣለች።
  • የሶማሊያን የግዛት አንድነት ባከበረ ሁኔታ ኢትዮጵያ አስተማማኝ የባሕር መተላላፊያ ማግኘቷ የሚኖረውን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታን ሁለቱ አገራት ዕውቅና ይሰጣሉ።
  • ሁለቱ አገራት በቱርክ አመቻቻነት በየካቲት ወር መጨረሻ ላይ የቴክኒካዊ ጉዳዮች ድርድር ማድረግ የሚጀምሩ ሲሆን፣ ይህም በአራት ወራት ውስጥ የሚቋጭ ይሆናል።
  • በሉዓላዊ የሶማሊያ መንግሥት ስር ኢትዮጵያ አስተማማኝ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ እና ዘላቂ የባሕር መተላላፊ እንድታገኝ የሚያስችል ለሁለቱም አገራት ጠቃሚ የሆኑ የኮንትራት፣ የኪራይ፣ እና ተመሳሳይ የንግድ አሠራር መንገዶችን በጋር በመሆን ለማጠናቀቅ ተስማምተዋል።
  • ሁለቱ አገራት የቱርክን ድጋፍ በመቀበል በስምምነቱ አተረጓጎም እና አተገባበር ጋር በተያያዘ የሚፈጠሩ ልዩነቶችን በቱርክ አማካይነት በንግግር እና በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ተስማምተዋል።
 ከካይሮ እስከ አስመራ ከአስመራ እስከ ሞቃዲሾ መሪዎቹን በድንጋጤ ያደነዘዙት ኢትዮጵያ የመዘዘቻቸው ካርዶች 
  • የኢትዮጵያ ፍላጎት ከሱማልያ አንጻር ግልጽ ነው።
    • ሱማልያ የኢትዮጵያ የጸጥታ ችግር እንዳትሆን፣
    • ሱማልያ የኢትዮጵያ ስልታዊም ሆነ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር እንዳታብር፣
    • የጋራ የምጣኔ ሃብት ትብብር እንዲኖር፣
    • ኢትዮጵያ ለሱማሌ ደህንነት በከፈለችው ዋጋ የሚመጥን ልክ ያለው ብሔራዊ ጥቅሟን ማስከበር የሚሉት ይጠቀሳሉ።

  • ከእነኝህ ፍላጎቶች አንጻር ሱማልያ ሁሉንም በሚጻረር መልኩ ለማፈንገጥ ሙከራ ማድረግ የጀመረችው የአሁኑ የሱማልያ ፕሬዝዳንት ፕሬዝዳንት ሐሰን ሼክ ሞሐመድ ወደ ስልጣን ሲመጡ ነው። በፕሬዝዳንቱ ሲመት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ሞቃዲሾ ድረስ ሔደው መገኘታቸው ይታወሳል። ይህም ሆኖ ግን አዲሱ ፕሬዝዳንት ብዙ ለመዝለል ሙከራ እንደሚያደርጉ ቀድሞውንም ይጠረጠሩ ነበር።

  • ይህ መዝለል እየበዛ መጥቶ ፕሬዝዳንቱ መጀመርያ ኢትዮጵያን መጎብኘት ትተው አስመራ ሲሄዱ ኢትዮጵያ እየተከታተለች ነበር። አስመራ ሄደውም አቶ ኢሳያስ ያሰለጠኑላቸውን ወታደሮች ጎበኙ፣ ምሳ ተበላ፣ ቡና ጠጥተው ወደ ሞቃዲሾ አመሩ።
  • በእዚህ ሂደት መሃል የምስራቅ አፍሪካ የምጣኔ ሃብት ጥምረት ሃሳብ ቀደም ብሎ በቀደሙት የሱማልያ ፕሬዝዳንት በበጎ የተጤነውን ጉዳይ አዲስ ፕሬዝዳንት ቸል አሉት።

  •   በእዚህ መሃል ኢትዮጵያ በእጇ ላይ ያሉትን ካርዶች መዘዘች፣ ጫወታውን ጀመረችው። ይህንንም እኤአ ጥር 1፣2024 ኢትዮጵያ ከሱማልያ ላንድ ጋር የወደብ እና የባሕር ኃይል ጣብያ ለመትከል የመግባብያ ስምምነት ተፈራረመች። የመግባብያ ስምምነት ማለት ዝርዝር ስምምነት ይቀረዋል።ነገር ግን በመሰረተ ሃሳቡ ሁለቱ ሃገሮች ተስማሙ ማለት ነው። 

  • በእዚህ ስምምነት ላይ ከወደቡ ጉዳይ ይልቅ ሱማልያ ላንድ በሃገርነት የመውጣቷ ጉዳይ ሱማልያን አመሰ። ኢትዮጵያ ዝም ብላ ጉዳዩን ትከታተል ነበር።

  • የሱማልያው ፕሬዝዳንት ከአስመራ ካይሮ ተመላለሱ። አቶ ኢሳያስ ድግሷ እንዳማረላት ወይዘሮ ካይሮ መመላለሱን ተያያዙት።

  • ቀጥሎ የግብጹ መሪ አስመራ የአንድ ቀን ውሎ አድርገው ከሱማልያ እና ከኤርትራ ጋር የጋራ ስምመነት ተፈራረሙ።ሱማልያ በቀጣይ የአውሮፓውያን ዓመት የኢትዮጵያ ጦር በሰላም አስከባሪነት በግዛቴ አይቀጥልም ብላ የመግለጫ ጋጋታ አወጣች።ግብጽ የጦር መሳርያ ወደ ሱማልያ መላክ ጀመረች። ሽር ጉድ አበዛጭ

  • በእዚህ ጊዜም ኢትዮጵያ አላወራችም። ይልቁንም ሸምቀቆውን አጠበቀች። በመቀጠል ሁለት እርምጃዎች ወሰደች። እነርሱም የመጀመርያው የግብጽ አየር ኃይል መሳርያ የሚያቀብልባቸው የሱማልያ ዋና ዋና የአይሮፕላይ ማረፍያዎችን ተቆጣጠረች። በመቀጠል በመቶዎች የሚቆተሩ ዘመናዊ ታንኮች የያዘ ሰራዊት ካለፈው ወር ጀምሮ የበለጠ አስገባች።

  • የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በሱማሌ በኩል ያላቸው ቁርጠኝነት ኤርትራን እና ግብጽን ብቻ ሳይሆን እራሳቸው የሱማሊያ ፕሬዝዳንትም እጅ በአፍ እንዲያደርጉ አስገደደ። ኢትዮጵያ የግብጽ እንቅስቃሴ በቀጥታ ከኢትዮጵያ የመልስ ምት እንደሚገጥመው ብቻ ሳይሆን የግብጽ ጦር ምን ሊያደርግ መጣ? ስንት ዓመት ሙሉ ያልረዳን ሰራዊት ዛሬ ምን ሊያደርግ መጣ? የሚሉ የሱማሊያ የጎሳ አለቆች ቁጣ አስፈሪ ሆኖ መጣ።

  • የኢትዮጵያ ሰራዊት በሱማሊያ ህዝብ ዘንድ ያለውን ተወዳጅነት እሩቡን ማግኘት ያልቻለው የግብጽ ሰራዊት ግምት እና እወነት ምን ያህል እንደሚለያዩ ግልጽ ሆነለት። በተለይ የኢትዮጵያ ጦር በበለጠ ወደ ሱማልያ መግባቱን ተከትሎ አቶ ኢሳያስ እና አልሲሲ በስልክ ረጅም ሰዓት እየተቀመጡ ጉዳዩን ሲወቅጡት ቢውሉም አንዳችም ጠብ የሚል ውሳኔ መድረስ ብቻ ሳይሆን የበለጠ ፍርሃት ለቀቀባቸው።

  • ይህ በእንዲህ እያለ የሱማልያ ጁባ ግዛት ግጭት ተነሳ፣መላዋ ሱማልያ ወደ ሌላ ሶስት ሃገር ልትከፋፈል እንደምትችል እና የኢትዮጵያ ተጽዕኖ የቱን ያህል የሚነዝር እንደሆነ የሱማልያው ፕሬዝዳንት ቆይቶም ቢሆን ገባቸው። በኢትዮጵያ ወታደሮች የምትጠበቀው ሞቃዲሾ ሳትቀር መልሳ ታመሰች።

  • ይልቁንም በፈረንጆቹ ዓመት መጀመርያ የኢትዮጵያ ወታደሮች ከወጡ ሱማልያ ምን እንደምትሆን ለመተንበይ በራሱ አስፈሪ ሆነ።

  • ኢትዮጵያ የመዘዘቻቸው ካርዶች አንድ በአንድ ከአስመራ እስከ ካይሮ፣ከካይሮ እስከ ሞቃዲሾ የዘለለውን ሁሉ ጸጥ አደረገው።

  • ሌላው ቀርቶ በሱማልያ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የጀመረችው ቱርክ ካለ ኢትዮጵያ የሱማልያ ጸጥታ የትም እንደማይደርስ የበለጠ ግልጽ ሆነላት።

  • ከእዚህ በተጨማሪ የግብጽ በአፍሪካ ቀንድ ሽር ጉድ ማለት በሊብያ ግብጽን እንዳሳፈረቻት በሱማልያም ማሳፈር እንዳለባቸው የቱርኩ ፕሬዝዳንት ዛቱ።ከሁሉም በላይ የኤርትራ ከግብጽ ጋር ያላት ትስስር ቆይቶም ቢሆን በቀይባርሕር ላይ ቱርክ ያላትን ጥቅም እንደማያስከብር ብቻ ሳይሆን አደጋ መሆኑ ገባቸው። በመቀጠል ኢትዮጵያና ሱማልያን አስማሙ።

  • የኢትዮጵያና የሱማልያ በአንካራ መስምማታን ተከትሎ ካይሮ እና አስመራ ከባድ ድንጋጤ ላይ ወደቁ። ድንጋጤው ይህ ጽሑፍ እየተጻፈም ገና አልለቀቃቸውም።

  • ኢትዮጵያን እንደከዷት የእኛዎቹ ዩቱበሮች በሱማልያ መንግስት ውስጥ ያሉ የኤርትራና የግብጽ አሽቃባጮችም ድንጋጤው አደነዘዛቸው ብቻ ሳይሆን የሱማልያውን ፕሬዝዳንት በሀገር ከሃጂነት ለመፈረጅም ቃ|ጣቸው።
ኢትዮጵያ ያስከበረችው ጥቅሞቿ ምን ምንድን ናቸው?
  1. ኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት ጥያቄዋ የቱን ያህል እርቀት እንደሚሄድ ዓለምን አሳምናለች። ሌላው ቀርቶ የሱማልያ ላንድን በሃገር የማወቅ ያህል እርቀት እንደምትሄድ አሳይታበታለች። 
  2. በባሕር በር ጥያቄ ጉዳይ ኢትዮጵያን አያስፈልግሽም የሚል አንድም ሃገር የመናገር ድፍረት አጥቷል።
  3. ኢትዮጵያ ለሱማሌ ላንድ የምትከፍለው መስዋዕትነት የቱን ያህል እንደሆነ አሳይታበታለች። ከአሁን በኋላ ሌላ ሃገር ቀድሞ የሱማልያ ላንድ እውቅና ቢሰጥም የኢትዮጵያና የሱማሌ ላንድ ግንኙነት  በማይበጠስ አንድነት ገምዳዋለች።
  4. የባሕር በር ለኢትዮጵያ ሳይሰጡ በሰላም አድሮ መዋል እንደማይቻል ግልጽ መልዕክት አስተላልፋለች።ይህ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የሀገራቱም ህልውና የሚወሰነው በኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት እና አለማግኘት መሆኑ ለሁሉም የጎረቤት ሃገሮች ግልጽ መልዕክት አስተላልፏል።
  5. ለሱማልያ አሁን የሱማልያ ላንድ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን የጁባ ሱማልያ ጉዳይም የኢትዮጵያን ሕክምና እንደሚፈልግ የሱማልያ ፕሬዝዳንት ዘግይቶም ቢሆን እንዲገባቸው አድርጋለች።
  6. ኢትዮጵያ የሱማልያ ላንድ የወደብ ስምምነት ብቻ ሳይሆን ከዋናዋ ሱማልያም የወደብ አገልግሎት እንደምታገኝ በሰሞኑ ስምምነቷ አረጋግጣለች። 
  7. በእዚህ ስምምነት ኢትዮጵያ የግብጽ ተጽዕኖ በሱማልያ እንዳይቀጥል አጥልታበታለች። በመቀጠልም ኢትዮጵያ ጋር የስትራቴጂክ ግጭት የሌለባት ቱርክ በግብጽ እንዲቀየር መንገዱን አመቻችታለች። በእዚህም ኢትዮጵያ የተሻለ የጸጥታ ዋስትና አግኝታበታለች።
  8. በቀጣይ ኢትዮጵያ የወደብ ጉዳይ ከኪራይ እና ውል ሃሳብ ወጥታ ወደ ዘለቄታዊ የባሕር በር ታሪካዊ እና ሕጋዊ ጥያቄዋ እንድትሸጋገር ሁኔታዎችን አመቻችቶላታል።
ስምምነቱ ካለፈው ይልቅ መጪውን የኢትዮጵያ አቅጣጫ ያመላክታል።

የኢትዮጵያና የሱማልያ የሰሞኑ ስምምነት ከሁሉም በላይ በአፍሪካ ቀንድ እና የቀይባሕር አካባቢ ትኩረት ያደረጉ ኃያላን ሀገሮችም ካለኢትዮጵያ ተሳትፎ ዋስትና እንደማይኖረው ስላወቁ እና የአቶ ኢሳያስ ከኢራን ጋር ያላቸው ግንኙነት ብቻ ሳይሆን በምዕራቡ ላይ ያላቸው ጥላቻ እራሷን ግብጽ እንድትወዛገብ ብቻ ሳይሆን ከአቶ ኢሳያስ ጋር መወገን የሚያመጣባትን የወጪ ክምር እያሰበች በከባድ ትካዜ ላይ ጥሏታል። አቶ ኢሳያስም በእዚህ ሳምንት ከጎበኙት የቆዩትን አሰብን ጎብኝተው አካባቢው ደስ አላለኝም ብለው ወደ አስመራ ተመልሰዋል። በትግራይ ለአቶ ኢሳያስ ለማደር የሚታትረው የደብረጽዮን ቡድን በትግራይ ህዝብ ከበባ ውስጥ እንደገባ ገብቶታል። ምናልባት አንድ ቀን ማለዳ ደብረጽዮን አስመራ ሸሽተው ገቡ ሊባል ይችላል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ሳታገኝ ውላ ማደሯ ዋጋ እንደሚያስከፍል እንደ የሱማልያው ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስም የበለጠ የሚረዱበት ጊዜ ከምንጊዜውም በላይ የቀረበ ይመስላል።መጪው የኢትዮጵያ አቅጣጫም ከእዚህ የተለየ አይመስልም። ዓለምም የሚያስበው ይሄው ነው።

Thursday, November 14, 2024

Beynouna Village - Ethiopia (Video) ባለፈው ሳምንት የተመረቀው መተሃራ እምብርት ላይ የተገነባው አስደናቄው የበይኑና ሪዞርት መንደር (ቪድዮ)

ባለፈው ሳምንት የተመረቀው መተሐራ እምብርት ላይ የተገነባው አስደናቄው የበይኑና ሪዞርት መንደር (ቪድዮ)



Tuesday, October 8, 2024

የመጀመርያዋ የኢትዮጵያ ሴት ፕሬዝዳንት የነበሩት ክብርት አምባሳደር ሣህለወርቅ ዘውዴን በክብር አለመሸኘት የኢትዮጵያን ክብር ብቻ ሳይሆን ለሴት ልጅ ያለንን የክብር ልኬት የሚያሳይ ነው።

የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ሣህለወቅ ዘውዴ

  • ጉዳዩ የዲሞክራሲ ባሕላችን ያኋልዮሽ ጉዞ ቁልጭ አድርጎ ያሳያል።
  • የኢትዮጵያ ታዳጊ ሴትና ወንድ ልጆች የምናስተምራቸው ምንድን ነው?
  • የመጀመርያዋ ሴት ፕሬዝዳንት ሲሰናበቱ እንዴት ተሰናበቱ ብሎ ታሪክ ይመዝግብ?
  • ለጄነራል ጻድቃንን እና ጌታቸው ረዳ ሐብል ያጠለቀች ሀገር ለሣህለወርቅ ዘውዴ የማታጠልቅበት ምክንያት ሊኖር አይገባም።

======
ጉዳያችን
======

ኢትዮጵያ በወታደራዊው መንግስት ትመራበት ከነበረው የፕሬዝዳንታዊ የመንግስት ስሪት ወደ የጠቅላይ ሚኒስትር አመራር የመጣችው በዘመነ ህወሃት/ኢህአዴግ ዘመን ነው። በእዚሁ የጠቅላይ ሚንስትር አመራር ዘመን የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት የማንኛውም ፓርቲ አባል ያልሆነ እና በስራ እና የትምህርት ዝግጅት የተ|ሻሉ የተባሉት እና ባለው ስርዓት አዎንታዊ አመለካከት ያላቸው ፕሬዝዳንቶች ሲሰየሙ ቆይተዋል።
በዘመነ ኢህአዴግ ከተሰየሙት ፕሬዝዳንቶች በተለየ እና ለረጅም ጊዜ በዲፕሎማሲው ዓለም አንቱ የተባለ ልምድ ያላቸው እና የመጀመርያ ሴት ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ናቸው።

ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ በቆዩባቸው ያለፉት ስድስት ዓመታት ዘመናት ሴቶች ወደ አመራርነት የመምጣታቸው አስፈላጊነት እና ይህንንም ውጤታማ እንዲሁን የበኩላቸውን ጥረት አድርገዋል። በእዚህ ጉዳይ ላይ ከሃገር ውስጥ እስከዓለም አቀፍ መድረኮች በርካታ ስብሰባዎች ላይ ይህንኑ ጉዳይ አስተጋብተዋል። 

ያለፉት ስድስት ዓመታት ኢትዮጵያ ባሳለፈቻቸው የውስጥ ፈተናዎች ፕሬዝዳንቷ በመንግስት የስራ አስፈጻሚው የዕለት ተዕለት ስራ ውስጥ መግባት ህጉም ስለማይፈቅድላቸው በአንዳንድ መንግስታዊ የሀገር ውስጥ ውስኔዎች የራሳቸውን ሃሳብ ለማንጸባረቅ እና እንዲህ ቢሆን የሚሉ ሃሳቦች እንደነበሯቸው አልፎ አልፎ በሚናገሯቸው ንግግሮች ተንጸባርቀዋል። ይህም ሆኖ ግን ፕሬዝዳንቷ በኢትዮጵያን መውደድ፣አንዱን ወገን ከአንዱ ላለማስበለጥ እና ለሰላም የጸና እምነት እንዳላቸው ማንም ጥያቄ አያነሳም።

ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ባለፈው ቅዳሜ መስከረም 25፣2017 ዓም በትዊተር ገጻቸው ላይ የድምጻዊ መሐሙድ አሕመድ ''ዝምታ ነው መልሴ'' እና ''ለአንድ ዓመት ሞከርኩት'' የሚሉ ቃላት ያለው መልዕክት ከለጠፉ ጀምሮ መነጋገርያ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቷል።የሣህለወርቅ ዘውዴ ትዊተር ባሉበት ደረጃ ያሉ ችግሮችን በእዚህ መልክ መግለጽ አለባቸው ብዬ አላምንም። ለምሳሌ የማይስማሙበት ጉዳይ ሲኖር በስልጣን ዘመናቸው ውስጥ ሳሉ ስልጣን እለቃለሁ ማለት ይችላሉ።ወይንም ይህንን ያህል ከተጓዙ በኋላ የፓርላማ ስብሰባ ሊደርገ አንድ ቀን ሲቀረው በትዊተር ላይ ያለፉ ጉዳዮች ከሚያነሱ።አስተማሪ እንዲሆኑ ከፕሬዝዳንትነታቸው በኋላ በመጽሐፍ መልክ አልያም በሚድያ ቃለ መጠይቅ ያላቸውን ሃሳብ መግለጽ ይችሉ ነበር ብዬ አምናለሁ።ከእዚህ በተለየ ግን ክብርት ፕሬዝዳንቷ የመንግስት ስራ አስፈፃሚ የሚወስናቸው ውሳኔዎች እና የችግር አፈታት ላይ የተለየ አስተሳሰብ መያዛቸው ጤነኛ አስተሳሰብ ነው።መርሳት የሌለብን ክብርት ፕሬዝዳንቷ የብልፅግና አባል አይደሉም።ስለሆነም በአንድ ፓርቲ አስተሳሰብና ፕሮግራም አልታሰሩም። በኢትዮጵያ ሕገ መንግስትም ፕሬዝዳንት የሚሆነው ከፓርቲ አባልነት የተለየ ነው።
ክብርት ፕሬዝዳንቷ የግጭቶች አፈታት ላይ በጣም የለሰለሱ አካሄድ መከተል እንደሚገባ በተለያዩ ጊዜ ንግግሮቻቸው ገልፀዋል። ይህ የተለየ ሀሳባቸውን ለመግለፅ ቢፈልጉ የመንግስት ስራ አስፈፃሚ "እኛ ይህን የወሰንነው ብዙ ነገሮች አይተን ነው" ወዘተ በሚል አንዳንድ የመንግስት እና የፓርቲው የቡድን ውሳኔዎች ላይ አይግቡ ብሎ ይሆናል። ክብርት ፕሬዝዳንት ደግሞ የጉዳዮች አካሄዶች ሊያስጨንቋቸው ይችላሉ። እዚህ ላይ ክብርት ፕሬዝዳንቷን ለማንቋሸሽ ብልፅግና ያላዘዛችሁን ክጣርያ በላይ ለመጮኽ የምትሞክሩ ከካድሬ በላይ ካድሬ ለመሆን የምትጋጋጡ አደብ ብትገዙ።በሌላ ጫፍ ደግሞ ክብርት ፕሬዝዳንቷ ይህን አሉ እያላችሁ የዩቱብ ፕሮፓጋንዳችሁ የማረጋገጫ ማኅተም የተመታላችሁ ይመስል "እምቧ ከረዩ" የምትሉ እና የዘር የብልቃጥ መርዛችሁን ለመነስነስ የምትሞክሩ ብትሰክኑ ጥሩ ነው። ክብርት ፕሬዝዳንት የሀገር ሀብት ናቸው።ቢቆጡ፣ለምን ይህ አልሆነም ቢሉ በሀሳቡ ላይ መነጋገር እንጂ መነታረክ አያስፈልግም። ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ፣ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅን አክብረው ለማነጋገር፣ለሚሰማቸው ቅሬታና ጥያቄም በትሕትና ለማስረዳት የሞራልና የግብረ-ገብነት ችግር ያለባቸው አይደሉም። ስለሀገር ሲባል ብዙ ከተሳደበ ጌታቸው ረዳ ጋር ለማውራት ዐቢይ አልተቸገሩም። ክብርት ፕሬዝዳንት የተከበሩ ሰው ናቸው።የተለየ ሀሳብ ሊኖራቸው ይችላል። ሀሳቦቻቸውን ከፕሬዝዳንት ዘመናቸው በኋላም ማካፈላቸውን ሊቀጥሉ ይችላሉ።የሀሳብ ልዩነት ለዘላለም ይኑር!

ይህ በእንዲህ እያለ ሰኞ መስከረም 27/2017 በኢትዮጵያ ፓርላማ የተደረገው የአዲስ ፕሬዝዳንት ስየማ ላይ ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ የስንብት ንግግር ሲያድርጉ አለመታየታቸው ብቻ ሳይሆን መንግስታዊ የሆነ የምስጋና ቃላት ከአፈ ጉባዔውም ሆነ የፕሬዝዳንት ስየማውን አስመልክተው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ባስተላለፉት የትዊተር መልዕክት ላይ አልገልትጹም። ይህ በጣም አሳፋሪ አሰራር ነው። ይህ በኢትዮጵያ ልክ የታሰበ አስተሳሰብ አይደለም። ለጄነራል ጻድቃንን እና ጌታቸው ረዳ ሐብል ያጠለቀች ሀገር ለሣህለወርቅ ዘውዴ የማታጠልቅበት ምክንያት ሊኖር አይገባም። በትዊተር ላይ ያውም ያልተብራራ ነገር ተጻፈ ብሎ የሚያኮርፍ ኢትዮጵያን የተረከበ መንግስት ከረሜላውን እንደነጠቁት ህጻን ሲያኮርፍ ማየት ያሳፍራል። መንግስት ስንሆን እንቻል እንጂ፣ዲሞክራሲን ስናሽቀነጥር በእዚህ ልክ መከስከስ ዋጋ ያስከፍላል።አይደለም ፕሬዝዳንት ማንም ሃሳቡን ቢገልጽ ለምን በመንግስት ደረጃ የሃገር ሃላፊነት የወሰዱ በተራ ካድሬ ልክ ለማሰብ እንደሚሞክሩ አይገባኝም።

አሁንም ነገሮችን ማረም ይገባል።ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ በፓርላማ የስንብት ንግግር ቢናገሩ ምን የተለየ የሚያስፈራ ነገር ይናገራሉ? ቢበዛ ስለሰላም አስፈላጊነት፣ስለሙስና፣ስለ ዜጎች መፈናቀል ነው። ይህንን እርሳቸው ባይናገሩስ ጸሃይ የሞቀው ጉዳይ አይደለም ወይ? አሁንም ቢቻል ፓርላማው እንደገና ተሰብስብስቦ የመሰናበቻ ንግግር እንዲያደርጉ መፍቀድ።በመቀጠል ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሌ በብሔራዊ ቤተመንግስት ለቀድሞ ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ የክብር ሽኝት እንዲደረግ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይም እንደልጅ ዝቅ ብለው ሰላምታ ሲለዋወጡ ማየት እንፈልጋለን። የኢትዮጵያ ታዳጊ ሴትና ወንድ ልጆች የምናስተምራቸው ምንድን ነው? የመጀመርያዋ ሴት ፕሬዝዳንት ሲሰናበቱ እንዴት ተሰናበቱ ብሎ ታሪክ ይመዝግብ? ነገሮች ታርመው ፕሬዝዳንቷ በፓርላማ ንግግር ማድረጋቸው እራሱ የነገሮች የማረም ታሪክ ሆኖ ይጻፋል። ዛሬ ሣህለወርቅ በፓርላማ የስንብት ንግግር ባያደርጉ የሚሉት ነገር ካላቸው ከቤተመንግስት ሲወጡ ሁሉን ይሉታል። ያለነው በ21ኛው ክ/ዘመን ነው። አሁንም የምለው የመጀመርያዋ የኢትዮጵያ ሴት ፕሬዝዳንት የነበሩት ክብርት አምባሳደር ሣህለወርቅ ዘውዴን በክብር አለመሸኘት የኢትዮጵያን ክብር ብቻ ሳይሆን ለሴት ልጅ ያለንን የክብር ልኬት የሚያሳይ ነው።
==================/////===============







Monday, September 2, 2024

በኢትዮጵያ የእገታ ወንጀል ተሳታፊ አራት አካላት ናቸው። ለችግሩ የመፍትሄ አካላት ሁለት ናቸው።ሁለቱ አካላት ምን ይስሩ?


=======
ጉዳያችን
=======

በኢትዮጵያ ዜጎችን እያገቱ ገንዘብ የሚቀበሉ ወንጀለኞች ከተራ ወንጀለኝነት አልፎ በታጣቂ ቡድኖች የገንዘብ ማግኛነት መዋል ብቻ ሳይሆን ዜጎችን የማሸበርያ ፋሺሽታዊ ተግባር ሆኗል። እገታ የፖለቲካ መሸቀጫም ሆኗል።አጋቹም ያግትና መንግስትን ውቀሱ ይላል። አክቲቪስቱም አጋቹን መውቀስ ትቶ መንግስትን መውቀስ ስራዬ ተብሎ ተይዟል።እዚህ ላይ የሀገር ጸጥታ ማስከበር የመንግስት ኃላፊነት መሆኑ ይታወቃል። የእገታ ወንጀል የመሰለ የተለያዩ ባለሃብቶች እና የራሱ የመንግስት አንዳንድ የጸጥታ አካላት በተሳተፉበት ወንጀሎች አንጻር የህዝብ ተሳትፎ ከሌለ ባደጉት ሀገሮችም ጭምር አስቸጋሪ ነው።

የእገታ ወንጀል ተሳታፊ አካላት

የእገታ ወንጀል ተሳታፊ አካላት አራት ናቸው።እነርሱም፡ 
  • ሸኔ ብሎ ራሱን የሚጠራው ቡድን፡ 
ሸኔ ከሰሜን ሸዋ እስከ ወለጋ በርካታ ዜጎች አግቷል፣ህይወት አጥፍቷል።
  • ፋኖ ብሎ እራሱን የሚጠራው ቡድን፡
በአማራ ክልል ፋኖ ሰው አላገተም ብለው ለሚናገሩ። የፋኖ ዘመድ ናቸው የተባሉ ሳይታወቁ ሲታገቱ፣የፋኖ አባላት ደውለው ማስለቀቃቸው ያገቱት እነማን እና የት እንደሚገኙ ያውቃሉ ለሚለው አባባል ማረጋገጫ ነው።
  • ተራ ወንጀለኞች እና አንዳንድ ባለሃብቶች
በከተሞችም ሆነ በክልሎች የህገወጥ ታጣቂዎች መብዛት ወንጀለኞች ማገትን የገንዘብ ማግኛ መንገድ አድርገውታል።
  • አንዳንድ የመንግስት የጸጥታ አካላት
የእገታ ወንጀለኞች እኩይ ተግባር የሚሸፋፈነው እና የወንጀል ክትትሉ ደካማ እንዲሆን ያደረገው የአንዳንድ የመንግስት የጸጥታ አካላት የወንጀሉ እና ወንጀሉን ተከትሎ ከሚገኘው ገንዘብ ተካፋይ መሆን ነው።

ለችግሩ የመፍትሄ አካላት ሁለት ናቸው

ለችግሩ የመፍትሄ አካላት ህዝብ እና መንግስት ናቸው።

ሁለቱ አካላት ምን ይስሩ?

ሁለቱ አካላት ማለት ህዝብ እና መንግስት ምን ይስሩ? ለሚለው ጥያቄ።

ህዝብ
  • ህዝብ ከእድር እስከ እቁብ፣ከአብያተ ክርስቲያናት እስከ መስጂድ በጉዳዩ ላይ መድረክ ከፍቶ መወያየት አለበት፣
  • ህዝብ አካባቢው የሚጠረጥረውን ቤት፣መንደር እና ጉረኖ መፈተሽ ከእገታ ጋር የተያያዘ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የተነካኩ ሁሉ ማጋለጥና ወደ ህግ ማቅረብ ይህ ሁሉ ደግሞ በከፍተኛ ህዝባዊ ንቅናቄ መደገፍ አለበት።
  • ንቅናቄው ሁለት ዋና ዋና ተግባራት ሊኖሩት ይችላሉ።እነርሱም ፡
    • በእገታ ፈጻሚዎች እና በዙርያው በተሳተፉ ላይ ማኅበራዊ ቅጣት ማጥበቅ፣
    • ወንጀሉን የፈጸሙ በፎቶም ጭምር በአደባባይ ማጋለጥ፣ለህግ ማቅረብ እና የህግ ሂደቱን መከታተል።
መንግስት
  • በእገታ ወንጀል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የተሳተፉ ላይ የሞት ቅጣት የሚያሳልፍ ህግ ማውጣት፣
  • በመንግስት የጸጥታ አካላት ውስጥ ሆነው የወንጀሉ ተባባሪዎች ላይ ተመሳሳይ እስከ የሞት ቅጣት የሚያደርስ ቅጣት መወሰን።
  • የጸጥታ ጥበቃ ኃላፊነቱ ከህዝብ ጋር የተሰናሰነ እንዲሆን ማድረግ እና 
  • መገናኛ ብዙኃን በወንጀሉ ዙርያ የተሰሩ ስራዎች እና ወንጀለኞች ምንነታቸው እንዲገለጽ ማድረግ።
=================////==============


Friday, August 9, 2024

''ኢትዮጵያ ልታመልጥ ነው።'' የግብፅ፣የሱማልያ፣የቱርክና የአቶ ኢሳያስ ጭንቀት ጨምሯል። እውን ብልጽግና ''ኒዎ ሊበራሊዝምን'' ሳያላምጥ ውጧል?

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ታዬ አጽቀ ስላሴ በኢትዮጵያ የግብጽ አምባአደር መሐመድ ኦመር ጋድ ሰሞኑን በአዲስ አበባ ከተወያዩ በኋላ (ፎቶ ውጉሚ)


==========
ጉዳያችን ወቅታዊ
==========

የሀገራችንን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ በየቀኑ ብዙ የሚነሱ ጉዳዮች አሉ።በጥቃቅን እና ቅጥልጣይ ጉዳዮች ላይ ብቻ ካተኮርን ትልቁ ሀገራዊ ስዕል ይጠፋል ብዬ አስባለሁ። እንደ ሀገር ብዙ መቀረፍ ያሉብን እራሳችን የፈጠርናቸውም ባዕዳን ያቦኳቸውም ችግሮች አሉብን። ሙስና፣የጸጥታ ችግር፣ጎሰኝነትን ማቀንቀን እና ድህነት ወቅታዊ ችግሮች ሆነው በመሬት ላይ የሚታዩ ችግሮች ናቸው። ሁሉንም ግን በበጎ ህሊና፣በህብረት እና ጠንክሮ በመስራት የሚቀረፉ ለመሆናቸው ቅንጣት ያህል የሚያጠራጥር ጉዳይ የለም።

ከጥቃቅን እና ቅጥልጣይ ጉዳዮች ወጥተን ትልቁ ኢትዮጵያ እየሔደችበት ያለውን ጎዳና ስንመልከት እና ወደመንገድ የገባችበትን አገባብ ተመልክተው የተደናገጡትን የቅርብም የሩቅም ሀገሮች ስንመለከት ከፍተኛ መራወጥ ላይ መሆናቸውን እንመለከታለን። ይህ በእንዲህ እያለም በዶ/ር ዐቢይ የሚመራው መንግስት ከሰሞኑ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ጋር ተያይዞ ብልፅግና ''ኒዎ ሊበራሊዝምን '' ሳያላምጥ ዋጠ የሚል አዲስ ፕሮፓጋንዳ ተከፍቷል።በሁለቱም ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ትንሽ እንበል።

''ኢትዮጵያ ልታመልጥ ነው።''  የግብፅ፣የሱማልያና የአቶ ኢሳያስ ጭንቀት ጨምሯል።

ግብጽ በእስራኤል ፍልስጤም ጉዳይ ተወጥራ ከርማ አንድ ዓይኗን ኢትዮጵያ ላይ ጥላ ከርማለች።ቱርክ ወደ 15ኛው ክ/ዘመን የምስራቅ አፍሪካ የባሕር ጠረፍ መቆጣጠር የናፈቃት ትመስላለች። በዘመኑ ቱርክ ከምስራቅ አፍሪካ እስከ ዛንዚባር ያለውን የባሕር ጠረፍ የተቆጥጠረችበት ''ወርቃማ ዘመን'' የምትለው ጊዜን ለማምጣት ሱማልያን ሰፈር ለማድረግ እየሞከረች ነው።በሊያ ጉዳይ ባላንጣ የሆኑት ግብፅና ቱርክ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ለመምከር ግን አፍ ለአፍ ገጥመው ማውራት ከጀመሩ ሰንብተዋል። አሁን ዘግይቶ የተሰሙ ዘገባዎች ደግሞ ግብጽ በሱማልያ ጦሯን ለማስፈር ማሰቧ ብቻ ሳይሆን የሚሰፍረው ጦር ደግሞ በኢትዮጵያ ድንበር አጠገብ መሆኑ ነው የተሰማው።

በእዚህ ሁሉ መሃል ወጡ እንዳማረላት ወይዘሮ ከካይሮ እስከ ሞቃዲሾ ደብዳቤ በመጻጻፍ እና እራሳቸው ካይሮ ላይ ብቅ ጥልቅ ያበዙት አቶ ኢሳያስ ናቸው።አቶ ኢሳያስ ሠላሳ ሦስት ዓመታት ሙሉ ልማት ያላመጡላት ግን ወጣቶችን በውትድርና በማሰልጠን የተጠመዱት አቶ ኢሳያስ ግራ መጋባታቸው በግልጽ እየታየ ነው። አቶ ኢሳያስ አንዳንዴ ''ከመምህሩ ደቀመዝሙሩ'' እንዲሉ የግብፅ አማካሪ ብቻ ሳይሆን አልሲሲ ከሚያስቡት በላይ ገፊ ሀሳብ እያመጡ የቆስቋሽነት ሚና የሚጫወቱት ለግብጾች ኢትዮጵያን በሚገባ የሚያውቁ ''ኤክስፐርት'' ነኝ የሚል አቀራረባቸው ነው ሲሉ አንድ የምዕራብ ዲፕሎማት መናገራቸው ተሰምቷል። 

በሌላ በኩል አቶ ኢሳያስ ሎተሪ ያመለጣቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አስመራ ድረስ ሔደው ስለ ምጣኔ ሐብታዊ ትስስር በተለይ የአቶ ኢሳያስ መንግስት ወደ ኢትዮጵያ ምጣኔ ሐብት እንዲቀርብ እና በምላሹ የኢትዮጵያን ታሪካዊ እና ጂዮግራፊያዊ ወደብ በር እንዲከፍቱ ለቀረበላቸው ጥያቄ ያሳዩት ዘገምተኝነት ነው። በወቅቱ የነበረውን ስምምነት ተከትሎ ወደ አሰብ የሚወስደው መንገድ ዕድሳት መጀመሩን እና መፋጠኑን በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ሳይቀር ተመልክተን ነበር። ሆኖም ግን አቶ ኢሳያስ ወደነበሩበት የ ''ስኩዌር ዋን '' ጉዳይ ሲመለሱ ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ጉዳዩን ወደ አደባባይ አመጡት። በመቀጠልም 120 ሚልዮን ሕዝብ በ20 ኪሎሜትር የባሕር እርቀት ላይ ታፍኖ ቢኖር ማንም በሰላም ውሎ እንደማያድር ይህ ተፈጥሯዊ ጉዳይ እንጂ ብዙ ትንተና እንደማያስፈልገው በግልጽ ተናገሩ። ይህ ብቻ አይደለም። ኢትዮጵያ ከሱማሌ ላንድ ጋር የባሕር ወደብ ብቻ ሳይሆን የባሕር ኃይል ሰፈርም እንደሚኖራት እኤአ ጥር 1፣2024 ዓም አዲስ አበባ ላይ ይፋ ሆነ። 

''ኢትዮጵያ ልታመልጠን ነው '' የሚለው የግብፅ፣ቱርክ፣ሱማልያ እና የአቶ ኢሳያስ ጭንቀት የኢትዮጵያ በቀይባሕር በኩል የመከሰቷ ጉዳይ ቀዳሚ ቦታ ይዟል። ይህንን ጉዳይ ደግሞ ከእነኝህ ሀገሮች ውጭ ዓለም አቀፋዊው ነባራዊ ሁኔታ በግልጽ መግለጫ አያውጣ እንጂ የኢትዮጵያን በቀይባሕር የመከሰት ጉዳይ የተቃወመ የለም። ይልቁንም አቶ ኢሳያስ ከየመን ሁቲ አማጽያን ያላዳኑት የቀይባሕር ባለ 120 ሚልዮን ህዝብ ሀገር እና በምስራቅ አፍሪካ ግዙፍ ምጣኔ ሐብት ያላት ኢትዮጵያ የተሻለ የንግድ መስመሩን ልትጠብቅ እንደምትችል ዓለም ገብቶታል።

ይህ በእንዲህ እያለ ኢትዮጵያ የምስራቅ አፍሪካን ብቻ ሳይሆን የግብጽና የኤርትራን ጂኦፖለቲካ የመሳብ ሚና (Pulling role) ኢትዮጵያ በሁለት መንገዶች እየተጫወቸች መሆኑ በግብፅም ሆነ በኤርትራ ላይ ጥላውን አጥልቷል። ይህ ጥላ ደግሞ ኢትዮጵያ አመለጠችን በሚል ያዙኝ ልቀቁኝ አስከትሏል። የኢትዮጵያ የመሳብ ሚና በግብጽ አንጻር የተከሰተው በዓባይ ግድብ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቅ ተረጋግጧል።በአጭሩ የግብፅ የቧንቧ ውሃ መክፈቻና መዝግያ በኢትዮጵያ እጅ መገኘቱን ዓለም አቀፍ ኃይሎች ግልጽ ሆኖላቸዋል። ኢትዮጵያ ደጋግማ የአባይ ውሃን በጋራ ተጠቃሚነት ላይ እንደምታምን መግለጿ ይታወቃል።ይህም ሆኖ ግን የጂኦ ፖለቲካውን የመሳብ አቅሟ ከግብፅ አንጻር መቶ ከመቶ የተረጋገጠ መሆኑ ላይ የሚጠራጠር የለም።

በሌላ አንጻር የኢትዮጵያ በህንድውቅያኖስና የቀይባሕር አካፋይ አካባቢ በባሕር ኃይል ይዛ መከሰቷ በጂቡቲም ሆነ በኤርትራ በኩል ከመሬት ሌላ በባሕር ኃይል መገኘቷ የኤርትራን ጂኦ ፖለቲካ ላይ በቀጥታ ያጠላበታል። ይህ ጥላ ደግሞ ያድጋል። አድጎ የት እንደሚደርስ አሁን ለመናገር አይቻል ይሆናል። ነገ ግን ይቻላል።

ቱርክ በሌላ በኩል ሱማልያ ከረጅሙ የእርስበርስ ጦርነት እንዳገገመች በመጀመርያ ከኢትዮጵያ ቀጥላ የተገኘች ሀገር ነች። ቱርክ በሱማልያ ግዙፍ የአይሮፕላን መንደርደርያ፣መዝናኛ ሆቴል እና ሌሎች ስራዎች ላይ መሰማራት የጀመረችው ቀድማ ነው። በያዝነው ዓመት ኢትዮጵያ ከሱማልያ ላንድ ጋር የወደብ ስምምነት መፈራረሟን ተከትሎ ደግሞ የወታደራዊ ስምምነት ከሱማልያ ጋር ለመፈጸም አልዘገየችም። ቱርክ ሱማልያ ላይ ያላት ፍላጎት የተፈጥሮ ሃብት ዝርፍያ እና አካባቢያዊ ተጽኖ ፈጣሪ ሆኖ መከሰት ፍላጎቷ ነው።ይህም ሆኖ ቱርክ ግብጽ ወደ ሱማልያ እንድትመጣባት አትፈልግም። ግብጽና ቱርክ በሊብያ በነበረው ጦርነት በነከሩት እጅ መጠን መቆሳሰላቸው ቢታወቅም ኢትዮጵያን ለመክበብ እና የሱማልያን የተፈጥሮ ሃብት ለመዝረፍ ግን ለመስማማት ሲሞክሩ ይታያሉ።
ይህም ሆኖ ግን ቱርክ በኢትዮጵያ ያላት መዋዕለ ንዋይ እና ከኢትዮጵያ ጋር መጣላት በምስራቅ አፍሪካም ሆነ በአፍሪካ አንጻር ያለውን ወጪ ስላሰሉት በኢትዮጵያ እና በሱማልያ መካከል የሰላም ንግግር አንካራ ላይ ማስጀመራቸው እና ሰሞኑንም ሁለተኛውን ክፍል ንግግር ለማድረግ እየተዘጋጁ ነው። እዚህ ላይ ግን ግብፅ፣ቱርክ፣ሱማልያ እና አቶ ኢሳያስ የገባቸው ጉዳይ አንድ ነገር ነው። ኢትዮጵያ ልታመልጣቸው መሆኑ ገብቷቸዋል። ሊያስቆሟት ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም። ነገር ግን አልቻሉም። አሁን እየሞከሩት ያለው ከበባ ለመፈፀም ነው። ቱርክ እና ግብጽ በሱማልያ በኩል፣ አቶ ኢሳያስ በሰሜን በኩል ኢትዮጵያን ለመክበብ ይሞክራሉ። ኢትዮጵያ በቀይ ባሕር በኩል መከሰቷ የሚያማቸው እንግዲህ ከበባው የተሟላ የማያደርገው ይሄው የኢትዮጵያ በባህር በር በኩል መከሰት ነው።

እውን ብልጽግና ''ኒዎ ሊበራሊዝምን'' ሳያላምጥ ውጧል?

ሰሞኑን አንድ ወዳጄ ደወለልኝና የእርሱ አባባል ነው፣ስለ ቃሉ ይቅርታ እየጠየኩ ''አንድ እንቁራሪት የዋጠ የሚመስል ዩቱበር ያቀረበውን ዘገባ ሰማህ?'' አለኝ። ዘገባው አቶ መለስን የኒዎ ሊበራል ተከላካይ እና የሀገር ሉዓላዊነት ጠባቂ አድርጎ ያቀርብና ብልፅግና ''ኒዎ ሊበራሊዝም ሳያላምጥ የዋጠ'' በማለት ያቀርበዋል።

ዘገባውም ሆነ ዘጋቢው አፍቃሪ ህወሓትም ቢሆንም የሚነገረን ታሪክ ግን የጥንት ታሪክ ሳይሆን በሕይወታችን ያየነውን እና የምናውቀውን ጉዳይ ነው። አቶ መለስ ''ልማታዊ መንግስት '' በሚል በዓለም ንግድ ማዕከል የነገሩን እና ሀገር ውስጥ መሬት ላይ የሰሩትን ማስታወስ ነገሩን ግልጽ ያደርገዋል። እዚህ ላይ ኢትዮጵያ በወታደራዊው መንግስት ዘመን በነበራት ምጣኔ ሀብት ደረጃ አቶ መለስ አቆይተዋታል የሚል ክርክር እያነሳሁ አይደልም። በመኖር ብቻ የሚመጣም ዕድገት አለ። ነገር ግን ልማታዊ መንግስት ብለው ኢትዮጵያን በምጣኔ ሀብት መንገድ የገፏት ወዴት ነበር? ብሎ መጠየቅ ግን ተገቢ ነው።

አዎን! አቶ መለስ በዓለም ንግድ ኮንፍረንስ ላይ የግል ባንክ አናስገባም፣ ቴሌን አንሸጥም ብለዋል። ቀጥለው ግን ወደፊት ግን እናደርጋለን የሚል ጨምረውበታል። ወደ ፊት ያሉት በ2016 ዓም ነው ወይንስ በፊት አይታወቅም። እርሳቸውን ሞት ስለቀደማቸው። አቶ መለስ ግን ይህንን ካሉ በኋላ የኢትዮጵያን ምጣኔ ሀብት በአፍሪካ ግዙፍ ብለው አቦይ ስብሐት በጠሩት በትግራይ ልማት ማኅበር የኢትዮጵያን ምጣኔ ሀብት ጠፍረውት በዓለም መድረክ ግን ልማታዊ መንግስት ነን የሚል ንግግር ማሰማታቸውን የዘነጋን ካለን የማስታወስ ችግራችን እንጂ በዘመናችን ያየነው እውነት ነው። ይህ ብቻ አይደለም። ኢትዮጵያ በጎሳ በተደራጀ የምጣኔ ሀብት አደረጃጀት ተፈርዶባት፣ከዓለም አቀፍ አበዳሪዎች ብድር ወስዳ ጨርሳ ኮሜርሻል ብድር የገባች ሀገር ብቻ ሳትሆን፣ 'ግሎባል ፋይናንሻል እንተክግርቲ'' የተሰኘ አለምአቀፍ ድርጅት ባወጣው ሪፖርት ከ 2000  እስከ 2009 ዓም እኤአ   ብቻ ከኢትዮጵያ ከ 11.7(አስራአንድ ነጥብ ሰባት ቢልዮን ዶላር) ቢልዮን ዶላር በላይ በህገወጥ መንገድ መውጣቱን የገለጠው በአቶ መለስ የልማታዊ መንግስት ስም በተጀቦነ ፖሊሲ በክሉ መሆኑን ከረሳነው እናስታውሰው።

በዶ/ር ዐቢይ የሚመራው የብልፅግና መንግስት ''ኒዎ ሊበራሊዝምን '' ሳያላምጥ ውጧል? የሚለውን ጥያቄ የጠየኩት መጀመርያ ለራሴ ነው። ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአማካሪ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ጋር የሄዱበት መንገድ ''ኒዎ ሊበራሊዝምን '' ሳያላምጡ የዋጡ መሪ አያደርጋቸውም። ይህንን ለመረዳት በመጀመርያ ኒዎ ሊበራሊዝም ምንድን ነው? የሚለውን በመጠኑ ማሳየት ያስፈልጋል።

ከቀዝቃዛው ጦርነት ማክተም ጀምሮ የኒዎ ሊበራሊዝም ፖለቲካል-ኢኮኖሚ ፍልስፍና በአለማችን ላይ በምዕራቡ ዓለም ሰፍኖ የቆየ ብቻ ሳይሆን የምስራቁን የኮሚኒስት ዓለም መገዳደርያ ርዕዮተ ዓለም ሆኖ በአዲስ መልክ ተነቃቃ። አዲሱ ሊበራሊዝም (Neo-liberalism) እንደ ሰደድ እሳት በተለያዩ አህጉሮችና ሀገራት ውስጥ እንዲቀጣጠል ያደረገው በእንግሊዝ የጠቅላይ ሚኒስትር ታቸር ወደ ስልጣን መምጣት እና በአሜሪካ ደግሞ የሮናልድ ሬገን ዋይት ሃውስ መግባት ለኒዮ ሊበራሊዝም መስፋፋት ወርቃማ ዘመኑን አመጣ። ኒዎ ሊበራሊዝም መሰረታዊ ፍልስፍናው ምጣኔ ሀብቱን ለግል ባለሃብቱ በመልቀቅ መንግስት ያለውን ሚና በሂደት እየለቀቀ ይምጣ የሚል ሃሳብ ገዢው ሀሳብ ነው። 

ይህንን መሰረታዊ ሃሳብ በምጣኔ ሀብት ጠበብት የራሱ የሆነ መከራከርያ ነጥቦች ቢይቀርቡበትም በኢትዮጵያ ግን ከኒዎ ሊበራሊዝም አንጻር የአቶ መለስ እና የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን የምጣኔ ሀብት ፖሊሲ አፈጻጸም በትንሽ ብልጭታ አንስተን መሄዱ ብዙ ነገር ግልጽ ያደርጋል ብዬ አምናለሁ። የአቶ መለስ የምጣኔ ሀብት አፈጻጸም ግዙፉን የምጣኔ ሀብት ባለቤትነት ኤፈርት ተቆጣጥሮ የቀረውን የመንግስት ተቋማት ደግሞ አሁንም በጎሳዊነት ላይ የተመሰረተ አሿሿም ላይ የተመሰረተ አካሄድ ተከትለዋል። ለምሳሌ የሜቴክን እንቅስቃሴ ማስታወስ በቂ ነው። ሜቴክ የህወሃት የጦር ሹማምንት የግል ንብረት በመሰለ መልኩ በኢትዮጵያ ሃብት ሲመዘብር ምዝበራውም በጎሳ በተደራጁ ግለሰቦች ኪስ እንዲገባ ተደርጎ ኖሯል።

የአቶ መለስ ልማታዊ እየተባለ የተጠራው ፖሊሲ የመንግስትን ተቋማት አጠናክራለሁ ቢልም ቁልፍ የሆኑ የኢትዮጵያ የገንዘብ ተቋማት ከማዳከም አልፎ ለመዘጋት እሩብ ጉዳይ አድርሶት ለውጡ መጥቷል። ለእዚህ ማሳያ የሚሆነው በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና በኢትዮጵያ ልማት ባንክ ላይ የደረሰው ጥፋት ነው። የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በተለይ ከ5 ቢልዮን ብር በላይ ዕዳ የገባው በብሔር የተደራጁ ብድር በጋምቤላ ለታደሉት ጠፍ መሬት በመስጠት ነበር። ከኒዎ ሊበራል የራኩ ነኝ። ኒዎ ሊበራልን ሳላላምጥ አልውጥም አሉ የተባሉት አቶ መለስ በተቃራኒው የመንግስታዊ ቁልፍ ተቋማትን ግን በእዚህ ደረጃ ሲያጎሳቁሉ ተዉ ያለ የለም።

ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ የደከሙባትን ቁልፍ መንግስታዊ ተቋማት ያጠናከረችባቸው ዓመቶች ናቸው። በኪሳራ መንገድ ላይ ሲቆዝም የነበረው የልማት ባንክ ዛሬ ከኪሳራ ወጥቶ በርካታ የሀገሪቱን ማክሮ ፕሮጀክት ላይ መሳተፍ ጀምሯል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዋና መስርያቤቱን ከመጨረስ አልፎ የነበሩበትን የተበላሹ ብድሮች ከመቀነስ አልፎ አሁን መልሶ የመሪነቱን ሚና በሚገባ እየተጫወተ ነው። የኢትዮጵያ ቴሌ ኮምዩኒኬሽን ዛሬ ከግዙፍ የመንግስት ተቋማት አንዱ ከመሆን አልፎ የገንዘብ ማስተላለፍ ስራ አልፎ በሚሰጠው የኦንላይን ክሬድት ጨምሮ ከ70 ሚልዮን በላይ የኢትዮጵያን ሕዝብ ተደራሽ ያደረገው ባለፉት አምስት ዓመታት ነው። 

ለማጠቃለል የጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ መንግስት ባለፉት አምስት ዓመታት ያሳየን የምጣኔ ሀብት ፖሊሲ ጭልጥ ብሎ የኒዎ ሊበራል መንገድን የተከተለ ላለመሆኑ ማሳያው የመንግስት ሚና ከምጣኔ ሀብቱ ውስጥ መገለል አይደለም ዋና ተዋናይ መሆኑን የሚያምን መሆኑን ለማወቅ ባለፉት አምስት ዓመታት ትኩረት ሰጥቶ ያጠናከራቸው ቁልፍ የመንግስት የልማት ድርጅቶችን መመልከት ነው። ሌላው ቀርቶ በቅርቡ ከዓለም ባንክ እና አይ ኤም ኤፍ ጋር በነበረው የማክሮ ኢኮኖሚ አፈጻጸም ድርድር ላይ የመንግስትን ቁልፍ የምጣኔ ሀብት ተዋናይነት ለድርድር አለማቅረብ ብቻ ሳይሆን ዝቅተኛው የህብረተሰብ ክፍልን መደጎም የሚለውን ሀሳብ የዓለም ባንክ የማይደግፈው ሃሳብ ቢሆንም መንግስት ለድርድር ያላቀረበው ብቻ ሳይሆን መንግስት በመሪነት የሚፈጽመው መሆኑን ገልጾ የገባበት ስራ ነው። በኒዎ ሊበራል ሀሳብ መንግስት በፍጥነት ከሁሉም የምጣኔ ሀብት ሚና ይውጣ የሚለው አባባል ሳትቀበል መሄድ የሚከፈልበት ዋጋ አለ። መንግስት ''ኒዎ ሊበራልን '' ሳያላምጥ ዋጠው ከማለት፣ የመንግስት በምጣኔ ሃብት ዘርፍ የሚጫወተውን ሚና እያጎላ የግል ዘርፉን ለኢንቨስትመንት በሚያግዝ መልኩ ለምሳሌ የውጭ ምንዛሪ ተመን እጁን አነሳ የሚለው አገላለጥ የተሻለ ነው። በውጭ ምንዛሪ ተመን አንጻርም አሁንም የአንበሳው ድርሻ የሚይዘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በመሆኑ ተመኑ ላይ አሁንም መንግስት በሚፈልገው መንገድ የማጥላት ዕድሉ ከተወሰኑ ወራት በኋላ አይመጣም ማለት አይቻልም። ምክንያት አሁንም አብዛኛውን የውጭ ምንዛሪ በንግድም ሆነ በብድር እጁ የማስገባት የአንበሳው ድርሻ የመንግስት መሆኑ ከኢትዮጵያ አንጻር ቢያንስ በአሁኑ ሰዓት ግልጽ ነው። ባጭሩ መንግስት ''ኒዎሊበራሊዝምን '' ሳያላምጥ ሲውጥ ቢያንስ በገሃዱ ዓለም አላየንም።ዩቱብ ላይ ግን እንደመጣ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ማውራት ይቻል ይሆናል።
========================//////=============


 


የግሪክ አቴንሱ ''ኢትዮጵያዊው'' አውርቶ አዳሪው ''ዲያቆን'' እና ከጥንትም የኢትዮጵያ ጠላት የሆነው የ''አውርቶ አደር'' ማንነት

============= የጉዳያችን ማስታወሻ ============= ከጥንትም የኢትዮጵያ ጠላት የሆነው ''አውርቶ አደር'' ማንነት  የኢትዮጵያ የታሪክ ስብራት ዋነኛዎቹ ምክንያቶች አውርቶ አደሮች ናቸ...