ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, January 30, 2018

የትግራይ ሕዝብ ይህ አጋጣሚ ባያልፈው ይመረጣል።የአድዋዎችን የመገንጠል እና ትግራይን ከቀረው ሕዝብ የማጋጨት ሥራ በመቃወም የሚነሳበት ጊዜ አሁን ነው (የጉዳያችን ማስታወሻ)


  • ህወሓት አሁን ለእርድ ያቀረበው የትግራይን ሕዝብ ነው
  • ህወሓት በእጁ የቀረው የትግራይ ሕዝብ ስለሆነ ከእጁ እንዳያፈተልክበት ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ገብቷል።
ህወሓት ሙሉ የስልጣን ዘመኑን ያሳለፈው ሕዝብ ከህዝብ ሲያጋጭ ነው።የምናውቀውን ኦሮምኛ ተናጋሪውን ኦነግ፣አማርኛ ተናጋሪውን ግንቦት 7፣ሱማልኛ ተናጋሪውን የኦጋዴን ገንጣይ እና የአልሸባብ ተላላኪ እያለ በጅምላ ሕዝብ እየፈረጀ እርስ በርስ ስንፈራራ እንድንኖር አድርጎናል።ለስልጣኑ ሲል ለእርድ የማያቀርበው ሕዝብ በህወሓት ዘንድ የለም።ህወሓት አሁን ለእርድ ያቀረበው የትግራይን ሕዝብ ነው።
አንዳንዶች ህወሓት ከትግራይ ስለተነሳ ለትግራይ ሕዝብ የሚጨነቅ አድርገው የሚያስቡ አሉ።ህወሓት የትግራይን ሕዝብ የምፈልገው ለስልጣን መንጠላጠያ ብቻ ነው።

የተቀሩትን የኢትዮጵያ ክፍሎች ለማናከስ በተለይ በኦሮሞ እና አማራ መካከል ያለው ግጭት አልፈጠር ሲል ህወሓት በእጁ የቀረው የትግራይ ሕዝብ ስለሆነ እርሱ እንዳያፈተልክበት ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ገብቷል። ይህንንም ስላወቀ ሕዝቡን በስጋት ውስጥ ከትቶ የፋሺሽታዊ ስራው ሙሉ በሙሉ ተባባሪ እንዲሆን እና እንዳያፈነግጥ ወጥሮ ይዞታል። ለእዚህ ማስረጃው ህወሓት በመጀመርያ የትግራይን ሕዝብ ከጎንደር ሕዝብ ጋር አጣላው በመቀጠል ከወሎ ሕዝብ ጋር ግጭት እንዲፈጠር አደረገ። አንዳንዶች ይህ ተግባር ለትግራይ ታስቦ የተደረገ ቢመስላቸው መጃጃላቸውን ከመግለፅ ሌላ ምንም ማለት አይቻልም። ሕዝቡን የሚወድ ድርጅት በተቻለ መጠን የሚወደው ሕዝብ ከሌሎች ጋር እንዳይጣላ የቻለውን ሁሉ ያደርጋል እንጂ እንዴት ለወልቃይት ችግር ክላሽ እናቶች አሮጊቶችን እያስያዘ ያስዝታል? ሕዝቡን የሚወድ ድርጅት እንዴት በወልዲያ ጫወታ ላይ ቀድሞ ካረዎቹን ልኮ በአደባባይ እየተፉ የሚዝቱ ጠብ ጫሪዎች  እንደ መንገድ ጠራጊ ነቢይ ቀድሞ ልኮ እሳት ይለኩሳል? ሕዝቡን የሚወድ ድርጅት እንዴት ሕዝቡን እንደ ግል እቃው ቆጥሮ ስለመገንጠል ያዜምለታል።
ሎሚ ፅባ በሶፍያ አፅብሃ (በኢትዮጵያ አንድነት የሚያምነው የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊትን ግንባር ድረስ ሄደው በ1970ዎቹ እና 80ዎቹ ላይ ያነቃቃ የነበረው የሙዚቃ ሉዑክ )
አሁን የትግራይ ሕዝብ በአድዋ ስብስብ አማካይነት የደረሰበትን ፍጥጫ እና ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር የገባውን መቃቃር የሚያደበዝዝ መልካም አጋጣሚ ህወሃቶችን የመገንጠል አጀንዳ በማንሳታቸው ምክንያት አትወክሉንም ብሎ መነሳት ካለበት ወቅቱ አሁን ነው።ሕዝብ ለዘላለም ይኖራል ድርጅቶች ግን በእየዘመኑ ተለዋዋጭ ናቸው።የትግራይ ህዝብም መመልከት ያለበት ይህንን የው።አሁን ምንም አይነት ቅሌን ጨርቄን የሚያስብለው ጉዳይ የትግራይ ሕዝብ በህወሓት ላይ መነሳት እና ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር መስመሩን ማስተካከል የቀረበለት መልካም ዕድል ነው። እድሉን መጠቀም ብልህነት ነው።ህወሓት እኛን አይወክልም።መገንጠል የሚል አጀንዳ የትግራይ ሕዝብ አይደለም! የጥቂት ህወሃቶች እብደት ነው! ብሎ ድምፅን ማሰማት የብዙ በሽታ መፈወሻ ነው።


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Friday, January 26, 2018

ሳተናው

ጉዳያችን / Gudayachn
ጥር 19/2010 ዓም (ጃንዋሪ 27/2018)


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Tuesday, January 23, 2018

ለቤተ መንግሥቱም ሆነ ለቤተ ክህነቱ አልቅሱለት! ጥቁሩ ሰማይ እየመጣ ነው (የጉዳያችን ማስታወሻ)

በጽሁፉ መጨረሻ ላይ የቴዲ አፍሮ የባህር ዳር ኮንሰርት ቪድዮ ይገኛል።
ጉዳያችን /Gudayachn
ጥር 17፣2010 (ጃንዋሪ 24/ 2018 ዓም )

የኢትዮጵያ ፖለቲካ መዳረሻ ብዙዎቻችን እንደምንመኘው አለመሆኑ ግልጥ እየሆነ ነው።ብዙዎች የስርዓቱ አቀያየር የሰውም ሆነ የንብረት ጥፋት ከሁሉም በላይ ደግሞ የነበረውን ማኅበራዊ አንድነት በማይነካ መልክ ወይንም ጉዳቱ በቀነሰ መልክ ቢሆን የሚል ምኞት ነበራቸው።ህወሓት ግን በጥላቻ በተመረዘ ልቡ አስከሬን ከወለጋ እስከ ወልዲያ እያነጠፉ በመምጣት ብቻ ስልጣን ለማስጠበቅ ወስኗል።ሕዝብም የህልውና ጉዳይ ነው እና እራሱን ከመከላከል ከተሞቹን እና ገጠሩን ከህወሓት በዘር ጥላቻ ከተወጋ ሰራዊት ማፅዳት ብቸኛ መንገድ መሆኑን እያመነ የመጣበት ወቅት ነው።

በኢትዮጵያ የትኛውም መንግስታዊም ሆነ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ውስጥ የህወሓት የመንደር ልጅ መሆን እንደ መስፈርት እየተወሰደ ድርጅቶቹን መቆጣጠር ከተጀመረ ሁለት አስር ዓመቶች አልፈውታል።ይህም በመሆኑ ከአሁን በኃላ የሥርዓት አካሄዶች እና ስለ ኢትዮጵያ ሲባል የነበሩ ጨዋነቶች ሁሉ የመጨረሻ እንጥፍጣፊ ደረጃ ላይ ደርሷል።

"ህወሓት እና የትግራይ ሕዝብ አንድ ነው" የሚለው አባባል ቀድመው የነገሩን ደጋግመው በየመድረኩ ላይ የሚዘፍኑልን የህወሓት ሲቪል እና ወታደራዊ አመራሮች ናቸው።እነርሱ ያሉትን ሌላው ሕዝብ ካነሳው ደግሞ "ዘረኛ" ይባላል።እሺ! ህወሓት እና የትግራይ ሕዝብ አንድ አይደለም ሲባል ደግሞ ሕዝቡን ከድርጅቱ ለመለየት ነው የሚል ነጠላ ዜማ ይለቀቃል።እውነታው ግን በኢትዮጵያ የሰፈነው የህወሓት የአፓርታይድ (የዘረኘንት) ስርዓት ከመቼውም በላይ የፋሽሽት ባህሪውን እየተፋ ነው።በቅርቡ በመቀሌ የተደረጉ የህውሓት ስብሰባዎች በስልጣን ለመቆየት በጅምላ መፍጀት የሚል እንደሆነ ያፈተለኩ መረጃዎች እንደደረሷቸው የሚናገሩ የመብዛታቸውን ያህል ከእሬቻ እስከ ነቀምት፣ከአምቦ እስከ ወልዲያ በህወሓት የተፈፀሙት የጅምላ ፍጅቶች ቤተ መንግሥቱም ቤተ ክህነቱም እንደማይተርፉ እና ጥቁሩ ደመና እየመጣ መሆኑን አመላካች ነው።

 ለቤተ መንግሥቱም ሆነ ለቤተ ክህነቱም አልቅሱለት! 

ላለፉት ዓመታት ለተፈፀሙት ግድያዎች ሀዘኑን በቅጡ መግለጥ ያቃታቸው ቤተ መንግስት እና ቤተ ክህነት ጥቁሩ ሰማይ እየመጣ መሆኑን መረዳት አለባቸው።የቤተ መንግሥቱም ሆነ የቤተ ክህነቱ ችግር እንደ ሸረሪት ድር ያደራባቸው የህወሓት ጎሳዊ መዋቅር እንጂ በእራሳቸው ያመነጩት እኩይ ባህሪ እንደሌለ ግልጥ ነው። ቤተ መንግስቱ ውስጥ ከምዕራብ አፍሪካ የፕሮቴስታንት ነቢይ ነን የሚሉ ግለሰቦች እያስመጡ ያስባረቁበት አቶ ሃይለማርያም እና አባ ዱላ ስለ እውነት ሊናገሩ ቀርቶ እበላ ባይ አንደበታቸውን ስርዓቱን ለማቆየት የውሸት ክምር ሲከምሩ በሃይማኖት ስም የቆሙ የአጋንንት ልጆች መሆናቸውን ነው በአደባባይ ያስመሰከሩት።

በሌላ በኩል በቤተ ክህነቱ በኩል ከፓትርያሪክ እስከ አጥብያ አስተዳዳሪ ከህወሓት መወለድ ብቻ እንደመስፈርት ተቆጥሮ ለሺህ ዓመታት ሕዝብ ከመንግስት እየዳኘች፣የፍትህ ምንጭ ሆና መሪዎችን በስነ ምግባር ብቻ ሳይሆን በአስተዳደር ጥበብ ሁሉ ስታንፅ የኖረች የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ልጆቿ ታቦተ ሕጉን በጥምቀት በዓል አጅበው ሲወጡ በመትረጌስ ሲፈጁ ድርጊቱን መቃወም አይደለም የፍትሐት ጸሎት የማያደርጉ ፓትርያሪክ እየመሯት መሆናቸው የታሪክ ቁስል ነው።ቤተ ክህነቱ እንደ አየር መንገዱ ተርሚናል ፈታሾች የስራ ቋንቋ ትግርኛ እስኪመስል ድረስ ከአጥብያ አጥብያ እየዞሩ የቤተ ክርስቲያን ገንዘብ መተዳደሪያቸው የሆኑ ህወሐታውያን ተግባር አሁን ላይ የመረረ ምላሽ ከህዝብ ሊያገኝ ጫፍ ላይ ደርሷል። የሚነሳውን ማዕበል የታንክ እና የመትረጌስ ጋጋታ አያድነውም።ቁስሉ የተዘጠዘው ሕዝብ ምንም አይነት ምድራዊ ኃይል አይመልሰውም።ህወሓትም ሕዝብ የሚያታልልበት ቃላትም ሆነ ሃሳብ አልቀውበት ባዶ አዳራሽ የሚንገላወድ ሰካራም ሆኖ ከወዲያ ወዲህ መንቆራጠጥ ብቻ ስራው ሆኗል።

ጥቁሩ ዳመና እየመጣ ነው

አሁን ለቤተ መንግሥቱም ለቤተ ክህነቱም አልቅሱለት።ሁኔታው ያስፈራል።ማስፈራት ብቻ ሳይሆን በስሜት የሚወሰደው የህዝብ እርምጃ ታሪካችንንም እንዳያጠለሽ ማሰብ ያስፈልጋል።በማሰብ ብቻ ግን የሚያስቀረው አንዳችም ነገር ያለ አይመስልም።አንድ ቀን ጧት ወይንም ቀትር ላይ አልያም ምሽት ላይ ፍልጥ የያዙ እናቶች፣አባቶች፣ወጣቶች እና ሕፃናት ሳይቀሩ በድንገት ቤተ ክህነቱም ሆነ ቤተ መንግስቱ በር ላይ ይደርሳሉ። ያን ጊዜ የሚፈልጉትን ሰው ያውቃሉ።በቤተ ክርስቲያን ገንዘብ መተዳደሪያቸው አድርገው  ቅምጥል ኑሮ እየኖሩ በነፃ ደፋ ቀና የሚሉትን የቤተ ክርስቲያኗን አገልጋዮች የምያስለቅሱት የት ናቸው ብሎ ግቢውን ይወረዋል።ያን ቀን የጥቁሩ ደመና ቀን ተብሎ ይጠራል።በእዚህ ቀን ፈድራል ፖሊስ ሆነ ህወሃታዊነት አይድንም። ያን ጊዜ የአቶ መለስን ፎቶ ከአቡነ ሺኖዳ እና አቡነ ጳውሎስ ጋር  የሰቀልኩ  ባለ ውለታ እኔ ነኝ ብሎ ማሽቃበጥ የለም።ያን ጊዜ በጠቆረ ሰማይ ስር አመልጣለሁ ማለት የለም። ይህ ቀን ያስፈራል።ፍትህ ሳያገኙ ሕዝብ እጅ የሚወድቁ ሊኖሩ ይችላሉ።

በተመሳሳይ ቤተ መንግሥቱም እንዲህ እንዳስፈራ አይኖርም።ሴቷ ማማሰያ ወንዱ ፍልጡን ይዞ ከመርካቶ ከኮተቤ ከእንጦጦ  እና ከተቀረው ክፍል ሕዝብ ይተማል። ያን ጊዜ የምዕራብ አፍሪካ የፕሮቴስታንት ነቢይ ተብዬዎች አያስጥሉም ። ፍትህ በሕዝብ እጅ በመውደቅ ምቾት እንደተሰማት በግልፅ ታውጃለች። በእርግጥ አሁንም ያስፈራል።ሆኖም ግን ስላላወራነው ይቀራል ማለት አይቻልም።ህወሓት በወልዲያ፣በአምቦ፣በሐረር ፣በሕር ዳር እና በጎንደር  ያደረገው ግድያ እና የጅምላ ጭፍጨፋ ይዘው የሚመጡት ይህንኑ ነው።ያን ጊዜ ለቤተ መንግሥቱም ሆነ ለቤተ ክህነቱ ግፈኞች አልቅሱላቸው። እውነታውን ከአሁኑ አውቆ መስመሩን የሚያስተካክል ቢኖር በአለቀ ሰዓትም ቢሆን እራሱን ያወጣል።ፍልጥ ግን ለቤተ መንግሥቱም ቤተ ክህነቱም ያሰጋዋል።ከእዚህ በፊት በጉዳያችን ላይ የተባሉት ነገሮች የማይደርሱ ሕልም የሜመስሏቸው ብዙዎች ነበሩ።ዛሬ ላይ ሆነው ሲመለከቱት ግን አይወቅሱም።የቤተ መንግሥቱም ሆነ የቤተ ክህነቱ ፍልጥ በያዘ ሕዝብ መከበቡ እና መመንጠሩ የማይቀር የቅርብ ጊዜ ክስተት አይሆንም ለማለት አያስደፍርም።

አዲስ ላይ ተከልክሎ ባህር ዳር ላይ የተፈቀደው የቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) የባህር ዳር ኮንሰርት  
ማስታወሻ : -ከላይ የቀረበው ፅሁፍ ከቴዲ አፍሮ ኮንሰርት  ጋር የተገናኘ አይደለም።


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Thursday, January 18, 2018

ሰበር ዜና - የአዲስ አበባ ሰአሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዛሬው የጥምቀት ከተራ በዓል ጥይት ሲተኮስ አምሽቷል።የታሰሩ ምዕመናን አሉ።ምዕመኑ ቤተ ክርስቲያናችንን እናስከብራለን ብሎ ተነስቷል።




  • የሰአሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ቤተ ክርስቲያናቸውን በእዚህ ደረጃ ለማስከበር መነሳት በሌሎች አጥብያዎች ያለውን ተመሳሳይ የቤተ ክርስቲያን ንብረት ዘረፋ እና ብክነት ጉዳይ ይቀሰቅሳል የሚል ሽብር በአባካኞቹ መንደር ሁሉ  ፈጥሯል።
  • ካለ አንዳች ጥፋት ታቦት አጅበው  ይዘምሩ የነበሩ  መዘምራን  በፖሊስ ታፍሰው ነበር።
  • ውጥረቱ ተባብሷል።ምእመን አብዛኞቹ የታሰሩትን አስፈትቷል።

በአዲስ አበባ ቦሌ ክ/ከተማ ሰአሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የዛሬ አስራ አምስት ቀን ምእመኑ በሙስና እና በቤተ ክርስቲያን ንብረት ዘረፋ የከሰሳቸውን የቤተ ክርስቲያኑን አለቃ የሂሳብ ሹም እና የሰበካ ጉባኤ  ታህሳስ 10/2010 ዓም በድንገት በቤተ ክርስቲያን በመድረስ የሂሳብ ሹሙ እና የሰበካ አባላት እንዳይወጡ ካደረገ በኃላ ለፓትርያሪኩ ፅህፈት ቤት፣ለአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት እና ለቅዱስ ሲኖዶስ ባለ 26 ነጥብ የያዘ ጥያቄ ማቅረቡ ይታወሳል።በወቅቱ የቀረበው ጥያቄ ዋና ጭብጥ ሐራ ዘተዋህዶ በድረ ገፁ እንደዘገበው የሚከተሉትን ነጥቦች የያዘ ነበር። እነርሱም : -

  • ዋና አስተዳዳሪው መልአከ ብርሃን ሩፋኤል የማነ ብርሃን፣ ዋና ጸሐፊው ዕፁብ የማነ ብርሃን፣ የሰበካ ጉባኤው ምክትል ሊቀ መንበር ካሳሁን ገብረ ሕይወት እና ሒሳብ ሹሙ ዘርኣ ቡሩክ ኣብርሃ ከሓላፊነታቸው እንዲነሡ፤
  • በሕገ ወጥ መንገድ ያለምእመን ተሳትፎ በዝግ አዳራሽ የተመረጠውና በቀሲስ ካሳሁን ገብረ ሕይወት የሚመራው ሰበካ ጉባኤ ፈርሶ በቃለ ዐዋዲው መሠረት ምእመኑንና የካቴድራሉን አገልጋዮች የሚወክል ሰበካ ጉባኤ እንዲመረጥ፤
  • በቀጣይም በካቴድራሉ አስተዳደር ላይ የቀረቡትን አቤቱታዎች አጣርቶ ለሕግ የሚያቀርብ ኮሚቴ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ከሀገረ ስብከት፣ ከወረዳ ቤተ ክህነትና ከአጥቢያው ምእመናን እንዲዋቀር፤
  • የውጭ ኦዲተር ተመድቦ የካቴድራሉ ገቢና ወጪ ኦዲት እንዲደረግ የሚሉ ነበሩ፡፡

በእዚህም መሰረት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አስተዳደር ጉባኤ ኀሙስ፣ ጥር 3 ቀን 2010 ዓ.ም ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ፣ ችግሩ በግልጽ ተጣርቶ የመጨረሻ እልባት እስኪሰጠው ድረስ፡-የሚከተሉት አገልጋዮች እንዲታገዱ ወሰነ።
  1. አስተዳዳሪው መልአከ ብርሃን ሩፋኤል የማነ ብርሃን፣
  2. ዋና ጸሐፊው ሊቀ አእላፍ ዕፁብ የማነ ብርሃን፣
  3. ሒሳብ ሹሙ ሊቀ ትጉሃን ዘርኣ ቡሩክ ኣብርሃ፣
  4. ተቆጣጣሪው ቀሲስ ሳሙኤል ደሳለኝ፣ 

ሆኖም እግዱ ከተፈፀመ በኃላ ቀን ከሌሊት ምዕመናን ቢሮው ውስጥ ያለው ሰነድ እንዳይሰረቅ እየጠበቁ ከአንድ ሳምንት በላይ ቀን ፀሐይ ሌሊት ብርድ እየተፈራረቀባቸው ዘልቀዋል።ቢሮው በክፍለ ከተማ፣በፖሊስ፣ከምዕመናን የተውጣጣ ኮሚቴ  እና በሀገረ ስብከት እማኝነት ብቻ እንዲከፈት አፅንኦ ምዕመኑ ሰጥቶ ቀንና ሌሊት እየተፈራረቀ መጠበቅ ጀመረ።ሆኖም በተደጋጋሚ ጉዳዩን ለመሸፋፈን የሞከሩ  የሀገረ ስብከት ሰዎች ለብቻቸው በመምጣት ለመክፈት እንደሞከሩ እና ምዕመኑ በተቃውሞ እንዳገዳቸው ተሰምቷል። ከአስተዳዳሪው ጋር የጠበቀ የጥቅም ግንኙነት እንዳላቸው የተወሳው ፓትርያርኩ ለአቤቱታ የሄዱ ምዕመናንን በአግባቡ ከማስተናገድ ይልቅ አግባብነት የሌለው ንግግር ብዙዎችን አሳዝኗል።

ምእመኑ በድንገት የአለቃውንም ሆነ የስራ ባልደረቦቻቸውን ቢሮ ማሸጉ  በፖሊስ ኃይል ለአባካኝ ክፍሉ አለቃውን ጨምሮ  ሽፋን ለመስጠት እየሞከረ ያለው የመንግስት ኃይልም ሆነ በጥቅም ትስስር የሚታሙት የቤተ ክህነት ሰዎች ትልቅ ዱብ ዕዳ ሆኖባቸዋል።በተለይ የተቃውሞው እለት ምእመኑን ሽጉጥ ቤተ ክርስቲያን ቅፅር ግቢ አውጥቶ ሊያስፈራራ የሞከረው የሂሳብ ሹም ''ጌታዋን የተማመነች በግ ላቷን ውጭ ታሳድራለች '' የሚለውን ተረት ተደጋግሞ በብዙ ምእመናን በዕለቱ ከመሰማቱም በላይ  ምዕመኑ በከፍተኛ ቁጣ ከአሁን በኃላ ማንንም ኃይል አንፈራም በሚል እንደቆረጠ ተስተውሏል። 

ይህ በእንዲህ እንዳለ ዛሬ የጥምቀት ከተራ በዓል ምሽት ከጉዳዩ ጋር ተያይዞ ፖሊስ መዘምራንን ማፈስ ጀምሮ ነበር።በመቀጠል ህዝቡ ሲቃወም ፖሊስ በተኩስ አካባቢውን አውኮ አምሽቷል።ሁኔታውን መምህር ዘመድኩን በቀለ  እንደሚከተለው የነበረውን ሁኔታ ገልጦታል።
      "ዘሬ ታቦቷን ወደ ባህረ ጥምቀቱ ላለማውረድ ወስነው በቤተክርስቲያኗ ቅጥር ግቢ ውስጥ ድንኳን መጣል ተጀምሮ ነበር ። በኋላ የመንግሥት አካላት መጡና " ለገፅታ ግንባታችን " ጥሩ ስላልሆነ ታቦቱ በተለመደው ስፍራ ይውጣ ፣ ጥበቃውን በጋራ ከእናንተ ጋር በመናበብ እንሠራለን ይላቸዋል ። ህዝቡም ተስማማ ። ነገር ግን የቤተክርስቲያን ጥበቃውን በተመለከተ የህወሓት ፖሊስም ባለስልጣንም እውነት በመናገር ያማይታወቁና የማይታመኑ በመሆኑ አብዛኛው ህዝብ በጥበቃው ላይ ሆኖ ሌላው ደግሞ ወደ ከተራው እንዲሄድ ይስማማሉ ።
ጉዞ ወደ ባህረ ጥምቀቱ ተጀመረ ። መሃል ላይ የፌደራል ፖሊስ ላይ ከች አለ ። እናም ታቦቷን አጅቦ የሚዘምሩትን ወጣቶች አያስገደደ ወዳዘጋጀው መኪና መጫን ጀመረ ። 'አረ ምንድነው በህግ አምላክ!' ቢባል ወይ ህግ " መስሚያዬ ጥጥ ነው " ብሎ ፖሊስ  ምእመናኑን እየደበደበ መጫኑን ቀጠለ ። እንዲህማ አይደረግም ብለው የቀረቡት አረጋውያንና አባቶች ላይም ጥይት ወደላይ መተኮስ ጀመረ ።  ፖሊስ  ሕዝብ እንደድሮው ጥይት ሲተኮስ የሚፈረጥጥ መስሎታል ። " የራበው ህዝብ መሪዎቹን ይበላል " እንዲል ዶር መረራ ጉዲና ህዝቤ እንዳንገሸገሸው አላወቀ ዝም ብሎ ይተኩሳል ።
ህዝቡም ተኩሱን እንደ ሙዚቃ በመቁጠር ያፈሳችኋቸውን ልጆቻችን ፍቱ! ያለበለዚያ ዛሬ ነገር ይበላሻል !ብለው ድርቅ አሉ ። ፖሊስ   ጨነቃት ፣ ድንጋይ በእጁ የጨበጠው በዛ ፣ ሊተናነቅና ጥሎ ሊሞት ያሰፈሰፈውም እንዲሁ በረከተ ። አዲስአበባ ወደ ጦር አውድማ ልትቀየር ደረሰች ። ይህን የህዝቡን ጽናት ያየውና የተመለከተው ፖሊስ ሆዬ ነገር አብርድ አለ ። እናም ከነቃችሁ አትገደዱም ፣ እኛ እናንተን አስቦክተን ግዳጃችንን ልንወጣ ነበር ፣ አልተሳክቶም ብሎ ያሠራቸውን ፈትቶ ሹልክ ብሎ ሔዷል ።"

በመጨረሻም  የሰአሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ቤተ ክርስቲያናቸውን በእዚህ ደረጃ ለማስከበር መነሳት በሌሎች አጥብያዎች ያለውን ተመሳሳይ የቤተ ክርስቲያን ንብረት ዘረፋ እና ብክነት ጉዳይ ይቀሰቅሳል የሚል ሽብር በአባካኞቹ መንደር ሁሉ  ፈጥሯል።


ጉዳያችን GUDAYACHN www.gudayachn.com

Monday, January 15, 2018

ኢትዮጵያ፣ግብፅ፣ሱዳን እና ኤርትራ ጦርነት ሊለኩሱ ነው? (የጉዳያችን ልዩ ዘገባ)

በእዚህ የጉዳያችን ዘገባ ስር የሚከተሉት ርዕሶች ተካተዋል -
  • የዛሬ የሰኞ ጥር 7/2010 ዓም ክስተቶች
  •  የአቶ ኢሳያስ የረጅም ጊዜ ወዳጅ -ግብፅ እውን ኤርትራ የለችም?
  • አቶ ኢሳያስ ህወሓትን የእዚህን ያህል ተናግረዋት አያውቁም ህወሓትም እንዲህ ስድብ ውጣ አታውቅም 
  • ኢትዮጵያ፣ግብፅ፣ሱዳን እና ኤርትራ ጦርነት ሊለኩሱ ነው?
  • ጦርነቱ ቢከፈት ማን ይጠቀማል? ማን ይከስራል?

President Sisi during the inauguration of developments projects in Egypt on Monday, 15 January 2017 (Photo: Ahram)

የዛሬ የሰኞ ጥር 7/2010 ዓም ክስተቶች 

"እኛ ወደ ጦርነት መሄድ አንፈልግም።ይህንን ለሱዳን እና ኢትዮጵያ ወንድሞቻችን ነግረናቸዋል" አሉ የግብፁ ፕሬዝዳንት አልሲሲ ዛሬ ሰኞ ጥር 7፣2010 ዓም ግብፅ ውስጥ አንድ የልማት ፕሮጀክት ከሚንስትሮቻቸው ጋር ሲመርቁ።አልሲስ ይህንን ይበሉ እንጂ ሱዳን አምባሳደሯን ከግብፅ ከጠራች ሁለተኛ ሳምንቷ ሆኗል።ሱዳን አምባሳደሯን ከግብፅ የጠራችው ከግብፅ ጋር ለዘመናት ካጨቃጨቃት በደቡብ ግብፅ የሚገኘው የሶስት ማዕዘን መልከዓ ምድራዊ አቀማመጥ እንዳለው የሚነገረው በሁለቱ ሀገሮች መካከል የሚገኘው ሃላይብ የተሰኘው ቦታ ጉዳይ ነው።የሱዳን ፀብ ከግብፅ ጋር ይህ ብቻ አይደለም።ግብፅ ከደቡብ ሱዳን ጋር ያላት ግንኙነት ከአንድ ዓመት በፊት ተጠናክሯል።ሱዳን በአንፃሩ ከኢትዮጵያው የአባይ ግድብ ጋር በተያያዘ ከግብፅ የተለየ መንገድ ይዛለች።ይህም ሆኖ ግን አሁንም ግብፅ እና ሱዳን ከሚገባው በላይ ፀብ ውስጥ ይገባሉ ወይ? የሚለው ጥያቄ በብዙዎች ውስጥ የምንገዋለል ነው። በእርግጥ ሱዳን አምባሳደሯን በእዚህ ወር መጀመርያ ሳምንት ከካይሮ ከማስጠራቷ በፊት ለተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ግብፅን ካሳጣች በኃላ መሆኑ ጉዳዩ በቀላል የሚታይ አለመሆኑን ያመላክታል።

አልሲስ በዲፕሎማሲ ንግግር "ከወንድሞቻችን ጋር ፀብ ውስጥ አንገባም" እያሉ አቶ ኃይለማርያም ከአዲስ አበባ ተነስተው ግብፅ ይገባሉ እየተባለ እየተጠበቀ ነበር። ዘግይቶ በተሰማ ዜና መሰረት የአቶ ሃይለማርያም የሰኞ ጉዞ መሰረዙ ተሰምቷል።"ኢጂፕት ቱዴይ" የአቶ ሃይለማርያም ጉዞ ወደ ሮብ መዞሩን ዘግይቶ ገልጧል።ለጉዞው መሰረዝ የተሰጠ ምክንያት የለም።የአቶ ኃይለማርያም ጉዞ በእራሱ  "ሀገር አሰዳቢ ጉዞ" ቢባል ይቀላል።ከወር በፊት ከአስራ አምስት በላይ የሚሆኑ የግብፅ ምክር ቤት አባላት ፊርማ አሰባስበው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር እንዳይመጡ ሲሉ ማመልከቻ ለአፈ ጉባኤው አስገብተው ነበር።ይህ በሆነ በሁለት ሳምንት ውስጥ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ "ጥቂቶች ናቸው" የሚለው የህወሓት አነጋገር ተጠቅመው የግብፅ ምክር ቤት አባላት ጉዞውን የተቃወሙ የግል ተወዳዳሪዎች እንጂ የፖለቲካ ፓርቲ የሚወክሉ አይደሉም አሉ። ቃል አቀባዩ ይህንን ለሀገር ውስጥ ዜና ማሰራጫዎች ይናገሩ እንጂ አንድ የምክር ቤት አባል ማለት ስንት ሚልዮን ሕዝብ ወክሎ ምክር ቤት መግባቱን ቢያሰሉት ጉዳዩ ምን ማለት እንደሆነ በተረዱት ነበር።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ነው ግብፅ ሰኞ ይገባሉ የተባሉት  አቶ ኃይለ ማርያም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩን አቶ ወርቅነህን ማስከተላቸው እየታወቀ አንዳንድ የግብፅ መገናኛ ብዙሃን "የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ኃይለ ማርያም" ግብፅ ይገባሉ እያሉ መፃፋቸው የተሰማው።  አቶ ኃይለማርያም ሀገር አሰዳቢ በሆነ የልምምጥ ፈገግታቸው ግብፅ ገብተው ምን ሊናገሩ እንደሚችሉ አምላክ ይወቅ።ኢትዮጵያ ከሃያ አምስት ዓመት በፊት የነበራትን የአካባቢ ተሰሚነት ሁሉ አፈር ድሜ ያበላው ህወሓት ድርድሩ ሁሉ ከስልጣኑ ጉዳይ ጋር እንጂ ከኢትዮጵያ ዘለቄታ ጥቅም ጋር የተቆራኘ እንዳልሆነ ያለፉት ዓመታት አስተምረውናል።

የአቶ ኢሳያስ የረጅም ጊዜ ወዳጅ -ግብፅ እውን ኤርትራ የለችም?

ግብፅ የአቶ ኢሳያስ የረጅም ጊዜ ወዳጅ ነች።ሻብያን አቶ ኢሳያስ እንዲያጠናክሩ የግብፅ እርዳታ ቀላል እንዳልነበር ብዙ የተባለለት ነው።በካይሮ ከሚገኝ የነዳጅ ማደያ ስጦታ አንስቶ ግብፅ ለሻብያ ያልሆነችው የለም።አቶ ኢሳያስም ወደ ካይሮ መመላለስ ያበዛሉ።የአሁኑ የግብፅ ፕሬዝዳንት አልሲስ ስልጣን ከያዙ ብቻ ባለፈው ሳምንት ካደረጉት ጉዞ ጨምሮ ካይሮን ከከፍተኛ ባለስልጣኖቻቸው ጋር ሲረግጡ አራተኛ ጊዜያቸው ነው።ግብፅ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት የጦር አማካሪ ልካ እንደነበር እና ይህንንም አዲስ አበባ በሚገኙ ዲፕሎማቷ ሳይቀር "ጡረታ የወጡ ጀነራሎች የት ሀገር እየሰሩ እንዳሉ የመከታተል ግዴታ የለብንም" በሚል ማመኗ ይታወሳል።ይህ በእንዲህ እያለ ግብፅ በኤርትራ መሬት ላይ ወታደር ማስፈሯን አልጀዚራ ሳይቀር የዘገበው በቅርብ ሳምንታት ውስጥ ነው።ይህንኑ ጉዳይ ኤርትራ ፈጥና ያላስተባበለች ሲሆን አቶ ኢሳያስ ካይሮ ደርሰው ከተመለሱ በኃላ ባለፈው እሁድ ምሽት ለኤርትራ ራድዮ እና ቴሌቭዥን በሰጡት መግለጫ ላይ የአልጀዚራን ዘገባ አስተባብለዋል።ይህ ማስተባበል ግን ከካይሮ ምክር በኃላ እንደመጣ የሚያስታውቀው አልጀዚራ ዘገባውን እንዳወጣ የኤርትራ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ፈጥኖ አለማስተባበሉ ነው።

አቶ ኢሳያስ ህወሓትን የእዚህን ያህል ተናግረዋት አያውቁም ህወሓትም እንዲህ ስድብ ውጣ አታውቅም 

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሱዳን በከሰላ በኩል የሚያዋስናት ድንበር ከመዝጋቷ በላይ ብዛት ያለው ሰራዊት እያሰፈረች መሆኑን የዜና ዘገባዎች በተከታታይ እየዘገቡ ነው።ዛሬ ሰኞ ጥር 7/2010 ዓም ብቻ ተጨማሪ ጦር ሱዳን መስደዷ ተሰምቷል።አቶ ኢሳያስ በእሁዱ ምሽት ቃለ መጠየቃቸው ላይ በከሰላ በኩል እየተከማቸ ያለው የሱዳን ወታደር ሳይሆን የህወሓት ሰራዊት ነው ካሉ በኃላ " እንደ ሕፃን አዝለን በታንክ እያገዝን አዲስ አበባ ስናስገባው የተሻለ ነገር ለኢትዮጵያ እና ለኤርትራ ያመጣል ብለን ነበር።ሆኖም ለአካባቢው ጠንቅ ሆኗል።የአንቀልባውን ገመድ በጥሰን እናወርደዋለን" ብለዋል።
አቶ ኢሳያስ ጥር 6/2010 ዓም ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ 
Photo : Asmara, 15 January 2018 - Eri-Tv and Radio Dimtsi Hafash

 አቶ ኢሳያስ በህወሓት አንፃር በርካታ መግለጫዎች ሲሰጡ ተሰምተዋል እንደ አለፈው እሁድ ያለ ንግግር ግን ተናግረው አያውቁም።" The game is over" "ጫወታው (ድብብቆሹ) አብቅቷል" በሚል ንግግር የታጀበው የፕሬዝዳንቱ ንግግር ህወሓት በምንም አይነት ጥገናዊ ለውጥ ሊያንሰራራ እንደማይችል አስረግጠው ተናግረዋል።እዚህ ላይ የህወሓት አድናቂዎች ልክዱት የማይችሉት አንድ አብይ ነጥብ አለ። ይሄውም ህወሓት በትክክል ድክሞ የሚያለከልክ ማረፍያ ጥግ የምያማትር ምስኪን ፍጥረት እንደሆነ ነው።ይህ ባይሆን ኖሮ አቶ ኢሳያስ ገና ስያነጥሱ ዶክመንተሪ ፊልም የሚያዝጎደጉድ ድርጅት ዛሬ አንቀልባውን እንበጥሰዋለን ሲባል  አንድም ምላሽ ለአቶ ኢሳያስ ሳይሰጥ ጀንበር መጥለቁ በእውነትም ህወሓት ከምንገምተው በላይ ደክሟል።የስርዓቱ ደጋፊ የሆነው የአዲስ አበባው የሚሚ ስብሃቱ ራድዮ ጣብያ ዛሚ  ይብሱን አቶ ኢሳያስን ከመውቀስ ይልቅ አቶ ኢሳያስ አንድም የግብፅ ወታደር ኤርትራ የለም አሉ የሚል ዜና ብቻ መዘገቡ ሌላው አስገራሚ ጉዳይ ነው።

አቶ ኢሳያስ 90 ደቂቃ በፈጀው የእሁዱ ቃለ መጠይቅ ላይ የግብፅ እና የኢምሬት ወታደሮች በኤርትራ አሉ የሚለው ዜና "ጆክ" ነው ይህ ዜና ሆን ተብሎ የተፈበረከ ነው ብለዋል። ሆኖም ግን የአቶ ኢሳያስ ምላሽ ብዙም ተአማኒነት የለውም።ምክንያቱም አቶ ኢሳያስ እንዳሉት ቢሆን ኖሮ እራሳቸው የግብፅ እና የኢምረት መንግሥታት ማስተባበል ነበረባቸው እንጂ አቶ ኢሳያስ እስኪያስተባብሉ ባልተጠበቀ ነበር።የአልጀዚራ ዘገባ ውሸት ቢሆን ኖሮ ግብፅ እና ኢምረት በአልጀዚራ ላይ ለመውረድ ሰዓታት አያጠፉም ነበር።ስለሆነም የአቶ ኢሳያስ ምላሽ ማለት ያለባቸውን ይበሉ እንጂ ብዙም ሚዛን የሚሰጠው አይደለም።አቶ ኢሳያስ በአንፃሩ ይልቁንም የቱርክ ጦር በቀይ ባሕር ዳርቻ በሚገኘው ምዕራባዊ ሱዳን መሬት ላይ መስፈራቸውን ወቅሰዋል።

ኢትዮጵያ፣ግብፅ፣ሱዳን እና ኤርትራ ጦርነት ሊለኩሱ ነው?

በኢትዮጵያ፣ግብፅ፣ሱዳን እና ኤርትራ በተለያየ ሁኔታዎች ውስጥ ይገኛሉ።ሁሉም የጋር የሚያደርጋቸው ጉዳይ የምጣኔ ሃብት ቀውስ ሰንጎ ይዟቸዋል።ይህ በአንዱ ሀገር ያለው ከሌላው የተለየ ሊሆን ይችላል።ግብፅ የአባይ ግድብ ጉዳይ እንደ አጀንዳ የምታነሳው ከእረጅም ጊዜ ስልት አንፃር እንጂ በአጭር ጊዜ ግድቡ ስጋት ይሆናል የሚል አይደለም።የግብፅ ህልውና ውሃው ነው አበቃ።ይህ ብዙ ምርምር አይፈልግም።ደጋግሞ እንደሚነገረው አባይ ከሌለ ግብፅ ዕቃዋን ጠቅልላ ሌላ ሀገር መሄድ አለባት።መጠጥ ውሃው፣እርሻው፣መብራት ኃይል ኢንዱስትሪው ሁሉም አባይን የተቆራኙ ናቸው።ይህ አዲስ ክስተት አይደለም።

ሱዳንን በተመለከተ ከፍተኛ የመዋለ ንዋይ ቁርኝት ከኢትዮጵያ ጋር ሳይሆን ከህወሓት ድርጅቶች ጋር ገብታለች። በአንድ ወቅት የሱዳን ትሪቡን ጋዜጣ ሱዳን በኢትዮጵያ መዋለ ንዋይ በማፍሰስ ቀዳሚ ሀገር እንደሆነች መዘገቡ (ስታስቲክሱን በሚገባ ባያሳይም)  የቁርኝቱን መጠን የሚያሳይ ነው።የሱዳን ፕሬዝዳንት የህወሓት ልደት የካቲት 11 ሲከበር በረው መቀሌ የሚገቡት ወደው አይደለም።በሌላ በኩል ለም የሆነውን የእርሻ መሬት የደቡብ ሱዳንን ካጣች ወዲህ ሱዳን እያደገ ለመጣው የህዝብ ብዛት በቂ የእርሻ መሬት የማግኘት ሕልም አላት።ሱዳን በሳህል ቀጠና እንደመገኘቷ እየተስፋፋ የመጣው የበረሃማ የአየር ጠባይ በመጪዎቹ ዓመታት ከፍተኛ ችግር ሊገጥማት እንደሚችል ይታወቃል።ስለሆነም ከህወሓት ጋር እየተሞዳሞደች ለማግኘት የምትጥረው የጎንደር ለም መሬቶችን ወደ ግዛቷ መጠቅለል ነው።ይህ ተስፋ በህወሓት በኩል ከመሰጠት አልፎ የአየር ላይ ፎቶ የማንሳት ሥራ እንደተከናወነ ተሰምቷል።ይህ ማለት ሱዳን አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ከህወሓት ጋር እድሉን አቆራኝቷል።ከእዚህ በመነሳት ነው ተሰምቶ የማያውቀው የአንድ ሀገር ከፍተኛ የኒሻን ሽልማት ለሌላ ሀገር የጦር ኢታማዥር ሽልማት ሰጡ የሚል የሰማነው።የሱዳን መንግስት ለሳሞራ የኑስ የተሰጠው የሱዳን መንግስት ከፍተኛ ሜዳልያ የቁርኚቱ ልክ ማጣት የሚያሳይ ነው።

አሁን ጥያቄው ሱዳን በኤርትራ ላይ ጦርነት ታውጃለች ወይ? የሚለው ነው። አቶ ኢሳያስ ባለፈው እሁድ እንደገለጡት በከሰላ በኩል ያለው የኢትዮጵያ ጦር ነው የሚለው አባባል ትንሽ እውነትነት ይሸታል።ምክንያቱም ሱዳን ከኤርትራ ይልቅ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታ ምክር ቤት ድረስ የሄደችበት ጉዳይ ከግብፅ ጋር ያላት እንኪያ ሰላምታ ነው።አምባሳደሯን የጠራቸውም ከካይሮ ነው።አሁን ወታደሮቿን ለምን ወደ ከሰላ ታስጠጋለች? ለእዚህ ሁለት ምክንያቶች ሊቀርቡ ይችላሉ።አንድ ህወሓት ሱዳን መተላለፍያ መሬት እንድትሰጠው እና ኤርትራን ከምዕራብ በኩል ለመውጋት ፈቃድ አግኝቶ በምትኩ የጎንደር መሬትን ጨምሮ ለሱዳን ለመስጠት ተዋውሎ አለበለዝያም አልጀዝራ እንደዘገበው ግብፅ በኤርትራ በኩል በመስፈሯ ስጋት ተፈጥሮበት።

ጦርነቱ ቢከፈት ማን ይጠቀማል? ማን ይከስራል?

ሱዳን እና ህወሓት በአንድ በኩል ኤርትራ እና ግብፅ በሌላ አንፃር ሆነው ጦርነት ቢከፈት ወይንም የውክልና ጦርነት ቢያደርጉ የመጀመርያ ተጠቂዎች ሱዳን እና ህወሓት ይሆናሉ። ምክንያቱም የሱዳን ወታደራዊ አቅም ለእረጅም ጊዜ ሲገነባ የኖረ ቢሆንም በመረጃ በኩል ግብፅ እና ኤርትራ ብዙውን ጉዳይ ያውቁታል።አቶ ኢሳያስ ደግሞ እንደ ሱዳን የሚንቁት ጎረቤት የላቸውም።ገና ወደ ስልጣን እርከን ሳይደርሱ በደርግ ዘመን የቢቢሲ "ፎከስ ኦን አፍሪካ" ጋዜጠኛ ለአቶ ኢሳያስ አንድ ጥያቄ አቅርቦላቸው ነበር። ጥያቄው " ለምንድነው ለሶስት አስርተ አመታት ስትዋጉ አስመራ መግባት ያልቻላችሁት?" የሚል ነበር። አቶ ኢሳያስ ሲመልሱ " የምንዋጋው ከሱዳን ወታደር ጋር አይደለም።ከኢትዮጵያ ወታደሮች ጋር ነው" ነበር ያሉት። አቶ ኢስያስ ይህንን ያሉት የሱዳንን አቅም ለማሳነስ ብቻ ሳይሆን የቢቢሲው ጋዜጠኛ የሱዳን ተወላጅ መሆኑን ስላወቁ ነበር። ሱዳን በእዚህ ሁሉ ሂደት የሚያሰጋት የተለመደው የመፈንቅለ መንግስት ስለሆነ ኤርትራ እና ግብፅ አንድ ቀን ካርቱም ውስጥ አንዱን ኮለኔል የመፈንቅለ መንግስት ማድረጉን ሊያሳውጁባት ይችላሉ።በሱዳን በኢኮኖሚ ቀውስ ሳብያ የዳቦ ዋጋ በመጨመሩ ከፍተኛ የተማሪዎች አመፅ ተነስቶ ከካርቱም እስከ ዳርፉር ባሉ ግዛቶች የሰው ሕይወት መጥፋቱ ከተነገረ ገና አንድ ሳምንቱ ነው።ስለሆነም ግጭቱ ከተፈጠረ ሱዳን እና ህወሓት ከውስጥ ከተነሳባቸው የህዝብ ማዕበል አንፃር ባጭር ጊዜ እጅ የሚሰጡ ሲሆኑ ኤርትራ እና ግብፅ የውስጥ ቀውሳቸውን ማስታገሻ ፓናዶል ሊያደርጉት ይችላሉ።

ባጠቃላይ በግብፅ፣ሱዳን፣ኤርትራ እና ኢትዮጵያ መካከል ግጭቱ መነሳቱን ሁሉም መንግሥታት  ከሀገራቸው ካለው ቀውስ አንፃር የሚፈልጉት ይመስላል።ግብፅ አልሲስ ለህዝባቸው የውሃ ጉዳይ በጦር ኃይል ያስከበሩ መሪ ተብለው መሞገጽ ይፈልጋሉ።በእዚህም በሕዝብ ዘንድ ያላቸውን ተሰሚነት ከፍ ያደርጉበታል።የግብፅ ሕዝብ ለስሙ እና ለዝኛው ትልቅ ቦታ ይሰጣል።በሱዳን አንፃር ሕልውናው ከህወሓት ጋር ተያይዞበት ተቸግሯል።ግብፅ ለዘብተኛ መንግስት ካርቱም ላይ እንዲኖር እየሰራች እንደሆነ ገብቶታል ስለሆነም የውጭ ፖሊሲው ከህወሓት ጋር ካልተናበበ ብዙ እርቀት መሄድ የማይችል አድርጎ ያሰበ ይመስላል።ይህንን መንገድ ግን የሱዳን ሕዝብ ይደግፈዋል ተብሎ አይታሰብም።በአቶ ኢሳያስ ኤርትራ በኩል ህወሓት እያለ እንቅልፍ የሚባል ነገር የለም።ህወሓት እንደከዳቻቸው አቶ ኢሳያስ ደግግመው ተናግረዋል።ህወሓት ለኤርትራ ብቻ ሳይሆን ለአካባቢው ፀር ነው።ለእዚህም ኃላፊነት የሚወስዱት ሲደግፉት የኖሩ ሁሉ ናቸው ነበር ያሉት አቶ ኢሳያስ ባለፈው እሁድ መግለጫቸው።በእዚሁ መግለጫቸው ላይ (በሀገር ውስጥ የሚመለከት ክፍል ሁለት ቃለ መጠይቅ በመጪው ቅዳሜ እንደሚኖር ተነግሯል) ህወሓት አብቅቶለታል የሚለው ንግግራቸው በህወሓት መንደር ትልቅ ሽብር ፈጥሯል።ህወሓት አሁን የጦር ኃይል ከመላ ሀገሪቱ አንቀሳቅሶ ወደ ጦርነት ለመሄድ የሚችልበት ቁመና ላይ አይደለም።እራሱ የፈጠራቸው ክልሎች በተለይ የኦሮምያ እና የዐማራ ክልሎች ከህወሓት ውጭ ሲንቀሳቀሱ እየታዩ ነው። ሌላው ቀርቶ ህወሓት የቴዲ አፍሮ ሙዚቃ ማስቆም የሚችለው አዲስ አበባ ያውም መስቀል አደባባይ ብቻ መሆኑ ተመስክሯል። ቴዲ በያዝነው ሳምንት መጨረሻ ላይ ባህር ዳር ላይ የተከለከለ ኮንሰርቱን እንዲያቀርብ የዐማራ ክልል ፈቅዷል።ዘመን ተገልብጧል።ከእዚህ በላይም ይገለበጣል።ህወሐቶች ከእዚህ በላይ ስልጣናቸው በአይናቸው እያዩ ያጣሉ።የኢትዮጵያ በሔራዊ ጥቅም ከአካባቢ ሀገሮች ስልታዊ እና መልከዓ ምድራዊ ጥቅም አንፃር እንዳይጎዳ ግን የኢትዮጵያ ጦር ኃይል ውስጥ የነቃው ክፍል አንድ አይነት እርምጃ መውሰድ ይገባዋል።ሕዝብ ኃይል ነው።ማንኛውም የጦር ኃይል በትክክል የህወሓትን እጅ መጠርነፍ እስከቻለ ድረስ ሕዝብ አብሮት ይቆማል።የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምም በትክክል ይከበራል።ጦርነቱ ካልቀረ ህወሓትም የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶችም ማፈር አለባቸው።ከህወሓት የበለጠ ጠላት ከኢትዮጵያ ፊት አሁን የለም።ህወሓት ሲገለጥ ግን ሌሎች እንደቆሙ በትክክል ማየት ይቻላል።ለእዚህ ነው የጦር ኃይሉ ውስጥ የነቁ ክፍሎች ፈጥነው እርምጃ መውሰዳቸው አንገብጋቢ የሚያደርገው።በህወሓት ጥገናዊ ለውጥ ኢትዮጵያ ትሰምጣለች እንጂ ትለማለች ብለን እንዳንጠብቅ።

ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Saturday, January 13, 2018

በሩብ ክ/ዘመን የጎሳ ፖለቲካ አመራር በሚልዮን የሚቆጠሩ ድሆች ያፈራች ሀገር የሕዝቧን አኗኗር እንደወረደ በተቀዳ ቪድዮ ይመልከቱ።

በኢትዮጵያ የሚሰሩ የቴሌቭዥን ድራማዎች፣ፊልሞች እና የኤፍ ኤም ራድዮኖች የሚነግሩን ስለ ጥቂቶች ሕይወት ነው።የራድዮ እና ቴሌቭዥን ማስታወቂያዎች ስለ ቅንጡ መኪናዎች እና የቢራ ማስታወቂያዎች ያሳዩናል። እነኝህ ሁሉ ግን የጥቂቶችን ሕይወት እንጂ ብዙሃኑ በ21ኛው ክ/ዘመን ውስጥ የሚኖር በማይመስል መልኩ የሀገሩ ሀብት እየተዘረፈ ከድህነት ወደ ድህነት እየወረደ ለመሆኑን ይህንን እንደወረደ የተቀረፀ ፊልም መመልከት ነው።ፊልሙ ሌሎች ከተሞች እና የገጠር አካባቢዎችም በመጠኑ ይዳስሳል፣ ፖሊሶች በሕዝቡ ላይ የሚያደርሱትን ግፍ ከፎቅ ላይ በተነሳ ፊልም ያጋልጣል። በእዚህ ሕዝብ ስም ብድር ተወስዷል።ሕዝቡ ለመኖር ይታትራል።ጥቂቶች በስሙ ተበድረው በቢልዮን የሚቆጠር ገንዘብ ዘርፈው በቅንጦት ይኖራሉ።ነፃነት ማለት ይህንን ድሃ ሕዝብ ነፃ ማውጣት የሀገሪቱን ሀብት እንደአቅሙ እንዲካፈል ማድረግ እና ከመከራ ኑሮ ማውጣትም ነው። 


ምንጭ (Source) : - paul carton Published on Sep 1, 2016


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Friday, January 5, 2018

የመካከለኛው ምስራቅ አጠቃላይ ጦርነት ሳይቀሰቀስ በኢትዮጵያ ለውጥ በቶሎ መምጣት እንዳለበት የለውጥ እድሉ እጁ ላይ ያለው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሊያውቀው ይገባል።

Photo: - Financial Times © FT montage; AP/Gettyፎቶ : - ፋይናንሻል ታይምስ 

በእዚህ ማስታወሻ ስር የተካተቱ ርዕሶች: -
  • የመካከለኛው ምስራቅ እና የአፍሪካ ቀንድ መግጠም
  • አፄ ዮሐንስ በ20ኛው ክ/ዘመን፣ህወሓት በ21ኛው ክ/ዘመን ኢትዮጵያን ለባዕዳን አጋልጠው ሰጥተዋል 
  • አንድ መቶ ሚልዮን የኢትዮጵያ ሕዝብ የመካከለኛው ምስራቅ አንዳንድ መንግሥታት ስጋት 
  • "ጣልያኖች ኢትዮጵያ የሚመጡት እኔ የሮም ገዢ ሆኘ ስሄድ ነው። ፈረሴ የቀይ ባህር ውሃ ሳይጠጣ አይመለስም፣የኢትዮጵያ ድንበር ቀይ ባህር ነው" ራስ አሉላ።

የመካከለኛው ምስራቅ እና የአፍሪካ ቀንድ መግጠም


የመካከለኛው ምስራቅ ውጥረት የአፍሪካ ቀንድን ጨምሮ አዳዲስ ''አካባቢያዊ ኃያላንን'' እያሳተፈ ግለቱ እየጨመረ ነው።በኢራን የሚደገፈው የየመኑ የሆውቲ (Houthi)  ሽምቅ ተዋጊዎች የሳውዲ አረብያ ስጋቶች መሆናቸውን ቀጥለዋል።ሳውዲ አረብያ በአካባቢው የነበራት የጦር ኃይል እና የገንዘብ ጡንቻ ከእስራኤል በቀር የሚያሰጋት እንደሌለ ታስብ ነበር።የሳውዲ የጦር ኃይል ከጥራት ይልቅ ውድ እና ውስብስብ ቴክኖሎጂ የታጠቁ የምዕራቡ ስሪት ጀቶች እና ሚሳአሎች አሏት። ሆኖም ግን አጠቃቀም ላይ በቂ የሰው ኃይል ያላፈራች ነች በማለት ባላንጣዎቿ ኢራን እና  ኳታር ያሟታል። የሳውዲ አረብያን የበላይነት በሚገባ እየተገዳደሯት ያሉት ኢራን እና ኳታር ናቸው።


ሳውዲአረብያ እና የተባበሩት አረብ ኢምሬት በየመን ላይ በፈፀሙት የአየር ጥቃት በሺህ የሚቆጠሩ የየመን ሕፃናት፣ወጣቶች እና አረጋውያን እረግፈዋል።ከተሞች ወደ ትብያነት ተቀይረዋል።ሆኖም ግን ሳውዲአረብያን የተናገረ የምዕራብ ሀገር የለም።በተባበሩት መንግሥታት በኩልም ይህ ነው የሚባል የረባ  ወቀሳ አልተሰማም።የገንዘብ ኃይል የመንግስታቱን ስሜትም፣ ሰብአዊነትን ሁሉ አጣሞ እና አንሸዋሮ አስቀምጦታል። 


ሳውዲ አረብያ እና የተባበሩት አረብ ኢምሬት ወታደሮቻቸውን ከኤርትራ እስከ ሱማልያ ድረስ አስፍረዋል። በአፍሪካ ቀንድ የሰፈረው ጦር ይህ ብቻ አይደለም።መሽቶ በነጋ ቁጥር ኢትዮጵያን ዙርያ የሚሰፍሩት የመካከለኛው ምስራቅ ጦር ኃይል እየጨመረ መጥቷል።ቱርክ ከአውሮፓ ድረስ ዘላ ሱማሌ ሞቃዲሾ አጠገብ ያሰፈረችው የጦር ኃይል ሀገሪቱ ከቱርክ ውጭ ያለው ጦሯ ከፍተኛውን ቁጥር ይዟል።ግብፅ በሌላ በኩል በኤርትራ ዘመናዊ መሳርያ የታጠቀ ጦሯን ማስገባቷ ተሰምቷል።የመካከለኛው ምስራቅ ጥልፍልፍ እንዲህ ቀጥሏል።ይህ ሁሉ ቦታ የመያዝ ሩጫ አንድ አይነት አካባቢያዊ ጦርነት እንደማይቀር አመላካች ነው። በተለይ በሳውዲ በኩል በተሰለፈው ኃይል እና በኢራን ጎን በተሰለፈው ኃይል መሃከል የአካባቢ ኃያልነት ሩጫ ወደ ማይቀረው ግጭት እንደሚያመሩ ግልጥ ነው። 


ሃገራቱ ግጭታቸው ባሉበት መልከአ ምድር ውስጥ ብቻ እንደማይሆን አንዱ አመላካች ነጥብ ደግሞ በተናጥል እየፈፀሙ ያሉት የወታደራዊ ስምምነት ጉዳይ ነው። ኤርትራ ከግብፅ፣ሳውዲ እና የተባበሩት መንግሥታት ጋር ስምምነት ያላት ሲሆን በህወሓት የምትመራው ኢትዮጵያ በቅርቡ ከታር ጋር በከፍተኛ ልዑክ ደረጃ ወታደራዊ ንግግር እንዳደረገች ተሰምቷል።በአጭሩ የመካከለኛው ምስራቅ ጉዳይ ከጀርባ ሃያላኑ እያቀጣጠሉት ወደ ጦርነት አፋፍ ላይ መድረሱ አይቀርም።ምናልባትም እስራኤል በእዚህ ጦርነት የመካከለኛ ምስራቅ ባላንጣዎቿን የምታደክምምበት መልካም ቀን ይመጣ ይሆናል የሚሉ ብዙዎች ናቸው።


አፄ ዮሐንስ በ20ኛው ክ/ዘመን፣ህወሓት በ21ኛው ክ/ዘመን ኢትዮጵያን ለባዕዳን አጋልጠው ሰጥተዋል


ኢትዮጵያ ባለፉት ሃምሳ አመታት ውስጥ ያልገጠማት ደካማ የውስጥ አስተዳደር እና ሃገራዊ አንድነት አደጋ ላይ ነች።ይህ ደግሞ ህወሓት ለስልጣኑ ብቻ ያለመ እጅግ አደገኛ እና የኢትዮጵያን ጥቅሞች አሳልፎ ከመስጠት ባለፈ የኢትዮጵያን የአንድ እናት ልጆች ሆን ብሎ በመከፋፈል ሃገራዊ አንድነታችንን አደጋ ላይ ጥሎታል። እዚህ ላይ በተቃዋሚ ጎራ ያሉ ከሀገራዊ አንድነት ያልቅ የጎሳ ፖለቲካን እንደ የመጨረሻ አልፋና ኦሜጋ ግብ በማስቀመጥ ሕዝብ ግራ በተጋባ ስሜት ውስጥ እንዲገባ ያደረጉ የስልጣን ጥማት ብቻ ያናወዛቸው ለሀገራዊ አንድነት መላላት አስተዋፅኦ አላደረጉም ማለት አይቻልም።


ኢትዮጵያ ያለው የፖለቲካ ንዝህላልነት፣የሀገርን ጥቅም አሳልፎ ለባዕዳን የመስጠት ሸፍጥ፣ ለባዕዳን   በኢንቨስትመንት ስም የተጋለጠው የሀገሪቱ ደህንነት እና የህዝቡ ሃገሩን የመከላከል አቅሙን በምጣኔ ሀብት ድቀት የማዛሉ ደረጃ ሁሉ ኢትዮጵያ እጅግ አደገኛ በሚባል ደረጃ ያለችበት ወቅት መሆኑን መካድ አይቻልም። ህወሓት አሁን እየሰራ ያለው አፄ ዮሐንስ ደጃች በዝብዝ በሚል ስያሜ በሚታወቁበት ደረጃ በቀጥታ ሀገሪቱን ለባእዳን ያጋለጡበት ወቅትን ይመስላል። የቀደሙት ደጃች በዝብዝ በኃላ አፄ ዮሐንስ ኢትዮጵያን በ20ኛው ክፍለ ዘመን በሁለት መንገድ ለባእዳን እንዳጋለጡ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም ከሶስት አመታት በፊት በ2007 ዓም በታተመው   'አዳፍኔ' በተሰኘው   መፅሐፋቸው ላይ ገልጠውታል።ይሄውም የመጀመርያው  የአፄ ቴዎድሮስን ጦር ሊያጠቃ የመጣውን የእንግሊዝ ሰራዊት ሙሉ የስንቅ እና የመንገድ መምራት ሥራ ሰርተው አፄ ቴዎድሮስ እንዲሞቱ አስተዋፅኦ ማድረጋቸው እና ራስ አሉላ አባነጋ የኢትዮጵያን ጦር በያኔዋ ባህረ ነጋሽ በአሁኗ ኤርትራ ላይ የነበራቸውን የበላይነት እና የኢትዮጵያን ድንበር የማስከበር አኩሪ ተግባር ራስ አሉላን ከስልጣናቸው ዝቅ በማድረግ እና ወደ ጣልያን ጦር እንዳይገሰግሱ ምክንያት በመስጠት መሆኑን ያብራራሉ።


 አፄ ዮሐንስ የእንግሊዝን ሰራዊት ወደ ኢትዮጵያ እንዲገባ አድርገው አፄ ቴዎድሮስ እራሳቸውን ከሰዉ በኃላ ለእንግሊዝ ንግስት የፃፉት ደብዳቤ የተወሰደ እንዲህ ይነበባል : - "ጥንቱንም በእግዚአብሔር ፈቃድ ለመንግስት የበቃሁ እርስዎ በሰጡኝ መድፍ፣ነፍት፣ባሩድ ነው" (ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም አዳፍኔ፣ገፅ 11)

"ጣልያኖች ኢትዮጵያ የሚመጡት እኔ የሮም ገዢ ሆኘ ስሄድ ነው። ፈረሴ የቀይ ባህር ውሃ ሳይጠጣ አይመለስም፣የኢትዮጵያ ድንበር ቀይ ባህር ነው" በሚሉ ታሪካዊ ንግግር የሚታወቁትን ራስ አሉላን የውግያ ሞራል የገደሉ አፄ ዮሐንስ መሆናቸውን ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ከጠቀሱት ጥቅስ ውስጥ እንዲህ የሚለው ይገኝበታል።
   ''ከዶጋሊው ጦርነት ወዲህ የጦር ጠቅላይ አዛዥነቱን ንጉሰ ነገስቱ ከራስ አሉላ አንስተው ለታላቅ ወንድማቸው ልጅ ለራስ ኃይለ ማርያም ሰጥተው አሉላን በሃማሴን ግዛት ስለወሰኗቸው (ራስ አሉላ) ቅሬታ ነበራቸው ይባላል።" (ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም አዳፍኔ፣ገፅ 13)

ከላይ እንደተጠቀሰው የአፄ ዮሐንስን ለስልጣን ሲሉ የባዕድ ወታደር ማስገባት በመቀጠልም የኢትዮጵያ አሉ የተባሉ የታሪክ ድርሳናት እና የብራና መፃህፍት ከመቅደላ (የመፃህፍቱን ብዛት 11 ግመል ሙሉ የተጫኑ የሚሉ አሉ) ተጭነው ወደ እንግሊዝ ሲሄዱ የኃላው አፄ ዮሐንስ የቀድሞው ደጃች በዝብዝ አጋፋሪ መሆናቸው የታሪካችን ጠባሳ ነው። ይህ ብቻ አይደለም የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ አለማየሁ ከቤተሰቡ ጋር ስጋዝ  አሁንም ደጃች በዝብዝ ለብረት ልዋጭ እና ለንጉሰ ነገስት ስልጣን የሀገር ክብር ሲያልፍ ቆመው ተመልክተዋል። በእርግጥ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጀግና አድናቂ ነው እና የአፄ ዮሐንስ ታሪክ ሲነሳ ሁለ የሚወሳው ለኢትዮጵያ ሲሉ መተማ ላይ መሰዋታቸው ነው።የዛሬው የህወሓት መንግስት ግን የአፄ ዮሐንስን አንገት ቆርጠው ካርቱም ገበያ ለገበያ እያዞሩ የተሳለቁትን የያኔዎች ደርቡሾች የዛሬ ሱዳኖች ጋር እየተሞዳሞደ የኢትዮጵያን ድንበር ቆርሶ እየሰጠ ነው። 


ኢትዮጵያ በ20ኛው ክ/ዘመን የገጠማት የባዕዳን ከበባ አሁንም ስልጣን ላይ ያለው መንግስት ልክ አፄ ዮሐንስ እንዳደረጉት ለባእዳን ሀገሪቱን አስረክቦ ስልጣኑን ለማቆየት ብቻ የሚያልም ነው።ህወሓት ኢትዮጵያዊ ጥቅም የሚል አጀንዳ እንደሌለው ከስሙ ጀምሮ ባለመቀየር ግልጥ ማድረጉ የሚታወቅ ነው።ለጎሳው ከጎሳውም ለአድዋ ቅድምያ የሚሰጠው ህውሓት በስልጣን ላይ መቆየቱ ብሔራዊ አደጋ ነው።በ20ኛው ክ/ዘመን የነበረው የአውሮፓውያን ኃይል በመካከለኛው ምስራቅ ኃይል ከመተካቱ ውጭ ጊዜው ለኢትዮጵያ ያለው አደገኛ ገፅታ ቀላል አይደለም።ይህ ማለት ኢትዮጵያ ህወሓት በስልጣን ላይ እያለ አደጋዋን ትከላከላለች ብሎ የሚያስብ ካለ በአሁኑ ነባራዊ የኢትዮጵያ ሁኔታ ውስጥ የሌለ መሆን አለበት። ህወሓት የብሔራዊ ደህንነት አደጋ ነው።አቶ ለማ መገርሳ የኦሮምያ ፕሬዝዳንት ደጋግመው የእኛ ስልጣን ከሀገር ደህንነት አይበልጥም የሚሉት የሚያውቁት በርካታ የህወሓት ምስጢሮች ስላሉ እንደሆነ መጠርጠሩ አይከፋም።አቶ ለማ በደህንነት መስርያቤቱ ውስጥ እንደመስራታቸው መጠን በርካታ መረጃዎች በተለይ ህወሓት የሀገርን ደህንነት አደጋ ላይ በሚጥል መንገድ የሄደበትን ሂደት መረዳታቸው ውስጣቸውን እየፈነቀለ እንዲናገሩ እንዳደረጋቸው መረዳቱ አይከፋም።ብዙ ስታውቅ ብዙ የውስጣዊ ስሜት መፈንቀል ያጋጥማል።ለእዚህ ነው አቶ ለማ  ኢትዮጵያ ሃገራዊ አንድነቷ መጠበቁ አስፈላጊ መሆኑን ደጋግመው ሲናገሩ የምንሰማቸው።

Picture source: Financial Times

አንድ መቶ ሚልዮን የኢትዮጵያ ሕዝብ የመካከለኛው ምስራቅ አንዳንድ መንግሥታት ስጋት 

በ20ኛው ክ/ዘመን  ሁለተኛ አጋማሽ ላይ አውሮፓውያን በአራቱም ማዕዘናት ከበዋት እና በኃላ ጣልያንን ሲልኩባት  ለድል የበቃችው በዳግማዊ ምንሊክ በተፈጠረው ውስጣዊ አንድነት ጭምር ነው።ዛሬም የመካከለኛው ምስራቅ አጠቃላይ ጦርነት ከመነሳቱ እና ኢትዮጵያ የጥቃቱ ኢላማ ከመሆኗ በፊት የውስጥ የቤት ሥራ መስራት ለኢትዮጵያ ሕዝብ እና ኃይሎች የተሰጠ የቤት ሥራ ነው።ህወሓት በስልጣን ላይ እያለ ሀገር የመከላከል ሥራ ፈፅሞ የሚታሰብ አይደለም።ስለሆነም ኢትዮጵያዊ የሆነ መንግስት ለማቆም ህወሓት ለሃያ ስድስት አመታት ከኖረበት ስልጣን ገለል ማድረግ ምንም አማራጭ የለውም።ስለሆነም የኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጣዊ አንድነቱን እያጠናከረ እና በጎሳ የሚከፋፍሉትን ማናቸውም  ውጫዊ ኃይሎች  ወደ ኢትዮጵያ የጋራ መድረክ እንዲመጡ ማስገደድ ይጠበቅበታል።


ለማጠቃለል  የመካከለኛው ምስራቅ አጠቃላይ ጦርነት ሳይቀሰቀስ በኢትዮጵያ ለውጥ በቶሎ መምጣት እንዳለበት የለውጥ እድሉ እጁ ላይ ያለው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሊያውቀው ይገባል።ጦርነቱ አካባቢያዊ አድማሱን ማስፋት እና በአጋጣሚው የውሃ ማማዎችን መቆጣጠርን ያለመ እንደሆነ ግልጥ እየሆነ መጥቷል።ኢትዮጵያ የጦር ሰራዊቷ ህዝቧ ነው። አንድ መቶ ሚልዮን የሚቆጠረው የኢትዮጵያ ሕዝብ የመካከለኛው ምስራቅ አንዳንድ ሀገሮች እንደ ስጋት ይመለከቱታል።ስለሆነም መከፋፈሉ ብቸኛ አማራጭ ሆኖ ቀርቧል። የመከፋፈሉን ሥራ የሰራው እና ለሰራበት እየተከፈለው የሚገኘው ህወሓት ደግሞ የበለጠ ለመሰነጣጠቅ በፖሊሲ ደረጃ ሲንቀሳቀስ 27 ዓመታት እያስቆጠረ ነው። ስለሆነም ህወሓት ከስልጣን መወገዱ የሀገሪቱ አንድነት ከመቼውም ጊዜ በላይ የሚጠነክርበት ሃገራዊ አጀንዳዎች ለሕዝቡ የሚደርሱበት ጊዜ መሆኑን የታመነ ነው።

=============////============

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።