የጉባኤተኞች ብዛት በጥቅሉ 401 ሲሆን 351 ድምጽ በመስጠት የሚሳተፉ፣ 50 ድምጽ መስጠት የማይችሉ ታዛቢዎች ነበሩ። በዚህ ስብሰባ ላይ ጻድቃን አልተሳተፉም ነበር ። ሆኖም ግን በምግበይና ወዲ አሸብር አሸማጋይነት ከሰአት በኋላ ተሳትፏል ። በጉባኤው ላይ ፣ ሰራዊቱ የመረጣቸው ተወካዮች፣ ከሙያ ማህበራት፣ ከሲቪክ ማህበራት ቢሳተፉም የተወከሉበት መንገድ ትክክል ባለመሆኑና ህወሃት የመረጣቻው በመሆናቸው በህዝቡ እና እንወክለዋለን በሚሉት አደረጃጀት ተቀባይነት ኣላገኙም ። የተቃዋሚ ፓርቲዎች ግን ሙሉ በሙሉ አልተሳተፉም።
የዚህ የጉባኤ አጀንዳና አካሄድ የሚዘውረው አሁንም የሽግግር ሂደቱን ከኋላ እየተቆጣጠረው ያለው የነጌታቸው አሰፋ ቡድን እንደሆነ በጉባኤው አጀንዳ አቅራቢና ተደራጅቶ በቀረበው ውይይት ባልተደረገበት አጀንዳ አጸዳደቅ የተረጋገጠ ሆኗል። አጀንዳ አቅራቢው አለም ገበረዋህድ፣ የነጌታቸው አሰፋ ቡድን ቀኝ እጅ ነው። የመጀመሪያው አጀንዳ ጉባኤውን የሚመራ ፕሬዚደየም መምረጥ ሆነ። አሰቀድሞ ድርጅታዊ ስራ በተሰራበት መንገድ ዶ/ር ደብረጽዮን ሊቀመንበር፣ ታደሰ ወረደ ምክትል፣ ሊያ ካሳ፣ ዘውዱ ኪሮስ፣ ሙሉወርቅ ኪዳነ ማሪያም፣ አባላት አድርጎ መረጠ። ምርጫውን በተመለከተ ጆን መዲድ(ጀ/ል) “አዲስ ፊት ያላየንበት አሳፋሪ ምርጫ ነው” በማለት በስብሰባው ላይ አስተያየቱን ሰጥቶበታል ።
በዚህ
ጉባኤ ላይ በአለም ገብረዋሃድ የተዘጋጀው የሽግግር መንግስት ሰንድ ላይ ውይይት ተደርጎ ስብሰባው ተበተነ። ሰኞ የካቲት 20/2015 አለም ገብረዋህድ የህወሃት ጽ/ቤት ሃላፊ የስራ አስፈጸሚ ኮሚቴ የማእከላዊ አባላት ስብሰባ ጠራ። በስብሰባው ላይም ፕሮፖዛል ይዞ መጣ። ፕሮፖዛሉ የሽግግር መንግስቱ መመራት ያለበት በወያኔ መሆኑን በማተት፣ ደብረጽዮን በፕሬዚደንት ይቀጥል፣ አቶ በየነ ምክሩ የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ፣ ሊያ ካሳ የተፈጥሮ ሃብት ክላስተር አሰተባባሪ፣ ወ/ሮ የአለም ጸጋይ የኢንፍራ ስትራክቸር ክላስተር አስተባባሪ፣ ፕሮፌሰር ክንደያ ገብረህይወት የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ፣ ዶር እያሱ እርሻ ቢሮ ሃላፊ ፣ ዶር አማኑኤል ሃይሌ የጤና ዘርፍ ሃላፊ ፣ ዶር ኪሮስ ትምህርት ቢሮ ሃላፊ ፣ ወ/ሮ ገነት አረፈ ታክኒክና ሙያ ስልጠና ቢሮ ሃላፊ ፣ ወ/ሮ አልማዝ ገ/ፃዲቅ ከተማ ልማት ቢሮ ሃላፊ ፣ ዶር ሃጎስ ጎዲፋይ ፕሬዚዳንት አማካሪ ፣ አቶ ዘበርህ የመሬት አጠቃቀም ሃላፊ፣ ወ/ሮ ምህረት የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ በማድርግ አዲስ ካቢኔ እንዲቋቋም የሚያደርግ ሃሳብ ያቀረበ ነበር፡፡
ይህ ፕሮፕዛል ደብረጽዮንን ሊቀመንበር አድርጎ ብቻ በማቅረቡ እንደ ደብረጽዮን በማእከላዊ ኮሚቴው ውስጥ የሚዋልል አቋም ያላቸውን አባላት ድጋፍ ስላገኘ ጸደቀ። በዚህ ፕሮፕዛል ውስጥ የደብረጽዮን ጉዳይ አንዳለ ሆኖ ከበየነ ምክሩ በስተቀር የተቀሩት ስራ አስፈጻሚ አባላት ቀንደኛ የነጌታቸው አሰፋ ጸረ ስላም ቡድን አባላት ናቸው። የካቢኔው አባላትም በአለም ገብረዋህድ አቅራቢነት በመምጣታቸው ከነጌታቸው አሰፋ ቡድን ውጭ ይሆናሉ ብሎ ማሰብ አይቻልም። አስገራሚው ነገር ጉባኤ እንዲመሩ የተመረጡ ሰዎች እራሳቸው በሚመሩት ስብሰባ ላይ ተመልሰው መመረጣቸው ነው። ደብረጺዮን እና ሊያ ካሳ ጉባኤ መሪዎች ተበለው ተመርጠው ነበር።
በእንዲህ አይነት ቅጥ አምባሩ በጠፋ የሴራ ሂደት የነጌታቸው አሰፋ ቡድን የሽግግር መንግስቱ ከወያኔ እጅ እንዳይወጣ በማድረግ የራሳቸው ሰዎች በበላይነት የሚቆጠጠሩት መንግስት አቁመው ለኢትዮጵያ መንግስት ውጤቱን አሳውቀዋል። በዚህ ስብሰባ ላይ የጌታቸው አሰፋ ቡድን ደጋፊዎች የተሰጡት አስተያየት፣ ይህን ወሳኔ የኢትዮጵያ መንግስት የማይቀበለው ከሆነ እስከመጨረሻው እንደሚታገሉትና ጉዳዩን ወደ አባሳንጆና ኡህሩ ኬንያታ እንደሚውስዱት ነው። ይህ ማለት ጉዳዩን ወደ አሜሪካ መንግስት በማቅረብ የአሜሪካ መንግስት በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ተጽእኖ በማድረግ የትግራይን ሽግግር መንግስት እንዲቀበለው ለማድረግ እቅድ እንደተያዘ የሚያሳይ ነው። አሁን ባላንበት ወቅት የኢትዮጵያ መንግስት ከትግራይ የቀረበለትን ፕሮፖዛል አልቀበልም ብሏል። ይህን ምላሽ የሰማው ህወሃት እንደገና ስብሰባ ተቀመጧል።
ዛሬም በወያኔ ውስጥ ያሉ ጸረ ሰላም አመራሮች አላማቸውን ማሳካት የሚያስችሉ ስራዎች እየተሰሩ ነው። የአመጽ እርምጃዎች ለመውሰድ ከሚያስችሉ ዝግጅት አንስቶ በተለያዩ ሰላማዊ የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ስልቶች ፍላጎቶቻቸውን ለማስፈጸም እንደሚችሉ በሙሉ ልብ እየተናገሩ ነው። ብልጽግና ውስጥ በመግባት አብይን መስሎ አብይን ማሸነፍ፣ የአማራ ክልል መንግስትን እና የኤርትራ መንግስትን የሰላም ስምምነቱ የማይደግፉ ሃይሎች አድርጎ በማቅርብ ከማእከላዊ መንግስት መነጠል፣ አልፎም ከማእከላዊ መንግስት ጋር በመሆን መውጋት፤ ይህን ለማደርግ የሚያስችል በፕሪቶሪያው ስምምነት ውስጥ “ሌሎች ችግሮች በህገመንግስቱ መሰረት ይፈታሉ የሚለው አንቀጽ” እንደሚጠቅማቸው፣ የወልቃይት ጉዳይ በህገ መንግስቱ መሰረት የሚፈታ ከሆነ ህገመንግስቱ ወልቃይት የትግራይ ግዛት አድርጎ ስለሚያስቀምጥ በቅድሚያ ሌላ መፍትሄ ከመታሰቡ በፊት ግዛቱ ወደ ህገመንግስታዊ ባላቤቱ መመለስ አለበት የሚለው ጥያቄያቸው ፍትሃዊ ተደርጎ በፌደራል መንግስቱና በአሜሪካኖች እንደሚታይ፣ ይህ የማይዋጥላቸው የአማራ ክልላዊ መንግስትና የኤርትራ መንግስት ተቃውመው እንደሚቆሙ፣ ይህን ተቃውሞ ምክንያት በማድረግ በሰላም ስምምነቱ ማስከበር ስም ሁለቱን ታሪካዊ ጠላቶች መውጋት እንደሚቻል፣ በአማራ ህዝብና በኤርትራ ህዝብ መሃል የተፈጠረውን ግንኙነት መበጠስ፣ በኢትዮጵያ መከላከያ ውስጥ ተመልሰን መግባታችን እና ሹመት ማግኘታችን የማይቀር በመሆኑ እንዲያውም በቅርቡ ሹመቱ ይመጣል በማለት ይህን ሹመት ትልቅ ተጽእኖ አሳዳሪ ጉልበት በመከላከያው ውስጥ እንደሚሰጣቸው፣ የፌደራል መንግስቱን መከላከያ አመራሮችን ከዚህ ቀደም ሲያደርጉት እንደነበረው በወያኔዎች እጅ ባላው ከፍተኛ ሃብት የወያኔ ፍላጎት ፈጻሚዎች ማድረግ እንደሚቻል፣ የሰሜን ጦር ከመጠቃቱ በፊትና በተጠቃበት እለት ከኢትዮጵያ የሰራዊት አመራሮች መሃል በጥቅማ ጥቅም የገዟቸውን፣ ጦርነቱ ከተጀመረ በኋላም በሚሊዮኖች ገንዝብ ስጥተው ማስከዳት የቻሏቸውን ዛሬ መቀሌ ተቀመጦ የኦነግ ሰራዊት አደራጅ የሆኑት አንዳንድ የጦር መሪዎች መመልመል እንደቻሉ ሌሎችንም መመልመል እንደሚቻል እቅድ እያወጡ ይገኛሉ።
በዲፕሎማሲ መስኩ ለሚያደርጉት ስራ አለም አቀፍ የትግራይ ምሁራን ድርጅት እና በውጭ የሚገኙ የስርአቱ ደጋፊዎች በሚያሰባስቡት ገንዘብና መንግስት በሚያቀረበው ገንዘብና እርድታ ተመስርቶ የኢትዮጵያን መንግስት ለማሳጣት የሚያስችል ዝርዝር የሆነ በሰብአዊ መብት ጥሰትና በጦር ወንጀለኛነት መንግስትን ሊያስፈርጅ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው። በኢትዮጵያ መንግስት በኩል በተመሳሣይ ግን በወያኔ በትግራይና በሌሎች ክልሎች በራሱ በወያኔ ሃይሎች የተፈጸሙ የአስገድዶ መድፈር የግድያ፣ ሌሎችንም ዘግናኝ ወንጀሎችን በተመለከተ በተደራጀ መንገድ መረጃ የሚያሰባስብ አካል አለመኖሩ የሚያስገርም ነው።
3) የሰላም ስምምነቱ ከወታደራዊ ጉዳዮች አንጻር
የሰላም ስምምነቱ ሌላው አካል፣ ወያኔ ሁሉንም ትጥቆቹን ያወርዳል ሰራዊቱንም በካምፕ ያስገባል የሚል ነው። ከትግራይ የሚሰብሰው መረጃ የሚያሳየው በአጉላ እና በአካባቢው የነብሩ ተተኳሽ ያለቀባቸው የተበላሹ ጥቂት ታንኮችና መድፎች ማስረከባቸውን ነው። ከዚህ ውጭ በመረጃ ስማቸው በሚታወቁ ከእይታና የትራንስፖርት መግቢያ የሌላቸው፣ ሚስጥር በመጠበቅ የማህበረስቡ አንድ ወጥ አሰፋፍር ባላቸው በርካታ ቦታዎች ላይ በርካታ ከባድና የቡድን መሳሪያቸውን አስቀምጠዋል።
ሰራዊቱ በካምፕ መሰብሰብን በተመለከተ፣ በመንገድ ዳር ከሚገኙ በቀላሉ በሚታዩ በመቀሌ ዙሪያ፣ ገረብ ግባ፣ምላዛት፣ ሳምረ፣ አዲ ጉደም፣ አራአ ሰገዳ፣ እና በቆላ ተንቤን ወረዳ በአግበ ከተማ ካሰባስቧቸው የሰራዊት አባላት ውጭ በሌሎች በመረጃ ተደግፈው መቅረብ በሚችሉ ከመንገድ በራቁ ለትራንስፖርት አመቺ ባላሆኑ በርካታ ቦታዎች ላይ ወታደራዊ ዝግጅቱ አሁንም እንደቀጠለ ነው። የውጊያ ስልት፣ የእግር ጉዞ፣ የወታደራዊ ጽንጸ ሃሳብ ትምህርቶች ያለፈው ውጊያ ግምገማዎች እየተካሄዱ ነው። ለትግራይ ህዝብ የተላከወን የእርዳታ እህል ወያኔዎች ይህን ሰራዊት ለማሰልጠኛነት እየተጠቀሙበት ነው።
ቀደም ተብሎ የተጠቀሰው ወያኔዎች ለሽብር ስራ እያዘጋጁት ካለው 7000 ከሚቆጠር ልዩ ሰልጣኝ እና በነጻ አወጭ ድርጅት ስም አሁንም ስለጠና እየሰጧቸው ያሉትን የኦሮሞ፣ የአገው፣ የአፋርና ሌሎችንም ነጻ አውጭ ሰራዊትን ስንጨምርበት ወያኔዎች እውን ለሰላም እየተዘጋጁ ነው የሚል ጥያቄ የሚያስነሳ ይሆናል። ሌላው በከፍተኛ ጥንቃቄ መታየት የሚገባው ጉዳይ ወያኔዎች በጃቸው ያለውን ከፈተኛ ሃብትና ከዚህ ቀደም ሰዎችን በሙስና የማጥመድ ችሎታቸውን በመጠቀም በቅርብ ጊዜ ውስጥ የማእከላዊ መንግስት ወደ ትግራይ የላካቸው የመከላከያ፣ የፖሊስ የደህንነት አባላት በጥቅም በገንዝብ በሌሎችም ዘዴዎች የመያዝ ስራ መጀመራቸው ነው። ይህ የሙስና ስንሰለት የት ድረስ ሊዘረጋ እንደሚችል በተለይ በሃገሪቱ ውስጥ ከሰፈነው የሙስና ባህል አንጻር መገመት ከባድ አይደለም። በጦርነቱ ወቅት የወያኔ የመረጃ ሃላፊ የነበሩ፣ በረሃ ገብተው ሲያዋጉና ሲዋጉ የነበሩ በወያኔ ዘመን በከፍተኛ ደረጃ የሰለጡኑ ሰዎች አንዳንዶቹ በቻርተር አይሮፕላን ሲንቀሳቅሱ የነበሩ ዛሬ አዲስ አበባ ከተማ መሃል በነጻነት የሚንቀሳቅሱበት ሁኔታ እያየን ነው። በመንግስት የሚያሳምን መግለጫ እስካልተሰጠበት ድረስ እንደዚህ አይነት ግለሰቦች ያለምንም ስጋት በአዲስ አበባ ከተማ የሚንቀሳቅሱበት ምክንያት የወያኔዎች የሙስና የስራ ውጤት ከመሆን አይዘልም። በወንጀል ሊጠየቁ የሚገባቸው ግለሰቦች የመቀሌን ኤርፖርት ብቻ ሳይሆን በቦሌ ኤርፖርት ጭምር ወደ ውጭ ሃገር የወጡበት ሁኔታ እንዳለ መረጃዎች አሉ። ከሰላም ስምምነቱ በኋላ ምን ያህል ሰዎች ወያኔ ወደፊት ላቀደው የኢኮኖሚና የሽብር ስራ ከትግራይ ወደ አዲስ አበባ ገብተዋል ሌላው መንግስትን እና ህዝብን ሊያሳስብ የሚገባ ጉዳይ ነው።
4) ኢኮኖሚያዊና ሁኔታዎች በተመለከተ
በመሰረተ ልማትና በተቋማት ውድመት ደረጃ በትግራይ ውስጥ ወያኔ እራሱ ካደረሳቸው ጥፋቶች፣ ለምሳሌ በአክሱምና በሽሬ፣ የአውሮፕላን ማረፊያዎችን የኢትዮጵያ መንግስት እንዳይጠቅምባቸው ለማድረግ ከተከናወኑ ጥፋቶች ውጭ ወያኔዎች በአማራና በአፋር ክልል ሆን ብለው ያወደሙትን አይነት የመሰረተ ልማትና የተቋማት ውድመት በትግራይ ውስጥ አልደረሰም። በተቋማት ውስጥ የነበሩ ንበረቶች በተለያዩ አካላት የተዘረፉ ቢሆንም ዘረፋው የተወሰኑ ቦታዎችን የሚመለከት እንጂ በአፋርና በአማራ ክልል ወያኔዎች ሆን ብለው የህዝቡን የመንግስትን ተቋማትን ንበረት በዘረፉበት ደረጃ የተዘረፈ አንዳልሆነ መረጃዎች ያመላክታሉ። ለምሳሌ ከኮመቦልቻ ደሴ በርካታ ማሽነሪዎች ፣ ጀነሬተሮች በገብረሊባኖስ የተባላው የሞንጀሪኖ ባል እንደዘረፈ እና እንደሽጣችው በሰኔ 15/2014 በአክሱም ሆቴል በነበረው የአመራር ስብስባ ላይ ተገምግሟል፡፡ እንዳውም አንዳንዶቹ ተቋማት በራሱ በወያኔ ትእዛዝና በወያኔ ተባባሪዎች ንብረቱን ለጦርነቱ በግብአትነት እንዲያስረክብ ተደርጓል። ዶ/ር ፋና ሃጎሰ የቀድሞ የትግራይ ክልል የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት የነበረች እና ፌዴራል መንግስት መቀሌን ሲቆጣጠር የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት ሆና የተሾመች ቀንደኛ የእነ መንጆሪኖ ደጋፊ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚደንትነቷ የዩኒቨርስቲዎን የምግብ ማብሰያዎች፣ ፍራሾችና ኮምፕዩተሮች እና ሌሎቸ ንብረቶች ለሰራዊቱ አሰርክባለች። ባሁኑ ወቅት መቀሌን ዩኒቨርስቲ ምንም አይነት የማስተማሪያ ግብአት የሌለው ሲሆን ሃላፊዋ መንግስት ዩኒቭርስቲውን መልሶ እንዲያደራጅ አይኗን በጨው ታጥባ ትምህርት ሚኒስቴርን እየወተወተች ነው ። ሌሎችም መንግስታዊ የሆኑና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት እንዲሁም የግል ድርጅቶች ከኤሌትሮኒክስ እቃ አንስቶ እስከ ሌሎች ቁሳቁሶች ለጦርነቱ መሳለጥ እንድያዋጡ በደብዳቤ ተጠይቀው በርካቶች አስተዋጽኦ አድርገዋል።
በትግራይ ውስጥ ያለው የኢኮኖሚ ችግር ጦርነቱ ምርት አንዳይመረት በማስተጓገል የእህልና የጥራጥሬና ሌሎችም የምግብ ፍጆታዎች እጥረትና ዋጋ ማሻቀብ ነው። የሰላም ስምምነቱ ከተደረሰ በኋላም የምግብ እርዳታ በገፍ ቢገባም ህዝብ ከምግብ እጥረት ጋር የተያያዘው ችግሩ አሁንም አልተፈታለትም። በተለያዩ ቦታዎች የእርዳታ እህል በተለያዩ መጋዘኖች ተከማችቶ ይታያል። ህዝብ እርዳት ሲጠይቅ የሚሰጠው መልስ “እህሉ ለከፉ ቀን የተያዘ ነው” የሚል ሆኗል። በወታደራው መስኩ ትግራይ ውስጥ ካለው ሁኔታ በመነሳት ክፉ ቀን ማለት ምን ማለት እንደሆነ መገመት ከባድ አይሆንም።
ሌላው በትግራይ ውስጥ ትልቅ ችግር የሆነው ጉዳይ በአንዳንድ ግልሰቦች እና ባለስልጣኖች እጅ የሚንቀሳቅሰው ከፍተኛ ብዛት ያለው ጥሬ ገንዘብ ነው። ይህ ጥሬ ገንዝብ ጦርነቱ አንድ ቀን ሲቀረው፣ ለትግራይ ንግድ ባንክ ተልኮ የነበረውን በወያኔዎች እጅ የወደቀውን በቢሊዮኖች የሚቆጠር ብር ጨምሮ፣ ከአማራና ከአፋር ህዝብና ባንኮች ወያኔዎች በመዝረፍ የሰበስቡት ተደምሮበት እንዲሁም በቅርቡ የኢትዮጵያ መንግስት ለባንኮች የላከው 5 ቢሊዮን ብርና ከዚህ ውጭ የተለያዩ አለም አቀፍ ድርጅቶች በየወሩ ወደ ትግራይ የሚልኩት ከ1 ቢሊዮን እስከ 1.5ቢሊዮን የሚደርስ ጥሬ ገንዝብ ነው። በተለይ ገንዘቡን የያዙ ግለሰቦች ከ20 እስከ 50 % የሚደርስ ወለድ በማስከፈል ለህዝቡ ብድር የሚሰጡ ሲሆን የህዝቡን ስቃይና መከራ እያባባሱበት ይገኛሉ ፡፡
በባንክ የሚደረግ የክፍያ ስርአት ፈጽሞ የለም፣ ገንዘብ ያገኘ ሰው ገንዘብ በእጁ ይዞ የሚዞርበት ከፍተኛ ግብይቶች ሳይቀሩ በካሽ የሆነበት ሁኔታ ተፈጥሯል ። አለም አቅፍ ድርጅቶ የሚልኩት ገንዝብ ለደሞዝና ለሌች ስራዎች ወጪ ተደርጎ በካሽ መልኩ ሆኗል ህብረተሰቡ ውስጥ የሚበተነውና የሚከማቸው። በትግራይ ውስጥ ያሉ ባንኮች ከሞላ ጎደል ሁሉም ባዶ ናቸው። ይህን ችግር ለመቅረፍ በሳምንት አምስት ችህ ብር በግለሰብ ደረጃ ወጪ እንዲደረግ ቢወሰነም ውሳኔው በዘምድ አዝማድ፣ በምልጃ በጉቦ ተፈጻሚ መሆን አልቻለም። ይህ የጥሬ ገንዝብ ዝወውር ብዛት በትግራይ ውስጥ ከየትኛውም የሃገሪቱ ክልል በላይ የዋጋ ግሽበት በማስከተል የተራውን ህዝብ ኑሮ የከፋ እንዲሆን አድርጎታል። ይህ ብር ቀደም ተበሎ እንደተገለጸው ከትግራይ አልፎ በተቀሩት የኢትዮጵያ ግዛቶች ውስጥ መበተን በመጀመሩ የውጭ ምንዛሪ የጥቁር ገባያ የሚያጠናክር፣ የደሃውን ህዝብ ህይወት የከፋ የሚያደርገውን ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ የሚያባባስ እየሆነ እየሄደ ነው። በተጨማሪም እነዚህ ግለሰቦች በራማ በኩል በዶላር እስከ 120 ብር ድረስ እንዲመነዘር በማድረግ ብሎም ብሩ የተለያዩ ንብረቶች እና የመሬት ግዥ ላይ በማዋል የአገሪቱ የመግዛት አቅም በማዳከም ላይ ይኛሉ ፡፡ በዚህም መሰረት እነሞንጀሪኖን ጨምሮ በትግራይ ውስጥ ከፍተኛ ብር ከዝነው ያሉ ግለስቦች፣
1 አባዲ ግርማይ { አዋሽ ትራንስፖርት }
2 ሃይለ ላምባ ፣ ትራንስፖርት እና ማደያ
3 ሃይለ አስፍሃ { ማይ ሱር ትራንስፖርት {
4 ሃይላይ ደስታ ሃደራ [ ትራንስፖርት
5 ሙሴ መርሳ
6 እንዳ ሃድጉ ቤተስብ
7 ራሄል ጣፍ
8 አብረሃ ተክለሃይማኖት
9 ሌሎችም
ሌላ ከኢኮኖሚው ጋር መጠቀስ ያለበት ጉዳይ የእነጌታቸው አሰፋ ቡድን በጁ ካስገባው ወርቅና ሳፋያር እንዲሁም ከእነዚህ ማእድኖች ጋር በተያያዘ ከሚያኪሂደው ሽያጭ በተጨማሪ የመቀሌን
ህዝብ አገልግሎቶች ለምሳሌ እንደ መብራት አገልግሎት አይነቶቹን ገቢ በቀጥታ የሚቆጣጠር መሆኑ ነው። በቅርቡ በመብራት ክፍያ ላይ 15 ከመቶ ጭማሪ በማድረግ የመቀሌ ህዝብ አፍንጫውን ተይዞ ክፍያ እንዲከፍል እየተደረገ፣ ክፍያው በጥሬ ገንዝብ ብቻ እየተሰበሰበ፣ በሞንጆሪኖ ቡድኖች እጅ በየሰው ቤት የሚቀመጥ ሆኗል። ይህን ክፍያ የሚያሰባስበው የመብራት ሃይል ሃላፊ የሞንጀሪኖ ቤተሰብ ነው ። በሌላው መልኩ ከአንዳንድ የወያኔ ወዳጅ ሃገራትና ከትግራይ ዳያስፖራ ለጸረ ድሮንና ለጦር መሳሪያ መግዢያ በሚል የተሰበሰበው ብዙ ሚሊዮን ዶላር በሞንጀሪኖ አካውንት መግባቱ በወያኔ ግምገማ የተደረገበት ጉዳይ ቢሆንም
እስካለነበት ሰአት የተቀየረ ነገር ባላመኖሩ ዶላሩ አሁንም በሞንጀሪኖ አካዎንት ይገኛል።
ተመሳሳይነት ያላቸው የማፍያ አይነት፣ የወያኔ አመራሮች በቀጥታ እጃቸውን የሚያስገቡባቸው የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ተበራክተዋል ። በቅርቡ የመስቦ ሲሚንቶ ፋብሪካ ስራ እንዲጀምር የቀረበውን ሃሳብ ተፈጻሚ ለማደርግ ፋብሪካው የሚያስፈልገውን የከሰል ድንጋይ ከደቡብ አፍሪካ እና ከአገር ውስጥ አስመጭዎች የሰራዊቱ አመራሮች እንዲሆኑ በወያኔ ተወስኗል ። ፋብሪካው ሲጀመር መቀጠር የሚችሉ ሰራተኞች የቅጥር መስፈርት የካቲት 25 2015 በ/ገሚካኤል ገብሩ ፊርማና ማህተም በወጣው ማስታወቂያ ላይ፣ በቁጥር 4) መታገሉን ከትግራይ ሰራዊት ማምጣት የሚችል፣ 5) ባላፈ ሁለት አመት ውስጥ ራሱን እና ቤተሰቡን ያታገለ 6) ቅድሚያ የሚሰጠው ከአንድ ቤት ሁለት እና ከዛ በላይ ላታገለ የሚሉ መስፈርቶች ተካተውበታል። የወያኔ መሪዎች በኢኮኖሚ መልኩ ለ27 አመት ያካባተቱን ሃብት በመጠቀም በትግራይ ውስጥ ህዝቡ እነሱ የፈለጉትን ነገር እንዲፈጽም ማድረግ እንደሚችሉ ሙሉ እምነት ያላቸው ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ህዝብም ላይ ተመሳሳይ ተጽእኖ ማድረግ እንደሚችሉ ተማምነው እየተንቀሳቅሱ ናቸው።
5) ማህበራዊ ሁኔታን በተመለከተ
ትግራይ ውስጥ የሰላም ስምምነት ይደረግ እንጂ ማህበረስቡ ሰላምና መረጋጋት እንደራቀው ነው። በጦርነቱ የተነሳ ከቀያቸው የተፈናቀሉ ሰዎች አሁንም በችግር ላይ ናቸው። በመሳሪያ የተደገፈ ዘረፋ፣ የመሳሪያ ሽያጭ፣ ጾታዊ ጥቃት የመሳሰሉት ወንጀሎች እንደቀጠሉ ናቸው። በመቀሌ ከተማ በአንድ ሳምንት ብቻ 31 ሰዎች በጩቤ ተወግተው አይደር ሆስፒታል ለህክምና ገብተዋል። ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ ማህበረሰቡ በተለይ ህጻናት ሴቶች አረጋውያን የገቡበት የስነልቦና ቀውስ ለመገመት ከሚቻለው በላይ ነው። የልጆቻቸው መኖርና አለመኖር ሃቁ ያልተነገራቸው ወላጆች በመርዶ ይደርሰኛል ስጋት በሰቀቀን እየኖሩ ነው። ከጦርነቱ ጋር በተያያዘ እጅና እግሩ የተቆረጠው አይኑ የጠፋው ሌላም የአካል ጉዳት የደረሰበት በርካታ ወጣት በከተሞች ማየት ራሱን የቻለ የስነልቦና ችግር ፈጣሪ ሆኗል።
ወያኔ በጀመረው ጦርነት ህይወቱን ያጣው፣ አካሉ የጎደለው የትግራይ ወጣት ብዛት በውል አይታወቅም። በልጆቻቸው ድጋፍ የሽምግልና እድሜያቸውን በሰላም እንገፋለን ያሉ በርካታ ወላጆች ያለ ጧሪና ቀባሪ ቀርተዋል። ስጋትና ፍራቻ የህዝቡ የቀን ተቀን ህይወት ድርና ማግ ሆኗል። እድል ቢያገኝ ከትግራይ ነቅሎ ለመውጣት የሚፈልገው ሰው ብዙ ነው። የተቻላቸው በተለያዩ ከተሞች የሚኖሩ ሰዎች ቤታቸውን እየሸጡ ጉቦ በመስጠት በተለያዩ አቅጣቻዎች በአየርና በመኪና ከትግራይ እየውጡ ነው። በዚህ ላይ በጦርነቱ ወቅት የቆሙ የትምህርት የጤና ሌሎችም መንግስታዊ አጋልግሎቶች ስራ አልጀመሩም። ባጭሩ የሰላም ስምምነት ይፈረም እንጅ የትግራይ ህዝብ ሰላም አላገኘም። በፖለቲካውና በወታደራዊ መስኩ የሚታየው የፀረ ሰላም ሃይሎች እንቅስቃሴ የትግራይ ህዝብ ሰላም እንዲህ በቀላሉ የሚያገኝ አይመስልም።
በህዝቡ ውስጥ ወያኔ ችግሬን ይፈታልኛል የሚል እምነት እየተመናመነ መሄዱን የሚያሳዩ በርካታ ምልክቶች አሉ። በፖለቲካ መስኩ የትግራይን ችግር የፈጠሩና ያባባሱ የፖለቲካ ሰዎችን ለማስወገድ ከተጀመረው ጥረት በተጫማሪ ህዝብ ወያኔ የተመሰረተበትን የካቲት 11ን እንዲያከበር ተጠይቆ ይህ በአል የኔ አይደለም በሚል በመላው ትግራይ በበአሉ ባለመገኘት አቋሙን ገልጿል። በወያኔ ጥሪ የተደረገላቸው ከዚህ ቀደም ወያኔ ዝለሉ ሲላቸው ስንት ሜትር በማለት ይጠይቁ የነበሩ ማህበራት ሳይቀሩ በበአሉ ላይ አልተገኙም። በአንዳንድ እንደ ሓሓይለ የመሰሉ የማእከላዊ ዞን ወረዳዎች ወያኔ በሹመት የላካቸውን አሰተዳዳሪዎች ህዝብ አንቀበልም ያለበት ሁኔታ ተፈጥሯል። በአጠቃላይ በአሁን ወቅት ስደት ፣ ህገወጥ የሰው ዝውውር ፣ ዝርፍያ ፣ የኑሮ ውድነት ፣ ፆታዊ ጥቃት እና የመሳሰሉት ችግሮች ከሰላም ስምምነት በኋላም ቢሆን ያልተፈቱ ችግሮች ሆነው ቀጥለዋል።
6) የዲፕሎማሲያዊ ሁኔታ በተመለከተ፣
ዝርዝሩ ብዙ ቢሆንም ዛሬ በትግራይ ውስጥ፣ ለውጥ በሚፈልገው የትግራይ ህዝብና የህወሃት ወጣት አመራርና በጸረ ስላም ሃይሉ የነጌታቸው አሰፋ ቡድን መሃል ያለውን ትግል በከፍተኛ ደረጃ ወደ ጸረ ሰላም ሃይሉ እንዲያዘነብል የሚያደርገው ጸረ ሰላም ሃይሉ በዲፕሎማሲ መስኩ ያለው ድጋፍ ነው። ይህ ድጋፍ የትግራይን ሰላም ብቻ ሳይሆን በጥንቃቄ ካልተያዘ የኢትዮጵያን እና የቀጠናውን ሰላም የማናጋት አቅም አለው። ይህ አቅም የተገነባው በሶስት መሰረታዊ ዋልታዎች ላይ ነው።
የመጀመሪያው፤ ረጅም ዘመን ያስቆጠረ ገና በትግሉ ጊዜ የጀመረ የወያኔ መሪዎች የአሜሪካን ጥቅም በምስራቅ አፍሪካ ለማስጠበቅ መሳሪያ ለመሆን ዝግጁነታቸውን ከገለጹበት ዘመን ይጀመራል። ወያኔ ስልጣን ከያዘ በኋላ በሂደት እንደታየው የአሜሪካ መከላከያ ተቋም፣ የአሜሪካ እና የእንግሊዝ የስለላ ድርጅቶች ከወያኔ ጋር እጅና ጓንት ሆነው የሚሰሩበት፣ ወያኔ በምስራቅ አፍሪካ አካባቢ የአሜሪካንን ቆሻሻ ስራ ፈጻሚ የሆነበት ሁኔት ተፈጥሯል። ወያኔ የአሜሪካኖችን ጥቅም ለማስከበር ከፔንታጎን ጀነራሎች ጋር ተስማምቶ አንድን ሏላዊ ሃገር ሶማሊያን እስከመውረር ደርሷል። ከስለላ ድርጅቶቹ ጋር በመተባባር የግድያ የአፈና ስራ ሲሰራ ነበር። የወያኔ ጀነራሎች የፔንታጎን፣ የወያኔ ሰላዮች የሲአይኤና የእንግሊዙ ኤም አይ6 ቤተኞች ነበሩ። ለ27 አመት የአሜሪካንን እና የምእራባውያን ጥቅም በማስጠበቅ ወያኔዎች ለእነዚህ መንግስታት የዋሉትን ውለታ እነዚህ መንግስታት የሚረሱት አይደለም። በተለይ በምእራቡ አለም ቁልፍ የሆነውን የሰው ለሰው ግንኙነት ኔትዎርክ ወያኔዎች በ27 የስልጣን ዘመናቸው በሚገባ ያደራጁት በመሆኑ በየትኛውም የምእራብ መንግስታት ተቋማት ውስጥ ሊተባበሯቸው የሚችሉ በርካታ ወዳጆች አፍርተዋል። ይህ የግንኙነት መረብ ከነጩ ቤተመንግስት አንስቶ፣ በመከካከያ፣ በስለላ ድርጅቶችና በሚድያ ተቋማቱ የተዘረጋ ለመሆኑ ወያኔ የአንድን ነጻ ሃገር የመከላከያ ሰራዊት አጥቅቶ ጦርነት በኢትዮጵያ ላይ በከፈተበት ወቅት ከአሜሪካና ከምእራብ መንግስታ እንዲሁም ከሚድያ ተቋማቱ ካገኘው ምንም ይሉኝታ በሌለው ድጋፍ ተገልጿል።
ሁለተኛው፤ ለጸረ ሰላም ሃይሉ የዲፕሎማሲ አቅም የሚሰጠው በጁ ያለው ሃብት ነው። ብዙ ጊዜ ስለሃብት ሲወራ ሰዎች የሚጠቅሱት ወያኔ ስልጣን ከያዘ በኋላ ከሀገር በተጭበረበረ ሰነድ አማካይነት ከንግድ ልውውጥ ጋር ተያያዞ ከኢትዮጵያ ስለወጣው ዶላር ፍሮብስ የተባለው መጽሄት ያቀረበውን ሃተታ ነው። ፍሮብስ ወያኔ ስልጣን በቆየባቸው 17 አመታት 17 ቢልዮን ዶላር በህገ ወጥ መንገድ ከሃገር መውጣቱን አስነብቦ ነበር። ይህ በአመት አንዲ ቢሊየን ዶላር የሚደርስ ዘረፋ ከኢትዮጵያ ህዝብ ወያኔዎች የዘረፉትን ሃብት ብዛት በጥቂቱ ብቻ የሚገልጽ ነው። በተጭበረበረ ደረሰኝ ዶላር የሚያወጡት ሁሉም ወያኔዎች ስላልነበሩ 17 ቢሊዮኑ በወያኔዎች ብቻ ካገር የወጣ አድርገን ማየት አንችልም።
በሌላ መንገድ ግን በቀጥታ በወያኔዎች ተዘርፎ ካገር የወጣ ገንዝብ ከ50 እና 60 ቢሊዮን ዶላር በላይ ሊሆን እንደሚችል መገመት ይቻላል። ሁለቱን የዚህ ገንዘብ ምንጮች እንጥቀስ። ወያኔ ኢትዮጵያውያን ከመላው አለም ከባንክ ውጭ ገንዝብ ለዘመዶቻቸው የሚልኩባቸውን መንገዶች በሙሉ ለብቻው መቆጣጠር ችሎ ነበር። በአለም ባንክ ግምት የኢትዮጵያ ዳያስፖራ በአመት ከ3 እስከ 4 ቢሊየን ዶላር ወደ ሃገር ቤት እንደሚልክ ይነገራል። አብዛኛውን ገንዘብ ባንክ ከሚሰጠው በላይ ህገወጥ በሆነ መንገድ ሲመነዘሩ የነበሩ የወያኔ ባላስልጣናትና ሸሪኮቻቸው ነበሩ። ዛሬም አላቆመም። ከዚህ ገንዘብ በአማካይ በአመት አንድ ቢሊዮን ዶላር መመንዘር ከተቻለ በ30 አመት 30 ቢሊየን ዶላር ወያኔዎች ወደ ውጭ ማሸሽ ችለዋል። በዚህ ላይ ስልጣናቸውን በመጠቀም ወያኔዎች በሱዳን እና በጅቡቲ በኩል ያለማንም ጠያቂ በቀጥታ እያወጡ የሸጡትን ሰሊጥ ወርቅና ሳፋየር ሲንደምርበት ዘረፋው ምን ያህል አስፈሪ እንደሆነ ያሳየናል።
በህገወጥ መንገድ እየወጣ ይሸጥ የነበረው ሰሊጥ ኢትዮጵያ ከቡና ከምታገኘው ከነበረው የውጭ ምንዛሪ የሚበልጥ እንደነበር ስለእዚህ ህገ ወጥ ንግድ እውቀት ያላቸው ሰዎች ይናገራሉ። ይህ በህገ ወጥ መንገድ በአውሮፓና በአሜሪካ ባንኮች የተከማቸ ገንዘብ ወያኔዎችና ዘርማንዘሮቻቸውን የድሎት ህይወት እንዲኖሩ ማስቻል ብቻ ሳይሆን፣ ገንዝብ ማንንም ምንም መግዛት በሚችልባቸው የምእራብ ሃገራት፣ የመንግስት ባላስልጣናትን ፖለቲከኞችን፣ የሚድያ ተቋማትና ጋዜጠኞችን ሌሎችንም ተጽእኖ ማሳደር የሚችሉ ግለሰቦችን መግዛት አስችሏቸዋል። የአሜሪካ መንግስት ለጥቅሙ ሲል ወያኔን በመደገፍ ከወሰደው ኢትዮጵያን የማጥቃት እርማጃዎች በተጨማሪ ወያኔዎች በጃቸው ያለውን ገንዘብ በመጠቀም የአሜሪካ መንግስት ይህን ውሳኔ እንዲወስን ተጽእኖ አሳዳሪ ግለሰቦችን በመግዛት የሚፈልጉትን ማስወሰን እንደቻሉ መታወቅ አለበት።
ሶስተኛው የትግራይ ዳያስፖራ ነው። የትግራይ ዳያስፖራ ስንል ወያኔ ስልጣን ላይ ከወጣ በኋላ ከወያኔ ጋር በቅርበት በተሳሰረ መንገድ የተፈጠረውን ዳያስፖራ ማለታችን ነው። ይህ አካል በውጭ ሃገር የተፈጠረለት የመማር፣ በድሎት የመኖር እድል በከፍተኛ ደረጃ ከወያኔ ጋር ተያይዞ የመጣ መሆኑ ይታወቃል። ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ በቀጥታ ከወያኔ ከፍተኛ እና መካከለኛ ደረጃ መሪዎች ጋር በቀጥታ በቤተሰብነት በዝምድና የተሳሰረ ነው። ይህ አካል ከየትኛውም በውጭ ከሚኖር የኢትዮጵያ ማህበረሰብ በላይ የገንዘብና የድርጅት አቅሙ የጎለበተ ነው። ወያኔ የከፈተውን ጦርነት በዲፕሎምሲና በገንዝብ ምን ያህል ለመደገፍ እንደሚንቀሳቀስ ታይቷል። የትግራይ ዳያስፖራ የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ተቃውሞ ሰልፍ የወጣበት ምክንያት ውግንናው፣ ጸረ ሰላም ከሆነው ሰላም ፈላጊዎችን ተንበርካኪዎች በሚል ከፈረጀው የትግራዩ የወያኔ ቡድን ጋር ስለሆነ ነው። ዳያስፖራው የሰላም ስምምነቱን ተቃውሞ ያወጣው መግለጫ ላይ የሰላም ስምምነቱን የፈረሙትን ግለሰቦች “ተንበርካኪ” በሚል ቃል መግለጹ የተራ አጋጣሚ አይደልም።
ከላይ በተጠቀሱት ሶስት ምሰሶዎች ላይ የቆመው የጸረ ሰላም ሃይሉ የዲፕሎማሲ ጉልበት ሊያስፈጽማቸው የተነሱት ግልጽ አላማዎች አሉት። እነዚህ አላማዎች ከአሜሪካ መንግስት ጋር በቅርበት በመነጋገር የተቀረጹ የአሜሪካንን መንግስት ድጋፍ የሚያገኙ ናቸው።
ወያኔን እንደ ድርጅት አትርፎ፣ የትግራይ ህዝብና የኢትዮጵያ ህዝብ በተጠያቂነት እንዲቀርቡለት የሚፈልጋቸውን ነባር የፖለቲካ የደህንነትና ወታደራዊ አመራሮች ከተጠያቂነት ነጻ ማድረግ፣
ወያኔ በኢትዮጵያ ፖለቲካና ኢኮኖሚ ውስጥ የነበረውን ያልተገባ ድርሻ በአዲስ መልኩ ማስቀጠል በተለይ የወያኔ ባልስጣናት በዘረፋ በሃገር ውስጥ ያካበብቱ ሃብት እንዳይነካባቸው ማድረግ። ወያኔዎች ጥቃት ሰንዝረው መሳሪያውን በገፈፉትና ሰራዊቱን ባረዱበት የመከላከያ ተቋም ውስጥ መልሶ ማካተት፣
በኢትዮጵያ በኤርትራ መንግስት መሃከል ተፈጥሮ የነበረው መልካም ግንኙነት እንዲሻክር፣ እንደቀድሞው ኢትዮጵያና ኤርትራ በጎሪጥ የሚተያዩ፣ ቢቻልም ወደሌላ ጦርነት እንዲገቡ ማድርግ፣ የኢትዮጵያ መንግስት በአሜሪካኖች ጉያ ውስጥ የተወሸቀ የአሜሪካኖችን ጥቅም አስከባሪ መንግስት እንዲሆን ነው። በመጪው ሳምንት ውስጥ የአሜሪካው መንግስት የውጭ ጉዳይ ሴክረታሪ ብሊንከን ኢትዮጵያን የሚጎበኘው እነዚህ ከላይ የተጠቀሱ አላማዎች ለማሳካት ነው። ለዚህ እንደካሮት የሚያገለግሉ የገንዝብ እርዳታ፣ ብድር የማግኘትን እድሎችን ወደ ከታክስ ነጻ ወደሆነ የአሜሪካ የንግድ ቀጠና (አግዋ) መመለስን የመሳሰሉ ጉዳዮችን ይዟል። በዱላ መልኩ የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ቀውስ ማባባስ፣ በጦር ወንጀል እና በጀኖሳይድ መሪዎቹን መክሰስ በሃገሪቱና በመሪዎቿ ላይ ተጨማሪ ማእቀብ ማድረግ የሚችል መሆኑን መጠቆም ነው።
7) እንዴት ከዚህ ችግር መውጣት ይቻላል።
በቅድሚያ ከትግራይ ጋር የተያያዘውና ትግራይ ውስጥ የሚታየው ችግር የትግራይ ህዝብ ብቻ ሳይሆን የተቀረው የኢትዮጵያም ህዝብም ችግር መሆኑ መታወቅ ይኖርበታል። ጦርነቱና ከጦርነቱ ጋር የተፈጠረው መመሰቃቅል ሁሉንም ህዝብ ሁሉንም ክልል ያዳረሰ ነው። ሞትና መፈናቀል፣ መዘረፍ መዋረድ መደፈር መጠኑ ይለያይ እንጂ በሁሉም የሃገሪቱ ክልሎች ተከስቷል። የኢኮኖሚው ምስቅልቅልም፣ ህዝብን ለከፍተኛ ስቃይ እየዳረገ የሚገኘው የኑሮ ወድነት፣ እየተስፋፋ የሄደው ሌብነት ግርግር ለሌባ ይመቻል እንደሚባለው ጦርነቱ በፈጠረው የተመቻቸ ሁኔታ ወስጥ የተስፋፋ ነው። በዲፕሎማሲው መስክ እየመጣ ያለው ጫና ቀጠናውን ሌላ ትርምስ ውስጥ የሚከት ነው።
ከጦርነቱ ርቆ በሃገር ውስጥና ከሀገር ውጭ የሚኖረው ኢትዮጵያዊ ይህ ጦርነት በሞት የቀጠፈው የሰው ህይወት ብዛት ትግራይ ውስጥ ደርሷል ከሚባለው በመቶ ሽዎች ከሚቆጠር እልቂት ወጭ ሌላ መረጃ የለውም። የሚሰጠው ስለሌለ። በሚገባ አልተነገረም እንጂ እልቂቱ በሌሎች ቦታዎችም አሰቃቂ ነበር። በቅርቡ በአማራ ክልል ከጦርነቱ ጋር በጦር ሜዳ ላይ ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች መርዶ ለቤተሰባቸው ተነግሮ ነበር። በምስራቅ ጎጃም ብቻ የ8020 ሰዎች ሞት መርዶ ተነጓሯል። ቀደም ብሎ የተነገረ በምስራቅ ጎጃም ዞን ውስጥ ከሸበል በረንታ ወረዳ ብቻ ከዘመቱ ሚሊሻዎች መሃል በአንድ እለት በአቀስታ ግንባር ዶባ ተራራ ላይ 19ኙ ተሰውተዋል። እነዚህ የሚሊሺያ አባላት ያለአባት ትተዋቸው የሄዱ የታዳጊ ልጆቻቸው ብዛት 96 ነው። በመላው ሃገሪቱ ከዚህ ጦርነት ጋር ብቻ በተያያዘ ያለቀውን የህዝብ ብዛትና ጥሎ ያለፈውን ሰቆቃ ከእነዚህ ሁለት መረጃዎች መገመት ይቻላል። በመሆንም የኢትዮጵያ መንግስት የሰላም ስምምነቱ ሂደት በተመለከተ ለህዝብ ወቅታዊ መረጃ የማቅረብ ግዴታ አለበት።
የኢትዮጵያ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የሰላም እጦት ቀውሶች እርስበርስ የተቆራኙ ናቸው። ዝርዝሩ ወስጥ መግባት አያስፈልግም። የዚህ ጽሁፍ አላማ በትግራይ ውስጥ ባለው ችግር ላይ ያተኮረ በመሆኑ ወደዛው እመለሳለሁ።
የትግራይ ብሎም የኢትዮጵያ ህዝብ ከሚገኝበት ችግር እንዲወጣ ከተፈለገ የኢትዮጵያ መንግስት በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት በተሰጠው ስልጣን የሚከተሉትን እርምጃ ቢወስድ በሚል ምክረ ሃሳቤን አቀርባለሁ። ምከረ ሃሳቡን ለትግራይ በጎ የሚመኙ በትግራይ ውስጥ የሚገኙ የትግራይ ወጣት ፖለቲከኞች እንደሚደግፉት ማሳወቅ እፈልጋለሁ።
ሀ) በፖለቲካ ዘርፉ
የፖለቲካው መፍትሄ በትግራይ ውስጥ ዛሬ የትግራይ ህዝብ ወያኔን እንዴት ያየዋል፣ በወያኔ አመራራ መሃከል ጸረ ሰላም የሆነው ሃይል ምን እየሰራ ነው፣ ሰላም እንዲስፍን የሚፈልገውስ አካል ምን እያደረገ ነው ከሚለው የወቅቱ የትግራይ ሁኔታ ጋር የተገናዘበ መሆን አለበት።
በፖለቲካ መስኩ፣ በፕሪቶሪያው ስምምነት መሰረት የሽግግር መንግስት የማቋቋም ዋናው ሃላፊነት የኢትዮጵያ መንግስት ስለሆነ መንግስት የማቆሙን ስራ በተደራጀ መንገድ ለግልና ለቡድን ጥቅማቸው መቆጣጠር ከሚፈልጉ የተደራጁ አካላት ነጻ ማድረግ መቻል አለበት። እስካሁን የተሄደበት መንገድ ህዝብ አምሮ የሚጠላቸውን እና የሚቃወማቸውን በዚህ አጋጣሚ ከጫንቃው ላይ ሊያነሳቸው የሚፈልጋቸው የወያኔ አመራሮች የልብ ልብ የስጠ ለለውጥ የተነሳሳውን በወያኔ ውስጥ ያሉትን ወጣት አመራሮችና ህዝቡን እራሱን ተስፋ የሚያስቆርጥ አካሄድ ባስቸኳይ መቆም መቻል አለበት።
አሁን በትግራይ ያለውን ሁኔታ ለመቀየር በቅድሚያ በሽግግር መንግስቱ ፈጠራ ሂደት፣ ትልቁን ስልጣን እና መብት፣ የመከራው ዋናው ገፈት ቀማሽ የሆነው የትግራይ ህዝብ የሚቆጣጠረው እንዲሆን ማድረግ ይገባል። የኢትዮጵያ መንግስት ቀድሞ የሚያውቃቸውን ወይም እራሱ ያደራጃቸውን ወይም በራሳቸው የተደራጁ የጥቂት ግለሰቦችን እና ቡድኖችን ከማመን የትግራይ ህዝብን ማመን የተሻለ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልገዋል። የትግራይ ህዝብ ሰላምና ፍትህ እንዲያገኝ ከገባበት የህይወት መከራ እንዲወጣ በንጽህና ከሚታገሉ ወጣት ፖለቲከኞች ጋር ተቀራርቦ መስራት የሚኖረውን ጠቀሜታ መረዳት ያስፈልገዋል።
አሁን ባለው ሁኔታ የብልጽግና መንግስት ከዚህ ቀደም እንዳደረገው የራሱን የብልጽግና ሰዎች የትግራይ ጊዜያዊ አሰተዳዳሪዎች አድርጎ መሰየም አይችልም። የዚህ አይነቱ ሙከራ ተሿሚዎቹን እንደ ወራሪ ሃይል አድርጎ ህዝብ እንዲያቸው በማድረግ ከዚህ ቀደም የተከሰተው የፖለቲካ ችግር እንዲከሰት ያደርጋል። ለጸረ ሰላም ወያኔዎችም ተቃውሞና አሻጥር የሚመች ሁኔታ ይፈጥራል።
በሌላ መልኩ የብልጽግና ሰዎች የቀድሞ ጓደኞቻቸውን መልሰው የትግራይ ጊዚያዊ መንግስት እንዲቆጣጠሩ የሚያደርግ ሂደት ከፈቀዱ በትግራይም ይሁን በተቀረው ኢትዮጵያ ሰላም የመጥፋቱ ሁኔታ እንዲቀጥል ከማድረግ እንደማይመለሱ ለማሳየት ሞክረናል። ከማያውቁት መልአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል በሚል ብሂል የሚመራ የሚመስለው የማእከላዊ መንግስት አካሄድ ሰይጣን ሁል ጊዜም ሰይጣን መሆኑን መረዳት ያስፈልገዋል።
የፕሪቶሪያው ስምምነት መንግስት በሃገሪቱ የደሃ ልጆች እጃቸው በደም የተጨማለቁ ግለሰቦችን መልሶ ወደ ስልጣን ማምጣት የሚል አንቀጽ አልተካተተበትም። እነዚህ ግለሰቦች ድጋሚ እድል ቢያገኙ በሃገርና በህዝብ ላይ ከሚያስከትሉት ውድመት በተጨማሪ የጥፋት እጃቸውን በማን ላይ በቅድሚያ ለማንሳት ሲዶሉቱ እንደሚውሉ የአዲስ አበባው መንግስት አልሰማ ከሆነ ልንነግረው እንችላለን። በህጻናት ጓንቲ በሚያሽሞነሙኗቸው፣ ከዚህ ሁሉ እልቂትና ውድመት በኋላ ምንም እንዳልሆነ በሚያመስል ደረጃ በሳቅና በፈገግታ የሚያቅፏቸው የወይን ብርጭቋቸውን እያነሱ ለጤናቸው በሚጠጡላቸው የብልጽግና አመራሮች ላይ ነው። አሁንም በድጋሚ ሰላም ፈላጊው በወያኔ ውስጥ ያለው የአመራር አካል የሚያነሳው ጥያቄ “መቼ ነው የፌደራል መንግስቱ በፕሪቶሪያው ስምምነት የተሰጠውን የሽግግር መንግስት የማቆም ስልጣን ተጠቅሞ መብቱ የሌላቸውን የወያኔ አመራሮች ጊዜያዊ መንግስት የማቆም ሆነ ሂደቱን የማስጀመር መብት የላችሁም የሚላቸው? እነዚህ ሃይሎች እየተሰባሰቡ ደብረጽዮን ፕሬዚደንት ጻድቃን ምክትል አድርገናል እያሉ መግለጫ ሲያወጡ ዝም ብሎ የሚያያቸው እስከመቼ ነው? የሚሉ ናቸው?
በሌላ በኩልም የፌደራል መንግስቱ የትግራይን ጊዜያዊ መንግስት በወታደር እጅ ማስያዝ አይችልም ። በወታደራዊ ስሌት አደገኛ ነው። ለከፍተኛ የፖለቲካ ኪሳራ፣ ለወያኔ አመጽ የተመቻቸ ሁኔታ ፈጣሪ ስለሆነ ሊታሰብ አይገባውም።
ያለው አማራጭ አንድና አንድ ብቻ ነው። በየቀበሌው ኗሪ የሆነው የትግራይ ህዝብ በአካል በማሰባሰብ በጊዚያዊነት የሚያስተዳድሩትን እየመረጠ በሁሉም እርከኖች እንዲሾማቸው ማድረግ። ይህን አሰራር የኢትዮጵያ የመከላከያ ሰራዊት በተቆጣጠረባቸው ቦታዎች በሙሉ በስራ ላይ መዋል የሚቻል ነው። እያንዳንዱን ቀበሌ በጊዜያዊነት የሚያስተዳደሩ፣ በወረዳ ደረጃ የሚወከሉ ሰዎቹን እየመረጠ፣ ወረዳቸዎችም በዞን የሚወከሉትን እየመረጡ ዞኖችም ትግራይ የሚያስተዳድሩትን ሰዎች መምረጥ የሚችሉበትን ብዙ ወጪ ግዜና ጉልበት የማይጠይቅ አሰራር በስራ ላይ ማዋል ይችላል። ይህ አሰራር ወያኔ ስልጣን እንደያዘ በኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ ተደርጎ በጊዜያዊነት በደንብ ሰርቷል።
ከዚህ የአስተዳደር ስራ ጋር እያንዳንዱ ቀበሌ ሰላሙን የሚያስጠብቁለትን ራሱ የመረጣቸውን ማእከላዊ መንግስት የሚያስታጥቃቸውን ግለሰቦች እንዲመርጥ በማድረግ ማስታጠቅና ማሰልጠን ነው። ይህን አሰራር በመላው ትግራይ ለመፈጸም የሰላምና የደህንነት ችግር ካለ፣ ችግር በሌለባቸው ቦታዎች መጀመርና በሂደት ወደሌሎች ከባቢዎች ማስፋት ይቻላል። በዚህ መንገድ ለተመረጡ የአስተዳደር እርከኖች በጀት መልቀቅና በፍጥነት መንግስታዊ አገልግሎቶች እንዲጀመሩ ማድረግ ነው። ይህ ተግባር እንዲሳካ ለእውነተኛ ሰላም የቆሙ በወያኔ አመርራና ከዛም በታች ባሉ የድርጅቱ እርከኖች ውስጥ ያሉ ተባባሪዎችን ድጋፍ መንግስት በቀላሉ ማግኘት ይችላል። የመከላከያ ሰራዊቱ ባልገባቸው ቦታዎች መግባት የሚቻልበትን ከፕሪቶሪያው ስምምነት ጋር ተያይዥነት ያላቸውን ወታደራዊ ውሳኔዎች ተፈጻሚ በማድረግ በመላው ትግራይ የጸጥታ ሃላፊነቱን መረከብ ነው። ይህን ለማድረግ፣
ለ) በወታደራዊ ዘርፉ መወሰድ የሚገባቸው እርምጃዎች
• የወያኔ መሪዎች የትጥቅ መፍታቱን ስምምነት ጥሰው በተለያዩና በሚታወቁ ቦታዎች ያከማቿቸውን መሳሪያቸው በአፋጣኝ እንዲያስረክቡ ማድረግ
• በተለያዩ በሚታወቁ ቦታዎች አሰባስበው አሁንም ስልጠና የሚሰጧቸውን የሰራዊት አባላት ስልጠና አቁመው እነዚህ የሰራዊት አባላት መንግስት በሚያዘጋጀው በቀላሉ በሚታዩና መደረስ በሚችሉ ካምፖች እንዲሰባሰቡ ማድረግ፣
• ለሽብር ስራ መልምለው የሚያዘጋጇቸውን ሰዎች ስልጠና እንዲያቆሙና አባላቱ እንደሌሎች የትግራይ ሰራዊት በካምፕ እንዲገቡ፣
• የትግራይን ሰላም ማረጋጋትና ህግ የማስከበር ስራ በሁሉም አካባቢዎች በህዝብ የተመረጡ የሰላምና መረጋጋት አባላት በሃላፊነት እንዲመሩት ማድረግ፣ በእነዚህ አባላት ውስጥ በከፍተኛ ደረጃ በወንጀል የተካፈሉ የመከላለካይ የደህንነትና የፖሊስ አባላት መሳተፍ የማይችሉ መሆናቸውን ግልጽ መመሪያ ማስቀመጥ
ሐ) በኢኮኖሚ ዘርፉ መወሰድ የሚገባው እርምጃዎች
• ህዝብ ጊዚያዊ አስተዳደር ባቆመባቸው አካባቢዎች በሙሉ የመንግስት አስተዳደር ማስጀመር የሚቻልበትን በጀት በቀጥታ በመመደብ ስራ እንዲጀምሩ ማድረግ። ጤና ጣቢያዎች ት/ቤቶች ስራ እንዲጀመሩ ጊዚያዊ መንግስቱ መቀሌ ላይ እስኪቋቋም መጠበቅ አያስፈልግም።
• በትግራይ ውስጥ ህገ ወጥ በሆነ መንገድ የተሰበሰበ የውጭ ምንዛሪና የሃገር ውስጥ ገንዘብ ወርቅና ሌሎች ማእድናት ተሰብስቦ በጦርነት ለወደሙ አካባቢዎችና በጦርነቱ የተነሳ አሳዳጊ ላጡ ህጻናት እንዲሁም ጧሪ ቀባሪ ላጡ አረጋውያን ወላጆች በስራ ላይ እንዲውል ማድረግ። ይህ ሃብት ከዚህ አላማ ውጭ ለሌላ ተግባር ወደ ሌላ ቦታ የማይሄድ መሆኑን ለትግራይ ህዝብ ግልጽ ማድረግ።
• ህገወጥ በሆነ መንገድ ጦርነቱን ሽፋን ተደርጎ፣ በተዘረፈ ገንዝብ የተገዙ የህዝብ መሬቶችን ወደ ህዝብ ማስመለስ።
• በተቻለ ፍጥነት የገበያው ልውውጥ ለትንንሽ ግብይት ካልሆነ በስተቀር ሌላውን በባንክ በኩል እንዲሆን ማድረግ፣ ከተወሰነ ገንዘብ በላይ በካሽ ገንዘብ ይዞ መገኘት የሚያስጠይቅ ማድረግ፣
መ) በማህበራዊ ዘርፉ
በትግራይ ውስጥ የሚገኝ ሰላም ከማንም በላይ የሚመለከተው የሚጠቅመው ራሱን የትግራይን ህዝብ ስለሆነ የትግራይን ህዝብ ያገለለ የሰላምና መረጋጋት ስራ የህግ ማስከበር ስራ ሊኖር አይገባውም። በመሆኑም፤
• በካድሬዎች የተሞላውና በጉቦ የነቀዘው ፍርድ ቤት በጊዚያዊነት አግዶ ፍትህ ከቀበሌ ጀመሮ ህዝብ በመረጣቸው የሸንጎ አባላት በሁሉም እርከኖች እንዲሰጥ ማድረግ፣
• የህዝቡን ሰላምና መረጋጋት የማስጠበቁ ሃላፊነት ህዝብ በመረጣቸው የሰላምና መረጋጋት ኮሚቴ አባላት አማካኝነት በከፈተኛ የህዝብ ድጋፍ ተፈጽሚ በማድረግ ዘረፋን፣ ወሲባዊ ጥቃትን ሁከትና ግድያን ማናቸውም ህገወጥ የመሳሪያ የገንዝብና የሰዎችን ዝውውር መቆጣጠር፣
• የፌደራል መንግስቱ አካል ሆነው በተለያዩ የስራ መስኮች የተሰማሩ አካላት በከፍተኛ ዲሲፕሊን እና ህዝብ አክባሪነት ከህዝቡ ጋር ተቀራርበው የሚሰሩበትን ሁኔታ መፍጠርና ስራዬ ብሎ እንቅስቃሴያቸውን መቆጣጠር። ካሁኑ የጀመረ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከቁጥጥር ውጭ ሊወጣ የሚችል ከማእከላዊ መንግስት በተመደቡ አካላት ዘንድ የሚታይ ጉቦኝነት ህዝቡን ከማስመረሩ በፊት በአጭር እንዲቀጭ ማድረግ፤
• በተለይ በሙስና ስራ የተካኑና ሙስንን በመጠቀም የመንግስት ባለስልጣናትን የማጥመድ ልምድ ካላቸው የወያኔ አመራሮችና ወኪሎቻቸው፣ የፌደራል መንግስቱ የመከላከያ፣ የደህንነትና የፖሊስ አመራሮች እንዲርቁ ጥብቅ መመሪያ መስጠትና መቆጣጠር። ካሁኑ እየታዬ ያለውን አደገኛ ከሆኑ አካላት ጋር የሚደረግ መቀራረብ ባስቸኳይ ማስቆም።
• በፕሪቶሪያው ስምምነት የተቀመጠውን የሽግግር ሂደት ፍትህ የትግራይን ህዝብ ባካተተ መልኩ በፍጥነት ተግባራዊ የሚሆነበትን መንገድ አቅዶ መንቀሳቅስ።
ሠ) በዲፕሎማሲ ዘርፉ
ትልቅ ጥንቃቄ የሚያስፈገው ዘርፍ ነው። በአለም ላይ የተፈጠረው አዲስ የሃይል አሰላለፍ፣ በተለይ አሜሪካንን ብቸኛ ለእለ ሃያል ሃገር ያደረገው ዘመን ማብቃት፣ አሜሪካኖችን የሚይዙትና የሚጨብጡትን እያሳጣቸው ነው። የአፍሪካ ቀንድ አንዱ ከተጽኖአቸው ውጭ እንዲወጣ የማይፈልጉት ስትራተጂክ ቀጠና ነው። ከወያኔ ጋር የሙጥኝ ብለው የተጣበቁበት አንዱ ምክንያት ወዳጃቸው ወያኔ ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ከወጣ በዚህ ቀጠና በሎሌነት የሚያገለግለን አካል አይኖረንም የሚል ስጋት ነው። የአሜሪካኖች አካሄድ ኢትዮጵያን በኢኮኖሚና በዲፕሎማሲ መስኮች እየጨመቁ ወያኔን በኢትዮጵያ ውስጥ ተጽእኖ ፈጣሪነቱ እንዲቀጥል ማድረግ ነው።
አሜሪካኖች በእርዳታ ስም የሚሰጡትን ገንዘብ ለመልቀቅ፣ ከአለም አቀፍ ተቋማት ኢትዮጵያ ብድር እንድታገኝ ወደ አገዋ እንደትመለሰ ቅደመ ሁኔታ ማስቀመጣቸው አይቀርም። ይህ ቅድመ ሁኔታ ደግሞ ወያኔን እንደ ድርጅት ማዳን ነው። ወያኔ የሚፈልገውን በተለይ ወልቃይትን በወያኔ አገዛዝ ስር መልሶ እንዲገባ ህገ መንግስቱን እያጣቀሱ መሞገት ነው። በኢትዮጵያና በኤርትራ መሃከል ያለው ግንኙነት እንዲሻክር ነው። ቢቻላቸው የኤርትራን መንግስት ቀድሞ ሲያደርጉት ወደነበረው አፈና ከበባ ውስጥ ማስገባት ነው። ኤርትራ ከሩሲያና ከቻይና ጎን በመቆም ለወሰደቻቸው አቋሞች ዋጋ እንድትከፍል ማድረግ ነው። በመጨረሻም ትልቅ ስትራተጂያዊ ጠቀሜታ ያላትን ኤርትራን መንግስቷን በመጣል የአሜሪካ አሻንጉሊት በሆነ መንግስት መተካት ነው።
የሚያሳስቡ ነገሮች እየታዩ ነው። አሜሪካኖች የሚፈልጉትን በመስጠት ኢትዮጵያ ከገባችበት ሁለንተናዊ ቀውስ ፋታ ታገኛለች በሚል የተሳሳተ ስሌት ሊሰራ የሚችል ነገር የከፋ አደጋ ይዞ ሊመጣ እንደሚችል መታወቅ ይኖርበታል። በአለም ላይ የተፈጠረው በሁለት የተከፈለው ጎራ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚሆነውን ሁሉ አሜሪካኖች በከፍተኛ ትኩረት እንዲከታተሉት እንዳደረገ ሁሉ የሩሲያውና የቻይናውም ጎራ ይከታተሉታል።
ቻይና እና ሩስያ በተከታታይ ምእራባውያኑ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ የኢትዮጵያ ጉዳይ እንዲነሳና በኢትዮጵያ ላይ ጎጂ ውሳኔ እንዲወሰን የተደረገውን ተደጋጋሚ ጥረት ኢትዮጵያን ወግነው አክሸፈዋል። ኤርትራ በክፉ ቀን ከኢትዮጵያ ጎን በመቆም መስዋእተነት ከፍላ አለኝታነቷን አሳይታለች። እነዚህ አካላት የኢትዮጵያ መንግስት ውለታቸውን ዘንግቶ የአሜሪካ ጉዳይ አስፈጻሚ ወደ መሆን ሲሄድ ዝም ብለው የሚያዩት አይሆንም። የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ አንዱን መምረጥ ይኖርበታል። አሜሪካኖች የአጭርና የረጅም ጊዜ ጥቅሞቻቸውን አስልተው ኢትዮጵያ እንድትፈጽም የሚፈልጓቸውን ነገሮች መፈጸም ወይም አሜሪካኖች የሚጠይቋቸውን ፍትሃዊ ያልሆኑ ጥያቄዎች አልቀበልም በማለት መከፈል የሚገባውን መስዋእትነት ለመክፈል መዘጋጀት።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ እየሄደበት ያለው መንገድ አሳሳቢ ነው። ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲ ስራዋ ሩቅ ካሉ ሃገሮች ይልቅ በአካባቢዋ ካሉት ጎረቤት ሃገሮቿ ጋር የሚኖራት መልካም ግንኙነት ዘለቄታ ጥቅሟን የሚያስከብር መሆኑን ማወቅ ይኖርባታል። ለአሜሪካኖች ተብሎ ከየትኛውም ሃገር ህዝብ በላይ የኢትዮጵያ ወዳጅ ከሆነ ከኤርትራ መንግስትና ህዝብ ጋር መቃቃር ለኢትዮጵያ ትልቅ ጉዳት የሚያስከትል ነው።
ኤርትራ አሜሪካ ብቸኛዋ ልእለ ሃያል ሃገር በነበረችበት ወቅት ተገልላ ስትኖር ከነበረበት አፈና የሚያወጣ አዲስ የአለም ስርአት ተፈጥሮላታል። እሷም ጥቅሟን ግምት ውስጥ በማስገባት አዲስ በተፈጠረው የአለም ጎራ ውስጥ የወሰደቻቸው በብልሃት የተሞሉ አቋሞች ትልልቅ ሃያላን ወዳጆች እንድታፈራ አድርጓታል። ዛሬ አሜሪካኖች ኤርትራን ከዚህ ቀደም ሲያደርጉት እንደነበር ማድረግ የሚችሉበት ሁኔታ የለም። የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ ይህን ሃቅ ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርበታል።
ዲፕሎማሲያችን አሜሪካ ላይ መለጠፍ ሳይሆን ከአሜሪካ ተጽእኖ እንዴት መላቀቅ ይቻላል በሚል ስሌት መመራት አለበት። ኢትዮጵያ በጦርነቱ ወቅት ከአሜሪካን ተጽእኖ ራሷን ለማላቀቅ ተፈጠሮላት የነበረውን እድል በማባከኗ፣ ወደፊት የምናየው ይሆናል፣ ብዙ ዋጋ ትከፍልበታለች። የበቃ እንቅስቃሴ በአጭር እንዲቀጭ በመደረጉ የምናዝንበት ቀን ይመጣል።
ሃቁ በአሜሪካ ተጽእኖ ስር ወድቀው የበለጸጉ፣ ሰላም ያገኙ፣ ዴሞክራሲያዊ ስርአት የገነቡ፣ የህዝባቸውን መብቶች ያስከበሩ ታዳጊ ሃገሮች ቀርቶ አንድም ሃገር የለም። ቢኖሩ ኖሮ የወይኔዋ ኢትዮጵያ አንዷ ትሆን ነበር። ይህን ሃቅ አገናዝቦ ብልሃትና ጥበብ በተሞላው መንገድ የዲፕሎማሲ አቅጣጫቻን ማስተካከል ይገባል። ይህ ጉዳይ ራሳቸው አሜሪካኖቹ እንደሚሉት “እንደሚናገሩት ቀላል እንዳልሆነ” ይገባኛል። ከባድ ያደረግነው እኛው ራሳችን መሆናችንን መገንዘብ ግን ይገባናል።
ስላነበቡ አመሰግናለሁ
አንዳርጋቸው ጽጌ
=================////==========