ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, March 21, 2023

የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በማኅበራዊ ሚድያ ብጥስጣሽ መልዕክቶች ከመመዘን በመውጣት ኢትዮጵያን ብንጠቅማት እጅግ የተሻለ ነው።




=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

የሃገራችንን የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታዎች መለኪያዎቻችን አጠቃላይ ስዕል ከሚያሳዩ ዕይታዎች ይልቅ፣ በእየዕለቱ የውንብድና ሥራ በሕዝብ ላይ የሚሰሩ ለጊዜው በመንግስት መዋቅር ውስጥ ለመሸሸግ ህገመንግስቱም የክልል አደረጃጀትም የፈቀደላቸው በሚሰሩት ግፍ የኢትዮጵያን የወደፊት የፖለቲካ ሂደት ሙሉ በሙሉ የጨለመ አድርጎ ማሰብ አጠቃላይ ሁኔታውን በሚገባ ካለማየት የሚመጣ ነው። አንድ ምንም ጥያቄ ውስጥ የማይገባው ጉዳይ የሕግ የበላይነት ለማስፈን የራሱ የሆነ ፈተና ገጥሞታል። ይህ ፈተና የአፈጻጸም ብቻ ሳይሆን የታችኛው የክልሎች መዋቅር ከላይ ካለው በሙስና ከተነከሩ ባለስልጣናት ጋር እየተናበበ የራሱን የጎሳ አሰራር ለመዘርጋት በሁሉም መስክ ሲሮጥ ይታያል። ይህ ቡድን በምንም ፍጥነት ቢሮጥ ግን የሕዝብ ተቀባይነት አላገኘም። አሁናዊ ሁኔታዎችም የሚያሳዩን ይህንኑ ነው።ስለሆነም የኢትዮጵያዊነት መንገድ ከምንጊዜውም በላይ የበላይነቱን እየያዘ መሄዱ ያለው የህዝብ ነባራዊ ሁኔታ የሚያሳየው ነው።

ትልቁ የሃገራችን የፖለቲካ ተስፋውም ይህ የበታኝ ኃይሎች አካሄድ በሕዝብ ተቀባይነት አለማግኘቱ ነው። የዛሬ አራት ዓመታት የነበሩ እጅግ ያገነገኑ የብሔርተኝነት ስሜቶች ዛሬ በእዛ ደረጃ አይደሉም። ይህ ማለት በሕዝብ ደረጃ ማለቴ ነው እንጂ የጎሰኝነት ፍም እንዳይጠፋ ከሚያርገበግቡት የጎሳ የፖለቲካ ድርጅቶች እና ቡድኖች አንጻር አይደለም። እነኝህኞቹ አሁንም ይህንኑ የጎሳ ፍም ወደ ምጣኔ ሃብት አደረጃጀት እንዲሰርጽ እሩጫ ላይ ናቸው። ይህ በተለይ በኦሮምያ ክልል በቡድን ደረጃ የነበረው አስተሳሰብ አሁን የክልሉ ምክርቤት እና የክልሉ ቢሮክራሲ ሁሉ እንዲወታተብ የማድረጉ ሂደት እንደቀጠለ ነው። ይህም ግን አሁንም በኦሮምያ ክልልም ህዝብ በክልሉ የጽንፍ አመራር ተማሯል ብቻ ሳይሆን እራሱም በጎሳ ስም እየተዘረፈ በመሆኑ ክልሉ ላወጣው አደረጃጀት ሳይቀር ከጉጂ እስከ ባሌ ያሉ አባገዳዎች ሳይቀሩ ከፍተኛ ተቃውሞ መነሳቱ የሚያሳየን የጎሳ እና የጽንፍ አቀንቃኞች የሚሂዱበት መንገድ ሌላውን ሲሰድቡ በቀጣይነት የራሳቸውን ቆምንለት ያሉትን ህዝብ ለመብላት ሲነሱ እራሱ ህዝብ እንደሚበላቸው ማሳያ ነው። ይህንን በህወሃት መመልከት ይቻላል። ህወሃት ቆምኩለት ያለውን ህዝብ አደህይቶ በዛሬው ዕለት ሳይቀር የህወሃት ታጣቂ የነበሩ በመቀሌ ጎዳና ሰልፍ የወጡት በራሱ በህወሃት ላይ ነበር። ህወሃትም አስለቃሽ ጭስ የረጨው በእነኝሁ የእርሱን ስልጣን ለመጠበቅ አካለ ስንኩል በሆኑት ላይ ነበር።

የእዚህ ምጥን መልዕክት ማጠቃለያ ዋናው ሃሳብ የጎሳ አደረጃጀቶች ምን ያህል የግፍ ዓይነት የእኔ አይድለም በሚሉት ላይ ቢያሳዩም ይህ የጥንካሪያቸው መለኪያ አይደለም። ይህ የበለጠ ከራሳቸው ጎሳ ጋርም የሚያጣላ ብቻ ሳይሆን የሚዘርፉትን ዝርፍያ መሸፈኛ ካባ የሌላውን ጎሳ በማጥቃት እና ጠላት በመፍጠር ምን ያህል ለመሸፈን ቢሞክሩ መጨረሻ እኝሁ ወንጀለኞች የሚበሉት በራሳቸው ቆመንልሃል ባሉት ህዝብ የውሸት መደለያቸው ተንጠፍጥፎ ሲያልቅ ነው።ይህንን በትግራይም በኦሮምያም እያየነው ነው። በኦሮምያ ክልል ከጀዋር እና የጨፌ ስግስግ አክራሪዎች ይልቅ የጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ የመደመር ሃሳብ በከፍተኛ ደረጃ በክልሉ ወጣቶች ዘንድ መነጋገርያ እና የተሻለ እንደሆነ በአማራጭነት እየተወሰደ ነው። ይህ እነጀዋር ዱላ ይዞ የሰው አናት እንዲመታ ሲመክሩት የነበረውን ወጣት በኢትዮጵያዊ ሃሳብ እያስተማረ ተንኮላቸውን ስላመከነባቸው ብሽቀታቸው ልክ አጥቷል። ሰሞኑን ከእነጀዋር ቡድን የተሰማው የጽሁፍ ጋጋታም አንዱ ምክንያት ይሄው ነው። በእዚህ ጊዜ የኢትዮጵያውያን የእኩልነት እና የጋራ ተጠቃሚነት እንዲመጣ የሚናፍቁ ሁሉ የኢትዮጵያ ጠላቶች እንድንፈስ በሚፈልጉት ቦይ ላለመፍሰስ የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በማኅበራዊ ሚድያ ብጥስጣሽ መልዕክቶች ከመመዘን መውጣት፣ስንጥቅ ልዩነቶችን ከሚያሰፉት ውስጥ ሳንሆን ስንጥቆችን ከሚደፍኑት መሆን ነው መፍትሄው።ተስፋ የሚያስቆርጡ ጉዳዮችን ስናጎላ ብንውል የአሁኑን ብቻ ሳይሆን መጪውን ትውልድ እናመክናለን። ስለሆነም ሁኔታዎች በትክክል መመዘን እና የኢትዮጵያን አንድነት ለመፈታተን የሚሰሩ ስራዎችን ስልታዊ በሆኑ ሁሉን ባቀፈ እና ያሉትንም መልካም ጅምሮች በማበረታታት ወደፊት በመሄድ ሃገር ይሰራል፣ የኢትዮጵያ ጠላት መርዝ ይመክናል። ክፉውን ብቻ እያየን ዘለቄታዊ መልካም ሥራዎችን የምንሸፍን እንዳንሆን እና ካበላሸን በኋላ እንዳለፈው ትውልድ የምንቆጭ እንዳንሆን ዛሬን በሚገባ መመርመር፣በተስፋ እና በመፍትሄ አመንጪነት ስንጥቆችን የምንደፍን እና ትውልዱ መልካም ሥራ የሚሰራበትን ጊዜ በማኅበራዊ ሚድያ ክፉ ወሬዎች በማስጮህ ወደ የበለጠ ችግር እንዳይሄድ መንቃት ያስፈልጋል።የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ በማኅበራዊ ሚድያ ብጥስጣሽ መልዕክቶች ከመመዘን በመውጣት ኢትዮጵያን ብንጠቅማት የበለጠ ጠቃሚ ነው። 

===================////====================== 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።