አፈ ጊንጥነቱ እና የውርደት ካባው
አፈ ጊንጥነት የሚለውን ቃል ለነገር ሰሪዎች እንዲመጥን አድርገው በልካቸው የገለጡት ኢትዮጵያዊው ሎሬንት ጸጋዬ ገብረመድሕን መሆናቸውን ከሰሞኑ አንድ ኢትዮጵያዊ የፍልስፍና ምሑር ሲናገሩ ሰምቼ በጣም ሲገርመኝ ነበር። ኢትዮጵያን ኢትዮጵያዊነትን ለማጎስቆል የሚፈልጉ ሁሉ የለመዱት እና የሚሰነዝሩት ያላቸውን አፈ ጊንጥነት ነው።ኢትዮጵያን ያሉ የቀድሙ የኢትዮጵያ መሪዎች የቀደሙት ባንዳዎች እና ባዳዎች በአፈ ጊንጥነት ሊነድፏቸው ሞክረዋል።ሆኖም ግን ታሪክ እውነትን ያነጥራልና ከኢትዮጵያ ታሪክ ሊፍቋቸው አልቻሉም። በዘመናቸው ግን ለኢትዮጵያ የበለጠ እንዳይሰሩ እንቅፋት አልሆኑም ማለት አይደለም። አፈ ጊንጦች በየዘመኑ ነበሩ። ዛሬም አሉ።
በዘመናችን በኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑት ላይ የተለያየ የሃሰት ስሞችን እየለጠፈ ኢትዮጵያን ወደ የበለጠ መከራ መክተት ዓላማው ያደረገው ቡድን በመጀመርያ የአፈ ጊንጥነት ካራውን በማኅበራዊ ሚድያ፣ በመቀጠል ወደ የኢትዮጵያ ማኅበራዊ ዕሴቶች ውስጥ ማለትም ከኃይማኖት ተቋማት እስከ ዕድር እና የተለያዩ ማኅበራዊ አደረጃጀቶች ውስጥ እየገባ ለኢትዮጵያ በጎ ያሰቡትን ሁሉ ሲነድፍ፣ሕዝብ በማያባራ የጦርነት ቋያ እንዲገባ ሲያደርግ፣ቡድኑ ግን እራሱን በዲያስፖራ እና ሀገርቤትም በስውር እራሱን ደብቆ ሀገርና ህዝብ ሲያምስ ከረመ። ይህ የማተራመስ ካራው ግን ቀስ በቀስ እየተነቃበት ሲመጣ የውርደት ካባውን ከፍና ዝቅ እያደረገ የሚሸሸግበት ጥግ ሲፈልግ ከረመ።የሚሸሸግበት ሲያፈላልግ ምቹ ሆኖ ያገኘው ደግሞ ስመ ጥሩ የሆኑ የኢትዮጵያ የኪነጥበብ ሰዎችን ነው። ከእዚህ ውስጥ በሰሞኑ አዲስ ዜማ ይዞ ብቅ ያለውን ቲዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) ላይ ለመንጠላጠል ያለው መጋጋጥ አስገራሚ ብቻ ሳይሆን አስቂኝ ሆኗል።
በዘመናችን በአፈ ጊንጦች ኢትዮጵያዊ አጀንዳቸውን ለማጣጣል ዘመቻ ከተከፈተባቸው ውስጥ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና የማኅበራዊ ጉዳይ አማካሪ ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ይገኙበታል።
የአፈ ጊንጡ ቡድን ከላይ የተጠቀሱት ሁለት ኢትዮጵያውያን ላይ የነገር መርዞቹን ሲረጭ ከረምረም ብሏል።
አፈ ጊንጦች በጠ/ሚ/ዐቢይ ላይ የረጩት የሃሰት ወሬ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ላይ የተሰነዘሩት ሃሰተኛ የአፈ ጊንጦች ወሬ ውስጥ ፡
- የብሔር እና የጎሳ ፖለቲካ አራማጅ ናቸው፣
- ከጀዋር የጽንፍ ሃሳብ ጋር አብረው ይሄዳሉ፣
- ኢትዮጵያን መከፋፈል ይፈልጋሉ፣
- የእገሌ ጎሳ ጠላት ናቸው፣
- የእገሌ ጎሳ ወዳጅ ናቸው፣
- ባሕርዳር ላይ፣ወለጋ ላይ አዲስ አበባ ላይ የተገደለው ሁሉ በእሳቸው ነው፣
- ሰሞኑን በኢራን የተዘጋው የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ በእሳቸው ነው ለማለት ሩብጉዳይ የቀረው አሉባልታ ወዘተ በአፈ ጊንጦች ተነዛ።
ይህንን ሁሉ አሉባልታ ዛሬ ላይ ውሸት መሆኑ ታውቆ እውነታውን ጊዜ ፈታው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሕብረ ብሔራዊነትን፣ኢትዮጵያዊነትን እና አብሮነት መመርያቸው መሆኑን በሦስት መንገዶች አረጋገጡ። አንድ ሰው በሦስት ነገር አንድን ጉዳይ ካረጋገጠ ምንም ጥያቄ አይነሳበትም።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በሦስት መንገዶች የአፈ ጊንጦችን አሉባልታነት አረጋግጠዋል። እነርሱም፡
1/ በቃል በመናገር (በሁሉም ንግግሮቻቸው)፣
2/ በመጽሐፍ መልክ መደመር በሚል ተከታታይ ጽሑፎቻቸው እና
3/በተግባር የኢትዮጵያን ልማት ለሁሉም አካባቢ በተቻለ እንዲዳረስ በማድረግ እና የጋራ የፖለቲካ ዐውድ ለመፍጠር በሚያደርጉት ተግባር እና መጪ ዕቅዶች ሁሉ የአፈ ጊንጦች ወሬ ውሸት መሆኑን አረጋግጠዋል።
ይህ እውነት የማይዋጥለት ካለ እራሱን በመዳፉ ሸፍኖ የገዛ ሕሊናውን ለማታለል የሚሞክር ሰው ይመስላል።
በሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ላይ የተሰነዘሩ የአፈ ጊንጦች ወሬዎች
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ እና በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ጥልቅ ምርምር በማድረግ የሚታወቀውን ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት ላይ ሆን ተብለው የተነሱ የአፈ ጊንጦች ወሬዎች ውስጥ ሦስቱን የውሸት ወሬዎች በናሙናነት እዚህ ላይ እጠቅሳለሁ።
1) ውሸት አንድ ፡ ዳንኤል ክብረት ''የትግራይ ሕዝብ መጥፋት አለበት'' አለ የሚለው የውሸት ትረካ
ይህች የውሸት ትረካ የተጀመረችው ሕወሃት በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ጦርነት ባወጀበት እና የሀገር ህልውና ጦርነት በተጀመረበት በ2014 ዓም ላይ ነበር። በእዚህ ጊዜ ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት የሕወሃት ህልውና ለሃገር አደጋ መሆኑን እና የድርጅቱ እና በታኝ አስተሳሰብ መኖር ስለማይጠቅም ከምድር ገጽ መጥፋት አለበት በሚል በአንድ የመከላከያ ሰራዊት ስብሰባ ላይ የገለጸውን አገላለጽ እነ አፈ ጊንጦች ገልብጠው ''የትግራይ ህዝብ ይጥፋ አለ'' በሚል ማውራት ጀመሩ። እውነታው ግን ለህወሃት እና በታኝ ሃሳቡ የተነገረ እንጂ ህዝብ ላይ ያነጣጠረ አልነበረም።ይህ ንግግር ዛሬም በድምፅ እና በጽሑፍ የሚገኝ ሆኖ ሳለ። አሁን ድረስ አውቀው ይህንኑ የሚያስተጋቡ አፈ ጊንጦች አሉ።
2) ውሸት ሁለት ፡ ዳንኤል ክብረት ለሀገር ታሪክ የሰራውን የጥንቱን ''ፋኖን '' እና የአማራን ሕዝብ አጥላላ የሚለው የውሸት ተረክ ነው።
ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በጻፋቸው መጽሐፎቹም ሆኑ ማብራርያዎቹ የኢትዮጵያ የነፃነት ዕሴት የሆነውን እና በተለይ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መግቢያ ላይም ሆነ ቀደም ባሉ ዘመናት ለኢትዮጵያ ኅልውና ዋስትና እና ማገር የሆነውን ''ፋኖ'' የተሰኘውን የኢትዮጵያን ነፃነት ያስከበረ ታሪካዊ አደረጃጀት አጣጥሎ አያውቅም።
የዳንኤል ክርክር በዘመናችን በአማራ ክልል የተነሳው ታጣቂ ፋኖ ሳይሆን ጃውሳ ነው። ሁለቱ በትርጉም ይለያያሉ ነው።
ባጭሩ በዳንኤል አገላለጥ በአማራ ክልል ውስጥ ጥንት የኢትዮጵያን ነጻነት ያስጠበቀው በፋኖ ስም የሚነግደውና በአማራ ህዝብ ላይ አሁንም ድረስ በአንዳንድ ቦታዎች ህዝቡን የሚያውከውን ታጣቂ በፋኖ ስም የሚነግድ እንጂ የታሪካዊው ፋኖ ስም ይዞ መንቀሳቀስ የማይችል ነገር ግን የጃውሳ ስብስብ ነው በሚል ነበር ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በተለያዩ ጊዜዎች የገለጠው። አፈ ጊንጡ ቡድን ግን ዳንኤል ክብረት የአማራ ህዝብ ላይ የጥላቻ ንግግር የተናገረ በማስመሰል በሃሰት ያላለው እና ያልተናገረው የለም። ለሁሉም ጊዜ ይፈታዋል ነውና። በአሁኑ ጊዜ በአማራ ክልል ያለው የከተማ እና የገጠር ነዋሪ በጥንቱ ፋኖ እና በጃውሳ መካከል ያለው ልዩነት በሚገባ እንደገባው ወረድ ብሎ ህዝቡን መጠየቅ ነው።በሚልዮን የሚቆጠር የአማራ ክልል ወጣት ከትምሕርት ገበታ ለሁለት እና ለሦስት ዓመታት ያፈናቀለው፣ህዝቡን እያገተ የገንዘብ ምንጭ ያደረገው እና ዛሬም በሕዝቡ ስም እየነገደ ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር የሚሞዳሞደው ፋኖ ሳይሆን ጃውሳ መሆኑን ለማወቅ ብዙ ምርምር አይጠይቀውም።
3) ውሸት ሦስት ፡ ዳንኤል ክብረት ''በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሀገር ቤት ለምን ቅበሩን ይላሉ'' አለ በሚል የተነገረው የሃሰት ወሬ ነው።
እዚህ ላይ ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል ክብረት በአንድ የምሁራን ስብሰባ ላይ በኢትዮጵያ ላይ የባንዳነት ተግባር የሚፈጽሙትን በተለየ ከጠቀሰ በኋላ እነኝህ ግለሰቦች በኋላ (ኢትዮጵያን ሲያቆስሉ ቆይተው) መልሰው ለምን ለቀብር ሲሆን ኢትዮጵያን ይፈልጓታል በሚል ''ለምን ቅበሩን ያላሉ?'' በሚል ያብራራውን ዲያስፖራው በኢትዮጵያ አይቀበር አለ እያለ የአፈ ጊንጡ ቡድን እየተቀባበለ ሲናገር ከረመ። ሙ/ጥ/ዲ/ዳንኤል የተናገረው ምንድን ነው? ብሎ የማያደምጠው እና ገባ ብሎ የንግግሩን ጭብጥ መነሻ ሳይመለከት የሚያወራውም እየተቀባበለ ''ዲያስፖራው በሀገርቤት አይቀበር'' ዳንኤል አለ አሉ እያለ በየስታርባክስ እና ቡና ቤት ማውራት ጀመረ። ሆኖም ግን በዕለቱ ዳንኤል ሲናገር ከቀብር ጉዳይ በፊት ያነሳው እና ያወራው ኢትዮጵያን በውጭ ሆነው ስለሚይቆስሉ እና ስለከዷት የባንዳና የባዳ ጉዳይ እንጂ መላው የዲያስፖራ ማኅበረሰብን እንዳልወቀሰ ግልጽ ነው። ዛሬም ድረስ እውነቱን እያወቁ ባላቸው የፖለቲካ ልዩነት እና ተራ ጥላቻ ከዚያም ሲያልፍ ላደሩበት የባንዳ ቡድን አስፈጻሚነት ሲሉ ብቻ ያልተነገረውን እንደተባለ ሲያወሩ የምንሰማቸው እነኝሁ አፈ ጊንጦች ናቸው።
ለማጠቃለል አፈ ጊንጦች የኢትዮጵያ የታሪክ አተላዎች ናቸው።የቀደሙ የኢትዮጵያ መሪዎችን በውሸት ነድፈዋል፣ለኢትዮጵያ የቆሙላት ሊቃውንቷን በወሬ ለመውጋት ሞክረዋል።አንዳንዶቹን ከመንገዳቸው አሰናክለዋል፣የቀሩትን አሁንም ድረስ ህዝብ በሚገባ እንዳይዘክራቸውና ከጀመሩት ስራ እንዳይማር በውሸት ትርክት ጋርደውበታል። አፈ ጊንጦች በባንዳነት እና የባዕዳንንን ተልዕኮ ለማስፈጸም ላይና ታች ሲሉ የኖሩ እና ዛሬም የሚሞክሩ ናቸው። የ21ኛው ክ/ዘመን ትውልድ እንደቀደስሙት አይደለም። የመረጃ እና ነገሮችን የማመዛዘን ከፍ ሲልም እውነትን የማንጠር ችግር የለበትም።ለእዚህም ነው።አፈ ጊንጦች የቱንም ያህል ቢጋጋጡ አይሳካላቸውም። ስላልተሳካላቸውም ነው መግቢያ መሸሸግያ ሲያጡና በውሸት ያወሩባቸው የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች በሥራ እየቀደሟቸው ህዝብና ሀገርን እያስደመሙ ሲያጡ በቴዲ ሙዚቃ ላይ ለመንጠልጠል የተውተረተሩት። እርሱም አልተሳካም። ምክንያት ቴዲ እራሱም አሳፈራቸው።ከኢትዮጵያዊነት ማማ ላይ አልወርድ አላቸው። ይሄው ነው።
=================///============
