ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, February 21, 2014

ካፒቴን ኃይለመድህን አበራ ለኢትዮጵያ ተላልፎ አይሰጥም።ከጉዳዩ ጋር የተያያዙ አዳዲስ ለውጦች (ጉዳያችን ጡመራ GUDAYACHN BLOG ዓርብ፣ የካቲት 14/2006 ዓም)

ካፒቴን ኃይለመድህን አበራ (ፎቶ ከማኅበራዊ ድረ-ገፅ)

የካቲት 10/2006 ዓም የኢትዮጵያ አየርመንገድ ንብረት የሆነውን ቦይንግ 767 አይሮፕላን ከኢጣልያዊው አብራሪ ጋር ይዞ ከአዲስ አበባ ወደ ሮም ያመራ የነበረው እና  ጄኔቭ ስዊዘርላንድ ላይ እንዲያርፍ ያደረገው ካፒቴን ኃይለመድህን አበራ በመልካም የጤንነት ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ እና የስዊዘርላንድ መንግስት ጠበቃ የመደበለት መሆኑ ታወቀ።

ካፒቴን ኃይለመድህን አበራ ለኢትዮጵያ ተላልፎ አይሰጥም።

ቀደም ብሎ አቶ ሬድዋን ሁሴን የኢትዮጵያ መንግስት ቃል አቀባይ ድርጊቱ በተፈፀመበት ቀን የኢትዮጵያ መንግስት  አንዳንድ የአለም አቀፍ ውሎችን ተንተርሶ የስዊዘርላንድ መንግስት አሳልፎ እንዲሰጥ እንደሚጠየቅ ፍንጭ ሰጥተው ነበር።ሆኖም ግን የስዊዘርላንድ መንግስት በምድሩ ላይ ያረፈው አይሮፕላን ጉዳይ የሚዳኘው በሀገሩ ፍርድ ቤት መሆኑን አምኖ ምርመራው ከማለቁ በፊት ለካፒቴን ኃይለመድህን አማካሪ ጠበቃ መድቦለታል።በብዙዎች እምነት ምርመራው እየተከናወነ ጠበቃ ማግኘቱ በብዙ መንገድ ካፒቴን ኃይለመድህንን እንደሚረዳው ያስረዳሉ።

በሌላ በኩል ትናንት የካቲት 14/2006 ዓም ኢሳት ቴሌቭዥን በሰበር ዜና እንደገለፀው ለስዊዘርላንድ ፈድራል ፖሊስ ዲፓርትመንት በኢሜል የካፕቴን ኃይለመድህንን ጉዳይ በጠየቀው መሰረት ክፍሉ በፅሁፍ ምላሽ መስጠቱን ለማወቅ ተችሏል።በምላሹ መሰረት ኃይለመድህን በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኝ፣ እስካሁን ወንጀለኛ ተብሎ እንደማይጠራ፣ምርመራው መቀጠሉን፣ጠበቃ እንደተመደበለት እና ፍርድቤት ሲቀርብ ቀሪው የፍርድቤት ተግባር እንደሆነ ያብራራል።

ዛሬ '' የአጃንስ ፍራንስ ፕሬስን'' ዘገባ ጠቅሶ ''ሲ ቢ ኤስ8''  እንደገለፀው ደግሞ የስዊዘርላንድ ፍርድ ቤት ካፒቴኑ በማረፍያ ቦታ እንዲቆይ እና ምርመራው እንዲቀጥል አዟል።ይህ ማለት ከማዕከላዊ የፖሊስ ምርመራ ጣብያ ወደ ማረፍያ ቤት የመዞሩ ሁኔታ  ቀድሞ ከነበረበት የተሻለ ማረፍያ እንደሚሆን ይገመታል።ምናልባት ማረፍያ ቦታው ላይ የተሻለ የግለሰብ ነፃነት የሚሰጠው እና ለምሳሌ አለም አቀፍ ዜና ለመከታተል ይረዳው ይሆናል የሚል ግምት አለ።በእርግጥ በምዕራቡ አለም እነኚህ መብቶች በምርመራም ላይ ሳለ የማይከለከሉ መሆናቸው ይታወቃል።

ድርጊቱን በተመለከተ የኢትዮጵያውያን ስሜት 

በሌላ በኩል የአይሮፕላኑ ጄኔቭ ላይ ማሳረፍ ተከትሎ በሀገር ቤት የተለያዩ ስሜቶች መፈጠራቸውን ከሀገርቤት የሚወጡ ዘገባዎች ያመላክታሉ።ስሜቶቹ ''ኢትዮጵያን በዓለም አዋረደ'' ከሚሉት የተወሰኑ በቅን ከሚሰነዘሩ  እስከ መንግስት ደጋፊዎች የሚሰሙ  ቢሆንም በአብዛኛው በውጭም ሆነ በሀገር ቤት ያለው ሕብረተሰብ ዘንድ ግን አንዳች አደጋ ካለመድረሱ እና የደንበኞችን ክብር ሳያዋርድ በሰላም ማከናወኑ ከሁሉም በላይ ደግሞ የሚልዮን ኢትዮጵያውያንን ብሶት ለማሰማት የቻለ ጀግና! ነው ብለው የሚናገሩ እና የሚፅፉ ናቸው። ከእዚህ የተረፉት ጥቂቶች ደግሞ ''ቆዩ እስኪ እርሱ የሚለውን እንስማ'' አንቸኩል የሚሉ ናቸው።

''የኢትዮጵያ አየር መንገድን የሶስት ሺህ  ሰራተኞችን ዋይታ ነው ይዞ የመጣው''አሁን ስዊዘርላንድ የሚኖረው ሚካኤል መላኩ የተባለ  የቀድሞ የአየር መንገዱ የበረራ ደህንነት ሰራተኛ

አሁን ስዊዘርላንድ የሚኖረው ሚካኤል መላኩ የተባለ  የቀድሞ የአየር መንገዱ የበረራ ደህንነት ሰራተኛ ለኢሣት በሰጠው ቃል ደግሞ አየር መንገዱን ከዘጠኝ አመት በላይ እንደሚያውቅ ጠቅሶ በአየር መንገዱ ውስጥ ከፍተኛ የአስተዳደር እና የዘር መድሎ ችግር መኖሩን ይህም ከስርዓቱ ጋር የተያያዘ መሆኑን፣ለእዚህ ማሳያ ያደረገው ጠንካራው የአየር መንገዱ የሰራተኛ ማኅበር በትናንሽ ማለትም የአብራሪዎች ሰራተኛ ማህበር፣የአስተናጋጆች የሰራተኛ ማህበር፣የቴክኒሻኞች የሰራተኛ ማህበር እየተባለ ለስርዓቱ የታዘዙ ካድሬዎች እየመሩት መሆኑን አብራርቷል። ይሄው የቀድሞ የአየር መንገዱ የበረራ ደህንነት ሰራተኛ ሚካኤል መላኩ ስለ ካፒቴን ኃይለመድህን ሲናገር  ደግሞ እንዲህ አለ -
''አውቄዋለሁ።በጣም ነው የማደንቀው የሚገርምህ እስከ ሮም ድረስ ከሁሉም የአየር ትራፊኮች ከራዳር እንዲሰወር አድርጎ ነው የበረረው በኃላ ነው ራዳር እንዲታይ ያደረገው። ከፍተኛ የመብት መጣስ ደርሶበት ነው።ሌላ ሊሆን አይችልም።የኢትዮጵያ አየር መንገድን የሶስት ሺህ  ሰራተኞችን ዋይታ ነው ይዞ የመጣው''


ጉዳያችን
የካቲት 14/2006 ዓም
(ከጉዳያችን ማናቸውንም ፅሁፍ ድረ-ገፅ ላይ ሲለጥፉ ምንጩን መግለፅ ጨዋነት ነው)


Wednesday, February 19, 2014

''ካፒቴን ኃይለ መድህን በአጎቱ ሚስጥራዊ ሞት ይሰጋ የነበረ ሰው ነበር።'' 'ስካይ ኒውስ ''በክፍልም ውስጥ ሆነ በሥራ ላይ 'ስማርት'የሆነ ልጅ ነበር'' አብሮት የተማረ እና የስራ ባልደረባው የነበረው ረ/አብራሪ ምስጢር ታዬ(ጉዳያችን አጭር ጥንቅር)




ዛሬ የካቲት 12/2006 ዓም 'ስካይ ኒውስ' ስለረዳት አብራሪ ኃይለ መድህን ጉዳይ አጎቱ አቶ ዓለሙ አስማማው ለአሶሼትድ ፕሬስ  በስልክ የሰጡትን ቃለ መጠይቅ መሰረት አድርጎ እንዲህ ብሏል።

''ኢትዮጵያዊው ፓይለት በአጎቱ አሟሟት ጉዳይ ጥርጣሬ (ስጋት ነበረበት)''

''የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ መምህር የነበሩት ዶ/ር እምሩ ስዩም ከቤታቸው ወደ ሚያስተምሩበት የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ሲሄዱ ሞተው ተገኝተዋል''

''የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ድረ-ገፅም ይህንንኑ አረጋግጦ ረዳት ፕሮፌሰር አለሙ አስማማው ጃንዋሪ 1 ቀን በድንገት ማለፋቸውን ፅፏል።''

''ሰኞ እለት የኢትዮጵያ መንግስት ቃል አቀባይ አቶ ሬድዋን ካፒቴን ኃይለ መድህን ከእዚህ በፊት ምንም አይነት የተመዘገበበት የወንጀል ሪከርድ የለም ብለዋል'' የስካይ ኒውስ ዜና መጨረሻ።

ከእዚሁ ጋር ተያይዞ ኢሳት በትናንትና ምሽት የራድዮ ዘገባው በአሜሪካ ከምትኖር የቤተሰቡ አባል ጋር እና አብሮት ከተማረ እና ከሰራ በኢንዶኔዥያ በሥራ ላይ ከሚገኘው ረዳት አብራሪ ምስጢር ታዬ ጋር ስለ ካፒቴን ኃይለ መድህን ቃለ መጠይቅ አድርጎ ነበር።

በቃለመጠይቁ ላይ የቤተሰብ አባሉም ሆኑ የትምህርት ቤት እና የስራ ባልደረባው ቃል አንድ ነው።በጣም ጎበዝ እና ሃገሩን የሚወድ ሰው የነበረ መሆኑን ሁሉም አረጋግጠዋል።

በተጨማሪም የተለያዩ ዘገባዎች ሰሞኑን ስለ ወጣቱ ካፒቴን ሲገልፁ-ኃይለ መድህን ጎበዝ፣ሃገሩን የሚወድ፣በአስራሁለተኛ ክፍል  የመልቀቅያ ፈተና ላይ በሙሉ ''ኤ'' በማምጣት ወደ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ገብቶ የኢንጅነሪንግ ትምህርት መማሩን እና በመጨረሻ ላይ የአብራሪነት ስልጠና ለመውሰድ ወደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ እንደገባ፣ከሀገሩ ውጭ የመኖር አንዳች ፍላጎት እንደሌለው፣በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የሚፈፀመው ጭቆና ግን እረፍት የነሳው ኢትዮጵያዊ መሆኑ ተነግሯል።በኢትዮጵያ አየር መንገድ የደሞዝ እስኬል መሰረት የአንድ ረዳት አብራሪ ደሞዝ ከ 27 ሺህ እስከ 30 ሺህ ብር እንደሚደርስ ዘገባዎች ያሳያሉ።

የዘገባው ምንጮች -

     ስካይ ኒውስ February 19/2014 እ ኤ አቆጣጠር  http://www.skynews.com.au/world/article.aspx?id=951493

    ኢሳት ራድዮ የካቲት 11/2006 ዓም  (February 18/2014)

ጉዳያችን 
የካቲት 12/2006 ዓም 
'

Tuesday, February 18, 2014

ለመግደል የሚፈለገው መስፈርት ኢትዮጵያው መሆኑ ብቻ ነበር።የካቲት 12 የሰማዕታት ቀን


ስድስት ኪሎ የሚገኘው የካቲት 12 የሰማዕታት ሃውልት ላይ 

ዘመኑ 1929 ዓም የካቲት ከገባ ገና አስራ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል።የ አዲስ አበባ አየር ደመናማ ነበር። የተለመደው የበልግ ዝናብ ሊመጣ ዳር ዳር የሚል ይመስላል። አዲስ አበባ መንገዶች በጣልያን ወታደሮች ይታመሳል። ሰሜን ሸዋ ላይ የሚዋጋው አንዳንዴም አዲስ አበባ መግብያ በር ደረሰ እየተባለ የሚወራለት የ አርበኛው የራስ አበበ አረጋይ ሰራዊት በየ ጠጅ ቤቱ በ ቅኔ አዘል ግጥም ይሞገሳል። ቅኔው የገባቸው ባንዳዎችም አዝማሪውን እየጠቆሙ ፍዳውን ያሳዩታል። አዝማሪው ገና አለ ገና በሚል መልክ ውግያው ይቀጥላል የሚል ቃና ያለው ግጥም  ያንቆረቁራል-

 '' የወንድ ልጅ እናት ታጠቂ በገመድ፣
  ልጅሽን አሞራ እንጂ አይቀብረውም ዘመድ''

እየተባለ ሴት ወንዱ ለውጊያ የተዘጋጀበት አርበኛ ሆኖ መሞት የተናፈቀበት  ጊዜ ነበር። የስድስት ኪሎ የያኔው ቤተመንግስት የአሁኑ ዩንቨርስቲ ከአዲስ አበባ በግድም በውድም በተሰበሰቡ ባብዛኛው ሴቶች ና ሕፃናት ተሞላ። እብሪት የተሞላበት የግራዝያኒ ንግግር ተጀመረ። በንቀት ያየው ሕዝብ ላይ ስለ ''ታላቂቱ ጣልያን'' መደስኮር ጀመረ። ግን ብዙ አልቆየም አብርሃም እና ሞገስ ሕዝቡን ጥሰው ከፊቱ ደረሱ ሰባት ቦንቦችን አከታትለው ወረወሩበት፣ግራዝያን ቆሰለ፣ የ አየር ኃይሉ ኃላፊ ተገደለ። አብርሃም እና ሞገስ በ ቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስትያን በኩል ባለው የ ቤተመንግስቱ የ ጋራ  አጥር ዘለው ወጡ እና ታክሲ ይዞ ወደሚጠብቃቸው ስምዖን ገሰገሱ፣ ስምዖን በታክሲ ወጣቶቹን ይዞ ነጎደ፣ እንጦጦ ተራራ ላይ ውጥተው አዲስ አበባን ቁልቁል አይዋት፣ ግራዝያን በቆሰለበት ሆኖ አዋጅ አውጆ ለካ የ አዲስ አበባ ወንድ ከሴት ሕፃን ከአዋቂ ሳይባል በ ጥይት፣በ አካፋ እና በዶማ በተገኘው ሁሉ መፈጀት ተጀምሯል።

ሶስቱ ወጣቶች ተቃቅፈው ተላቀሱ።ጊዜው እስኪመሽ ጠበቁ እና ስምዖን ወደ ደብረሊባኖስ ይዟቸው ነጎደ።ለ ሰሜን ሸዋ ራስ አበበ አረጋይ ቅርብ የሆነችው -ደብረሊባኖስ አመቺ መስመር እንደሆነች ሁሉም አምነውበታል። ስምዖን ተልኮውን ፈፅሞ ወደ አዲስ አበባ ተመለሰ። አብርሃም ና ሞገስ ከ ራስ አበበ አረጋይ ጦር ጋር ተቀላቀሉ።

የካቲት አስራ ሁለት ቀን  ከ ሰላሳ ሺህ በላይ ነዋሪዎች ሰማአትነት ተቀብለዋል። በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ቤቶች ተቃጥለዋል። ግድያው በመንገድ ላይ የተገኘ ማንኛውም ሰው ላይ ሲሆን ለመግደል  የሚፈለገው መስፈርት ኢትዮጵያው መሆኑ ብቻ ነበር።

ስድስት ኪሎ የሚገኘው የካቲት 12 የሰማዕታት ሃውልት

የ አብርሃም ፣የ ሞገስ ና ስምዖን የ ሀገር ፍቅር እስከ መቃብር


ስምዖን 

ስምዖን አብርሃም እና ሞገስን ደብረሊባኖስ ወደ ሰሜን ሸዋ መንገድ ከሚያውቃቸው አርበኞች ጋር አገናኝቶ ተመለሰ።ብዙም አልቆየ በፋሽስቱ ጥቁር ለባሾች ተይዞ በብዙ መከራ እና ስቃይ ተገደለ። የታሪክ ምሁራን እንዳስቀመጡት ስምዖን የእጁም ሆነ የእግሩ ጥፍር በጉጠት እየተነቀለ ጣቶቹን እየሰባበሩ አሰቃይተው ገደሉት።

አብርሃም ደቦጭ እና ሞገስ አስገዶም 

አብርሃም ደቦጭ ና ሞገስ አስገዶም ከራስ አበበ አረጋይ የአርበኞች ጦር ጋር ከተቀላቀሉ በኃላ ራስ አበበ አረጋይ ልዩ እንክብካቤ እንዲያገኙ አደረጉ።ቆይተው ግን የነበራቸውን የትምርት ደረጃ በመረዳት ከሀገር ውጭ ወጥተው ለሀገራቸው ቢሰሩ ይጠቅማሉ ብለው በማሰብ ከስንቅ እና ገንዘብ ጋር ወደ ሱዳን እንዲሄዱ መከሯቸው። ሆኖም  ግን በጉዞአቸው ላይ ሱዳን ሊገቡ ትንሽ ሲቀራቸው  ፎቶዋቸው በገጠር ባሉ የፋሺሽት ወታደሮች ሁሉ ተናኝቶ ነበርና በፋሺሽቶች  ተይዘው በስቅላት ሰማዕት ሆኑ።በኃላ ግን አፄ ኃይለሰላሴ በ ሱዳን በኩል ጣልያንን ከእንግሊዝ ሰራዊት ጋር ሆነው ድል ሲያደርጉ የ አብርሃም እና  የሞገስ አስከሬን ተቆፍሮ ወጥቶ አሁን አዲስ አበባ በሚገኘው የ ቅድስት ስላሴ አርበኞች ሃውልት ስር እንዲያርፍ አድርገዋል።

ጉዳያችን GUDAYACHN

የካቲት12/2006 ዓ.ም. 

www.gudayachn.com

የ ፅሁፉ መርጃዎች 

፩/ http://www.ethioobserver.net/forgoten_heroes.ሕትም በ ፍቅረ ቶሎሳ 

፪/ ኢሳት ራድዮ የካቲት 11/2004 ዓም 

፫/ ግሎባል አልያንስ ኢትዮጵያ http://www.globalallianceforethiopia.org 



Monday, February 17, 2014

'' ለኢትዮጵያ መንግስት ተላልፈን የማንሰጥ ለመሆናችን ዋስትና እና ጥገኝነት እንዲሰጠን እንፈልጋለን'' የኢትዮጵያ አየር መንገድ ጠለፋ ጉዳይ (latest)

 የኢትዮጵያ አየር መንገድ ንብረት የሆነው የተጠለፈው አይሮፕላን 

-ከ አዲስ አበባ ወደ ሮም ይበር የነበረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በረራ ቁጥር 702 ጄኔቭ ላይ ዛሬ የካቲት 10/2006 ዓም በማዕከላዊ የአውሮፓ ሰዓት ከማለዳው 12 ከ 02 ሲሆን  እንዲያርፍ ተገዷል።

-  ሁሉም ተሳፋሪዎች እና አይሮፕላኑም በደህና ሁኔታ ላይ ይገኛሉ።

- ለ 2 ሰዓት ከ 45 ደቂቃ ተዘግቶ የነበረው የጀኔቭ አየር ማረፍያ  ተመልሶ ተከፍቷል።

- ጠላፊው ረዳት አብራሪው ነው።

- ዋና አብራሪው ወደ ሽንት ቤት ሲሄድ ረዳቱ ሽንትቤቱን ቆለፈበት እና አይሮፕላኑን ጠለፈው።

- አብራሪው ካለ አንዳች ማንገራገር እጁን ለስዊዝ ፖሊስ ሰጥቷል።ጥገኝነት እንዲሰጠውም ይፈልጋል።

- አይሮፕላኑ ውስጥ ከነበሩት ተሳፋሪዎች 143ቱ ጣልያናውያን ናቸው።

- ''ዘ ሎካል'' የተሰኘው የስዊዝ ጋዜጣ ዛሬ እንደዘገበው በስዊዘርላንድ ሕግ መሰረት ወንጀሉ እሰከ 20 አመት እስር ሊዳርግ ይችላል።

- ''ዘ ሎካል''  ጋዜጣ  አክሎም በድረ-ገፁ ላይ የጠላፊውን ቃል በድምፅ እንዲህ ሲል አሰምቷል '' ለኢትዮጵያ መንግስት ተላልፈን የማንሰጥ ለመሆናችን ዋስትና እና ጥገኝነት እንዲሰጠን  እንፈልጋለን''
''The local'' Switzerland news paper http://www.thelocal.ch/20140217/ethiopian-plane-lands-in-geneva-after-hijacking

ጉዳያችን
የካቲት 10/2006 ዓም 

Thursday, February 13, 2014

ሰበር ዜና የደቡብ ሱዳን ጉዳይ እየጋለ ነው።ሻብያ እና ኢህአዲግ/ወያኔ ከሱማልያ ቀጥሎ ለሁለተኛ ጊዜ ደቡብ ሱዳን ላይ በእጅ አዙር ፍልምያ እንዳይገናኙ ያሰጋል።(የጉዳያችን አጭር ጥንቅር)

ዩጋንዳ ሰራዊቷን በደቡብ ሱዳን ማስገባቷ ኢህአዲግን አላስደሰተም።ባለፈው ሰሞን የደቡብ ሱዳን የዜና ወኪል ይህንኑ ገልጦ ነበር።በሳልቫኪር የሚመራው የደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ መንግስት የዩጋንዳ ጦር መኖሩን የፈለገ መስሏል።በቀድሞው ምክትል ፕሬዝዳንት ሪክ ማቸር የሚመሩት የደቡብ ሱዳን ተቃዋሚዎች በሌላ በኩል ''ኢትዮጵያ ጣልቃ ትግባ'' ቀረሽ ቅስቀሳ እያደረጉ ነው።
http://www.southsudannewsagency.com/opinion/columnists/ethiopia-will-lose-its-hegemony  በየካቲት 10/2014 እ ኤ አቆጣጠር  በደቡብ ሱዳን ዜና አገልግሎት ድረ-ገፅ ላይ በታተመ ፅሁፍ ላይ ኢትዮጵያ ጣልቃ እንድትገባ ይጋብዛል።

በሌላ በኩል ''ሻብያ በደቡብ ሱዳን የውስጥ ጉዳይ እየገባ ነው'' ሲል ኢህአዲግ የከሰሰው የዛሬ ሶስት አመት የኖርዌይ የውጭ ጉዳይ ልዑክ ኢትዮጵያን ሲጎበኝ መሆኑ ይታወሳል።አሁን የዩጋንዳ ጦር ደቡብ ሱዳን መገኘቱን ተከትሎ የመጣው ቀውስ ሳይበርድ ሻብያ ከዩጋንዳ ጋር መቆሙን የሚያመላክቱ ምልክቶች እየታዩ ነው።

የሻብያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ኦስማን ሳላህ ካምፓላ መግባታቸው እየተነገረ ነው።ቀደም ብሎ በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የአፍሪካ ጉዳይ ኃላፊ  አምባሳደር ሊንዳ ቶማስ ግሬንፊልድ ዩጋንዳን መጎብኘታቸው እና ዩጋንዳም ጦሯን እንድትስብ ማሳሰባቸው ይታወቃል።የሻብያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዩጋንዳ መግባት ዝርዝሩ ባይታወቅም ከዩጋንዳ ጎን የመቆም ጉዳይ ለመሆኑ ግን ብዙዎች አይጠራጠሩም።ሻብያ እና ኢህአዲግ/ወያኔ ከሱማልያ ቀጥሎ ለሁለተኛ ጊዜ በደቡብ ሱዳን ላይ በእጅ አዙር ፍልምያ እንዳይገናኙ ያሰጋል።
አምባሳደር ሊንዳ ቶማስ ግሬንፊልድ

'ጉዳያችን ጡመራ' የደቡብ ሱዳን ጦርነት ሲጀመር ለዩጋንዳው ሙሰቨኒ ጉዳዩ 'የሰርግ እና ምላሽ 'ያክል ነው ቀድመው ጦር ሊልኩ የሚችሉ መሪ እንደሚሆኑ ገምታ ነበር።እንዲህ ይነበባል -
 ''አሜሪካ ለጊዜው ጉዳዩ ላይ በቀጥታ መግባት ባትችልም የአካባቢው ሃገራትን '' 'ቀኝ እጄን ሰጥቻለሁ'  እንደእኔ ሆነህ ይህንን አድርግ'' የምትለው ሀገር የሚታዩዋት ምናልባት ኢትዮጵያ እና ዑጋንዳ ብቻ ናቸው።ኢትዮጵያ ደግሞ በአሜሪካ ፍቃድ ብቻ ላለመሄድ የሚያደርጋት የሱዳን ፊት አለ።ሱዳን ተፅኖ ለመፍጠር በኤርትራ የሚገኙ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ኃይሎችን መሸጋገርያ እንዳትሰጥ ያሰጋል።በመሆኑም ኢትዮጵያ በደቡብ ሱዳን ጉዳይ እንደ ሱማሌው ችግር ሙሉ በሙሉ የመግባቷ አዝማምያ እምብዛም አይታይም።ለዑጋንዳው ዩዌሪ ሙሰቨኒ ግን ሰርግ እና ምላሻቸው ነው።''  ሰበር ዜና-በደቡብ ሱዳን የሪክ ማቸር ኃይሎች ውግያ ጀመሩ። ትናንት ምሽት ቁልፏን ከተማ ቦርን ተቆጣጠሩ።ኢትዮጵያና ዑጋንዳ በደቡብ ሱዳን አንፃር (ጉዳያችን አጭር ዘገባ ታህሳስ 10/2006 ዓም)ጉዳያችን ታህሳስ 10/2006 ዓም

የአሁኑ ሁኔታ ደግሞ አሜሪካ  በሻብያ እና ህወሓት ላይ የተለየ አዲስ ፖሊሲ ልትከተል እንደምትችል ወይንም እንደምትገደድ እንጠብቅ? ጉዳዩን ከሰሞኑ የምናየው ይሆናል።

ጉዳያችን
የካቲት 6/2006 ዓም 

ጠቅላይ ሚኒስትር 25% የአዲስ አበባ ሕዝብ ውሃ አያገኝም ማለት 1,000,000 የሚጠጋ ሕዝብ ማለት መሆኑን ልብ ያሉት አልመሰለኝም።...የውሃ፣የመብራት እና የስልክ ነገር።




የመብራት ነገር 


በያዝነው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ አንድ ጋዜጠኛ የመብራት፣የውኃ እና የስልክ መስመር  ችግርን የገለፀበት አገላለፅ የችግሩን ስፋት የሚያሳይ ነበር።ጋዜጠኛው በጥያቄ መልክ ሲያቀርብ - ''መብራት በተደጋጋሚ ከመጥፋቱ የተነሳ (ብልጭ ድርግም ሲል) የአዲስ አበባ ቤቶች የናይት ክለብ የሚመስሉበት ሁኔታ ነው ያለው''

የስልክ ነገር 


ስልክን በተመለከተ ጋዜጠኛው ቀጠለ- '' ስልክ አንዳንድ ቀን እንድያውም በጠቅላል በከተማው ይጠፋል። ሰው ይታመማል አምቡላንስ መጥራት ብንፈልግ እንዴት እንሆናለን አስቡበት እንጂ?''ብሎ ሲጠይቅ አቶ ኃይለማርያም ቴክኖሎጂው ከኖርዌይ እና ዴንማርክ ጋር እኩል እንደሆነ ኮራ ብለው ነገሩት።''ችግሩ'' አሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቀጥለው የቀደመውን ሲስተም በአዲስ ስንቀይር ሊቆራረጥ ይችላል'' አሉ።

ቴሌ ከእዚህ በፊት ለመስመር መቆራረጥ የሰጠው መልስ ግን የተለያየ ነበር። አንድ ጊዜ ''ኬብል እየተሰረቀ ነው።''ሌላ ጊዜ ''ህንፃዎች እየከለሉት ነው-----ህንፃ ላይ እንትከል ስንል ባለቤቶች ይከለክሉናል።'' ዛሬ ጠቅላይ ሚኒስትር ደግሞ ''በአመት 6 ቢልዮን ትታለባለች'' ያሏት ቴሌ መስመር በኖርዌይ እና ዴንማርክ የስልክ ደረጃ እየዘረጋን ስለሆነ ነው። አሉን።ሙስና፣የተማረ የሰው ኃይል ፍልሰት፣ወዘተ የሚሉትን እውነተኛ ምክንያቶች ታሽገው የሚፈታቸው ጠፋ።

ባለፈው ወር ይመስለኛል አዲስ አበባ በሚገኝ  አንድ ኤፍ ኤም መዝናኛ ፕሮግራም ላይ የስልክ ኔት ወርክ ችግርን ሲያስረዳ ጋዜጠኛው እንዲህ አለ '' አሁን አሁን ስልክ እያወራህ መስመር ሊጠፋ ስለሚችል መጀመርያ የምታወራውን ሰው ስታገኝ ''ስልኩ ከተዘጋ ቻው! ልበልህ  ትልና ነው ወደ ንግግርህ የምትገባው ስልኩ በመሃል ቢቆም ወዳጅህ ቻው! አላለኝም ብሎ አይቀየምህም'' ብሎ አስቆን ነበር።በነገራችን ላይ ባለፈውም አመት ሆነ በእዚህ አመት የአዲስ አበባ ኤፍ ኤም ራድዮኖች ካስተናገዱት የስልክ ጥሪ ውስጥ አብዛኛው መብራት እና ውሃ ሄደብን መሆኑን እራሳቸው ደጋግመው የሚያሰሙት ጉዳይ ነው።ህዝቡ መብራት እና ውሃ መስርያቤት አልሰማ ሲሉት ኤፍ ኤም ራድዮኖች ላይ እየደወለ ያለቅሳል።

የውሃ ነገር 


ሌላው ለአቶ ኃይለማርያም የቀረበው ጥያቄ የውሃ ጉዳይ ነው። ''ውሃ በከተማው የለም ሰው ቢጫ ጀሪካል ይዞ እየተንከራተተ ነው አንዳንድ ቦታዎች እስከ 15 ቀናት ያክል ውሃ አያገኙም መፍትሄው ምንድን ነው?'' ተብለው ሲጠየቁ

'' የከተማው ሕዝብ 25% ነው ውሃ በበቂ ሁኔታ የማያገኘው የቀረው 75% እያገኘ ነው።''ካሉ በኃላ የጋዜጠኛው ሰፈር ከ 25% ውስጥ ሊሆን እንደሚችል ነግረውት አረፉ።

በነገራችን ላይ ውሃ ከድሬዳዋ እስከ መቀሌ ድረስ ከፍተኛ ችግር አለ።አንድ ሕዝብ እድገት ቢቀርበት መሰረታዊ ፍላጎቶች ምግብ፣ልብስ እና መጠለያ ባይሟላለት ውሃ ግን የመኖር እና ያለመኖር ጉዳይ ነው።ቀን አይሰጠውም። አቶ ኃይለማርያም 25% የአዲስ አበባ ሕዝብ ውሃ አያገኝም ያሉት ከጠቅላላው የአዲስ አበባ ነዋሪ 1/4ኛው ማለትም  1,000,000 የሚጠጋ ሕዝብ መሆኑን ያሰቡት አልመሰለኝም።ምናልባት ቢሮ ከገቡ በኃላ ሲያሰሉት ይደነግጡ ይሆን?

ጉዳያችን
የካቲት 6/2006 ዓም


Monday, February 10, 2014

በኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ከ 100 ሺህ በላይ የኖርዌይ ክሮነር በሳውዲ ለተጎዱት ወገኖቻችን አዋጡ በመርሃ ግብሩ ላይ አቶ ኦባንግ ሜቶ እና ጋዜጠኛ ገሊላ መኮንን ተገኝተዋል።


አቶ ኦባንግ ሜቶ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ሲቀበሉ


በሳውዲ አረብያ በወገኖቻችን ላይ በደረሰው ጉዳት በመላው አለም የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ቁጣቸውን በሳውዲ ኢምባሲዎች ፊት ለፊት ሲገልፁ የነበረ መሆኑ ይታወሳል።ይህ ሁኔታ ከቁጭት ባለፈ በአለም አቀፍ ደረጃ ለተመሰረተው ''አለም አቀፍ ህብረት ለኢትዮጵያውያን መብት በሳውድ አረብያ'' (Global Alliance for the Rights of Ethiopians in Saudi Arabia) በኩል ለአለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (International Organization for Migration - IOM) የሰበሰቡትን ገንዘብ ሰጥተዋል።ለምሳሌ ባለፈው ወር በአሜሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ያሰባሰቡትን በድርጅቱ በኩል ለ አለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (IOM) 30 ሺህ ዶላር አስረክበዋል። http://ecadforum.com/2014/01/06/global-alliance-donates-funds-to-international-organization-for-migration-iom/

ትናንት የካቲት 2፣2006 ዓም  በኦስሎ ከሳውዲ አረብያ ለተፈናቀሉ ወገኖቻችን መርጃ የሚሆን የገቢ ማሰባሰብያ መርሃ ግብር በኖርዌይ የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ተዘጋጅቶ ነበር። ማኅበርሰቡ ከተለያዩ የሕብረተሰቡ ክፍሎች በተውጣጡ ኮሚቴዎች አማካይነት ከትኬት ሽያጭ እና በኖርዌይ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ከ100 ሺህ በላይ የኖርዌይ ክሮነር ( ከ 300 ሺህ ብር በላይ) ለማሰባሰብ ችሏል።

የትናንቱ የኦስሎ ዝግጅት የአለም አቀፉ የኢትዮጵያውያን እንቅስቃሴ አካል ሲሆን በመርሃ ግብሩ ላይ የአዲሲቷ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ኦባንግ ሜቶ እና ዝነኛዋ የመድረክ ሰው እና ጋዜጠኛ ገሊላ መኮንን ተገኝተዋል።

ገሊላ መኮንን የኢትዮጵያውያን እንቅስቃሴ እና ለወገን ደራሽነታቸው እጅግ የሚያስደስት መሆኑን ገልፃ በእዚሁ በጎ ተግባራቸው ጠንክረው እንዲቀጥሉ አሳስባለች።ቀጥላም  የሳውዲ አረብያውን ጉዳይ ኢትዮጵያውያን እንዲያውቁት ያደረገው የኢሳት አካል መሆኗ የሚያኮራት መሆኑን ስትገልፅ ከተሳታፊው ሞቅ ያለ ጭብጨባ ተቸሯታል።

ጋዜጠኛ ገሊላ መኮንን ኦስሎ 

በዝግጅቱ ላይ የታደሙት ሌላው እንግዳ የአዲስቱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ኦባንግ ሜቶ ነበሩ።አቶ ኦባንግ  ግልፅ እና ከልብ የመነጨ ሃገራዊ ፍቅር በምነበብበት ንግግራቸው ውስጥ ከተናገሩት የሚከተሉት ይገኙበታል-

''የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ ሰው አልገደለም።ኢትዮጵያዊነት መከበር ያለበት ነው''
''እኛ ድሃ አይደለንም በተፈጥሮ ሀብት፣በውሃ በሁሉ ሃብታም ነን።ደንቆሮም አይደለንም ብዙ የተማሩ ሰዎች በመላው አለም አሉ…..ነፃነታችንን ተባብረን ማግኘት አለብን…ነፃነታችንን ከራሳችን መጀመር አለብን'' ካሉ በኃላ
በመጨረሻ እንዲህ አሉ '' እኛ ስንሰቃይ አሜሪካ ዝም ብላ ይሆናል፣የአውሮፓ ህብረት ምንም አላለ ይሆናል የኢትዮጵያ አምላክ ግን ከእኛ ጋር ነው ያለው''

በእዚህ ዝግጅት ላይ የኢህአዲግ/ወያኔን አንድ ለአምስት የመጠርነፍ ስታሊናዊ ተግባር የሚያሳይ ሙዚቃዊ ድራማ እና በሳውዲ አረብያ የሚኖሩ እህቶቻችንን ሕይወት የዳሰሰ ትረካን ጨምሮ ልዩ ልዩ ዝግጅቶች ቀርበዋል።

ጉዳያችን ጡመራ
(ፅሁፎችን ከጉዳይችን ጡመራ ሲወስዱ ያገኙበትን ምንጭ መጥቀስ ጨዋነት ነው)
የካቲት 3/2006 ዓም
ኦስሎ

Friday, February 7, 2014

ወደ አዋጅነት ይቀየራል የተባለው ‹የሃይማኖት ተቋማት ምዝገባና የዕድሳት አገልግሎት›› ረቂቅ መመርያ ኃላፊነት የጎደለው እንዳይሆን የብዙዎች ስጋት ነው።

ፎቶ- ሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን 

 የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ከ‹‹ኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ›› ጽ/ቤት ጋራ በመተባበር ያዘጋጀውና ከጥር 30 – የካቲት 2 ቀን 2006 ዓ.ም. በሐዋሳ – ሌዊ ሪዞርት ‹የሃይማኖት ተቋማት ምዝገባና የዕድሳት አገልግሎት›› ረቂቅ ላይ ለውይይት እንደሚቀርብ ለማወቅ ተችሏል። ይህ ከመመሪያ ወደ ዐዋጅነት ይቀየራል እየተባለ የሚነገርለት መመርያ ምንነት እስካሁን በዝርዝር አልታወቀም።

‹ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የአዋጁ ረቂቅ እንዲሰጣት እና አስተያየትና አቋም ለመውሰድ ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ያቀረበችው ጥያቄ ምላሽ  አለማግኘቱን ሐራ ተዋሕዶ የተሰኘው ብሎግ ጥር 28/2006 ዓም ገልጧል።

በኢትዮጵያ ከ 1952 ዓም ወዲህ ምንም አይነት ሃይማኖትን የተመለከተ አዋጅ  ወጥቶ አያውቅም። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ከ 40 ሚልዮን በላይ ተከታዮች ያሏት እና ክርስትና ከተመሰረተ ጀምሮ ላለፉት ከ 2000 አመታት በላይ ለሆኑ ዘመናት  በኢትዮጵያ መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት የፍቃድ እና የምዝገባ መስፈርት ተጠይቃ እንደማታውቅ ይታወቃል።ደርግም በዘመኑ ምንም አይነት ሃይማኖታዊ አዋጅ አለማውጣቱ ይታወሳል።ይህ ወደ አዋጅ ያድጋል የተባለው መመርያ ኃላፊነት የጎደለው እንዳይሆን የብዙዎች ስጋት ነው።

ጉዳያችን
ጥር 30/2006 ዓም 

Thursday, February 6, 2014

እባክህ ክፈለኝ ያስተማርኩበትን (አጭር ግጥም የኢትዮጵያን ገበሬ ለተሳደቡት የኢህአዲግ ከፍተኛ ባለስልጣን)



አንጀቴን አስሬ ፣
ከእኔ ይቅር ብዬ አንተን አስተምሬ፣

ዛሬ ያወቀ መስሎት…. ''ባዶ እግር'' ነህ አለኝ፣
  ትስቅብኝ ጀመር ጫማ ስለሌለኝ፣

ባለጫማ መሆን  መቼ ጠፋኝ እኔ፣
መልበስ መሽቀርቀሩ አንተን አደንቁሬ።

ላስተምርህ ብዬ እንጂ ነገ እንድትሻገር፣
መስሎኝ----እኔ መራቆቴ ላንተ ልሆን ማገር።

ግና ምን ያደርጋል አንተም አልተማርክም፣
    ማስተዋል ነስቶሃል ከእኔ አልተሻልክም።

እናም ---እኔ ባዶ ሆኘ ያለበስኩበትን፣
            እባክህ  ክፈለኝ ያስተማርኩበትን።

ጉዳያችን
ጥር 30/2006
ምሽት ኦስሎ፣ኖርዌይ

በምስራቅ ሐረርጌ የኦሮምኛ ተናጋሪ ተፈናቃዮች የሰሚ ያለህ! እያሉ ነው።የክልሉ ፕሬዝዳንት ለግል መታከምያ ከ 38 ሚልዮን ብር በላይ ከመንግስት ካዝና አውጥተው ታከሙ።


የሐረር ግንብ የጀርባ ገፅታ 

በምስራቃዊቷ ሐረርጌ  ከሱማሌ ክልል የሚነሱ ታጣቂዎች የኦሮምኛ ተናጋሪ ነዋሪዎችን በድንገት እየደረሱ ለተደጋጋሚ ጊዜ ሲያጠቁ የነበረ መሆኑ ይታወሳል።ባለፈው አመት ከተለያዩ ወረዳዎች ተፈናቅለው ቁምቢ ወረዳ ሚኖ ከተማ ዙርያ የሰፈሩት ሰፋሪዎች አሁንም የደህንነት ስጋት እንዳለባቸው ገለፁ።
አቶ መሐመድ ይባላሉ  በሱማሌ ታጣቂዎች የደረሰባቸውን በኦሮምኛ  ከኢዣ ጎዳ ወረዳ በታጣቂዎቹ ከተፈናቀሉ ወደ አንድ አመት እንደሆናቸው ሲያስረዱ እንዲህ ይላሉ-

''ችግሩ ሲጀመር የሱማሌ ክልል ሰዎች ድንገት ተኩስ ከፈቱብን እኛ ምንም ስለጉዳዩ መረጃ አልነበረንም።ብዙዎች ተገደሉ የቀሩት ወዴት እንደሄዱ ሳይታወቅ ጠፉብን።አውሬ የበላቸው አሉ።እስካሁን ድረስ ምንም ያየነው መሻሻል የለም።''

ወ/ሮ አልያ አልበከሪሽ ሌላዋ ተፈናቃይ ጉዳዩን እንባ እየተናነቃቸው ይገልፃሉ-

 '' የሱማሌ ክልል ታጣቂዎች ድንገት ተኮሱብን። ከብቶቻችንን፣ግመሎቻችንን፣ፍየሎቻችንን ሁሉ ያለንን ሁሉ ፈጁብን ቤታችንን ሁሉ አቃጥለውብን ሀብታችንን ሁሉ አጥተን ይሄው እዚህ ሰፍረን እንገኛለን። ባሌን አረዱብኝ። በተጨማሪም ሀብቴን በሙሉ ወሰዱ ሁለት ልጆቼን ገደሉብኝ።'' ብለዋል።

ወ/ሮ ዋሸካ የተባሉ ሌላ እናት ጉዳዩን ሲገልፁ-
'' ተኩስ ሲ ከፍቱብን ካለ ጫማ እና ልብስ ባዷችንን ተሰደድን።ልጆቻችንን በትነን በእግራችን ሽሽት ያዝን።የሞተብኝ ልጅ አለ የጠፋብኝም አለ።በረሃብ ምክንያት የሞተችብኝም አለች።'' በማለት አስረድተዋል።

ዜናውን ጥር 27/2006 ዓም ያጠናቀረው የቪኦኤ አማርኛው ክፍል ዘጋቢ መለስካቸው አምኃ የኦሮምያ ክልል የአደጋ መከላከል እና ዝግጁነት ቢሮ ኃላፊ ስለጉዳዩ ሊያናግሩት እንዳልቻሉ እና ስብሰባ ላይ መሆናቸው እንደተነገረው ገልጧል።ከተፈናቀሉ አንድ አመት ያለፋቸው ዜጎች የሰሚ ያለህ! እያሉ ይጣራሉ።

ሰሞኑን አባ ዱላ የቀድሞ የኦሮምያ ክልል ፕሬዝዳንት( የአሁኑ የምክርቤት ቃል አቀባይ) የ 7 ሚልዮን ብር መኪና መንዳት ተገቢ ስለመሆን አለመሆኑ ማብራርያ መስጠታቸው ይታወቃል።አባ ዱላ የሀገር ውስጥ አዲስ የተገጣጠሙ መኪናዎችን ከ 7 ሚልዮን ከሚያወጡ መኪናዎች ጋር እያነፃፀሩ የኢህአዲግ ባለስልጣናት የትኛው እንደሚሻል ሃሳብ ሲሰጡ ምስራቅ ሐረርጌ ላይ ዜጎች ከተፈናቀሉ አመት አልፏቸው የሰሚ ያለህ ይላሉ።

ከሁለት ወር በፊት በእዚህ ደረጃ ግፍ የተፈፀመባቸው ዜጎች ጉዳይ ወደ ጎን ተትቶ ነው እንግዲህ ''የብሔር ብሔረሰቦች በዓል'' ተብሎ በሱማሌ ክልል ጅጅጋ በሚልዮን የሚቆጠር ገንዘብ ሲወጣ የነበረው።ከሱማሌ ክልል ልዩ ሚሊሻ ታጣቂዎች ጅጅጋን በበዓሉ ሰሞን ሲያሸብሩ መክረማቸው ለድርጊቱም ዳጎስ ያለ ገንዘብ ከኢህአዲግ ማግኘታቸው ይታወቃል።ይህ ብቻ አይደለም የኦሮምያ የወቅቱ ፕሬዝዳንት አቶ አለማየሁ አቶምሳ በአውሮፓ እና ሲንጋፖር ለህክምና ከ 38 ሚልዮን ብር ከመንግስት ካዝና መውጣቱ የተዘገበው እና በኢትዮጵያ ትልቅ የመነጋገርያ አጀንዳ የሆነውም በእዚህ ሳምንት ውስጥ ነው።ዜጎች ከአንድ አመት በላይ ተፈናቅለው የሚሰማቸው አጥተዋል የክልሉ ፕሬዝዳንት 38 ሚልዮን ብር አውጥተው ይታከማሉ።እሳት ስለ ጉዳዩ ሲዘግብ በኦሮምያ ምክር ቤት ውስጥ የነበሩ የ 38 ሚልዮኑን የህክምና ወጪ ጉዳይ ሲነሳ ''ተመልካች ያጣ'' ማለታቸውን ጠቅሷል።ምስራቅ ሐረርጌ ላይ የተፈናቀሉት ኦሮሞዎች ግን ሁለት የብርድ ወራት አሳልፈው ሶስተኛውን እየጠበቁ ነው።ጠባቂ፣ተመልካች፣አዛኝ የሌላት ሀገር፣ ሹማምንቶቿ በገንዘብ የናወዙባት ሀገር-ኢትዮጵያ።

ጉዳያችን
ጥር 28/2006 ዓም

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።