ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, December 31, 2022

የእነደብረጽዮን ወደ አዲስ አበባ መምጣት ለፖለቲካዊ እርቅ ወይንስ ለአገራዊ እርቅ?



=============
ጉዳያችን ምጥን
=============

በኢትዮጵያ ፌድራን መንግስት እና በህወሃት መሃከል በደቡብ አፍሪካ ከተደረገው የሰላም ስምምነት ወዲህ የሰላም ሂደቱ በፍጥነት እየሄደ ነው። በሂደቱ ላይ ግን ከኢትዮጵያ ወገንም ሆነ ከህወሃት ወገን ያለው ትችት እንደቀጠለ ነው።ሁሉንም ወገን ያስማማው እና ያስደሰተው አንዱ እና ብቸኛው ጉዳይ የትግራይ ህዝብ በተለይ በከተሞች ያለው ህይወት ወደነበረበት ቦታ የመመለስ ሂደቱ መፋጠኑ ነው።የመብራት እና የስልክ አገልግሎት የጀመረ ሲሆን የባንክ አገልግሎትም በሁሉም ቅርንጫፎች ባይሆንም አገልግሎት ጀምረዋል። በቅርብ ቀናት ደግሞ ሙሉ በሙሉ ይጀምራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ይህ በእንዲህ እያለ በመንግስት ወገን የተሄደበትን ሂደት የሚተቹት በተለይ የመርህ ጥሰት የህዝብ ተወካዮች ምክርቤት አፈጉባዔ በድንገት የአሸባሪነት ፍረጃ ያልተነሳለት ህወሃት ጋር መገናኘታቸው ከፍተኛ ትችት ከማስነሳቱ በላይ መንግስት ለራሱ ሕግ ያለውን የማክበር ደረጃው ጥያቄ ላይ ጥሎታል።ፓርላማው በትናንትናው ዕለትም ባደረገው ዝግ ስብሰባ የራሱ የብልጽግና አባል የፓርላማ አባላትም በከፍተኛ ደረጃ የአካሄድ ስህተቱን አስመልክተው አስተያየት ሰጥተዋል።

በሌላ በኩል የህወሃት ደጋፊዎች በሃሰት የውጭውን ዓለም ''ጀኖሳይድ ተፈጸመ ሺዎች ተደፈሩ'' እያሉ ሲዋሹ ስለነበር የአሁኑ የህወሃት እርቅ የሚይዙት የሚጨብጡትን አሳጥቷቸዋል።በተለይ እነደብረጽዮን ወደ አዲስ አበባ መምጣት እና ''ፋሽሽት '' እያሉ ሲሰድቡት ከነበረው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ጋር ይገናኛሉ የሚለው ዜና እንደሰሙ ድበረጽዮን እና ጌታቸው ድሮም ለዶ/ር ዐቢይ በስውር ሲሰሩ የነበሩ ናቸው የሚል ርቀት ያህል ሄደዋል።

በእዚህ ሁሉ መሃል ግን በትግራይም ሆነ በቀረው የኢትዮጵያ ክፍል ያለው ህዝብ ሰላም መምጣቱን ከከፍተኛ ስጋት ጋር ተቀብሎታል።
ዛሬ ሰላም ሆነ ማለት ግን ቀጣይ ነው አይደለም የሚለውን ምላሽ በጥራት ይሰጣል ማለት አይደለም።ይህ ሰላም የመጣው የኢትዮጵያ መከላከያ ከጥምርጦሩ ጋር ሆኖ የትግራይን 90% በላይ ከተማና ገጠር ነጻ ካወጣ በኋላ መሆኑ ይህ ድል ባይመጣ ኖሮ ህወሃት መቼም ወደ ድርድር ጠረንጴዛ እንደማይመጣ የታወቀ ነው።ይህንን መሰረታዊ ጉዳይ ስናስብ ነው ይህ እርቅ ፖለቲካዊ ነው ወይንስ ሃገራዊ እርቅ ነው? የሚል ጥያቄ እንድንጠይቅ የሚያስገድደን።

አሁን ባለበት ደረጃ በመንግስት እና በህወሃት መሃከል የተደረገው ስምምነት ፖለቲካዊ ነው።ፖለቲካዊ እርቅን ወደ ሃገራዊ እርቅ ለመውሰድ እና በፖለቲካዊ እርቅ የታረቁት ሁሉ ከመስመሩ እንዳይወጡ የሚያደርግ የህዝብ አስገዳጅነት የሚኖረው እርቁ ሃገራዊ እርቅ መሆን ከቻለ ብቻ ነው።የኢትዮጵያ ህዝብ ድሮም ከህወሃት ጋር የነበረው ጦርነት በኢትዮጵያ ህልውና ላይ ህወሃት በመዝመቱ እና ከአሁን በኋላ የህወሃትን የበደል ቀንበር መሸከም የሚችል ትከሻ ስለሌው ነው።

ፖለቲካዊ እርቅን ሃገራዊ እርቅ ለማድረግ የሚነሱ በርካታ ጉዳዮች አሉ።ሃገራዊ እርቅ ርትዕ የሆነች ፍትሕ ይፈልጋል።የተበደለው እና የተዘመተበት ሃገር እና መከላከያ ነውና ይህ ወንጀል ለወደፊቱ ትውልድም እንዳይቀጥል አንድ ዓይነት ያጠፋው የሚቀጣበት የተበደለም የሚካስበት ዓይነተኛ መንገድ ይፈልጋል።በአፋር እና በአማራ ህዝብ ላይ የተፈጸመው በደል እና የግፍ ዓይነት ለፈጻሚዎቹ የሚያስተምር የፍርድ ሂደት ያስፈልጋል። በተመሳሳይ በትግራይ ህዝብ ላይ የተፈጸመ የህግ ጥሰት በመከላከያ አባላት በኩል የተፈጸመ ካለ መንግስት ከእዚህ በፊት በጀመረው የማጣራት ሂደት መሰረት አጣርቶ ለፍርድ ማቅረብ አስፈላጊ ነው።

ሰላም የሚጠላ የለም።በትግራይ የሚኖረው ሰላማዊ ህዝብ የመሰረተ አገልግሎት ማግኘቱ እና ከሁሉም በላይ ለሁለት ዓመታት በህወሃት ከታገተበት እገታ በመከላከያ እና ጥምር ጦር ብርቱ መስዋዕትነት ከእገታው ተላቆ ከተቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ ጋር መገናኘቱ ሁሉ ያስደስታል።ከእዚህ ሁሉ ጋር ግን እርቁ የቀድሞ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች እርቅ እንዳይመስል ህወሃት የተጣላው ከአገር ጋር ነው እና አገራዊ እርቅ የሚሆንበት መንገድ ቢፈለግ መልካም ነው።ይህ ሲባል ደግሞ ከአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር የሚደረገውን ምክክር ይጠብቅ ማለት አይቻልም።ሌላም ጥያቄ አለ።በኢትዮጵያ መከላከያ ላይ ህወሃት ጥቃት ሲፈጽም ከኢትዮጵያ ጎን ቆማ የተራዳችው የኤርትራ ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ እነደብረጽዮን መጥተው የእርሳቸው አለመገኘት ፍትሃዊ አያደርገውም የሚሉ አሉ።የአዲስ አበባ ህዝብ ደግሞ ''ኢሱ! ኢሱ!'' ማለት እንጂ ደብረጽዮን! ማለት አልለመድም።አሁን ባለው ተጨባጭ ነባራዊ ሁኔታም አይልም።አቶ ኢሳያስስ እሺ ብለው ይመጣሉ ወይ? 

ይህ በእንዲህ እያለ በህወሃት እና በመንግስት መሃል የተደረገው የሰላም ስምምነት በሚፈልጉት መጠን እጃቸውን መጥለቅ ያልቻሉት አንዳንድ የምዕራብ መንግስታት ብሽቀት እንደፈጠረባቸው ተሰምቷል።የብሽቀቱ መነሻ ደግሞ ሁለት ናቸው። አንዱ የአፍሪካ ሕብረት በእዚህ ያህል አቅም አደራድሮ በመቶሺዎች የተሰለፉበትን ጦርነት ወደሰላም ማምጣቱ አንድ የተሞክሮ ልምድ ሆኖ አፍሪካ ያለማንም የምዕራባውያን ጣልቃገብነት ወደፊት እንድትራመድ ያደርጋትና ጥቅማችንን ማሳካት አንችልም የሚል ሲሆን፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ስምምነቱ በቶሎ አይጠናቀቅም የተራዘመ ክርክር ውስጥ ይገባሉ የሚለው የሃገራቱ ግምት አለመሳካቱ ነው።ድርድሩ በጣም ቢራዘም ኖሮ እነኝሁ የውጭ መንግስታት በተለያየ አጀንዳዎች እየበለቱ ጉዳዩን አክርረው ጥቅማቸውን ለማስከበር ያመቻቸው እንደነበር ያምናሉ።ባለፈው ዓርብ ወደ መቀሌ የበረሩት ዲፕሎማቶች ስብሰባው ላይ ነበር ለማለት እንጂ በቀጥታ የሚገቡበት እና ከእነ ኦባሳንጆ ጋር የሚስተካከል ቀጥታ ሚናቸው ታይቶ ለአፍሪካውያን ይህንን ሰራን የሚያስብል አንዳች ለሚድያ የሚበቃ ጉዳይ ይዘው አልመጡም።ይህ ማለት አሜሪካ የመሳሰሉ ሃገሮች እጅ በተዘዋዋሪ አይታይም ማለት አይደለም።ነገሮች በቶሎ ባይቋጩ ኖሮ ከእዚህ በበለጠ መልኩ የስቴት ዲፓርትመንት በየቀኑ መግለጫ ሲሰጥ እና በኋላም ሂደቱን በእጃቸው ሙሉ በሙሉ ለማስገባት አይሞከርም ማለት አይቻልም።

ለማጠቃለል፣የሰላም መምጣት የማስደሰቱን ያህል ህወሃት የሸር ፖለቲካውን መልሶ እንዳይረጭ ህዝብ ዋስትና ይፈልጋል።ማንም ደግሞ ህወሃት የሰራው ወንጀል ተለባብሶ  ታልፎ፣እርቁም ፖለቲካዊ እርቅ ብቻ ሆኖ ፍትህ ሳይጨምር ከሄደ ስጋታችን ያይላል።ስጋቱ ደግሞ ይህንን ለማስተካከል የሚነሳ ሌላ የህዝብ ንቅናቄ ተነስቶ ከምርጫ ፖለቲካ የራቅን ሌላ ፍትጊያ ውስጥ የምንገአብ ሃገር እንዳንሆን ከመስጋት የሚመነጭ ነው።የጀርመን ህዝብ የናዚ ፓሪትን ከሽንፈቱ በኃላ በዕርቅ ልፍታው ቢል ኖሮ ዛሬ ለደረሰበት የልማት ደረጃ አይደርስም ነበር።የጣሊያን ህዝብ የሞሶሎኒ ፋሺሽት ፓርቲ በጥምር መንግስት ውስጥ ይቆይ ብሎ ቢተውው ኖሮ ዛሬ ምናልባት የምናውቃት ጣልያን ላትኖርትችላለች።ህወሃትም ከእርቁ በኋላም ታደሰ ወረደ በግልጽ እንዳሉት የእርቁ ዓላማ እርሳቸው ጠላት የሚሏቸውን የኢትዮጵያ መንግስት እና የኤርትራ መንግስትን መከፋፈል መሆኑን ተናግረዋል።በመሆኑም ፖለቲካዊ እርቅ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ሲጠፉ አብሮ ይጠፋል።አገራዊ እርቅ ኝ ያሻግራል።በመሆኑም እነደብረጽዮን አዲስ አበባ መጥተው እርቁን ይፈጽማሉ የሚለው የሰሞኑ ወሬ ጥያቄ ይዞ መጥቷል። ይሄውም እርቁ ፖለቲካዊ ነው ወይንስ አገራዊ? የሚል ነው።
==========////=======

Wednesday, December 28, 2022

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በታላቅ ግርማ ሞገስ በሰዓታት ውስጥ ከመቀሌ አሉላ አባነጋ አየር ማረፍያ ጀምሮ መቀሌን መቆጣጠር ይጀምራል!

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ


በእዚህ ምጥን ጽሑፍ ስር ፡ 
  • ምስጋና ለኢትዮጵያ ህዝብ ይገባዋል፣
  • አድናቆት ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አመራር ያስፈልጋል።
  • የትግራይ፣አፋር እና አማራ ክልሎች በጋራ በየትኛውም ወገን ለሞቱ ወገኖች ለሦስት ቀናት የሃዘን ቀናት ቢያውጁ፣ 
  • የኢትዮጵያ ሕዝብ ዐይኑን በጨው ሳይሆን በአጃክስ አጥቦ ለታየው የህወሃት አመራር እንዴት ዓይነት ንስሃ እንደሚገባ እየጠበቀ ነው።
=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

የኢትዮጵያን አንድነት ለማስጠበቅ የደም እና የአጥንት መስዋዕትነት የከፈለው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በታላቅ ግርማ ሞገስ ከሰዓታት በኋላ የመቀሌን አሉላ አባነጋ አየርማረፍያን ጨምሮ መቀሌን ይቆጣጠራል።መከላከያ ላለፉት ተከታታይ ወራት የህወሓትን ታጣቂ ኃይል በተቀናጀ እና ልዩ በሆነ ኦፕሬሽን በሦስት አቅጣጫዎች በመግባት የትግራይ ሁሉንም ከተሞች ነጻ ካወጣ በኋላ መቀሌን በቅርብ እርቀት ከቦ መቆየቱ ይታወቃል።በእዚህም መሰረት ወደ መቀሌ የመግባቱ ሂደት እንደተጀመረ ህወሓት ትጥቅ ለመፍታት እና ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለመደራደር በመስማማቱ መከላከያ መቀሌን ከቦ እንዲጠብቅ ታዞ ነበር።በመቀጠል በፕሪቶርያ፣ደቡብ አፍሪካና ናይሮቢ፣ኬንያ ድርድር ከተደረገ እና ህወሃት ትጥቅ ለመፍታት በፊርማ ካረጋገጠ በኋላ መከላከያ ወደ መቀሌ ከሰዓታት በኋላ በታላቅ ግርማ ሞገስ ወደ መቀሌ እንደሚገባ ታውቋል።

ምስጋና ለኢትዮጵያ ህዝብ ይገባዋል!

የኢትዮጵያ ሕዝብ ህወሃት በከፈተው ኢትዮጵያን የመበተን ዘመቻ ወቅት ኢትዮጵያ አንድነቷን ጠብቃ እንድትኖር ከህይወት መስዋዕትነት እስከ ንብረቱ ከፍሏል። እዚህ ላይ ግን ለማንሳት የምሞክረው ህዝብ ውስጣዊ አንድነቱን ከመጠበቅ ባለፈ ህወሃት ህዝቡን ለማጫረስ በትግራይ ህዝብ እና በቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ መሃል ግጭት ለመፍጠር የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ቢከፍትም በመሃል ሃገር በሚኖሩ በሚልዮን የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች ላይ አንዳች የግጭት ኮሽታ ሳይሰማ እርስ በርሱ ተደጋግፎ የህወሓትን የመሃል ሃገር የግጭት ድግስ አክሽፏል።ለእዚህም ምስጋና ይገባዋል።

አድናቆት ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አመራር ያስፈልጋል።

ኢትዮጵያ ባለፉት አራት ዓመታት ውስጥ እጅግ ፈታኝ ሁኔታዎች ውስጥ አልፋለች።ይህም ሆኖ ደግሞ እጅግ ጥበብ የተሞላበት እና ትዕግስት የሚፈልግ አመራር የሚያስፈልግበት ጊዜ ነበር።የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አመራር ከህወሃት ጋር የሰላም መንገድ ለመከተል የቻለውን ሁሉ አድርጓል።የሰላም ጥረቶቹን በተመለከተ ይህንን ሊንክ ተጭነው ማዳመጥ ይችላሉ።

በእነኝህ ሁሉ ጥረቶች ሳይሳኩ ሲቀሩ እና የኢትዮጵያ አንድነት አደጋ ላይ ሲወድቅ ደግሞ በቀጥታ ወደ ጦር ግንባር በመዝመት ለኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን መሪ መሆናቸውን አሳይተዋል።ይህ ብቻ አይደለም በአሁኑ የሰላም ሂደት ላይም በርካታ ውጣ ውረዶችን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያን ብቻ በመመልከት ብዙ ጉዳዮችን በትዕግስት እንዳለፉ እና አሁን ለተደረሰበት የሰላም ሂደት ደረጃ እንዲደርስ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ብቻ ሳይሆን የአጠቃላይ አመራሩ ጥረት እና ቅንነት የተሞላበት ሂደት ያደረገውን አስተዋጾ ለመረዳት ይቻላል።ለእዚህ የሰላም ሂደት የመንግስት አመራር ሚና በቀላሉ የሚታይ አይደለም።ይህንን ለመረዳት አንድ ሰው ቤተመንግስት ውስጥ መሆን የለበትም። የህወሃትን እኩይ አካሄድ በመመልከት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እና አመራራቸው ለሃገር ሲባል ብዙ ትዕግስት ለማድረጉ በቀላሉ ማወቅ ይቻላል።

የትግራይ፣አፋር እና አማራ ክልሎች በጋራ በየትኛውም ወገን ለሞቱ ወገኖች ለሦስት ቀናት የሃዘን ቀናት ቢያውጁ፣

በአማራ እና በአፋር ክልል በህወሃት ዘመቻ በብዙ ሺህ ሰላማዊ ዜጎች ላይ እልቂት ተፈጽሟል፣ሴቶች ተደፍረዋል፣ንብረት ተዘርፏል።በተመሳሳይ መንገድ በትግራይ በህወሃት አስገድዶ ዘመቻ እንደ የአፍሪካ ህብረት የሰላም አደራዳሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና የናይጀርያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ገልጻ ከሆነ ከግማሽ ሚልዮን በላይ ህይወቱ አልፏል።

ይህ በእንዲህ እያለ በትግራይ ቤተሰባቸውን ያጡ ሰዎች ለቅሶ እንዳይቀመጡ የህወሃት ካድሬዎች እያስፈራሩ እንደሆነ ተሰምቷል።ከእዚህ ሁሉ በላይ ግን በሦስቱ ክልሎች በጦርነቱ የብዙ ሰው ቤት በሃዘን ተውጧል።ሃዘን ደግሞ ጊዜ ተወስኖለት ስሜቱን መግለጹ በራሱ የሰላም ሂደት ነው።አብሮ መብላት ብቻ ሳይሆን አብሮ ማልቀስም ያስማማል።እዚህ ላይ በቀረው የኢትዮጵያ ክፍል ወለጋን ጨምሮ የነበረው የሞት ቁጥር ሳይገባ በሦስቱ ቦታዎች ብቻ ሃዘን ለምን? የሚል ጥያቄ ሊያስነሳ ይችላል።ሆኖም ግን ይህ የሶስት ክልሎች በአንድነት በሚጋሩበት ቦታ የነበረው የንጹሃን እልቂት ቁጥር እና ውድመት እጅግ ከባድ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን በቀጣይም ተመሳሳይ ችግር የፖለቲካ አካሎች ቢያስቡም ህዝብ ግን ባለው ጊዜ ህመሙን በጋራ ሃዘን አስታሞ በመጪው ጊዜም ህወሃት መልሶ ወደ ግጭት እንዳይመራው ውስጣዊ አንድነቱን ማጠናከሩ ጥቅም አለው።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ዐይኑን በጨው ሳይሆን በአጃክስ አጥቦ ለታየው የህወሃት አመራር እንዴት ዓይነት ንስሃ እንደሚገባ እየጠበቀ ነው።

ለእዚህ ምንም ዓይነት ማብራርያ አያስፈልገውም።የህወሃት አመራሮች ከግማሽ ሚልዮን በላይ ህዝብ አጫርሰው በከረቫት ብቅ ብለው መታየታቸው እና አለማፈራቸው የኢትዮጵያ ህዝብ የእየቤቱ መነጋገርያ ነው።አሁን ለራሳቸው ንስሃ ገብተው ዳግም ኢትዮጵያን ከልብ ይቅርታ ይጠይቃሉ ወይንስ በለመዱት አፋቸው ደልለው መልሰው ሃገር ያምሳሉ? የሁሉም ጥያቄ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ ግን እየጠበቀ ነው።

በመጨረሻም አሁን ኢትዮጵያ እየሄደችው ያለው መንገድ ወደ ጽኑ ሰላም እና አንድነት እንዲመራልን ለእዚህም አምላኳ እንዳይለያት የሁላችንም ጸሎት ሊሆን ይገባል።
=================////=========

Monday, December 19, 2022

ወቅታዊው የኢትዮጵያ ሁኔታ በተመለከተ ልናውቅቸው የሚገቡ አምስት ወሳኝ ዐበይት ጉዳዮች


========

ጉዳያችን
=========

የጎሳ ጉዳይ በተመለከተ በምናስበው ደረጃ አይደለም።


የኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ሲነሱ በተለይ አዕምሮ የሚረብሹ ጉዳዮች በዜና ሲነገሩ ብዙ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈጥሩት የስሜት መዋዥቅ አና የተስፋ መቁረጥ ስሜት ቀላል አይደለም።በተለይ በአብዛኛው የፖለቲካ ጉዳዮችን ሳይሰሙ የኖሩ ወይንም በግማሽ ልብ አልፎ አልፎ የሚከታተሉ ኢትዮጵያውያን በድንገት የሚሰሟቸው ክፉ ዜናዎች መጪውን በከፋ ደረጃ እንዲያዩ ያደርጋቸዋል።ይህ ደግሞ ወደ ዲያስፖራው ማኅበረሰብ ሲመጣ አጅግ የከፋ ይሆናል።ዲያስፖራው በሚኖርበት ሀገር የተረጋጋ አካባቢያዊ ሁኔታዎች ከመኖራቸው አንፃር ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ክፉ ነገር ብቻ የሚናገሩ የውጭ ሚድያዎች አና እንደ አሸን የፈሉት የዩቱብ ገፆች ሁሉ የሚሉት በአዕምሮ ላይ የሚፈጥሩት ጠባሳ ቀላል አይደለም። የእዚህ ዓይነት ዜናዎች ተጠራቅመው ተስፋ የቆረጠ አና ስሜታዊ ውሳኔ የሚወስን ማኅበረሰብ የመፍጠሩ አደጋም ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ ነው።


ይህ ማለት በኢትዮጵያ በፅንፍ ኃይሎች እና በሰሜኑ ህወሓት በጫረው ጦርነት ሳብያ እየጠፋ ያለው ሕይወት ቀላል ነው ወይንም በንፁሃን ላይ የደረሰው ሁሉ የሚቃለል ነው እእስከ አፋር አና አማራ ክልል ሁሉ የሆኑትና ዜጎች ላይ የደረሰው ሞት፣ስደት አና የንብረት መውደም አጅግ አሳዛኝ ነው።የሆነው ሁሉ ግን ዳግም እንዳይሆን አና የበለጠ ኢትዮጵያን አንዳይጎዳይ መጪውን ማስተካከል የሚጀመረው የዜጎችን የአዕምሮ ሁኔታ በሚገባ በመቃኘት አና የጠነከረ እንዲሆን በማድረግ ነው።


በአሁኑ ጊዜ የኢትዮጵያ የእርስበርስ የብሔር (ጎሳ) ግንኙነት በህዝብ ደረጃ የተበላሸ የሚመስላቸው፣አንዳንዱ ከወጣበት አካባቢ ውጭ ያለው ሁሉ አስጊ አድርጎ የማየት አደጋ አለ። ይህ ከበቂ መረጃ በራቀ መልኩ እራስን በአጥፊ ዩቱበሮች አና ሚድያዎች ልክ ወስኖ የመኖር የስህተት መንገድ ነው።ነባራዊ ሁኔታውን ለመረዳት ግን የኢትዮጵያ የጎሳ ግጭቶች ባህሪዎች የተለዩ አና ወደ ሕዝብ አንዳይመጡ የሚያደርጋቸው በርካታ ተፈጥሯዊ ጉዳዮች አሉ።ይህ ማለት አሁን ካለንበት ሁኔታ አንጂ ሕዝቡም ሆነ መንግስት በጋራ መሰረታዊ ለሆኑ የምጣኔ ሀብት አና ፖለቲካዊ ጉዳዮች መፍትሄ ካልሰጠን ለወደፊቱ ትውልድ የምናወርሰው አደጋ የለም ማለት ግን አይደለም።


ኢትዮጵያ የተለየች ሀገር የሚያደርጋት አና የጎሳዊ ጉዳዮች የሀገሪቱን ስር አንደማይነቅል በአርግጠኘትን መናገር የሚቻለው በሚከተሉት መሰረታዊ ነባራዊ ሁኔታዎች ነው።

  • ኢትዮጵያ ውስጥ ካለው ሕዝብ ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆነው ቢያንስ ከሁለት ጎሳ የሚወለድ ነው።ነገር ግን ይህ የህብረተሰብ ክፍል አሁን ያለው የፖለቲካ አደረጃጀት አግልሎታል።ለመብቱ ሲነሳ ግን ኢትዮጵያዊነት ቦታውን ያስከብራል።

  • በኢትዮጵያ የጎሳ ግጭቶች ከመንግስት ባለስልጣናት የሚነሱ አልያም የፖለቲካ ድርጅቶች በቢሮ ቀምመው የሚሰሯቸው አንጂ ታሪካዊ የግጭት መሰረት ይዘው የሚመጡ አይደሉም።ይህንን ለማብራራት ብዙ ቦታ ስለሚወስድ አንዳለ አስቀምጠዋለሁ።እውነታው ግን ይሄው ነው።

  • በኢትዮጵያ የተደረጉ የእርስ በርስ ጦርነቶች ምን ያህል ጎሳን አየቀሰቀሱ ቢመጡም ኢትዮጵያ በቅኝ ተገዝታ ስለማታውቅ አና በማኅበረሰቡ ውስጥ የቆየ የመለያያ ሥራዎች አንደ የሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ስላልተተከሉ ሕዝብ በራሱ ማኅበራዊ መስተጋብር የሚያመክንበት የራሱ አሰራር አለው።ይህ አሰራር ደግሞ በማኅበራዊ ትስስር ብቻ ሳይሆን በታሪካዊ መንገዶች ሁሉ የተሰናሰለ ነው።


ከላይ ለተነሱት ነጥቦች ማስረጃ የሚሆነን የቅርቡን ከህወሓት ጋር የተደረገውን ጦርነት አና በወለጋ አየሆነ ያለውን መመልከት በቄ ነው።ህወሓት የትግራይን ሕዝብ የቀረው ኢትዮጵያዊ ሊያጠፋህ ነው የሚል የሐሰት ፕሮፓጋንዳ ሲነዛ ከሦስት አስር ዓመታት በላይ ሆኖታል።ይህንን ዘመቻውን በማድረግ የትግራይ ሕዝብ ሁሌ አየደነገጠ አንድኖር አና ህወሓት ከሌለ የማይኖር አድርጎ አንዲያስብ ብዙ ሰርቶበታል።ይህ ሁሉ ዘመቻ ፍፃሜ ለማድረስ ደግሞ መከላከያ ላይ የተቀናጀ ጥቃት በመፈፀም  ከሃያ ዓመታት በላይ አብሮት የኖረውን ብቻ ሳይሆን ከሕዝቡ ጋር ተዋልዶ አና ተዛምዶ የኖረውን የትግራይ ማኅበረሰብ ለማቆራረጥ ሞከረ።ይህ ብቻ አይደለም።በአማራ አና አፋር ሕዝብ ላይ ሦስት ዙር ወረራ ሲያደርግ የትግራይን ሕዝብ ከአማራ አና ከአፋር አቆራርጦ የፍርሃት ስሜቱን በማናር አና ህወሓት ከሌለ ትግራይ አትኖርም የሚል ስሜትም ለመፍጠር በማለም ነበር አጅግ የሚዘገንኑ ግፎች በሰላማዊው የአማራ አና አፋር ሕዝብ ላይ አንዲፈፀም ያደረገው።የህወሓት ፍላጎት የጠላትነት ስሜት በማናር የትግራይ ሕዝብ ለህልውና በሚል ከህወሓት ጋር አብሮ ገደል አስቀመግባት ድረስ ለመያዝ ያለመ ነበር።ከአዚህ በተጨማሪ በመሃል ሀገር ከሚኖሩ በሚልዮን የሚቆጠሩ የትግራይ ተወላጆች ላይ ሌላው ሕዝብ ይነሳል ይህም የትግራይ ሕዝብ ከህወሓት ጋር የበለጠ ያጣብቀዋል የሚል ከንቱ ስልት ይዞ ነበር የግፍ ስራውን ሲፈፅም የነበረው። ይህ የህወሓት ሕልም ግን አልሰራም።በመሃል ሀገር በሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች ላይ ሕዝብ አንዳችም የተለየ መልክ አላሳየም።ህወሓት ወንድሙን ወሎ አና አፋር ላይ የገደለበት መሃል ሀገር የሚኖር ኢትዮጵያዊ ጎረቤቱ የትግራይ ተወላጅ ተጠይቂ አንዳልሆነ ጠንቅቆ ያውቃል።

በተመሳሳይ መንገድ በወለጋ የተፈፀመው በንፁሃን በአብዛኛው  የአማራ ተወላጆች አና አንዲሁም  የኦሮሞ ማኅበረሰብ ላይ የደረሰው የጅምላ ግድያ አቀናባሪው የፖለቲካ ድርጅቶች አንጂ ሕዝብ አንደህዝብ ተነስቶ የፈፀመው አይደለም።ለምሳሌ በወለጋ ለዓመታት የኖሩ የአማራም ሆነ የኦሮሞ ማኅበረሰብ ጎረቤቴ ተሰብስበው አንዲህ ዓይነት ግፍ ፈፀሙብኝ ያኛው መንደር ሰው በአዝህኛው መንደር ሕዝብ ላይ ይህንን አደረገ የሚል ክፉ ወሬ አልተሰማም። በፖለቲካ ድርጅቶች የተደራጁ የታጠቁ ኃይሎች አና የአነርሱ የሴል አካላት ከልዩ ኃይል ወይንም በመንግስት መዋቅር ውስጥ ተሸሽገው የፈፀሙት ወንጀል ነው በኢትዮጵያ አየታዬ ያለው።የፖለቲካ ድርጅቶች አና በመንግስት ውስጥ የተጠለሉ ወንጀለኞች መሆናቸውን ሕዝብ ስለሚያውቅ በጥቃቱ የሚሰደዱትን ስደተኞች ቦታ ቀይረው በሰፈሩበት ሁሉ የሚረዳቸው የአካባቢው ማኅበረሰብ ማለትም የኦሮሞም የአማርም ማኅበረሰብ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።


ከላይ በትግራይም ሆነ በወለጋ ለሆኑት ሁሉ የኢትዮጵያ ሕዝብ እንደህዝብ ያለው ጥንቁቅነት፣የይቅርባይ መንፈስ ይዞ ነገ ላይ የሚያሻግር ሥራ ላይ ማትኮሩ አና አሁንም የፖለቲካ ድርጅቶች አና በመንግስት ውስጥ የተጠለሉ ወንጀለኞች የሚሰሩበትን ወንጀል ወደ ጎረቤቱ ሳያጋባ የመኖር ጥበቡን ማድነቅ አና ይህንን አጉልተን ማሳየት አስፈላጊ ነው።ከብዙ መጥፎ ነገሮች ውስጥ መልካም ነገሮችም አሉ አና ይህንን የኢትዮጵያን ሕዝብ መልካም ነገር አውጥተው የሚያሳዩ ሚድያዎች ስለሌሉ አና ክፉ ክፉው ብቻ ስለምነገረኝ አራሳችንን ሳናውቅ አንድንኖር አየተደረግን ነው።ባለው አጋጣሚ ግን ይህንን መልካም ጉዳይ አሁንም አጉልቶ አና ተጨባጭ ታሪኮችን ይዘው ሚድያዎች ሊመጡ ይገባል።ይህ ደግሞ አሁን ያለውን ትውልድ አንድነት ለማጠንከር ብሳይሆን ለመጪው ትውልድ አንዴት ይህንን ጊዜ አንዳለፍን ማሳያ ተጨባጭ ትምህርት ስለሚሆንም ጭምር ማለት ነው።



በአእምሯችን ላይ ሚድያዎችና የመንደር ወሬዎች የፈጠሩብንን ጥቃቅን ቀበሮዎች እንንቀላቸው።


ሕዝብ ዝምብሎ አይለያይም መጀመርያ አዕምሮ ላይ የመለያየት ጥቃቅን ቀበሮዎች በእየለቱ እንእንዲፈጠሩ ይደረጋል።ጥቃቅን ቀበሮዎቹ ሌላው ሕዝብ መጥፎ እንደሆነ የማሰብ፣እራስ ከተወለዱበት አና የመጡበት አካባቢ ውጭ ያለ አደገኛ አና አጥፊ ነው የሚል የሐሰት ትርክት በየአለቱ የምንሰማው የማኅበራዊ ሚድያ መጥፎ ጎርፎች የሚመጣ ነው።በማኅበራዊ ሚድያ ላይ የሚጣሉት አንዱን ጎሳ ከሌላው የሚያብጠለጥሉ አና የራስን ጎሳ የሚያሞካሹ ጥቅሶች፣ንግግሮች አና የምናከብራቸው ሰዎች የተሳሳተ የጥላቻ ሃሳቦች ሁሉ በጥቃቅን የጥላቻ ቀበሮዎች አእምሮአችንን ይበክሉታል። ይህ አጅግ አደገኛ ሁኔታ ነው።በአዚህ ዓይነት ስሜት ውስጥ ሰዎች የሚያውቁትን ጎረቤት ብቻ ሳይሆን  የተለይ የጎሳ አባል ነው የሚሉትን የሚያውቁትን አና አብረው ለዘመናት የኖሩትን ዘመድ ሳይቀር ሳያውቁት ክፉ ስሜት አንድሰማቸው ያደርጋል። ስለሆነም ሰውን በሰውነቱ የማክበር አና የተሳሳተ ቢኖርም የሚታርም መሆኑን የማመን ስብእና ማዳበር ያስፈልጋል።ይህንን ለማድረግ ያማያስፈልጉ የውሸት ትርክቶችን አለመስማት፣ጆሮን ከመጥፎ ወሬ መጠበቅ አና የሰውነት ክብርን ጠብቆ መኖር ያስፈልጋል። ይህንን ለማድረግ ደግሞ በተለያየ ጊዜ ወደ አእምሮ የገባውን ጥቅቅን የጥላቻ ቀበሮ መንቀል ያስፈልጋል።


ኦሮሞ ሁሉ ወንድሜ ነው፣ትግራይ ሁሉ ኢትዮጵያዊ ወገኔ ነው፣አማራ ሁሉ ወገኔ ነው፣ሱማሌ ቤተሰብ ነው፣አፋር የአኔው ነው አያልን በአግባቡ አእምሮ የማከም ሥራ ያስፈልጋል። ይህንን በተገቢው መንገድ መስራት የሚገባቸው ሚድያዎች አሁንም፣ አሁንም ብዙ ይጠበቅባቸዋል።



ኢትዮጵያን የሚመራ መሪ በማጥላላት የኢትዮጵያን ርዕይ ለማጨለም መሞከር የተለመደው የባዕዳን ስልት በመሆኑ እንንቃ! 


ችግሮችን ሁሉ የሀገር መሪ ላይ አስቀምጦ የሚፈለገውን ሀገር ማፍረስ የቀዝቃዛው ጦርነት አንዱ ስልት ነው።ይህ ስልት በወቅቱ የምስራቁ ጎራ ሊጠቀምበት አልቻለም።ምክንያቱም የምዕራብ ሀገሮች መሪዎች ተቀያያሪ ናቸው። በተወሰነ ጊዜ ምርጫ ማድረጋቸው መሪዎቻቸው በስልጣን አስካሉ ድረስ ላለው አጭር ጊዜ ኢላማ ቢደረጉም አዳዲስ ተመራጭ መሪዎች ከአዲስ ሃሳብ ጋር ስለሚመጡ የህዝቡንን ስሜት የመግዛት አቅማቸው ከፍ ያለ ሆኗል።በአዚሁ የቀዝቃዛው ጦርነት ጊዜ የምዕራቡ ዓለም ግን በምስራቁ ዓለም ለነበሩ መሪዎች ላይ በሚገባ ተጠቅሞበታል።በጊዜው የነበሩት የኢትዮጵያ መሪ ኮለኔል መንግስቱ ኃይለማርያም አንዱ ሰለባ ነበሩ።የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፣ማኅበራዊ አና ምጣኔ ሃብታዊ ችግሮች ሁሉ ተጠያቂ ተደርገው አንዲቀርቡ የተደረጉት ኮሎኔል መንግስቱ ነበሩ።በአዚህም የኮሎኔል መንግስቱ መወገድ ብቻ የኢትዮጵያን ችግር ይፈታል የሚል ቂላቂል ሃሳብ ተጠቂ የሆነው ተራው ሕዝብ ብቻ ሳይሆን በኮሎኔል መንግስቱ ዙርያ የተሰበሰቡ ከፍተኛ ባለስልጣናት መሆናቸው የፕሮፓጋንዳው ኃይል ምን ያህል አንደሰራ አአላካች ነው።ለአዚህም ነው ግንቦት 13፣1983 ዓም ኮሎኔል መንግስቱ ከኢትዮጵያ መውጣታቸውን አስመልክቶ በወጣው የመንግስት መግለጫ ላይ ‘’የኮሎኔል መንግስት ከስልጣን መወገድ ለአገራችን ሰላም አስፈላጊ በመሆኑ’’ የሚል ዓረፍተ ነገር የተጨመረበት እና ለኢትዮጵያ ሕዝብ በራድዮ አና ቴሌቭዥን የተነበበው።በጊዜው መንግስቱ ኃይለማርያም ከአስፈሪ ሰው ጋር ብቻ ሳይሆን ከመጥፎ ነገር ጋር ሁሉ የተዛመደ ተደርጎ አንድሳል ተሰርቶ ነበር።


በቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ የስልጣን ማብቅያ ላይም የታየው ይሄው ነው።ንጉሱን የማጥላላት ዘመቻ ውስጥ ውስጡን በተቻለ መጠን በተለይ በወቅቱ በነበረው ወጣት ዙርያ ተሰርቷል።ኢትዮጵያን ወደዘመናዊ አስተዳደር ለማምጣት ከትምህርት አስቀ ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ ድረስ ብዙ የሰሩት ቀዳማዊ አፄ ኃይለሥላሴ ላይ የተደረገው የማጥላላት ዘመቻ አስቀ ቤተሰባቸው ድረስ አንዲዘልቅ ከመሞከሩ የተነሳ የራሳቸው ልጆች ብቻ ሳይሆኑ በወቅቱ የነበሩት ባለስልጣናት ሳይቀሩ ከንጉሡ ጋር አብረው ለኢትዮጵያ መፍትሄ ለማምጣት አስከመዘናጋት አድርሷቸዋል።በወቅቱ ጥቂት ምሁራን ብቻ ችግሩን ከንጉሡ ጋር ብቻ ማያያዝ አና የአርሳቸው መወገድ ብቻውን የኢትዮጵያን መፍትሄ አንደማያመጣ ይልቁንም አርሳቸውን በቦታቸው በሀገር ክብርነት አስቀምጦ አስተዳደሩን በሕዝብ በተመረጠ መንግስት መቀየር አስፈላጊ መፍትሄ ነው ያሉት አንዴ ደራሲ አና ዲፕሎማት ሐዲስ አለማየሁ ያሉ ምሑራን ብጎተጉቱም የሰማቸው የለም።ይልቁንም የጥላቸው ዘመቻ ንጉሡ አፍሪካ ላይ የነበራቸውን የቅኝ ግዛት አንዳስጣሏቸው ያሰቡ ቅኝ ገዢ መንግሥታት ጭምር የተደገፈ ስለነበር አና ሕዝቡም ንጉሡ የሁሉ ችግር መነሻ ተደርገው ስለተነገሩት አና ይህንኑ በየዋህነት የተቀበሉ የጦር መኮንኖች ሳይቀሩ ንጉሱን በቭኦልስዋገን መኪና ከቤተመንግስት ወደ አራተኛ ክፍለጦር ይዞ መሄድ አንደትልቅ ጀብዱ ቆጠሩት።በወቅቱ የነበረው ወጣትም የኢትዮጵያ ችግር ሁሉ የሚወገድ መስሎት ጨፈረ።


ዛሬም ያለንበት ጊዜ ተመሳሳይ ነው።ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይን በኢትዮጵያ ላይ የጥቅም ፍላጎት ያላቸው ኃይላኑ መንግሥታት በመጀመርያ የስልጣን ዘመናቸው አካባቢ በጣም አሞገሷቸው።በማሞገስ ብቻ አልቆሙም የኖቤል ተሸላሚ መሆናቸውን አድንቀው ፃፉ።የኢትዮጵያ ሕዝብም ከፍተኛ ድጋፉን ገለፀ።በመቀጠል ችግሮች ሲፈጠሩ የችግሮቹ ሁሉ ምንጭ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው የሚል የሞኛሞኝ ሃሳብ በበታኝ ኃይሎች መስተጋባት ጀመረ።ይህንኑ ሃሳብ የሚቀምር አራሱን የቻለ ቡድን ከህወሓት አስቀ ኦነግ አና በአማራ ስም ከሚነግዱ አክራሪ ቡድኖች አስከ ባህር ማዶ የደህንነት ቡድኖች በአንድነት አየተገመደ ለፕሮፓጋንዳነት ዋለ።አዚህ ላይ ብዙ ሰበብ መስጠት ይቻል ይሆናል። በኢትዮጵያ የተፈፀሙት ግድያዎች፣ስደቶች አና የንብረት መውደም ምንም አንኩዋን አያንዳንዱን ጉዳይ በዝርዝር መመርመር ቢያስፈልግም መንግስትን አይመለከተውም አያልኩ  አይደለም።ነገር ግን አያነሳሁ ያለሁት በአሁኑ ጊዜ የኢትዮጵያ ችግሮች ሁሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸው የሚል የጅላጅል ሃሳብ በአእምሯቸው ለምመላለስ አና ይህንኑ አንደመፍትሄ ለሚመስላቸው ዜጎች ቆም ብለው አንድያስቡ ደጋግሜ አየነገርኩ ነው።


አዎን! ጧት ማታ ዓቢይ! ዓቢይ! የሚል ንግግሮች በአያንዳንዱ የኢትዮጵያ ችግሮች ላይ የሚነገሩት ሆን ተብሎ አና የተለመደ የስነልቦና ዘመቻ መሆኑን ልብ ማለት ይገባል።ለምሳሌ የህወሃቱ ጌታቸው ረዳ አና በኢትዮጵያ ጥቅም ላይ የቆሙ ከባአዳን ድርጎ የምላክላቸው ዩቱበሮች ስንት ጊዜ የጠቅላይ ሚኒስትር አብይን ስም አንደሚጠሩ ቁጠሩት።ይህ በአጋጣሚ የሚመስለው ካለ ተሞኝቷል።በስነ ልቦና አማካሪዎች የተጠና አና ችግሩን በዋናነት የጥፋት አጀንዳቸውን ለማስፈፀም አላስቻለኝም ያሉትን መሪ ስም ደጋግሞ በጥላቻ በመጥራት ከህዝብ መነጠል አና ሕዝብ የችግሩ ሁሉ ምንጭ መሪው ነው ብሎ አንድያምን አና በርሱ ላይ አንድነሳ ለማድረግ የሚሞከር ሙከራ ነው።በቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ ላይ አና በኮ/ል መንግስቱ ላይ የተፈፀመው ይሄው ነው።የኢትዮጵያ ችግር መውጫ ሌላ መንገድ ምሑራኑ አንዳይፈልጉ በጭፍን ፕሮፓጋንዳ የኢትዮጵያ ችግር የሚወገደው ንጉሡ አና ኮለኔሉ ሲወገዱ ነው የሚለውን የጅል ሃሳብ አብረው አቅደው ሲያስፈፅሙ የነበሩትን ባለስላጣናት ሁሉ አታለሉበት።አንድ ሀገር ምንም ልምድ የሌላው መሪ ይዛ ችግር ለመፍታት ከምትሞክር በአንድሳምንትም ቢሆን በመምራት ልምድ ያለው መሪ የችግሮችን አፈታት አና መጪውን የመረዳት አቅም አለው።


ስለሆነም ዛሬም ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ላይ የሚከፈቱ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻዎች ግብ ሕዝብ የችግሩ ብቸኛ መፍትሄ የአርሱ አለመኖር አንድመስል አና በኃላ ኢትዮጵያውያን መሪ በድንገት አጥተው በሚያደርጉት ሹክቻ የባአዳን አራት ለማድረግ የታሪካዊ ጠላቶቿ ዋና ግብ ነው።ልብ ያለው ልብ ይበል።መሪ ሲሳሳት ባለበት ለማረም አና ሲወርድም በሥርዓት አና በሕግ ይህም በምትፈልገው ጊዜ መጥቶ የሚያማክርበት አመቺ ሁኔታ ተፈጥሮ አንጂ በማጥላላት አና በመገፍጠር ኢትዮጵያን አናጠፋ ይሆናል አንጂ ያለፈውን ስህተቶች አያርምም።አዚህ ላይ መሪዎች የማይወቀሱ፣የማይቀሰሱ ናቸው የሚል መልአክት አያስተላለፍቁ አይደለም።ለአዚህ ሕዝቡም ምድያዎችም መሞገት አለባቸው።ነገር ግን ለሀገር ያላቸውን የመሪነት ሚና አና የሰብአዊ መብታቸውን በሚያጥላላ ደረጃ መሄድ ከራስ አልፎ መጪውን ትውልድ መበከል ነው።መሪዎችን ኢላማ አድርጎ የችግሮች ሁሉ ምክንያትም መፍትሄም አድርጎ ማቅረብ ግን ታሪካዊ ስህተት ነው።



ማክበር የሚገባንን የያዝነውን የፖለቲካ አቅጣጫ ምሕዋር አለመልቀቅ 


መንግስት አንዴት ይመሰረታል? የሚለው ጥያቄ ሁሌ ሊያቀራክሬን አይገባም።መንግስት ወደ ቤተመንግስት የሚገባው ወደፊትም መቀጠል ያለበት መንገድ ለጊዜው አንድ መሆኑን በትክክል ማመን ይገባል።ችግር በተፈጠረ ቁጥር ትንንሽ ዘውድ መድፋት የሚፈልግ ሁሉ አንዴ በክላሽ ሌላ ጊዜ የራስን ስም ለማግነን በመዋተት የኢትዮጵያን ሕዝብ መከራ የሚያሳዩት ስልጣን ከምርጫ ውጪ ሊገኝ ይችላል በሚል ነው።የያዝነው የፖለቲካ አቅጣጫ አና ምሕዋሩ ስልጣን በምርጫ የሚለው ነው።ይህንን ማዳበር አና ወደ የበለጠ ጥራት ያለው የምርጫ ሂደት ለማሳደግ ሁልጊዜም መስራት ይገባል።ለአዚህ ደግሞ የሚድያው፣የሕግ አውጪው አና ሕግ አስፈፃሚው አንዲሁም የሁሉም ዜጋ ጥረት ይጠይቃል።ስለሆነም ህዝብም አቅጩን መንገር ያለበት ከምርጫ ውጪ የስልጣን መንገድ የለም ነው።ያለው መንግስት ያልተስማማው በመጪው ምርጫ ላይ ለመስራት ይነሳ።ከአዚህ በተለየ ሌላው መንገድ ዝግ በምሆኑን ደጋግሞ መንገር አና ማሳየት በራሱ የብዙ ሰላም ምንጭ ነው።



የምጣኔ ሀብት አድገት ለማምጣት የሚደርገው ጥረትን ወደ መስዋአትነት ደረጃ ማስመንደግ 


ሀገር የሚያፈርሰው የፖለቲካ ስርዓት መፈረካከስ ብቻ አይደለም።የምጣኔ ሃብቱ አለመስተካከል አና ቀጣይነት አና ተከታታይ ትውልድን የሚያሳትፍ የአድገት ሂደት ላይ አለመገኘት በራሱ ሀገር ያፈርሳል።በድህነት ውስጥ የሚዳክር ተከታታይ ትውልድ ለባአዳን ባርነት የመሰጠቱ አደጋ የበዛ ነው።ቀጣይነት አና ተከታታይ አድገት ሲኖር የትውልዱ ተስፋ ይለመልማል።በሀገሩ ላይ ያለው ተስፋም ከፍ ያለ ስለሚሆን ለበለጠ ፈጠራ ይነሳሳል።በመሆኑም የምጣኔ ሀብት አድገት ለማምጣት የሚደረገው ጥረት የህልውናችን አንዱ አካል መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።ህልውና መሆኑን ከተረዳን የህልውና ጉዳይ በተራ ጥረት አና ያዝ ለቀቅ በሚደረግ ሥራ ለውጥ ማምጣት አይቻልም ማለት ነው።

ለማጠቃለል፣ኢትዮጵያን ውጤታማ ወደሆነ የእድገት ደረጃ ለማሸጋገር በትክክል የሚቻልበት መስመር ላይ ሆነን በተሳሳቱ አስተሳሰቦች እና ተስፋ መቁረጥ ወደኃላ የመሄድ ምንም ዓይነት ችግር አንዳይገጥም ሁሉም ከተለመደው አና በመንጋ ከሚሄድ እሳቤ መውጣት አስፈላጊ ነው።የመንግስት ስርዓት ትክክለኛውን መስመር አንዳይለቅ ጋዜጠኞች ተግተው መስራት አለባቸው።ይሄውም ችግሮችን ነቅሶ ከመፍትሔ መፈለግ ጋር ለሕዝብ ማድረስ ይገባል።ህዝብም አንደህዝብ በጋራ በውስጡ ልከፋፍሉት የሚሞክሩትን የሚመለሰውን በፍቅር አና በማስተማር፣የማይመለሰውን ደግሞ በሕግ በማረቅ ስራዎች መስራት ያስፈልጋል።ለእዚህም የተለያዩ ማኅበራዊ አደረጃጀቶች፣የህዝብ ንቅናቄዎች እና ግለሰብ ምሑራን ከላይ የተጠቀሱትን አምስት ጉዳዮች ላይ በጋራ መግባባት አና ግንዛቤ አንድኖር ቢሰራ ብዙ ነገሮች ይቀላሉ።ኢትዮጵያም በሚፈለገው መልክ ከምትፈልገው ደረጃ ለመድረስ አጅግ የተቃና ጎዳና ይሆንላታል።

=============///======

Friday, December 16, 2022

ብልጽግና የኢትዮጵያ የነገ ተስፋ የሆኑ ልጆቿን የሚከፋፍል አጀንዳ በአዲስ አበባ እያራመደ ነው።አስገራሚው ነገር የፓርቲው የሌሎች ክልል አባላት ይህንን ሃገር በታኝ አጀንዳውን ለማስቆም ምንም ጥረት ሲያደርጉ አለመታየታቸው ነው።



  • ድርጊቱ ምንም ዓይነት የጎሳ ፖለቲካ ቅብ ለመቀባት ቢሞከር የድርጊቱ ዋና ግብ የኢትዮጵያን መጪ ትውልድ መከፋፈል እና ኢትዮጵያን ማዳከምን መድረሻው ያደረገ የመርዝ ብልቃጥ ነው።
  •  በምድር ላይ ያለ ማንም መንግስት የብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማውን የሚገዳደር  የአንድ ክልል ሰንደቅ ዓላማ እና መዝሙር ተማሪዎቹ እየዘመሩ እርስበርሳቸው እንዲከፋፈሉ ሲያደርግ ተሰምቶ አያውቅም።

=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

አንድ ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ብልጽግን በጎሳ ፖለቲካ የማያምን እንደሆነ ሲናገሩ '' እኛን ብልጽግናዎችን አትከፋፍሉን።እኛ ብልጽግናዎች ከዘር የተከፋፈለ አስተሳሰብ የጸዳን ነን። እኛ የምንሰራው ለአንዲት ኢትዮጵያ ነው።'' ማለታቸውን አስታውሳለሁ።ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ይበሉ እንጂ በብልጽግና ውስጥ የተሰገሰጉ ህዝብ የሚያውቃቸው ዋልታ ረገጥ የለየላቸው አክራሪ የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች ግን መኖራቸው የአደባባይ ምስጢር።ይህም በመሆኑ ዛሬ ላይ ኦሮምያን እንደ አንድ ሃገር የምትመስላቸው ለሕግም ለሕዝብም የማይገዙ ጡቷን አጥብታ ያሳደገቻቸው ኢትዮጵያ ነገ ልጆቿ በአንድነት እና በፍቅር ተምረው አድገው እኩል ብሔራዊ ስሜት እንዳይኖራቸው ለማድረግ እንቅልፍ ያጡ ፖለቲከኞች የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ''እኛን አትከፋፍሉን በጎሳ አናስብም '' ካሉት ከብልጽግና ውስጥ ነው።

ሰሞኑን የብልጽግና ኦሮምያ ክልል ተወካዮች በየትኛውም የሕግ አግባብ የሌለ እና የኢትዮጵያ የነገ ተስፋ ልጆች ነገ አድገው እንዳይግባቡ ለማድረግ ከፋፋይ ዘመቻ በይፋ ተከፍቶባቸዋል። በየትኛውም የዓለም ክፍል የሌለ በአንድ ትምሕርት ቤት ውስጥ ሁለት መዝሙር እና ሁለት ሰንደቅ ዓላማ ለመስቀል ከራሱ ከብልጽግና የተወከሉ የአዲስ አበባ ባለስልጣናት ካለምንም እፍረት በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እና ፋና ብሮድካስት እየቀረቡ ይህንን የመከፋፈል አጀንዳ ሲመጻደቁበት መታየታቸው ነው።

በአዲስ አበባ ትምሕርት ቤቶች የኦሮምያ ክልል ዓርማ  የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ በሚገዳደር መልኩ እንዲሰቅል፣የክልሉ መዝሙርም የሃገሪቱን ብሔራዊ መዝሙር በሚጋፋ መልኩ እንዲዘመር የአዲስ አበባ ክልል አስተዳደር ባለስልጣናት የጀመሩት ተግባር የኢትዮጵያን መጪ ትውልድ ለመበተን ያለመ እና የባዕዳን ተልዕኮ ያለበት ነው።ምንም ዓይነት የጎሳ ፖለቲካ ቅብ ለመቀባት ቢሞከር የድርጊቱ ዋና ግብ የኢትዮጵያን መጪ ትውልድ መከፋፈል እና ኢትዮጵያን ማዳከም ነው።ይህ ምንም ዓይነት ምርምር የማይጠይቅ ግልጽ እና ጥርት ያለ ጉዳይ ነው። በምድር ላይ ያለ ማንም መንግስት የብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማውን የሚገዳደር  የአንድ ክልል ሰንደቅ ዓላማ እና መዝሙር ተማሪዎቹ እየዘመሩ እርስበርሳቸው እንዲከፋፈሉ ሲያደርግ ተሰምቶ አያውቅም።

የኢትዮጵያ ሕዝብ የቱ ጉዳይ ምን ያህል እርቀት ሃገር እንደሚበትን፣የትኛው በትዕግስት ቢታለፍ ለጊዜው ችግር እንደሌለው ጠንቅቆ እና ልቅም አድርጎ ያውቃል።የቱ ጋር መሞት እንዳለበት የቱን በትዕግስት ማለፍ እንዳለበት ይረዳል። ችግሩ መሪዎቹ ያወቁት ሲመስላቸው አያውቁትም።የተረዱት ሲመስላቸው ሁል ጊዜ እንደ እንግዳ ደራሽ ሲደናገሩ ህዝቡ ቀድሞ ከፊታቸው ይደርሳል። በሰሞኑ የአዲስ አበባ ተማሪዎች የብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማን እና መዝሙር በሚጋፋ መልኩ የኦሮምያ ክልል መዝሙር እና ዓርማ እንዲዘመር እና እንዲሰቀል የሚወተውቱት ባለስልጣናት በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን እና በፋና እየቀረቡ የሚናገሩት አሳፋሪ፣አንድ ፊደል ቆጥርያለሁ ኢትዮጵያ ጡቷን አጥብታ አሳድጋኛለች ብሎ የሚያስብ ዜጋ የማይናገረው ኃላፊነት የማይሰማው ንግግር ነው።

በመጀመርያ ከከንቲባ አዳነች ጀምሮ ምክትል ከንቲባው አቶ ዣንጥራር እና የአዲስ አበባ ክልል አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሳምሶን መለሰ ከንቲባዋ ሕዝብ ሲያወያዩ የተናገሩት አቶ ዣንጥራር በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ታኅሳስ 6/2015 ዓም የተናገሩት እና ታኅሳስ 7/2015 ዓም አቶ ሳምሶን መለሰ ደግሞ በፋና ቴሌቭዥን ቀርበው ሲናገሩ ጉዳዩን የአዲስ አበባ ህዝብ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው ኦሮምኛ የሆኑ ኢትዮጵያውያን በቋንቋቸው እንዳይማሩ ከመፈለጉ አስመስሎ ለማቅረብ ብዙ ሲጋጋጡ ማየት እራሱን የቻለ ድራማ ነው። ይህ በራሱ የተቀመጡበትን የሕዝብ ወንበር ክብር አለመስጠት ነው። አቶ ሳምሶን ፋና ቴሌቭዥን ላይ ጋዜጠኛ ዳዊት መስፍን ደጋግሞ የአፍ መፍቻ ቋንቋ ላይ አይደለም ጥያቄው እያለው መልሶ ወ/ሮ አዳነች እና አቶ ዣንጥራር ሲሉት የነበረውን ስለአፍ መፍቻ ቋንቋ ለማስረዳት በመሞከር ዋናውን ጥያቄ ለማለፍ የሞከረው ሙከራ አስቂኝ ነበር።ጋዜጠኛ ዳዊት ግን አልለቀቀውም ደጋግሞ ወደ ዋናዋ ጥያቄ ''በአዲስ አበባ የኦሮምያ ዓርማ እና የክልል መዝሙር ከብሔራዊ መዝሙር ጋር እንዲዘመር የሚያዝ የሕግ አግባብ አለ ወይ?'' በማለት ጠየቀ።

የእዚህን የጉዳያችን ምጥን የማጠቃልለው ድርጊቱ ምን ያህል የኢትዮጵያን መጪ ትውልድ ለመከፋፈል የታለመ የባዕዳን እጅ እንዳለበት የሚያመለክተውን መልዕክት ከላይ በፋና ቴሌቭዥን ዓርብ ታኅሳስ 7/2015 ዓም አቶ ሳምሶን መለሰ በግልጽ አስቀምጠውታል። በእዚሁ ቃለ ምልልስ ላይ ጋዜጠኛ ዳዊት ጠየቀ -
''የኦሮምያ ዓርማ እንዲሰቀል ያደረግነው እና የክልሉ መዝሙር እንዲዘመር የተደረገው ኦሮምኛ የሚማሩ ልጆች ስላሉ ነው ብለዋል።አዲስ አበባ ደግሞ ብዙ ብሔሮች አሉ እና ነገ ሌሎቹ ኢዲስ አበባ በቋንቋቸው ሲማሩ እነርሱም የክልላቸውን ሰንደቅ ዓላማ እንዲሰቀል፣የክልላቸውም መዝሙር እንዲዘመር ታደርጋላችሁ?''

አቶ ሳምሶን የአዲስ አበባ ትምሕርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ሲመልሱ ''አዎን እናደርጋለን '' ነበር ያሉት።

ይህ ምላሽ በራሱ የሚገልጸው የኦሮምያ ክልል መዝሙር፣ዓርማ የተባለው ሁሉ ግቡ የኢትዮጵያን መጪ ትውልድ ዋና እምብርት የሆኑትን ትምሕርትቤቶች ማዕከል አድርጎ ኢትዮጵያዊ ብሔራዊ ስሜትን ማጥፋት እና መከፋፈል ነው።ይህ ደግሞ እየተሰራ ያለው በብልጽግና ውስጥ ከፍተኛ ባለስልጣናት በብሔር ከተደራጁ የጽንፍ ኃይሎች ጋር እጅና ጓንት ፈጥረው እያራገቡት ያለው አጀንዳነው።ብልጽግና የኢትዮጵያ የነገ ተስፋ የሆኑ ልጆቿን የሚከፋፍል አጀንዳ በአዲስ አበባ እያራመደ ነው።አስገራሚው ነገር የፓርቲው የሌሎች ክልል አባላት ይህንን ሃገር በታኝ አጀንዳውን ለማስቆም ምንም ጥረት ሲያደርጉ አለመታየታቸው ነው።

==========////==========

ይሄንን በልጅነቱ በኢትዮጵያ ፍቅር የተቃጠለ ትውልድ ለመበተን ነው ዓላማው።
የዜግነት ክብር!



Monday, December 12, 2022

ህወሓት ቀርጾ የሰጠውን የኦሮምያ ክልል ዓርማ እና ደርሶ የሰጠውን መዝሙር ከልሉ ውጭ በአዲስ አበባም ካልዘመርኩ ማለት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ነው።የአዲስ አበባ ህዝብ ኢትዮጵያውያን በፈቃዳቸው ኦሮምኛ አይማሩ አላለም።ይህንን በሃሰት የሚያራግቡ አመራሮች ቆም ብለው ማሰብ አለባቸው።



  • አዲስ አበባ ከኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ጎን የአፍሪካ ሕብረት ሰንደቅ ዓላማ ብትሰቅል ይመጥናታል።
  • አሁን በአዲስ አበባ የኦሮምያ ሰንደቅ ዓላማ እና የክልሉን መዝሙር በተመለከተ ያሉት አራት እውነታዎች 
  • የኦሮምያ ክልል ህዝብ በጊዜ መንቃት አለበት።
  • መንግስት ማድረግ የሚገባው 
==========
ጉዳያችን ምጥን
==========
ዛሬ ታህሳስ 3፣2015 ዓም በአዲስ አበባ ሽሮሜዳ አካባቢ በሚገኘው እንጦጦ አምባ ትምህርት ቤት  እና የአየርጤና ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የኦሮሚያ ክልል ዓርማ እና መዝሙር ተማሪዎች በግዳጅ እንዲዘምሩ በተደረገ ሙከራ ሳብያ ድጋሚ ተቃውሞ ተነስቷል::አዲስ አበባ የሁሉም ብሔሮች መኖርያ ሆና ሳለ የአንድ ክልል ዓርማ ይሰቀል የሚሉ በፌደራል አስተዳደር ስር የተሸሸጉ የፅንፈኛ ቡድኖች ዋና አቀንቃኞች ናቸው::በዛሬው ውሎ ከሽሮሜዳ ወደ አሜሪካ ኤምባሲና ወደ ጉስቋም ማርያም የሚወስደው መንገድ ለተወሰነ ጊዜ ዝግ ነበር::እዚህ ላይ ማወቅ የሚገባን ጉዳይ በኃይል ለመጫን የሚሞከር ማናቸውም ዓይነት ባሕል እና አመለካከት የበለጠ በህዝብ እየተጠላ ይመጣል::ይህ የታሪክ ሀቅ ነው::አሁን ይዘመር እየተባለ ያለው የኦሮምያ ክልል መዝሙር በህወሓት ተደርሶ ለኦሮምያ ክልል የተሰጠ ሲሆን መዝሙሩ በይዘቱ ከፋፋይና የቂም ቃላትን የያዘ ነው::የመዝሙሩ ይዘት ምንም ይሁን ምን፣አዲስ አበባ እንደ አንድ በህገ መንግስቱ እንደተመሰረተ ክልል የራሷ የሆነ የውስጥ መተዳደርያ ደንብ ሊኖራት ይገባል።ይህ መብት የክልል የመስፋፋት ፖሊሲ የያዙ የጽንፍ ኃይሎች እንደፈለጉ ከሕግ ውጭ እንዲፈነጩ አረንጓዴ መበራት እያሳዩ ያሉት አሁንም በስልጣልን ላይ ያሉት የቀድሞ ኦህዴድ እና ዘግይተው የተቀላቀሉት የኦነግ የጽንፍ አራማጆች ናቸው።

ዛሬ በአንዳንድ የአዲስ አበባ አንዳንድ ትምሕርትቤቶች የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማም ሆነ የኦሮምያ ዓርማ ሳይሰቀል ትምሕርቱ የተካሔደባቸው አካባቢዎች አሉ:: የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ሳይሰቀል በትምህርትቤቶች ሳይሰቀል ትምሕርት ማስተማር በራሱ የመንግስት ብቻ ሳይሆን የሀገር የአንድነት ዓርማ ከተማሪዎች አዕምሮ በማራቅ የማድረግ ሙከራ ብቻ ሳይሆን የሕገመንግስት ጥሰት ነው።የመንግስት ህልውና መገለጫው የሰንደቅ ዓላማ በሚገባው የመንግስት ተቋማት ትምሕርትቤቶች ጨምሮ በሥነስርዓት መሰቀሉ አንዱ እና ዋነኛው ነው።

አሁን በአዲስ አበባ የኦሮምያ ሰንደቅ ዓላማ እና የክልሉን መዝሙር በተመለከተ ያሉት አራት እውነታዎች 
  • በእዚህ ጊዜ አጀንዳው የተነሳበት ምክንያት በኦሮምያት ክልል ውስጥ በጽንፈኛው የኦነግ ሸኔ የቀረውን የክልሉን የኦሮምኛ ተናጋሪ አንዱን የኦህዴድ ሌላውን የሸዋ ኦሮሞ እያለ እየከፋፈለ ስለሆነ በእዚህ ሳብያ በተነሳው የክልሉ የውስጥ ውጥረት እንደ ማብረጃ ተደርጎ ተወስዷል።
  • በእዚሁ የመከፋፈል አጀንዳ ላይ የጋራ የክልሉ አጀንዳ በመፍጠር የውስጥ አንድነት ያመጣል በሚል ይህ የባንዲራ ጉዳይ ተፈልጓል።
  • በኦሮምያ ክልል እና በአዲስ አበባ አስተዳደር ውስጥ እና በአዲስ አበባ ዙርያ ጋር በተቀናጀ የተፈጸሙ ዘግናኝ የሙስና ዘራፊዎች በሰሞኑ የመንግስት እንቅስቃሴ ሊመቱ እንደሆነ ስላወቁ ይህንን የባንዲራ አጀንዳ ማንሳት እና ክልሉ እንዳይረጋጋ እና ቀጥሎም መንግስትን ማዋከብ ተፈልጓል።
  • በእዚህ ሁሉ እንቅስቃሴ ላይ ከውስጥ ሆነው በአዲስ አበባ አስተዳደር ውስጥ በክፍተኛ አመራር ላይ ያሉ ከጽንፈኞቹ ጋር የሚሰሩ አሉ።እነኝህ ከሁሉም ገለልተኛ መስለው ሁሉንም እየወቀሱ ግን የጽንፍ ኃይሉን የሚደግፉት አጀንዳውን በይበልጥ ከመንግስት ወገን ሆነው በማራገብ ነው።
የኦሮምያ ክልል ህዝብ በጊዜ መንቃት አለበት።
  • አሁን በትምሕርትቤቶች ውስጥ ህጻናቱን ኦሮሞ የሆነ እና ያልሆነ የሚል ክፍፍል ለመፍጣር በንጹሃን አዕምሮ ላይ ወንጀል መስራት ተጀምሯል።ይህንን የኦሮሞ ህዝብ በስሙ የሚደረገውን ንግድ ሊቃወመው ይገባል።
  • የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የጸናችው በእነ ጀነራል ጃጋማ ኬሎ፣ ኮሎኔል አብዲሳ አጋ እና በሌሎች ሚልዮኖች የኦሮሞ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ነው።ዛሬ ከህወሃት የተሰጣቸውን ዓርማ እና መዝሙር ይዘው አዲስ አበባ ላይ ህዝብ ለመከፋፈል የሚነሱ የጽንፍ ኃይሎችን መቃወም ከኦሮምኛ ተናጋሪው ኢትዮጵያዊ ይጠበቃል።
መንግስት ማድረግ የሚገባው 
  • ፌድራል መንግስት ላይ ተቀምጠው እንደኦሮምያ ክልል አስተዳደር ኢትዮጵያን ለማስተዳደር የሚሞክሩትን በጊዜ አደብ ማስገዛት አለበት።እነኝህ ናቸው የአዲስ አበባ ህዝብ ጥላቻ ስላለበት ነው የሚል የተሳሳቱ ቃላትን በመግለጫዎቻቸው ላይ እየሰነቀሩ ጉዳዩን ሌላ ቅርጽ እንዲይዝ የሚያደርጉት። የአዲስ አበባ ህዝብም ሆነ የኢትዮጵያ ህዝብ ኢትዮጵያዊ የሆነ የማንም ክልል ቋንቋ ማንም በፍላጎቱ አይማር የሚል ቅሬታ የለውም። 
  • አዲስ አበባ በተለየ መልኩ የሁሉም ክልል መኖርያ መሆኗን የኦሮምያ ክልል የጽንፍ ኃይሎች እንዲያውቁ ለመጨረሻ ጊዜ ማሳወቅ ብቻ ሳይሆን ህገመንግስቱ በሚያዘው መሰረት አዲስ አበባን መብቷን ሊያከብርላት ይገባል።አዲስ አበባ ከኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ጎን የአፍሪካ ሕብረት ሰንደቅ ዓላማ ብትሰቅል ይመጥናታል።
  • በሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች በአዲስ አበባም የሰንደቅ ዓላማ አሰቃቀል ሥነ ስርዓት በተለይ በትምህርት ቤቶች በሚገባ እንዲተገበር ልዩ የቁጥጥር ሥርዓት ማውጣት አለበት። ዛሬ በአዲስ አበባ ከእዚህ በፊት የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ይሰቅሉ የነበሩ ሁሉ ከጭቅጭቅ በሚል ያልሰቀሉ መኖራቸው ተሰምቷል። ይህ የመንግስት የመኖር እና አለመኖር መገለጫ አንዱ ማሳያ ነው። በሃገሪቱ ዋና ከተማ የሃገሩ ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማን በአግባቡ ማሰቀል ያልቻለ መንግስት ማለት ትርጉሙ ብዙ ነው።
ለማጠቃለል የሰንደቅ ዓላማ ጉዳይ ከኦሮምያ ክልል አርማ እና ህወሓት ቀርጾ የሰጠውን የኦሮምያ ክልል ዓርማ እና ደርሶ የሰጠውን  መዝሙር ከልሉ ውጭ በአዲስ አበባም ካልዘመርኩ ማለት የጽንፈኝነት የመጨረሻው ጥግ ነው።የአዲስ አበባ ህዝብ ኢትዮጵያውያን በፈቃዳቸው ኦሮምኛ አይማሩ አላለም።ይህንን በሃሰት የሚያራግቡ አመራሮች ቆም ብለው ማሰብ አለባቸው።እደግመዋለሁ፣በፍላጎቱ ማንም በቋንቋው አይማር በሚል የአዲስ አበባ ሕዝብ አልተቃወመም።አዲስ አበባ የሁሉም ክልሎች መኖርያ ስለሆነች አንድ ክልል ለብቻው ተነጥሎ ዓርማውን በትምሕርትቤቶች መስቀሉ ግን አደጋ አለው ሕገመንግስታዊም አይደለም እያለ ነው።ከጭቅጭቅ በሚል አጓጉል አካሄድ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ያልተሰቀለባቸው ትምሕርት ቤቶችም በፍጥነት ሰንደቅ ዓላማውን መስቀል ሕገመንግስታዊ ግዴታቸው ነው!

Thursday, December 8, 2022

ክቡር ጠ/ሚ/ር ዐቢይ አሕመድ ትናንት በጽሑፍ ዛሬ ደግሞ በቀጥታ ንግግር ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያስተላለፉት መልዕክት ፍጹም ኢትዮጵያዊ እና ታሪካዊ መልዕክት የያዘ ነው።በአጽንኦት ማዳመጥ የሁሉም ኢትዮጵያዊ ፋንታ ነው።


  •  ከሃሰተኛ ዩቱበር ተንታኞች እራስን ለመጠበቅ ከምንጩ አድምጦ በተሰጠን አዕምሮ ተጠቅመን ማገናዘብ፣ ጤናማ አስተሳሰብ ነው።
  • የዛሬውን የንግግራቸው እና የትናንቱን የጽሑፍ መልዕክት፣ ሁለቱንም በቪድዮ እና ኦድዮ ከስር ያገኛሉ።



የትናንቱ የጽሑፍ መልዕክት በንባብ

የቪድዮ ምንጭ = ፋና ብሮድካስት

Tuesday, December 6, 2022

ኢትዮጵያ የጎሳ ፖለቲካን መርዝነት የተረዳ መሪ አላት ወይ? እንደርሱ ችግሩን የተረዱ የመንግስት ባለስልጣናትስ አሉ ወይ? መልሱ አዎን! ነው። መሪዎቿ ከሁሉ በፊት የሰው ህይወት ለመታደግ መንቀሳቀስ አልነበረባቸውም ወይ? አሁንም መልሱ አዎን! ነበረባቸው ነው።ኢትዮጵያውያን! ወቅታዊውን ችግር በቅንጥብጣቢ ጊዜያዊ መፍትሔ አንፈታውም።



ለውስጣዊ የጸጥታ ችግሮቻችን መፍትሔነት ሦስቱ መፈታት ያለባቸው መሰረታዊ ጥያቄዎች።


==========
ጉዳያችን ምጥን
==========
በማንነት ጥቃት ኢትዮጵያውያን ሲገደሉ፣ሲታሰሩና ሲሰደዱ ዓመታት ተቆጠሩ።በተለይ ባለፉት አራት ዓመታት እጅግ ጽንፈኛ እና ዘረኛ አደረጃጀት የነበራቸው እንደ ኦነግ ያሉ አደረጃጀቶች ወደ ሃገር ውስጥ ገብተው በፌድራል እና በተለየ በኦሮምያ ክልል ከልዩ ኃይል አባልና አመራር እስከ የክልሉ ምክርቤት ድረስ ገብተዋል። ይሄው ኃይል የነበረውን የኢትዮጵያን የመጥላት እና በአማራ ላይ የተተረከለትን ትርክት እና እራሱ የፈጠራቸውን ፈጠራዎች ይዞ ትውልድ በክሏል። 

በወለጋ በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ ዘርን መሰረት አድርጎ እየተፈጸመ ያለው የሰሞኑን ጥቃት ከእዚህ በፊት ከነበረው በተለየ የክልሉ ልዩ ኃይል ከእዚህ በፊት በርካታ በደሎችን እና ግድያዎችን ቢፈጽምም እንደ የሰሞኑ ያለ ከሸኔ ጎን ተሰልፎ መንደሮችን እየለየ አብሮ የሚያጠቃ ሆኖ ዓይን ያወጣ ተግባር የለም።አሁን ክልሉ እራሱን መቆጣጠር ያቃተው ልዩ ኃይሉ በራሱ እንደፈለገው የሚሔድ ሆኗል።በሌላ በኩል እራሳቸውን ለመከላከል የተነሱ ሚሊሻዎችም ኢትዮጵያ ሃገራችን ነች መንግስት ካልተከላከለልን እራሳችንን እንከላከላለን ብለው ቢያንስ ቤተሰባቸውን ሊከላከሉ እየታገሉ ነው። በእዚህ ሁሉ መሃል እዚህም እዚያም ክፉ አካሄዶች ይኖራሉ።በምንም መለክያ ግን አማራ በሚል ዘርን በመለየት የተፈጸመውን ያህል ግፍ ግን በሌላው አልታየም።ከአርባጉጉ እስከ ጉርዳፈርዳ፣ከወለጋ እስከ ሻሸመኔ በጥላቻ ያልተፈጸመ የግፍ ዓይነት የለም።

የብዙዎች አፍ ማሟሻ በተለይ የወለጋው ዓይነት ችግር ሲፈጠር በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ የስድብ ውርጅብኝ ማውረድ ነው።አንዳንዶች ደግሞ መንግስት ቢቀየር መፍትሔ የሚመጣ፣አብዮት ቢካሄድ ኢትዮጵያ የምትቀየር ወይንም የእኛ ትውልድ ሰፈር ሰው አራት ኪሎ ቢገባ መፍትሄ የሚገኝ ሁሉ ነገር ጸጥ የሚል ይመስለናል። ይህ ሞኝነት ነው። በ1966 ዓም የኢትዮጵያ አብዮት ይዞት የተነሳው መሰረታዊ የህዝብ ተገቢ ጥያቂዎች ቢኖሩም የመንግስት ስሪቱን በሆይ! ሆይ! እና ድንጋይ በመወርወር ያፈረሱት ዛሬ ድረስ የማይለቀን የሃገር ውርደት አብሮ እንዳመጣ መካድ አይቻልም። ዛሬም የችግሩን ሥር መረዳት እና መፍትሄውም አንዱን ክር ለማሰር ሌላውን መፍታት ዓይነት እንዳይሆን ሁሉን ያማከለ መሆን አለብት። ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብ ከማንም የዓለም ክፍል በተለየ የብዙ ችግሮችን የማለፍ እና በይቅርታ መጪውን መሻገር የሚችል ህዝብ ነው።ይህንን ሌላ እማኝ መጥራት አያስፈልግም የሰሜኑ ጦርነት ቆመ ሲባል ህዝብ የቂም በትሩን ሳይመዝ ወደ ቀሪ ህይወቱ ሄደ እንጂ እንዲህ ሆኜ እንዲያ ተደርጎ በሚል ክርክር ውስጥ አልገባም። ይህ ትልቁ ግን ያላደነቅነው ዕሴታችን ነው። ስለሆነም ዛሬም ይህንን ችግር የመፍታቱ ክህሎት እኛው ጋር አለ።

ወደ አንዱ መገለጫ እና የብዙ ንጹሃን ኢትዮጵያውያን በተለይ የአማራ ተወላጅ በሚል የተገደሉበት፣የተዘረፉበት እና የተሰደዱበት የወለጋው ጉዳይ ስንመጣ ኦነግ ሸኔ የብሔር ጥያቄውን ወደ የመሬት ጥያቄ በማውረድ የኦሮሞ ህዝብ እና የአማራ ህዝብን ለማጋጨት የሞከረበት ሙከራ ሰሞኑን ወደ አደገኛ ደረጃ እየተቀየረ ነው።ወለጋ የኦሮሞ መሬት ብቻ ጎጃም የአማራ መሬት ብቻ ወይንም ጅጅጋ የሱማሌ ብቻ የሚለው አስተሳሰብ መሰረታዊ የአስተሳሰብ ችግር ብቻ ሳይሆን የህወሃት/ኢህአዴግ የተከለው መርዝ ነው። መርዙ አለ።ልንክደው አንችልም።የሰዎች አስተሳሰብ ቀይሯል።ይህንንም መሬት ላይ ያለ ሃቅ ነው አንክደውም። መፍትሔዎቹ በአጭር ጊዜ ቆራጥ አቋም የሚፈልጉ እና በረጅም ጊዜ የሚሰሩ ሥራዎች ይፈልጋል።

ኢትዮጵያውያን! ወቅታዊውን ችግር በቅንጥብጣቢ ጊዜያዊ መፍትሔ አንፈታውም። 

ቅንጥብጣቢ ጊዜያዊ መፍትሔዎች ችግሩን አይፈቱትም።የፖለቲካ አደረጃጀቶች እና ክልሎች በህዝቡ ስም በሚያደርጉት ጊዜያዊ ስምምነት እና ጎን ለጎን በመቀመጥ በሚደረግ ዲስኩር አይፈታም።ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን በወለጋ ጉዳይ ላይ ቸልተኝነት አሳይተዋል የሚሉ የብዙዎች ድምጽ ነው።ይህ ቸልተኝነት የሚገለጸው ችግሮች በተፈጠሩ ጊዜ የሚያሳዩት የምላሽ እና የቁጣ መጠን በሚድያ አልታየም ብቻ ሳይሆን ወዲያው የጦር ኃይል አዝምተው ንጹሃንን ለመታደግ አልቻሉም የሚለው ነው። ይህ ተገቢ ጥያቄ ነው።ማናቸውም ችግር ከመታየቱ በፊት የማይተካው የሰው ህይወት መታደግ ይቀድማል።የጸጥታ ችግር አተናተን እና ቅድምያ ዝግጅት እና ህዝብን የመከላከል ደረጃ መንግስት በኦሮምያ ክልል ያሳየው መዝረክረክ የትም አልታየም።የሻሸመኔን ጥቃት እና የወለጋ የሰሞኑ ሁኔታዎች በቂ ማሳያዎች ናቸው።

ከእዚህ በተለየ ግን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከኦነግ ጋር አንድ አድርገው የሚያዩ ሰዎች ሁሌ የሚረሱት ጉዳይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኢህአዴግ ስር ሆነው ከኦነግ ጋር የነበረውን የአይጥና ድመት መሳደድ፣በኋላም ይሄው ቡድን በጠቅላይ ሚኒስትሩ ላይ ከናይሮቢ ድረስ ሰው ልኮ ግድያ መሞከሩን እና ወለጋ ላይም የጠቅላይ ሚኒስትሩን ህይወት ለመቅጠፍ ተደጋጋሚ ሙከራ ማድረጉን ይረሱታል።ምክንያታዊ ዕሳቤዎች መልካም ናቸው።አሁን በወለጋ ባለው በሰሞኑ ጉዳይ በኦነግ ሸኔ በኩል በዋናነት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፋኖን እንዳዘመቱ ነው ቅስቀሳ የተያዘው።ሌላው ቀርቶ የጨፌ ኦሮምያ ምክርቤት አባላት ሳይቀሩ በትናንትናው ዕለት በመንግስት ላይ እየዘመቱ የሸኔን ቀጥተኛ አቋም ያንጸባረቁ ለእዚህ ሁሉ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩን የኦሮሞ ጠላት አድርገው ነው ያቀርቧቸው። 

በመሆኑም ይህንን ችግር በስሜት እና በግርግር የሚፈታ አይደለም።የጉዳዩ ቁልፍ ያለው እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣የኢትዮጵያ ህዝብ እና የመከላከያ ኃይል በቅደም ተከተል መመለስ ያሉባቸው  እና ለመልሱም ሁሉም ሊያግዛቸውም የሚገባው የችግሩ ማጠንጠኛ ቁልፍ የሚሆነው አሁንም በሦስቱ ጥያቄዎች አመላለስ ላይ ነው።ኢነርሱም ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የኢህአዴግ/ህወሃት እና ኦነጋዊ የጎሳ ፖለቲካን እንዴት መንቀል ይችላሉ? ህዝቡስ ይህንን በምን ያህል ደረጃ ለማገዝ ቆርጦ ይነሳል? የሕግ የበላይነት እንዴት ይከበራል? የሚሉት ናቸው።መልሶቹን መስጠት ያለብንም ሁላችንም የሚመለከቱን ጥያቄዎች እንደየደረጃችን እነኝህ ይመስሉኛል።
=================

Wednesday, November 30, 2022

A Global Conference, like the UN, does not get attention from the western media when it is held in Africa.

17th UN International Internet Conference is going on in Addis Ababa, Ethiopia


=============

December 1,2022

==============

This Monday, November 28, 2022, Addis Ababa was busy hosting a huge Global Conference, the 17th UN International Internet Conference, that gathered over 3,000 participants worldwide. The meeting, continuing till December 2, 2022, is so important and expected to generate new ideas to the internet world. The Ethiopian Ministry of Innovation and Technology, the Ethiopian Government as a whole, and the African Union make the meeting so pleasant and comfortable for the participants. Addis Ababa, one of the top three diplomatic cities in the world, has a tremendous experience hosting such big conferences. It is impossible to ignore such a vital meeting by any media service that feels responsible to the International community.

On Monday evening, the same day the UN conference opened, I tried to visit different TV channels like BBC, CNN, …and some other known western media. My expectation was that the UN International Internet Conference would be their primary news headline. Because this is a very key meeting that the UN has organized, General Secretary António Guterres's Video message was viewed by the participants, the deputy Secretary presented physically and over 3000 participants from all over the world are attending. So how can the media dare to undermine such a big conference as if it is not useful and universal?   As far as my visit, ‘’all africa.com’’, the UN News Agency, and all Ethiopian local and global media were the major media that took responsibility to update the world on the day-to-day activities of the conference. But other media are almost nothing they did on this very current and annual conference.


I am not talking about local, regional, or continental meetings. I am talking about the Global conference organized by the UN on the issue of our world’s futurity related to the internet. What could be the primary news for any International media, if this conference couldn’t be a focus?

Last year, the 16th Global Internet Conference was held in Poland. I tried to visit how it was reported by similar media on the same issue. We are sharing the same world. Media is responsible for focusing at least on our world’s strategic common issues, like the 17th UN International Internet Conference.


Now here are my questions: what are the criteria of the media for a conference to get attention and be reported primarily? Is it to be an International? Should it be organized by the UN? The 17th UN International Internet Conference fulfilled all these criteria. But not yet get attention or reported by ‘’International’’ media. Yes, the meeting is in Addis Ababa, the Ethiopian capital, where the African Union Headquarters is. My last word is that Africa needs its own media that can at least report to the world, such as a huge global conference.
================

Getachew Bekele

Gudayachn Editor


Saturday, November 26, 2022

የዋጋ ንረት ጉዳይ የፀጥታ አና የሀገር ደህንነት ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ የዋጋ ንረትን ለማቃለል መንግስት መከለስ ያለበት ቁልፍ የፖሊሲ ጉዳይ።


=========
ጉዳያችን ልዩ
=========

አይኢም ኤፍ የዋጋ ግሽበትን (ንረትን) ሲተረጉም ''በተወሰነ ጊዜ ውስጥ የሚለካ አጠቃላይ የዋጋ ንረት ሲሆን ይህ የዋጋ ንረት አጠቃላይ ሀገራዊ የኑሮ ውድነትን ያስከትላል '' በማለት ይገልጸዋል።የዋጋ ንረት የአዳጊው ዓለም ችግር ብቻ ሳይሆን የበለፀጉትም ሀገሮች እራስ ምታት ነው። ይህ ግን በቃ! በአኛ ሀገር የሚፈታ አይደለም ተብሎ አጅ ተጣጥፎ የሚቀመጡበት ጉዳይ አይደለም። ሲጀምር የአዳጊ ሀገሮች የዋጋ ንረት እና ያደጉ ሀገሮች የዋጋ ንረት በገበያ ባህሪውም ሆነ በሕዝቡ የገበያ የመግዛት አቅም አንዲሁም ያለው ነባራዊ የፖለቲካ፣የማኅበራዊ፣የምጣኔ ሃብታዊ አና የሕዝብ ብዛት (ዲሞግራፊ ) ሁኔታ ሁሉ የተለየ ነው። ስለሆነም ከራሳችን ሀገር አንፃር የችግሩ ዓይነትም የተለየ እንጂ በስመ የዋጋ ንረት በቀጥታ የምጣኔ ሀብት ሳይንስ መርሆዎች ብቻ ለመፍታት የሚሞከር አይደለም የሚል አምነት አለኝ። ይህ ማለት መሰረታዊ የዋጋ ንረት የተመለከቱ የምጣኔ ሀብት መርሆዎችን መቃረን ማለት አይደለም።ከአዚህ ይልቅ የአኛ ሀገር የዋጋ ንረት ጉዳይ ከምርት ማነስ አና የብር የመግዛት አቅም መውረድ ባሻገር መታየት ያለባቸው ሦስት ቁልፍ ጉዳዮች ላይ ለማትኮር ነው።

የነፃ ገበያ የተረዳንበት አግባብ ''ከመምህሩ ደቀመዝሙሩ'' ሆኗል።

የነፃ ገበያ የሚለው ፅንሰ ሃሳብ ከተወለደበት ያደጉ ሀገሮች ወደ አፍሪካ አና የአኛ ሀገር ሲመጣ የሆነ ልቅ የሆነ የገበያ አስተሳሰብ አንዳለ ተደርጎ ተተርጉሟል ወይንም ያደጉት ሀገሮች የአኛን ምሁራን ሲያስተምሩ አጋንነው ነግረውብናል አልያም በሚገባ አልተረዳነውም።ነፃ ገበያ ጥሬ ትርጉሙ ዋና ማጠንጠኛ የሚያርፈው ዋጋ የሚወሰነው በፍላጎት ስፋት አና ጥልቀት መሰረት ኩባንያዎች በሚያደርጉት የአርስ በርስ ነፃ ውድድር ነው የሚል ነው። ይህ ፅንሰ ሃሳቡ ነው። በአዚህ መሰረት ብቻ ነው ግን ያደጉት ሀገሮች የሚሰሩት? የአሜሪካ መንግስት አንዳንድ ኩባንያዎች ከሚገባው በላይ ስያብጡ ከአዚህ በላይ ማበጥ አትችሉም።አደጋ አለው በሚል በከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ ከሩቻቸው አልገታቸውም? 

አሜሪካ አንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 1890 ዓም ያወጣችው ''የሻርመን ሕግ'' አንዱ አና በዋናነት የሚያዘው ግዙፍ ኩባንያዎች አና ነጋዴዎች ገበያውን ባላቸው የመቆጣጠር አቅም ምክንያት የዋጋ ንረቱን አንደፈለጉ አንዳያወጡት ብቻ ሳይሆን ገበያውን ሕገወጥ አንዳያደርጉት የታሰበበት ነው።በአዚህ መሰረት አንደማይክሮሶፍት ያሉ ግዙፍ ኩባንያዎችን የአሜሪካ ፍርድቤት አየጠራ የማስተካከያ የሕግ ''ሞረዱን'' አሳይቷል። አዚህ ላይ ከኢትዮጵያ አንፃር ሲታይ ይህ የሞኖፖል የገበያ ሁኔታ ላይ መች ደረስን? የሚል ጥያቄ ሊያስነሳ ይችላል። ጉዳዩ የተነሳው የነፃ ገበያ በመርህ ደረጃ ያለ አንጂ በአውነታው ሲታይ ግን መንግሥታት በተለያዩ ፖሊሲዎቻቸው የዋጋ ሁኔታዎችን የመቆጣጠራቸው ሚና የማይተካ መሆኑን ለማሳየት የቀረበ ነው።የነፃ ገበያ ፅንሰ ሃሳብ አመንጭዎችም ሆኑ አራማጆች ቆይተው የተረዱት ብቻ ሳይሆን አየተገብሩት ያለው።ገበያውን ለነጋዴው ለቆ ቤተመንግስት የከተተ መንግስት ፈፅሞ አንደሌለ አና ወደፊትም ሊኖር አንደማይችል ነው።አዚህ ላይ ያለው ችግር ገበያውን ላቃና ብሎ የሚነሳ መንግስት ሹማንቶቹ በገበያው ገዢዎች የብር አቅም በመማለል የመንግስትን የቁጥጥር አቅም ሽባ የማድረጋቸው አደጋ መኖሩን የሚክድ የለም።ይህ አራሱ አውድ ከሙስና ጉዳዮች ጋር የሚታይ በመሆኑ ወደአርሱ ከመግባታችን በፊት በራሱ የዋጋ ንረት ዙርያ ላይ አንቆይ።

የዋጋ ንረት መዘዝ ቀላል አይደለም።

የዋጋ አለመረጋጋት አና ንረት የዋዛ መዘዝ አያስከትልም።ብዙ ሀገሮችን የተራዘመ አለመረጋጋት ከከተታቸው ውስጥ የዋጋ ንረት አንዱ አና ተጠቃሹ ነው።የማዕከላዊ ባንክ (በሌሎች ሀገሮችም ያሉ) የዋጋ ንረትን የዋጋ ግሽበት በምትል ማቆላመጫ ይጠሩታል።ይህም ችግሩን ከፖሊሲ ውጭ የማራቅያ መንገድ መሆኑ ነው።የብዙ ሀገሮች የፖለቲካ መሪዎች ወደ ስልጣን መውጫ አንዱ መሰላል የዋጋ ንረት አስወግዳለውሁ፣የኑሮ ውድነቱን አሻሽላለሁ የሚሉ የተለመዱ አባባሎች ናቸው።በቅርቡ በአንግሊዝ የጠቅላይ ሚኒስትር ለውጥ አንደ ፎጣ በቶሎ ስፋጠን ያየንበት ምክንያት ይሄው የዋጋ ንረት አና አርሱን ተከትሎ በመጣው የኑሮ ውድነት ሳብያ ነው።አንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 1974 ዓም በኢትዮጵያ የ1966ቱ አብዮት በፈነዳበት ዓመት የአሜሪካ ፕሪዝዳንት ጂራልድ ፎርድ በአሜሪካ የተከሰተውን የኑሮ ውድነትን ''የህዝብ ጠላት'' በማለት ሰይመውት የነበረው ከጉዳዩ አስከፊነት አንፃር ነበር።

ዛሬም የዋጋ ንረት ሕዝብን ገፋፍቶ ወደ ተሳሳተ አስተሳሰብ የመምራት አደጋ አለው።ሕዝብ የሚመለከተው የዕለት ኑሮውን ለማሸነፍ መሮጥ ላይ አንጂ የነገውን ጉዳይ የመመልከት አቅም ውሱንነት አንደየግንዛቤው ይለያያል።ስለሆነም ተስፋ የሚሰጡ ጮሌዎች በኑሮው ጉዳይ አየገቡ በማታለል ዘለቂታዊ የሀገር ጥቅም ላይ ተረማምዶ ጠንካራ ለሀገር አሳቢ መንግሥታት ላይ በጥላቻ አንድነሳ ይቀሰቅሱታል።በዙምባቤ፣በብራዚል አና ሌሎች ሀገሮች የሆነው ይሄው ነው።ስለሆነም የዋጋ ንረት ጉዳይ የፀጥታ አና የሀገር ህልውና ጉዳይም ነው።

ኢትዮጵያ የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጂን) ለከት የሚለካ ጥብቅ ደንብ ያስፈልጋል።

ትርፍ ማለት በጥሬ ትርጉሙ አንድ የንግድ ድርጅት ወይንም ነጋዴ ጠቅላላ ገቢው ከጠቅላላ ወጪው በልጦ የመገኘቱ ሁኔታ ነው።የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) የትርፉ መቶኛ መገለጫ ነው።ይህ የትርፍ መቶኛ መጠን በቀጥታ ለንግዱ ባለቤት የሚገባ ወይንም ለኩባንያዎች ሲሆን ደግሞ  ለባለ አክስዮኖች የሚከፈለውን መጠን  ወይንም ለኩባንያው አድገት መልሶ መዋዕለ ንዋይ ለማፍሰስ  ውሳኔ ለመስጠት የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) ማወቅ ይጠቅማል።

የአንድ ነጋዴ የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) ለማግኘት ቀመሩ ጠቅላላ ገቢ ሲካፈል ለትርፍ ሲባዛ ለመቶ ( ጠቅላላ ገቢ /ትርፍ x 100= የትርፍ ህዳግ) ነው።ኢትዮጵያ ውስጥ መረን የተለቀቀው አና ነጋዴ ይሉኝታ ያጣበት ጉዳይ ይህ ነው።መሰረታዊ ችግራችን የነጋዴዎቻችን የጨዋነት አና የስብዕና ጥራት (ሌላ የተሻለ ቃል ባለማግኘቴ ይቅርታ እየጠየኩ) አጅግ መውረዱ ነው።ነጋዴ (በእንግሊዝኛው ''ቢዝነስ ማን/ዉመን'') የሚለው ቃል የራሱ የሆነ የጥብቅ ስነ ምግባር አና የመታመን መገለጫ ቃልም ነው።በአኛ ሀገር ታሪክም ነጋዴ የሚታመን ለመሆኑ ለዘመናት ብዙ የአደራ ልውውጦች፣መልዕክቶች ሰው ልጁን ሳይቀር ወደ ሌላ ሀገር ሲያሻግር አደራ ብሎ የሚልከው ያለውን ወረት (ገንዘብ) በአደራ የሚያስቀምጠው በነጋዴዎች በኩል ነበር።የቀደሙት ነገሥታቶቻችን ሀገር አልፈው የሚመጡ ነጋዴዎች የሚሰጧቸው መረጃዎች፣ከተመለከቱት አና ካላቸው ልምድ የሚመክሩት ምክር ይደመጣል።አየቆየ ግን ነጋዴ የሚለው ቃል ''የትም ፍጭው ዱቄቱን አምጪው'' ዓይነት ምንም ብለህ ምንም አድርገህ ትርፍ አምጥተህ ሃብታም መሆን የሚለው አስተሳሰብ የነጋዴ ነው የሚል የተሳሳተ እሳቤ በህብረተሰባችን ላይ አየተስፋፋ መጣ።

ይህ አስተሳሰብ በተለየ መንገድ የሰፈነው በወታደራዊው በኃላ ደግሞ አጅግ በከፋ መልኩ በህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን ነው።በወታደራዊው መንግስት ዘመን የግል ሀብት የካፒታል መጠን ከግማሽ ሚልዮን በላይ አንዳይወጣ ስለተደነገገ ነጋዴው የሀብት መጠኑን በተለያየ ቦታ መደበቅ ብቻ ሳይሆን የገቢ ምንጩም ''አየር ባየር'' በሚል የንግድ ስም ተቀየረ።ቢሮ የሌላቸው፣ግብር የማይከፍሉ ነገር ግን ቦርሳቸውን ይዘው የሚንቀሳቀሱ ሀብታሞች ተከሰቱ።ይህ ጉዳይ በከፋ አና በአሰቃቂ መልኩ የተከሰተው ግን በህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን ነው።

በወታደራዊው ዘመን ባለስልጣናቱ በሙስና የሚታሙ አልነበሩም።በህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን ግን በነጠላ ጥልፍልፍ ጫማ አና መልኩን በቀየረ ጃኬት አዲስ አበባ የገቡት የህወሓት የወቅቱ ''ታጋዮች'' በጥቂት ጊዜ ውስጥ የቅንጡ መኪና ባለቤት ብቻ ሳይሆን የግዙፍ ህንፃዎች ባለቤት ተባሉ።አነኝሁ ዘራፍ ባለስልጣናት፣ካድሬ አና ታጣቂዎች ደግሞ ነጋዴ ተብለው የኢትዮጵያን ገበያ ከታች ችርቻሮ አስቀ ግዙፍ አስመጪና ላኪ ኩባንያዎች ባለቤትነት ያዙት።የዝርፍያቸው መጠን ለማሳየት በዓባይ ግድብ ላይ ሜቲክ የተባለው የህወሓት ሰዎች የሚያሽከረክሩት ድርጅት የሰራው ጥፋት አና የኢትዮጵያን መርከቦች መሸጥ የደረሰ ቡድን አስቀ መፍጠር ተደረሰ።
ከስር የመጣው ትውልድ ነጋዴ ማለት የሚያውቀው ዘራፊ፣ስነምግባር አና ሞራል የተለየው ብቻ ሳይሆን በወገኑ ደም ነግዶ ማትረፍ አንዴ ''ጎበዝ የንግድ ሰው'' የሚያስቆጥር አስተሳሰብ የሰረፀበት ሕብረተሰብ ቆየው።ስለሆነም በኢትዮጵያ ነጋዴ ማለት አና በሌላ ሀገር ነጋዴ ማለት ያሉት ትርጉሞች በአስተሳሰብም ሆነ በተግባር የሰማይና ምድር ያህል ተለያይተው ተገኙ።ይህ የኢትዮጵያ ነጋዴ የተገለፀበት አገላለፅ ለሁሉም ነጋዴ ይሰራል ማለት አይደለም።ሆኖም ግን መሰረተ ሃሳቡ መናጋቱ አና መልካም ነጋዴዎች ስማቸው በተበላሹት ስም መለወሱ የሚያስማማ ጉዳይ ነው።

ወደ ዋና ፍሬ ነገሩ አንመለስ።የዋጋ ንረት ጉዳይ በኢትዮጵያ ከፈጠሩት በርካታ ምክንያቶች ውስጥ (ምጣኔሃብታዊ ትንታኔው የኢትዮጵያን ነባራዊ የገበያ ባሕሪ ባገናዘበ መልኩ መታየቱ አንዳለ ሆኖ) አንዱ አና ዋናው ምክንያት በወሳኝ አና ስልታዊ የሀገር ምርቶች በተለይ በሁለቱ መሰረታዊ የሰው ልጅ ፍላጎቶች ላይ ማለትም የምግብ አና የመጠለያ ዋጋ  በተመለከተ የነጋደው የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) በመንግስት በጥብቅ መልኩ አለመወሰኑ ነው።ይህ የመንግስት የፖሊሲ ድክመት ነው።

ይህ የትርፍ ህዳግ የመወሰን ሂደት የግል ዘርፉን የማደግ ጣርያ የመገደብ ጉዳይ አይደለም።ይልቁንም በአዚህ ሂደት የበለጠ ትርፋማነት አና ብዙ ነጋዴዎች ወደ ገበያው በተረጋጋ አና በአስተማማኝ መልኩ አንድገቡ ያደርጋል።ይህንን በሰፊው ለመዘርዘር ይህ ፅሁፍ ዓላማው አይደለም።ነገር ግን መንግስት ኢትዮጵያን ካለባት ቀውስ ለማዳን በምግብ አና ከመጠለያ ጋር የተያያዙ ምርቶችን ብቻ ሳይሆን ቀዳሚ ግብአቶች ላይ የትርፍ ጣርያ ልክ ማስቀመጥ አለበት።ይህ የሚሆንበት ዋናው ምክንያት አሁን ያለው የዋጋ ንረት ሳብያ ነጋዴዎች አያገኙ ያለው ትርፍ ፈፅሞ ምክንያታዊ ያልሆነ፣ካወጡት ወጪ ከአንድሺህ ፐርሰንት በላይ ትርፍ የምያፍሱበት ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ አሁን የሚታየው የምግብና የቤት መግዣ ዋጋ በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በአውሮፓ አና አሜሪካ ካለው የበለጠ አና የተጋነነ ነው።ለአዚህም የብር ዋጋቸውን ወደ ዶላር አና ኢሮ ቀይሮ መመልከት ይቻላል።

አሁን በኢትዮጵያ ያለው የዋጋ ንረት ከአፍሪካ ከተሞች ብቻ ሳይሆን በዓለም ላይ የኑሮ ውድነት የሚታወቁት ከተሞች ከጄኔቭ ስዊዘርላንድ፣ኦስሎ ኖርዌይ እና ቶክዮ ጋር ለመድረስ እየተንደረደረ ነው።በአፍሪካ ከተሞች ላይ ያለውን የምግብ እና የቤት ዋጋ ዝርዝር ላይ ስንመለከት አዲስ አበባ ብዙዎቹን በዋጋ ንረት እየጣለች መሄድዋ አሳሳቢ ነው።ይህ በያዝነው የፈረንጆች ዓመት 2022 ዓም የዓለም የከተሞች የኑሮ ውድነትን የሚያወጣው ''ኑምቦ'' ድረገጽ አዲስ አበባ በሬስቱራንት ዋጋ ያለውን ንጽጽር መመልከት በቂ ነው።

የኢትዮጵያ የዋጋ ንረት ፈጽሞ ምክንያታዊ አይደለም።በእዚህ ጽሑፍ ላይ በዋናነት መንግስት በተለየ መልክ የምግብ እና የቤት ዋጋ የትርፍ ህዳግ መወሰን ወሳኝ መሆኑን ለማወቅ እነኝህን ጥያቄዎች እናንሳ:
  • አያት አካባቢ አንድ ቪላ ቤት አዲስ አበባ ውስጥ (ይህ ጽሑፍ ከመዘጋጀቱ በፊት በአንድ ማስታወቂያ ላይ እንደተመለከትኩት) 38 ሚልዮን ብር የሚል ዋጋ ያሳያል።ይህንን ወደ ዶላር እንቀይረው እና በሩብ ሚልዮን ብር እና በግማሽ ሚልዮን ብር ናይሮቢ እና ካምፓላ እንዲሁም አውሮፓ እንበል ውድ የሆኑ ከተሞች እንደ ኦስሎ፣ኖርዌይ ቅንጡ ቤት የሚገዛበት ነው። እዚህ ላይ ጥያቄው አውሮፓ እና አሜሪካ ከአዲስ አበባ በታች በሆነ ዋጋ ቤት የተገኘው የተሰራበትን ወጪ ሸፍኖ የሻጩን ትርፍ ሁሉ መልሶ መሆኑ የታወቀ ሆኖ ሳለ በኢትዮጵያ ከወጣበት ወጪ በላይ ትርፉ ምን ያህል ተቆጣጣሪ የሌለው እና ይሉኝታ ቢስ እንደሆነ ማየት አይቻልም ወይ?
  • ኦስሎ ኖርዌይ በዓለም ካሉ ከተሞች የምግብ ዋጋዋ ከፍ ካለባቸው ከተሞች ውስጥ ነች። ነገር ግን በኦስሎ ሱፐርማርኬት ውስጥ አንድ ሙል ዶሮ ከሙሉ ብልት ጋር ታጥቦ እና ታሽጎ የሚሸጥበት ዋጋ አዲስ አበባ አንድ ዶሮ ከነነፍሱ ከሚሸጥበት ዋጋ ይቀንሳል። ይህንን ዋጋ ወደ ጀርመን፣ጣልያን እና ሌሎች የአውሮፓ ሃገሮች ስንወስደው በእጅጉ የቀነሰ ነው። እዚህ ላይ ጥያቄው በአውሮፓ ሱፐር ማርኬት የሚሸጠው የዶሮ ስጋ ከማምረት ሂደቱ እስከ ማጠብ እና ማቆያ ብሎም ማጓጓዣ ዋጋ ሁሉ ተጨምሮ እና ትርፉን ጨምሮ የሚሸጥ ዋጋ ሆኖ ነው ከአዲስ አበባ የቀነሰው። አዲስ አበባ ላይ ገና ያልታረደ፣ሽንኩርት ያልወጣለት፣ቅቤ ያልተገዛለት ዶሮ ዋጋ ከአውሮፓ ዋጋ እንዴት በለጠ?
ከላይ የተጠቀሱት ሁለት ማሳያዎች በተለይ የምግብ ዋጋ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተለይ ባለፉት አስር ዓመታት በባሰ መልኩ ደግሞ ባለፉት አራት እና አምስት ዓመታት ውስጥ የጨመረበት ምክንያት ምንድን ነው? የአዲስ አበባ የቤት ዋጋ እና የምግብ ዋጋ ንረት ከአውሮፓ እንዴት ይበልጣል? ብለን ስንጠይቅ አንዳንዶቻችን አውሮፓ በብዛት የማምረት አቅም ስላለ፣ቴክኖሎጂው እና አሰራሩ ወጪውን ቀንሶት ነው ብሎ የሚያስብ ይኖራል። ሆኖም ግን ቴክኖሎጂው ምን ያህል ቢያድግ፣ምርት ምን ያህል ቢጨምር የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) ገደቡን መንግስት ይቆጣጠራል እንጂ ገበያ አገኘሁ ብሎ ነጋዴ እንደፈለገ አይጨምርም።

የኢትዮጵያ የዋጋ ንረት በልጓም የሚለጉመው መንግስት ያጣ ነው እንጂ የአቅርቦት እና የፍላጎት መጣጣም ቢመጣም አይገታውም።ምክንያቱም ነጻ ገበያ ማለት መረን የለቀቅ ነጋዴ እንደፈለገ ህዝቡን ሲበዘብዘው መመልከት ማለት ሆኗል።ቀድሞ ነገር ነጻ ገበያ የሚለውን ጽንሰ ሃሳብ በኢትዮጵያ ሙሉ በሙሉ ለመተግበር ያደጉ ሃገሮች ነጻ ገበያ እንዲኖር የሚያስፈልጉ ቅድመ ሁኔታዎች ስንቱ ተሟልተዋል? ከ80 በመቶ በላይ በግብርና የሚተዳደር ህዝብ ያላት ሃገር ገበያውን ለጥቂት ''እፍረት የለሽ '' ነጋዴዎች በነጻ ገበያ ሥም እንደፈለጉ እንዲሄዱ ተፈቅዶ ሃገር ሃገር አይሆንም።

ለማጠቃለል፣የዋጋ ንረት ሲነሳ የምርት እጥረት ጉዳይ ብቻ ወይንም የገንዘቡ የመግዛት አቅም መውደቅ የሚሉ አገላለጾች ብቻ የችግሩ መግለጫ ሊሆን አይችልም።ምክንያቱም ምርቱ እየጨመረ ቢሄድም ነገ ዋጋ ከነበረበት አይወርድም።ምክንያቱም ነጋዴው የትርፍ ህዳጉን የሚመጥን ሕግ የለበትም።ሰው በባሕሪው ደግሞ በቃኝ አይልም። አንድ ከረጅም ጊዜ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ የሔደ ወዳጄ ምልከታውን ሲነግረኝ። በአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን በደንብ በሚያውቃት የክልልል ከተማው ውስጥ ያሉትን ገበያዎች ተመልክቶ ያለኝ ''እኔ እስከ ገባኝ ደረስ ሁሉም ቦታ ገበያው በሚሸጥ የምግብ እና ፍራፍሬ የተሞላ ነው።እንዲያውም ቀድሞ ከማውቀው በላይ የተትረፈረፈ ነገር ገበያው ላይ ተሰጥቶ ይታያል።ዋጋው ግን ሰማይ ነው።'' ነበር ያለኝ።በነጻ ገበያ አመክንዮ የፍላጎትል እና የአቅርቦት መቀራረብ ዋጋን ይወስነዋል የሚለው ኢትዮጵያ ላይ እንዳይሰራ ያደረገው የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) ልጓም የሚያስገባ የመንግስት ጥብቅ ፖሊሲ ያስፈልጋል። ለነዳጅ ዋጋ ሲወጣ ነዳጁ የመጣበት ዋጋ ሲደመር ነዳጁ ከወደብ የሚጓጓዝበት ከተማ እርቀትን እየለካ እንደእርቀቱ ዋጋው ይለያያል።በእዚሁ መሰረት የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊትማርጅን) በተለይ በተለይ ለምግብ እና ለቤት ዋጋዎች መንግስት በፍጥነት ማውጣት አለበት።

የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) ለምግብ ሸቀጦች እና ለቤት ለመወሰን መንግስት ከንግድ ምክርቤቶች ጋር ቁጭ ብሎ በዝርዝር ምክንያታዊ በሆነ ዋጋ ላይ ይስማም።የዋጋ መስማምያ ነጥቡ የነጋዴውን ምክንያታዊ ትርፍ የማይነካ ነገር ግን በምስኪኑ ህዝብ ላይ ገደብ የለሽ ትርፍ የማይካበትበት የመስማምያ ነጥብ ላይ ይድረስ።እዚህ ላይ መጠንቀቅ የሚገባው የምርቱ ዋጋ የትርፍ ህዳግ ላይ ከመሔድ በፊት ዋና ግብአቱ ዋጋ ላይ ተመን ያስፈልጋል።ለምሣሌ፣ የአንድ እንጀራ ዋጋ ከመተመን በፊት ዋናው ግብአት አንድ ኪሎ ጤፍ ከመመረት እስከ ገበያ ያለው መስመር የሚኖረው ወጪ ተደምሮ የነጋዴው ምክንያታዊ ትርፍ ተጨምሮ ስንት፣የት ከተማ ላይ መሆን እንዳለበት ከንግድ ምክርቤቶች ጋር በጋራ መወሰን ያስፈልጋል። አንድ ቤት ለመስራት የፈጀው ወጪ አንድ ሚልዮን ብር ሆኖ ሳለ የሚሸጥበት ዋጋ 15 ሚልዮን ማለት የትርፍ ህዳጉ ስንት ቢሆን ነው? ከወጪው በላይ 1500 ፐርሰን ትርፍ ምን ማለት ነው? የት ሃገር ነው ይህ የሚፈቀደው? የአንድ ቤት ወጪ ላይ ሻጩ ማግኘት ያለበት ትርፍ ስንት መሆን አለበት? ዝርዝር ወጪው ሲደመር ምክንያታዊ ትርፉ ይሰላ! ምርት ምንም ያህል ቢጨምር ዋጋ አይቀንስም።ነጋዴው የትርፍ ህዳጉ ካልተገደበለት ዋጋ እየጨመረ ይኖራል።በድሃው ህዝብ ላይ በዶላር እና ኢሮ ሲመነዘር እንኳን ትልቅ ገቢ ካለው የአውሮፓ እና አሜሪካ ህዝብ በላይ ዋጋ ተጭኖበት የሚሰቃይ ኢትዮጵያዊ ወሳኝ ውሳኔ ይፈልጋል።

እዚህ ላይ አንድ ሊነሳ የሚችል ጥያቄ ለመመልስ ልሞክር እና ጽሑፉን ላጠቃል።ጥያቄው የትርፍ ህዳግ (ፕሮፊት ማርጅን) በነጋዴው ላይ ሲወሰን ነጋዴው ብዙ እንዳያመርት፣ገበሬው ብዙ እንዳይሰራ አያደርግም ወይ? የሚል ነው። መልሱ አያደርግም ይልቁንም ምርት ያሳድጋል። ምክንያቱም የትርፍ ህዳግ ወሰን መኖር ለነጋዴውም ሆነ ለገበሬው ብዙ ትርፍ የሚመጣው ከብዛት ከመሸጥ እንደሆነ ግልጽ ስለሚሆን ምርት ያድጋል እንጂ አይቀንስም።የትርፍ ህዳጉ መወሰን የገበያውን ፍላጎት ይጨምራል።ዋጋ ሲቀንስ ፍላጎት እንደሚጨምር የምጣኔ ሃብት መሰረታዊ አመክንዮ ነው።ስለሆነም ፍላጎት ይጨምራል።አቅርቦትም እንደ ድሮ ትንሽ በብዙ ዋጋ ሸጦ መቀመጥ በነጋዴው ዘንድ ስለሚቀር።ብዙ በማቅረብ ብቻ የትርፍ ህዳግን ማሳደግ ዋና አማራጭ ይሆናል።ስለሆነም በገበያው ውድድር ላይ በብዛት ማምረት የቻለ ብቻ የሚያተርፍበት ገበያ ይፈጠራል።ይህ ብቻ አይደለም።የትርፍ ህዳጉ የታወቀ እና አስተማማኝ መሆን ብዙዎች ወደ ምርት ገበያው እንዲገቡ ያበረታታል።በመጨረሻም ገበያ ያረጋጋል።የትርፍ ህዳግ መረን ይለጎም።ከአንገብጋቢዎቹ ምግብ እና ቤት ይጀመር።ወደ ልብስ ይቀጥል።ቢያንስ ከአውሮፓና አሜሪካ እንዲሁም ከአፍሪካ የባሰ የኑሮ ውድነት ውስጥ ገብተናል።ዝም ከተባለ ደግሞ ሃገር ያፈርሳል።
 
=================
ጌታቸው በቀለ

Thursday, November 17, 2022

ሙስና የወጋቸው - አምስት አጫጭር እውነተኛ ታሪኮች።



በእዚህ ጽሑፍ ስር 
  • ሲቪል አቬሽን፣
  • ባለ 10ቱ ትዕዛዛት፣ባለ 30 መክሊት ወይንስ ባለ 60 መክሊት
  • ለአሜሪካ ኤምባሲ የተጻፈው ደብዳቤ ጉድ
  • የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሰራተኛ መስራት አቃተኝ
  • ቶሎ ወደ ናይሮቢ ሒዱ
==============
ጉዳያችን/Gudayachn
==============
ማሳስቢያ ፡ በእዚህ ጽሑፍ ላይ የሚጠቀሱት ድርጅቶች ስም አሁን ያሉበትን ወቅታዊ ሁኔታ ላይገልጽ ይችላል።ታሪኮቹ ግን እውነተኛ ናቸው።

ሙስና የሚለውን ቃል ብዙ ጊዜ ከመስማት የተነሳ ብዙዎች አቅልለው ይመለከቱታል።የአስከፊነቱን ክርፋት የምንረዳው ግን የወጋቸው ሰዎች ምን ያህል ሃገር ይጠቅሙ እንደነበር ስናስብ ነው።በእዚህ ጽሑፍ ላይ የቀረቡት ታሪኮች በሙሉ እውነተኛ እና የእዚህ ጽሑፍ አቅራቢ ከባለታሪኮቹ በቀጥታ ያገኘው እና በኢትዮጵያ በተለያዩ ዓመታት ውስጥ በሙሰኞች የተወጉ አሳዛኝ ታሪኮች ናቸው።ታሪኮቹ የሙስናው ስብጥር እና አካሄድ በትንሹ ያሳያል።ይህንን በሰፊው እና በብዛት ሲፈጸም በሃገር ደረጃ ያለው ግዙፍ ውድቀት ለመመንዘር ይረዳል።

ሲቪል አቬሽን 

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሥራ ከጀመርኩ ገና ሁለት ዓመት ነበር።በኢትዮጵያ አየርመንገድ ግቢ ውስጥ ብቸኛው የባንክ አገልግሎት ሰጪ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነበር።ባንኩን ከሚገለገሉት ውስጥ የኢትዮጵያ አየርመንገድ፣ሲቪል አቬሽን እና የኢትዮጵያ ንግድ ቱሪስት ንግድ ሥራ ድርጅት የሚባሉ ነበሩ። አንድ ቀን ጧት የቁጠባ ሒሳብ ክፍል ላይ አገልግሎት እየሰጠሁ በጣም ንቁ የሆነች እና ከካናዳ ወደ ሃገሯ ገብታ ለመስራት ልጆቿን ይዛ ጠቅልላ መጥታ በሲቪል አቬሽን ድርጅት ውስጥ በተማረችው የኢንጅነሪንግ ሙያ ታገለግላለች።ወደ ባንኩ ስትመጣ ለሃገር ስለመስራት፣ስለየውጭ ሃገር ኑሮ አንዳንድ ነገሮች ጣል አድርጋ ትሄዳለች። ይህ ብቻ አይደለም ወጣቷ ወ/ሮ ለሲቪል አቬሽን ስፖርት ክለብ የቅርጫት ኳስ ቡድን እንዲጠናከር የራሷን ድርሻ መወጣቷን አሁንም ባንኩ ጋር በምትመጣበት ጊዜ ካጫወተችኝ የማስታውሰው ነው።

የቅዳሜ ጧት ለቅሶ

ወጣቷ ወ/ሮ አንድ ቅዳሜ ጧት ወደ የቁጠባ ሒሳብ ክፍል መጣች። ካውንተሩ በደንበኞች ተጣቧል።ወጣቷ ቱታ ለብሳለች።ያን ቀን ፊቷ ከእዚህ በፊት እንደነበረው አይደለም። እንቅልፍ የተኛች አትመስልም።ሌላ ጊዜ ፈገግ ብላ ስቃ እያወራች ነበር በገንዘብ ማውጫ 'ቫውቸር ' ላይ የምትጽፈው። ያን ቀን ግን ቀና ብላ ከጎኗ ያሉትን የሲቪል አቬሽን ባለስልጣናት ገልመጥ አድርጋ አይታ የገንዘብ ማውጫው ላይ ጽፋ ''እቸኩላለሁ! ቶሎ አሳልፍልኝ '' ብላ ከባንክ ደብተሯ ጋር ሰጠችኝ።የጻፈችውን የገንዘብ መጠን ስመለከት ሁሉንም ገንዘብ ለማውጣት የሚያዝ ነው። የወረፋ መጠበቅያ ቶክን እየሰጠሁ ''ሰላም ነው አይደል?'' አልኳት።''ቆይ ገንዘቡን ካወጣሁ በኋላ መጣሁ'' ብላኝ ወደ የገንዘብ ካውንተሩ ሄደች።

ከደቂቃዎች በኋላ ተመልሳ መጣች።ካውንተሩ ላይ የነበሩ ደንበኞች ሁሉ ተስተናግደው ሄደዋል። እንደመጣች ምንም ሳትናገር አይኖቿ ላይ እንባዋ ግጥም ብሏል። ወዲያው አንድ ዘመድ ሞቶባት እንደሆነ ወድያው ገመትኩ። ግምቴ ግን ልክ አልነበረም።

''ዛሬ ቻው ልልህ ነው የመጣሁት '' አለች። ቀጠለችና ''ቅድም ዝም ያልኩህ የሲቪል አቬሽን አለቆቼ እዚህ ስለነበሩ ማውራት ስላልፈለኩ ነው '' አለችና ''መሔዴ ነው።አላሰራ አሉኝ። እኔ ሕልሜም ምኞቴም ሃገሬ መስራት ነበር።ነገር ግን አላሰሩኝም።እንደነሱ እንድሰርቅ ይፈልጋሉ። እኔ ደግሞ ከድሃ ሃገሬ ላይ የመስረቅ ሞራል የለኝም።ይህንን ከማደርግ እዛው የማልወደው ካናዳ ልጆቼን ይዤ ለመመለስ ወስኛለሁ።'' ብላ ጧ! ብላ ማልቀስ ጀመረች።ከእርቀት አካውንታቱ እና ምክትል ሥራ አስኪያጁ ይመለከታሉ።ወዲያው ተከታትለው መጡ እና ''አላለፈልሽም እንዴ ያንቺ፣ምንድነው ችግር አለ?'' አለ ምክትል ሥራ አስኪያጁ አቶ ጉታ። ችግር እንደሌለ ገንዘቧን እንደወሰደች ሳግ በተናነቀው ቃላት እራሷ ነገረቻቸው። አካውንታቱ እና ሥራ አስኪያጁ ከሄዱ በኋላ ፈተና ያለ ነው ታግለሽ እንዴት አትቋቋሚም? ወዘተ እያልኩ ቀባጠርኩ። እርሷ ግን ሥራውን ትታ ዩንቨርስቲ ሥራ አግኝታ እንደነበር ነገር ግን የትም ብትሔድ እንደማይለቋት፣ የተከራከረቻቸው ጉዳዮች ከባድ እንደሆኑ እና ለራሷም ሆነ ለቤተሰቧ ከሃገር መውጣት ብቻ አማራጭ መሆኑን በሃዘን አስረዳችኝ። ከፊቷ ላይ የሚነበበው ከገነት ወደ ሲኦል የሚገፉት ሰው የሚሰማው ዓይነት ስሜት ነበር የሚታይባት። ባለፉት ጊዜያት ሁሉ ስትነግረኝ የነበረው በሃገር የመስራት ሞራል፣የሃገር ፍቅሯን ሁሉ እንደገደሉባት ገባኝ። 

በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ውስጥ እጅግ ብዙ ብሩህ አዕምሮ ያላቸው ወጣት ኢትዮጵያውያን በሙስና መረብ በተተበተበ መዋቅር እንዲሰቃዩ እና በመጨረሻ አቅመ ቢስ ሆነው ሥራቸውን እንዲለቁ ወይንም የባርነት መንፈስ ውስጥ ሆነው እንዲሰሩ እንደተደረጉ ቤት ይቁጠረው።የሲቪል አቪየሽኗ ወጣት ወይዘሮ ግን ሁሌ የደረሰባትን አስታውሳለሁ።በጊዜው የሲቪል አቬሽን ባለስልጣናትን ስመለከት በጅምላ ጥሩ ስሜት አይሰማኝም ነበር።

ባለ 10ቱ ትዕዛዛት፣ባለ 30 መክሊት ወይንስ ባለ 60 መክሊት

አውሮፓ ውስጥ የሚኖር በአገልግሎቱም የማውቀው ካሕን ነበር።የአውሮፓ ኑሮውን ትቶ ወደ ሃገር ቤት ገባ።በቤተክርስቲያን ትምህርቱ ዕውቀቱ ያላቸው እንደነገሩኝ የትኛውም ቦታ ሊያገለግል የሚያስችል ትምሕርት አለው። ሃገር ቤት በገባ ከወራት በኋላ ደወልኩለት። የትኛውም አጥብያ ቤተክርስቲያን እያገለገለ እንደሆነ ጠየኩት። 
''አዬ ባለ 30 ወይንስ ባለ 60 መክሊት ነህ?'' ብለው ጠየቁኝ አለኝ።ይህ ምን ማለት ነው? በማለት ጠየኩት። ነገሩ እንዲህ ነው። አዲስ አበባ ሃገረ ስብከት በኩል አጥብያ አብያተ ክርስቲያናት ለመቀጠር ጉቦ የሚቀበሉ የሃገረስብከቱ ሰራተኞች የሚቀበሉትን ጉቦ መጠን ለመግለጽ የሚጠቀሙት አስር ሺ አምጣ ለማለት ባለ 10ቱ ትዕዛዛት፣ 30 ሺህ አምጣ ለማለት ባለ 30 መክሊት እና 60 ሺህ አምጣ ለማለት ባለ 60 መክሊት የሚል ቋንቋ ይጠቀማሉ።

በአሁኑ ጊዜ በእየአጥብያ አብያተ ክርስቲያናት ሊቃውንቱ የሚሰጡት ጉቦ ስለሌላቸው በመጠለያ ተቀምጠው ጸሎታቸውን አድርሰው ሲመለሱ።ምንም ትምህርት የለላቸው ግን ከየትም ቃርመው ያገኙትን ጉቦ እየከፈሉ ይቀጠራሉ።ጉቦ የመስጠትም ሆነ የመቀበል ኃጢአትነት የተረዱ ግን እየተከዙ ዘመን ይገፋሉ። ይህ እውነተኛ ታሪክ ነው።

ለአሜሪካ ኤምባሲ የተጻፈው ደብዳቤ ጉድ 

የሙስና ልክ ዐይን ያወጣ አካሄያዱ እፍረት የለሽ ነው። ይህ ደግሞ በእምነት ተቋማት ሲሆን የበለጠ አስጸያፊ ነው።ጊዜው በፓትርያሪክ አቡነ ጳውሎስ ጊዜ ነው።የአሜሪካ ኤምባሲ አንዲት ወጣት ለቪዛ ኢንተርቪው ትቀርባለች። ወጣቷ ለቃለ መጠይቁ ለመቅረብ ከያዘችው ሰነድ ውስጥ የድጋፍ ደብዳቤ አብሮ ተያይዟል።ቃለ መጠይቅ አድራጊው ኦፊሰር ሰነዶቿን በሙሉ እያየ ምልክት ካደረገ በኋላ የድጋፍ ደብዳቤዋ ጋር ሲደርስ ግራ ገባው። የድጋፍ ደብዳቤው የተጻፈው ከቤተክህነት ነው። የወጣቷ ስም የሙስሊም ስም ነው። ኦፊሰሩ ቀና ብሎ ወጣቷን ተመለከተ እና ሃይማኖሽ ሙስሊም ነሽ አይደል? ብሎ ጠየቀ። አዎንታዊ መልስ አገኘ።ታድያ እንዴት ቤተክህነት ለምን ዓይነት ሥራ የድጋፍ ደብዳቤ ጻፈልሽ? ማለት በእምነት አትገናኙም።ተሳሳትኩ? ብሎ ጠየቀ። ወጣቷ ሌላ መቀባጠር ውስጥ ገባች።ደብዳቤው ሲጣራ በጉቦ ከቤተክህነት አንድ ማኅተም ያዥ የጻፈው ነው።

የእዚህ ዓይነት በርካታ ጉዶች በየቦታው አሉ። በውጭ ሃገር ሃይማኖታዊ በዓል ሳይኖራቸው።በዓል እንደሚያደርጉ አድርገው መዘምራን ናቸው፣ሰባክያን ናቸው እያሉ ዘመዶቻቸውን ወደ ውጪ የሚያወጡ የሃይማኖት ተቋማት ሙስና ቤት ይቁጠረው።ለማንኛውም የቤተክህነት ጉዳይ ብዙ መታየት ያለበት ጉዳይ አለ።

የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሰራተኛ መስራት አቃተኝ

ወጣቱ የህክምና ዶክተር ነው።ለአጭር ጊዜ ስልጠና ወደ አውሮፓ መጣ።ከስልጠናው ጊዜ ውጭ ከተማ ላሳየው ሻይ ቡና እንላለን።አንድ ቀን በሚሰራበት የአንድ ክልል የጤና ሚኒስቴር ስር ያለ ቢሮ ያለውን የሙስና ዓይነት ከራሱ መንፈሳዊ ህይወት ጋር እየፈተነው እንደሆነ ነገረኝ። መጀመርያ ጉዳዩን ሳልረዳ። ሙስና ሙስና ነው አልተባበርም፣አልፈልግም ብሎ መሞገት ነው ምን ምክር ያስፈልገዋል አልኩት። ቡናውን ፉት ብሎ ጉዳዩን ማስረዳ ጀመረ። ነገሩ እንዲህ ነው፣

ወጣቱ በሚሰራበት የጤና ቢሮ ውስጥ አለቃው በርካታ ስልጠናዎች እንዲዘጋጅ ያደርጋል። ስልጠናውን የሚሰጣቸው ሰራተኞች ከሰለጠኑበት በላይ አበል ይከፈላቸዋል።በመጀመርያ ስልጠናው አስፈላጊ ሆነም አልሆነ ስልጠና ውሰዱ ይባላሉ። ሰራተኞቹ ስልጠና አንወስድም ማለት አይችሉም።የሥራው አካል ነውና።ሥልጠናው እንዲሰጥ የሚደረግበት ድርጅት ግን በአለቃው ዕውቅያ የሆነ እና የራሱ ኮሚሽን እንዳለው ይታወቃል። በእዚህ ሁኔታ ስልጠናው የሙስና ሥራ እንዳለበት እያወቀ ስልጠናውን አልፈልግም ማለት አለመቻል እና አበሉን መውሰድ ለእዚህ ወጣት ዶክተር ከእመንቱ ጋር እያወቀ እያጠፋ እንደሆነ ተሰምቶታል።


ቶሎ ወደ ናይሮቢ ሒዱ

የባሕር ማዶ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ነው። ድርጅቱ በኤችአይቪ ላይ የሚሰራ ነው። በአዲስ አበባ ቅንጡ በሆነ ህንፃ ላይ ቢሮውን ከፍቷል። በዶክትሬት ደረጃ ያሉ ከፍተኛ ባለሙያዎች ቀጥሯል። ከእነኝህ ባለሙያዎች ውስጥ አንዱ ባለሙያ ያጫወተኝ ነው። የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ ለጊዜው ሃገሩ ይቆይና የውጭ ሃገር ዜጋ ነች።የሚገርመው ከሃገሯ የሚላከውን በጀት አለአግባብ በጥቅም በምትተሳሰራቸው ድርጅቶች የሥራ ውል እንደሰጠች እያደረገች ባጀቱን ታጣጣዋለች።

''አንድ ቀን አለኝ'' ይህ ኢትዮጵያዊ ባለሙያ ''አለቃችን ድንገት ወደ ቢሮዬ መጣች እና በሁለት ቀን ውስጥ ሸራተን የኤች አይቪ ግንዛቤ መስጫ ስልጠና ከተለያዩ የመንግስት መስርያቤቶች ሰዎች ጠርተው ስልጠና ስጥ '' አለችኝ።''ቀጠለችና በሚቀጥለው ሳምንትም ሁላችሁም የክፍሉ አባላት ናይሮቢ የሦስት ቀን ስልጠና ትሄዳላችሁ '' አለችና ከፍሉ ወጣች። በኋላ ይህ ባለሙያ ከሥራ አስኪያጇ እንደተረዳው የዓመቱ የሒሳብ ሪፖርት መዝጊያ ስለሆነ ባጀቱን ለመጨረስ ብቻ በሸራተን እና የናይሮቢ ስልጠና ለማጥፋት ተፈልጎ ኖሯል።ሃገር ውስጥ በአግባቡ ሥራ ላይ እንዲውል የተላከው ገንዘብ እንዲህ በግርግር ስብሰባ ይባክናል።ይህ ባለሙያ አለቃውን በጉዳዩ ላይ ሞግቷል። ያገኘው መልስ። ገንዘቡን የምታመጣው የኔ ሃገር ያንተ እንዲህ መሆን አልገባኝም የሚል መልስ ቃል በቃል ተሰጥቶት ነበር።

ባጠቃላይ ከላይ ለማቅረብ እንደተሞከረው በኢትዮጵያ ያለው ሙስና የማይዳስሰው ተቋም እና ቦታ የለም። ሙስናው በገንዘብ ኦዲት ብቻ ሳይሆን ሥራው በተሰራበት የሥራ ሂደትንም በመመርመር የሚገኝ ነው። ከስራው በጀት ላይ ስንት ተወሰደ ሳይሆን የሥራው ሂደት በመመርያው መሰረት ነው ወይንስ ከመመርያ ውጭ ነው? የሚለው እና የሂደቱ ጤናማነት ሁሉ መመርመር ይገባዋል።ኢትዮጵያ ሙስናን ለመዋጋት በጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ ቢሮ ስር የሚታዘዝ አዲስ ኮሚቴ ተመስርቷል።ኮሚቴው ሥራው እንዲሳካ እና ኢትዮጵያ ሃብቷን እንድታድን ሙስናን የምናይበት መንገድ እና የሚገባበት ጓዳ ጎድጓዳ ሁሉ መፈተሽ የሕዝብም ሃላፊነት ነው።ይቅናሽ ኢትዮጵያ!
==========///////==========

Wednesday, November 16, 2022

አንዳንድ የህወሓት አመራሮች መሳርያ መሸከም በራሱ ለውጥ እንደማያመጣ ቆይቶም የገባቸው ይመስላል።አሳማኝ ምክንያቶቹ ሦስት ናቸው። አሁንም በተለይ የትግራይ ህዝብ በስሙ ከሚንቀሳቀሱ በንቃት ሊጠብቀው የሚገባው አደጋ።


የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የትግራይ ህዝብን በአጨዳ እና እህል መሰብሰብ ሲያግዝ
ህዳር፣2015 ዓም

  • ከጽሑፉ ስር በደቡብ አፍሪካ በኢትዮጵያ ፌድራል መንግስት እና በህወሃት መሃል የተደረገው ስምምነት የተፈረመው ሙሉ ሰነድ ያገኛሉ።
(ጉዳያችን ምጥን)

የፕሪቶርያው እና የናይሮቢው በኢትዮጵያ ፌድራል መንግስት እና ህወሃት መሃከል የተደረጉት ስምምነቶች ኢትዮጵያውያንን አስደስቷል።በትግራይ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም ዘንድ የዕለት ከዕለት ኑሮ ላይ ቀስ በቀስ ለውጥ እያመጣ ነው። የምግብ ዋጋ አንጻራዊ በሆነ መልኩ መቀነስ አሳይቷል፣ ገበያዎች ከጸጥታ ስጋት ተላቀው መከላከያ በሚያደርገው ጥበቃ ግብይቶች ተጀምረዋል፣የምግብና የመድኃኒት አቅርቦት ተጀምሯል።እርዳታው መቀሌ ድረስ መጓጓዝ መጀመሩን የእራሱ የህወሃት አመራሮችም ሳይክዱ እያረጋገጡ ነው። 

ህወሓት መሳርያ መሸከም በራሱ ለውጥ እንደማያመጣ ቆይቶም የገባው ይመስላል።

ህወሃት በመጀመርያ የነበረው ህልም ኢትዮጵያን አሸንፋለሁ የሚል ቅዠት ላይ ነበር።ይህንን ቅዠቱን ደግሞ በትዕቢት እንዲታጀብ የኢትዮጵያ የቅርብ እና የሩቅ ጠላቶች አይዞህ ባይነት እራሱን ከሚገባው በላይ እንዲኮፍስ አድርጎት ነበር።ቆይቶ ግን ተከትሎ የመጣው አደጋ ለተወሰኑት የገባቸው ይመስላል።እዚህ ላይ ግን ሁሉም ግን ገብቷቸዋል ለማለት ጊዜው አሁን አይደለም። ቀድሞ የሚገባቸው፣ሲያጣጥሙ የሚገባቸው እና ፈጽሞ የማይገባቸው ዛሬም የሉም ማለት ግን አይደለም።

አሳማኝ ምክንያቶቹ ሦስት ናቸው

ህወሃት ወደ ትጥቅ መፍታት ያደረሱት ምክንያቶች ሦስት ናቸው።

1) ግልጽ የሆነው የመከላከያ እና የጥምር ጦሩ አብዛኛዎቹን የትግራይ ከተሞች እና ገጠር ነጻ በማውጣቱ እና በመጨረሻም ህወሃት ሙሉ ህልውናውን ሊያጣ ስለሆነ ነው።

2) ኤርትራን በአጋጣሚው ታጠፋኛለች የሚል ስጋት ነው።ከኤርትራ ጋር ያለውን ድንበር ደግሞ ህወሃት ሊጠብቅ እንደማይችል አውቋል።ይህ ድንበር ሊጠበቅ የሚችለው በመከላከያ እና በመከላከያ ብቻ ነው።የኤርትራ ከኢትዮጵያ ፌድራል መንግስት ጋር ያላት መልካም ግንኙነት ስላሰጋው የመከላከያን ልዕልና ከመቀበል ሌላ አማራጭ የለውም።

3) ሦስተኛው  መሳርያ ይዞ ህዝቡን ሁሉ ወደ ጦርነት መምራት  በእዚህ በ21ኛው ክ/ዘመን ቢያሸንፍም ባያሸንፍም  ምን ያህል ወደኋላ እንደሚያስቀር ደግሞ በዓይኑ አይቷል። በሺህ የሚቆጠሩ ተማሪዎች ከትምህርት ገብታ ተጓጉለዋል፣ገበሬው እርሻ ማረስ አልቻለም፣ነጋዴው ሱቁን ዘግቷል። ይህ ሁኔታ ህዝቡ በራሱ ህወሃት ላይ መጠቆም ጀምሯል ብቻ ሳይሆን መከላከያ ወደ ትግራይ ሲገባ በደስታ ከመቀበል አልፎ በሁሉ ነገር ተባባሪ መሆኑ አስደንግጦታል።

አሁንም በተለይ የትግራይ ህዝብ በስሙ ከሚንቀሳቀሱ በንቃት ሊጠብቀው የሚገባው አደጋ

ህወሃት ስለ ትጥቅ መፍታት ቢፈርምም አሁንም ግን በራሱ ውስጥም ሆነ በውጭ ያለ ትግራይን የመገንጠል ዓላማ የያዙ እንቅስቃሴዎች ለትግራይ ህዝብ ሌላ አደጋ አለበት።ይህንን መገንጠል የሚል ሃሳብ በራሱ በህወሃት ውስጥ የሚደግፉም የማይደግፉም አሉ።የሚደግፉት የመከላከያ በትግራይ መኖር በዋናነት ለተገንጣይ ሃሳብ አራጋቢዎች መድኃኒት እንደሆነ ስለሚያስቡ ይህንን ስምምነት ይደግፋሉ።በሌላ በኩል ደግሞ የተገንጣዩ አንጃ የጠነከረ ሲመስላቸው መገንጠል የማይደግፉት አካላት ከተገንጣዮቹ ጋር ለመመሳሰል የሪፈረንደም ጉዳይን በማውራት የተገንጣዩን አንጃ ግልምጫ ለማምለጥ ይሞክራሉ።በሌላ በኩል የመገንጠል እንቅስቃሴ በትግራይ እንዲኖር ከሚገፉት ውስጥ የውጭ ኃይሎች ዋና አቀጣጣዮች ናቸው።እነኝህ ኃይሎች ከመገንጠሉ በላይ የተራዘመ ጦርነት ኢትዮጵያ ላይ እንዲኖር ነው ዋና ግባቸው።በውጤቱም የተዳከመች ኢትዮጵያ ማየት ነው።

በመሆኑም የትግራይ ህዝብ ነቅቶ መጠበቅ ያለበት ትግራይን ለመገንጠል በህወሃት ውስጥ ባሉ እና በውጭ ከተደራጁት እንደ ባይቶና ያሉት አደረጃጀቶች የአጭር እና የረጅም ጊዜ ግብ ከባዕዳን ጋር እየቀረጹ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል።ለእዚህም ግብ መሳካት የዘር ማጥፋት በትግራይ ላይ ተፈጽሟል የሚለውን የሃሰት ትርክት በብዛት በማሰራጨት ነገ ገንጥለው ለባዕዳን ለማስረከብ የሚሞክረው አካል ስልት መሆኑም የትግራይ ህዝብ ሊያውቀው የሚገባ ነው።የትግራይ ህዝብ የተለያዩ አደረጃጀቶችን በመፍጠር ከተገንጣይ እና በመገንጠል ከባዕዳን መተዳደርያቸውን ለመቀበል ከሚቋምጡ በህወሃት ውስጥም ሆነ በውጭ ከተደራጁ ባንዳዎች እራሱን መጠበቅ አለበት። በእዚህ ጉዳይ ላይ የትግራይ ምሑራን ህዝቡን በማንቃት የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል።

የኢትዮጵያ ፌድራል መንግስት እና ህወሃት በደቡብ አፍሪካ፣ፕሪቶርያ የተስማሙበት የተፈረመ ሰነድ








=======================///==============


Friday, November 11, 2022

በማኅበራዊ ሚድያም ሆነ በጽሑፍ መልካም እና ሕዝብ አስተማሪ ሥራዎችን ይዘው ብቅ የሚሉ ሴቶችን ማበረታታት አልለመድንም።ቧልት ይዘው የሚመጡትን ግን አድናቂው ብዙ ነው። ጉዳያችን ዛሬ የዶ/ር ፍቅርተ፣ የማኅሌት እና የእንግዳወርቅን ስራዎች በምጥን ታስተዋውቃችኋለች።


================
ጉዳያችን እናስተዋውቃችሁ
================

1/ ዶ/ር ፍቅርተ አረጋ

ዶ/ር ፍቅርተ አረጋ ብልኋ ጦጢት በሚል ርዕስ የተረት መጽሓፍ ክፍል አንድ ይዛ ቀርባለች። መጽሓፏ በአሁን ጊዜ በአማዞን እየተሸጠ 

ይገኛል። 


የዶ/ር ፍቅርተ መጽሓፍ በእንግሊዝኛ፣በአማርኛ እና በኦሮምኛ ተዘጋጅቶ የቀረበ ሲሆን የትግርኛ ትርጉሙ በቅርቡ እንደሚደርስ ገልጻለች።አማዞን ላይ ለመክፈት ይህንን ሊን ይጫኑ። መጽሓፎቹን በሦስቱም ቋንቋዎች የሚያገኙበትሊንክ ከእዚህ በታች ያገኛሉ።

 ብልኋ ጦጢት (Kindle edition only) 

Totit the Baby Monkey & Her Wise Family

Qamalee Qarute (Afaan Oromo version) -  (Kindle edition only) 


2/ የጋዜጠኛ ማኅሌት ሊባኖስ ሚድያ

በዩቱብ ትውልዱ የጎደለበትን የማንበብ ባሕል እንዲያድግ የተለያዩ መጽሓፎችን እያስተዋወቀች የምትገኝ ወጣት ነች። ከመጽሓፎቹ ውስጥ አጓጊ ክፍሎቹን እየመዘዘች ትውልዱ እንዲያነብ እያበረታታች ነው። ብዙዎች እንዲህ ዓይነት የቁም ነገር ዩቱቦችን ሳይሆን የፌዝ እና ቧልት ሲሆን ብዙ ተከታይ እና ተመልካች አለው። ይህ በራሱ የስብራታችን ማሳያ ነው። የማኅሌት የመጽሃፍ ዳሰሳዎች ግን አስተማሪዎች ናቸው። 

የሊባኖስ ሚድያ ሊንክ ከእዚህ በታች ያገኛሉ።



3/ የእንግዳወርቅ Engida Vlogs ዩቱብ 

እንግዳወርቅ ከምትኖርበት ኬንያ ባላት ጊዜ ወገኖቿን ለማስተማር፣ያገኘችውን ለማካፈል ትተጋለች።ኬንያ ውስጥ ያሉ ልምዶች፣የህይወት ተሞክሮ፣የቤት አያያዝ፣የምግብ አዘገጃጀት ወዘተ ለወገኖቿ ለማካፈል ትተጋለች። አሁንም ግን የቧልት ዩቱበሮች ይሰማሉ እንጂ ቁምነገር የያዙትን የሚከታተለው ጥቂት ነው።

የእንግዳ ወርቅ ዩቱብ ሊንክ ከእዚህ በታች ያገኛሉ።


ባጠቃላይ ሴት ጸሓፊዎች፣የቁምነገር ዩቱብ አቅራቢዎች ብዙ የሉንም።ብዙ የቧልት ዩቱቦች እና ጽሑፎች ግን ሞልተዋል። ብዙው የሚከታተለው የቧልቱን ነው። የቁም ነገር ጸሓፊዎችን የሚከታተል ብዙም የለም። በመሆኑም ቁም ነገር ይዘው ብቅ የሚሉትን ማበረታታት አስፈላጊ ነው።ጉዳያችን ዛሬ ለጅማሮ ለመጠቆም ሞክራለች።ሌሎች ሚድያዎችም ሊቀጥሉበት የሚገባ ነው።
=================///፟=============

Thursday, November 10, 2022

የናይሮቢው ድርድር ካልተራዘመ ከአሁን በኋላ ህወሓት በዝርዝር የትጥቅ አፈታት ሂደት ላይ ለመስማማት 36 ሰዓታት ብቻ ይኖሩታል።

36

  • የድርድር ጊዜው ካልተራዘመ በቀጣዮቹ 36 ሰዓታት ውስጥ የትጥቅ መፍታት ዝርዝር ሂደቱ ላይ ስምምነት ይደረሳል ተብሎ ይጠበቃል። ስምምነት ባይደረሰም በትግራይ ሰላም የማምጣት ኃላፊነት የወደቀው መከላከያ ትከሻ ላይ ብቻ መሆኑን የትግራይ ህዝብ በተለይ ባለፈው አንድ ሳምንት ውስጥ የበለጠ ገብቶታል።
===========
ጉዳያችን ምጥን
===========

ጥቅምት 23/2015 ዓም በፊርማ የተጠናቀቀው በደቡብ አፍሪካ ዋና ከተማ ፕሪቶርያ ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ፌድራል መንግስት እና በህወሓት መሃከል የነበረው ንግግር (ድርድር) የኢትዮጵያ መከላከያ ከፍተኛው እርከን በፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የተመራ የመከላከያ መኮንኖች ከህወሃት መሪዎች ጋር በናይሮቢ እየቀጠለ ነው።

የናይሮቢው ንግግር እንደደቡብ አፍሪካው በዝግ እየተደረገ ሲሆን ትናንት ረቡዕ ይጠናቀቃል ተብሎ ባለመጠናቀቁ እስከ ነገ ዓርብ እንደቀጠለ ከስፍራው መረጃ አገኘን ያሉ የምዕራብ ዜና አውታሮች የገለጹ ሲሆን አሁን ንግገር እየተደረገ ያለው ህወሃት ትጥቅ የሚፈታበት ዝርዝር አካሄድ ላይ እና ለትግራይ የዕለት ደራሽ ምግብ፣ኤሌክትሪክ እና ኢንተርኔት የሚለቀቅበት ጉዳይ ላይ ነው።ይህንኑ አስመልክቶ ዋሽንግተን ፖስት ዛሬ በኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ከቀትር በኋላ በለቀቀው ዘገባ የኢትዮጵያ ፌድራል መንግስት ወክለው በድርድሩ ላይ የተገኙት አቶ ሬድዋን ሁሴን ሰብዓዊ ዕርዳታው በእዚህ ሳምንት መጨረሻ ወይንም በመጪው ሳምንት አጋማሽ ላይ ትግራይ እንደሚደርስ መናገራቸውን ዘግቧል።

ይህ በእንዲህ እያለ የኢትዮጵያ መንግስት ቃል አቀባይ ወ/ሮ ሰላማዊት ዛሬ ጧት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ለሰብዐዊ እርዳታ የሚያንቀሳቅስ ልዩ ቡድን መንግስት ማደራጀቱን እና መንቀሳቀሱን ገልጸዋል። በእዚህ መሰረት በአራት ቡድን የተደራጀ የእርዳታውን ሥራ የሚያቀላጥፍ ቡድን በሰሜን ወሎ በኩል እና በሰሜን ጎንደር በኩል እንደተንቀሳቀሰ እና የመሰረተ ልማቶች ግንባታንም መንግስት እያቀላጠፈ መሆኑን ገልጸዋል።

የሰላም ንግግሩ በጥሩ ሁኔታ ማለቁ እና ህወሃት አሁን የትግራይን ህዝብ ለማዳን ብቸኛ አማራጩ ትጥቅ ፈትቶ ወትሮም ሲጠብቀው የነበረው መከላከያ ሥራውን እንዲቀጥል ማድረግ ወስኛለሁ ያለው ህወሃትም ከእዚህ ውጭ ሌላ አማራጭ አለመኖሩን ማወቁም መልካም ዕይታ ነው።እዚህ ላይ ይህ ውሳኔ የመጣው የኢትዮጵያ መከላከያ እና ጥምር ጦር አድዋ፣አክሱም እና ሽሬን ጨምሮ በርካታ የትግራይን ከተሞች እና ገጠር አካባቢዎች ነጻ ካወጣ በኋላ ነው። 
 
የስምምነቱ ውጤት ምንም ቢሆን በትግራይ ሰላም የማምጣት ሂደቱ ኃላፊነት የወደቀው መከላከያ ትከሻ ላይ ብቻ መሆኑን የትግራይ ህዝብ በተለይ ባለፈው አንድ ሳምንት ውስጥ የበለጠ ገብቶታል።ከቀደመው በላይ የቅርብ ክስተቶች ለትግራይ ህዝብ የሰጡት የሰላም ጭላንጭሎች የበለጠ ግልጽ አድርገዋል።ከእዚህ የሰላም ጭላንጭል ማንም የትም ቢሰለፍ ፈልቅቀው ሊወስዱበት እንደማይችሉ ህዝብ ይገባዋል።ለእዚህም የመከላከያ ሚና እጅግ የጎላ እንደሆነ ከምንጊዜውም በላይ ግልጽ እና ግልጽ ሆኗል።ከእነኝህ ክስተቶች ውስጥ 
  • ህወሃት ትጥቅ የሚፈታ እንጂ አይነኬ አለመሆኑን የትግራይ ህዝብ ከእዚህ ድርድር ተምሯል።
  • መከላከያ የዘር ማጥፋት ፈጸመ እያሉ በውሸት ሲያወሩ የነበሩት ሁሉ ውሸታቸውን ለመሆኑ እራሱ ህወሃት መከላከያ ይጠብቀን የሚል ሰነድ ላይ በመፈረሙ አረጋግጧል። ህወሃት በእዚህ ሰነድ ላይ ሲፈርም ለትግራይ ህዝብ ከኢትዮጵያ መከላከያ በላይ ማንም እንደማይደርስለት ለትግራይ ህዝብም ደግሞ ነግሮታል።
  • የትግራይ ህዝብ የማይነኬው ህወሃት ሊወገድ የሚችል መሆኑ ተነግሮታል።የህወሃት ሚድያዎች የኢትዮጵያን መንግስት ''ፋሽሽት'' እያሉ ከሳምንት በፊት ሲጠሩ የነበሩ በአንድ ሳምንት ውስጥ የኢትዮጵያ መንግስት ሲሉ ሰምቷል።
  • የትግራይ ህዝብ በተለይ በውጭ የሚኖሩ እና ከኢትዮጵያ እና የትግራይን ንብረት ዘርፈው የወጡ፣ለትግራይ ህዝብ አንድ ብርጭቆ ንጹህ ውሃ ያልሰጡ የትግራይ ህዝብ ሰላም ሲመጣ ሲቃወሙ አይቶ ከህወሃት በላይ የሆኑ ህወሃቶች ምን ያህል ጠላቱ እንደሆኑ ከመቼውም ጊዜ በላይ ለይቶ አውቋቸዋል።
  • ጥቅምት 24/2013 ዓም ህወሃት በመከላከያ ላይ የፈጸመው ግፍ ምን እንዳስከተለ የትግራይ ህዝብ ተመልሶ ለማየት የበለጠ ፍንትው ብሎ የታየበት ጊዜ ነው።
በመሆኑም መከላከያ አሁን ያለበት አቋም በበለጠ በትግራይ ህዝብ ዘንድ የመፈለጉ ብቻ ሳይሆን ከመከላከያ ውጭ በትግራይ ማንም ሰላም እንደማያመጣ ከምንጊዜውም በላይ ለትግራይ ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለራሱ ለህወሃትም ግልጽ ሆኗል። የትጥቅ አፈታቱ ሂደት ላይ ህወሃት ነገሮችን ለማጓተት ቢያስብም ባያስብም በተሰጠው የጊዜ ገደም ውስጥ ካልተከናወነ መከላከያ ወደ መቀሌ የመግባት እና አሁን ከፍተኛ ዝርፍያ በከተማዋ እየተፈጸመ እንደሆነ የሚነገርባትን ከተማ የማዳን ብሄራዊ ሃላፊነት አለበት።

================///==========

Friday, October 28, 2022

A Loud and Clear Lesson – For Ethiopia and the World

ዓለም እና ኢትዮጵያ (ከምዕራቡ ዓለም የሰሞኑ የሽብርተኛው ህወሃትን መደገፍ) ትልቅ ትምሕርት ይውሰዱ! በሚል የእንግሊዙ ጸሓፊ ዛሬ ያወጣው ሙሉ ጽሑፍ በርካታ ጉዳዮችን ይዳስሳል።
  • Without US support — militarily and politically — the TPLF would have been unable to wage war on the Ethiopian State.
  • No US support no war
===============
The British writer - Graham Peebles
      October 28/2022
================

First things first: as I write so-called peace talks are underway between the democratically elected government of Ethiopia and The Terrorist TPLF. That in itself is a bizarre sentence, and prompts an array of related questions, and issues around law and order, justice, national governance. To be clear, the TPLF have never wanted peace, and are not in South Africa (where the talks are taking place) to find a way to end the conflict that they started and perpetuated for two long and deeply painful years. They want power, they have engaged in talks because they have been defeated, but talks about what?

Holding hands with the TPLF men at, or more likely, under the table — out of sight — are US/UN ‘observers’. The reason for their attendance is, one assumes, to ensure TPLF bosses are kept out of prison and allowed to slip away in the night and find amnesty somewhere. Canada has been mentioned as a possible destination, although why the Canadians (or anyone else in fact) would want them is a mystery. A cell in the Hague would be my choice as they eke out their days waiting to be tried in the International Criminal Court.

In the days and weeks leading up to the negotiations, the Ethiopian National Defence Force (ENDF) has taken control of remaining towns in Tigray, including the capital Mekelle, and the fighting appears to have subsided. The only thing left to negotiate, then, is what to do with the TPLF leaders; this is not a difficult conundrum that requires hours or diplomatic chit-chat, and foreign advisers. They, the TPLF are terrorists, and should be treated in the same way that say, ISIS commanders would be, i.e., like criminals — arrested, imprisoned and tried. Their foreign assets (they stole an estimated $30 billion when in office) frozen and seized, and the monies utilized to fund rebuilding work.

The TPLF may have a few members of the “international community” rubbing up against them in Pretoria, but the Ethiopian government sits proud with millions and millions of Ethiopians and friends of Ethiopia packed into the room, and they are roaring! Wide-ranging support for the government, and love for their countrymen and women, of all ethnic backgrounds, was displayed on 22 October, when, in cities throughout the land people, young and old, assembled, marched, sang and danced. Massive crowds demanded an end to foreign intervention in the internal affairs of the nation, and wrapped their arms around the government as it prepared for the African Union convened ‘peace talks’.

No US support no war

Throughout their destructive 27 year reign, the TPLF worked relentlessly to divide communities; systematically setting ethnic groups, that had for generations lived together harmoniously, against one another. But nothing unites a nation more than a shared enemy, and Ethiopia has had two since November 2020 – the TPLF and America/The West, three if we include corporate media. The people are now united, and that sense of fellowship includes the people of Tigray – all are Ethiopians, all share the pain of the nation and all long for peace. The TPLF is the enemy, the US is the enemy, corporate media is the enemy, not Tigrayans.

Without US support — militarily and politically — the TPLF would have been unable to wage war on the Ethiopian State; no war, no death, no rape, no displacement of persons, no destruction of property burning of land, killing of livestock, no national trauma. The US is not simply complicit in the terrorism carried out by the TPLF over the last two years, and indeed during their 27 years in office, they are the enabler. The US Policy of Aggression and Derision directed against the Ethiopian government and the people, the economic sanctions, against one of the poorest nations in the world, the conspiring and duplicity, the misleading briefings and media dis/misinformation campaign emboldened the TPLF and granted them false legitimacy.

And where the US goes her allies and puppets, follow, including corporate media, which has been integral to the mis-dis information campaign, as have, somewhat bizarrely, the US Holocaust Museum, which has recently joined the party. And as talks go on these forces of duplicity and confusion continue to treat the TPLF as if they were an equivalent party to the government, rather than the monsters they are. It is shameful, but when truth and facts become a matter of opinion to be spun according to motive and self-interest it is extremely dangerous. Groups like the TPLF can only exist in the shadows, within Caves of Deceit; throw the light of truth upon them, and like the Many Headed Hydra, they shrivel up and die.

Looking for real friends

The US-supported war in Ethiopia has revealed, if demonstration were needed, in the most vivid manner, the fabric of US foreign policy and where American/Western loyalties lie. Unsurprisingly it’s with their own vested interests, or what they perceive these to be; geo-political reach, regional power, no matter the cost — human, environmental and/or social.

So, the lesson loud and clear, and perhaps this is something worth articulating in Pretoria, is the realization that, the US and ‘the West’ more broadly, including media and some institution are not to be trusted. This fact and the hurt caused by what Ethiopians rightly regard as a betrayal, will no doubt influence how Ethiopia moves forward, who it sees as ‘friends’ and allies, where it looks for support, and who it can trust and depend on.

Outrage has been felt, not just in Ethiopia but across Africa, both at the terrorist attack on their neighbour, and the response of the US/West. This will strengthen pre-existing suspicions and further energise Pan Africanism, already strengthened in recent years, and foster greater unity across the region and continent.

African nations have long been exploited by colonial powers, post-colonial institutions — the International Monetary Fund, World Bank etc, and imposed financial systems (the scandalous Structural Adjustment Programmes e.g.), which, while masquerading as ‘aid’ and/or ‘development programmes’, have ensured countries remain more or less poor, dependent and therefore malleable.

Former colonial bodies of repression and violence (US, European countries, UK), are now in crisis themselves. Economic and political instability, ideological failure and cultural insecurity abound. And as the socio-economic model that has dominated policy making (including foreign affairs) for decades disintegrates in front of our eyes, politicians, lacking humility and vision, wedded to the past, have no answers and continually stack failure upon failure.

The legacy of the global Neo-Liberal experiment is deeply divided societies of largely unhealthy people, and a man-made environmental catastrophe. Mental health illness is at epidemic proportions and climate change/ecological breakdown caused by reckless consumerism threatens the very survival of the race.

A development model, shaped around the same socio-economic paradigm that has caused the chaos has been forced on Ethiopia and all Sub-Sharan African nations. Countries are not seen as nation states with rich individual cultures, but potential marketplaces and natural resource banks.

The model is inherently unjust, benefitting a few at the expense of the many, and is made more so when applied to so-called developing nations (such terms, like the ideals they refer to and the divisions they strengthen should be consigned to the past). It is a corrupt model that, as Ethiopia moves forward and African nations look increasingly towards one another, needs to be closely examined, and in the light of need, not exploitation and profit, re-defined.

Discussions around theses issues, as well as the nature of development, democracy, environmental concerns and regional/continental unity can slowly begin to be taken up, nationally and regionally. Platforms for debate and participation established throughout the country and a vibrant space created in which people from all ethnic groups can contribute. For now though, as Ethiopia gently emerges from the violent shadow of the TPLF, united but scarred, the focus must firstly be on healing and re-construction.

Many will be traumatized and recovery will take time; the rebuilding work will be immense (construction/repair of schools, health services, housing etc), and government will require substantial support, both financial, technical and practical.

But there is no limit to what can be achieved by a united populace, building upon a platform of peace and brotherhood. The people are resolute, weary yes, but strong, supportive of one another and deeply kind, and this is potentially (we must add that caveat), the beginning of a new chapter in the life of the country. An ancient nation with a rich diverse culture that has suffered much and for far too long; a new day, quiet and full of joy let us pray, a time free from conflict and the vile poison of the TPLF.

========

Graham Peebles is a British freelance writer and charity worker. He set up The Create Trust in 2005 and has run education projects in Sri Lanka, Ethiopia and India.  E: grahampeebles@icloud.com  W: www.grahampeebles.org

=========

You can read also read the above article on counterpunch.org

=======

Gudayachn

========

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።