ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, August 24, 2012

አልቦ ብሔርነት የ ኢትዮዽያ ህዝብ'' ሶፍት ዌር ''

  •   የ አምባገነኖች መሸሸጊያ ጉረኖ ዘረኝነት እና የዘር መርዝ መንዛት ነው፤
  •  የ አቶ መለስን ስ ህተት የ አቶ መለስ ካድሪዎች'' እሱ ብሎ ነበር አልሰማ አሉት'' በሚሉ ወሬዎች ህዝቡን ሰለባ አድርገውታል፤
  • በ ሳምንቱ ለ አቶ መለስ እረፍት የ ኢህ አዲግ ፎረም አባለትን ጨምሮ (ለኑሮ የገቡቱ) እና ታዳጊው ወጣት ሁሉ የ ኢህ አዲግን ፖሊሲ ደጋፊ ሆኖ የወጣ አይደለም። ከ እዚህ ይልቅ ሁኔታው ያመላከተው ሁለት ነገሮች ናቸው፤
  • ከ ነሃሴ 27 የ ቀብር ስነ ስርዓት ቀጥሎ ትልቁ የ ህዝቡ ስራ በ ብሔር የተደራጀውን ኢህአዲግን በ አልቦ ብሔር መሰረት ባለው ኢትዮዽያዊ መንግስት በ ማንኛውም መንገድ መመስረት ቅድምያ የሚሰጠው የ አዲሱ አመት ስራ መሆኑን አልቦ ብሔር ሶፍት ዌሩ ይነግረዋል::
የ አራዳ ልጅ  ብሔር? ሲባል ምን እንደሚል ታውቃላችሁ? ''አልቦ ብሔር  '' ነው። አልቦ ብሔር ማለት  ብሔር የሌለኝ ግን ኢትዮዽያዊ ነኝ ሲላችሁ ነው።በ 1960 ዎቹ መጨረሻ ላይ የተነሳው እና በ ¨ት ሃ ቶች¨ ታሽቶ በ 1987 ዓም ¨እስከ መገንጠል¨ የሚል ቃል አክሎ፤ በ ህገ መንግስቱ ላይ ጨምሮ ፤አስጨብጭቦ፣ ሰው በቋንቋ መከፋፈልን (¨ከ¨ ሲላላ) እና መከፋፈልን (¨ከ¨ ሲጠብቅ) በሃገሪቱ ላይ የነገሰው አስተሳሰብ በትክክል ግብአተ መሬቱ ሊከናወን ሰዓታትን መቁጠር ግድ ይለዋል። ይህ የሚሆነው በ ተፈጥሯዊ ሂደት ነው።
የ ዘር ፖለቲካ ለ አለማችን አዲስ ክስተት አይደለም።የ አምባገነኖች መሸሸጊያ ጉረኖ ዘረኝነት እና የዘር መርዝ መንዛት ነው። ሂትለር የጦርነት ጥማቱን ለማርካት የ ጀርመንን ህዝብ የተለየ ህዝብ አድርጎ ማቅረብ ነበረበት። ¨እናንተ የ ጀርመን ህዝቦች የ 'አርያን'ዘሮች ¨ እያለ ይሸነግል ነበር።ሰዎች በባህሪያችን ብልህ የመሆናችንን ያህል  የመሆኑን  ጅልነትም አያጣንም።ሰው እኮ በዛፍ የማመን፣ አምላክ ነው የማለት አስቂኝ ሞራል ያለው ፍጡር ነው።¨አንተ ዘርህ የ እገሌ ነው፤ታላቅ ነህ፤ ያንተ ዘር እገሌ ድሮ እንዲህ ያደረገ፤ እገሌ የተባለው መሪህ ካንተ መንደር የተወለድ¨ ሲባል ልቡ ደንገጥ የሚል ይጠፋል ብለን አናስብ። 
 የ ሁለተኛው አለም ጦርነት እልቂት  አቶ ሂትለር ''ጀርመን ሆይ! ¨አንተ እኮ የ አርያን ዘር ነህ¨ ብሎ ነው ለ አለም የ ጥፋት እሳቱን የለኮሰው። ሞሶሎኒም ለ ኢጣልያ ህዝብ ኢትዮዽያን መውረር እንዳለበት ለማሳመን ¨የ ታላቋ ሮማ ህዝብ ሆይ!¨ የምትለዋን የ ዘረኝነት ቃል መጠቀም በቂው ነበር። አምባገነኖች የ ዘር ፖለቲካቸው ሲናድ ይደነግጣሉ፣ይርዳሉ።ስለ እዚህ ዘረኝነትን ይንከባከቡታል::
ኢትዮዽያ በ እዚህ ሳምንት ያየነው እውነታ ምንድን ነው?
ማክሰኞ ነሃሴ 15/2004 ዓም ማለዳ ላይ አቶ በረከት የ አቶ መለስን ማረፍ ለ ኢትዮዽያ ቴሌቭዥን እንዲናገር ፈቀዱለት። ቀደም ብሎ ዜናውን ከ ኢሳት የሰማ ቀድሞ ተለማምዶ ነበር እና ምንም አልመሰለውም። ብዙው ህዝብ ግን ለመረጃ እሩቅ ስለሆነ ቢያንስ አዲስ ነገር ሲሰማ ስሜታዊነት ውስጥ መግባት ሰዋዊ ባህሪው ነው። እና ሁለት አይነት ስሜት ተሰማው።
 የመጀመርያው በ አይነ ህሊናው ተቃዋሚ መሪ፤ አማተረ የለም።የሚሰማ ተስፋ የለም። ኢትዮዽያ ያለ ምንም የቀረች መሰልው እና ቀድሞ አቶ መለስን በሚገባ ቦታ ሰጥቶ የማይውቅ ሁሉ በነገሩ ክስተት ለሃገሩ አለቀሰ።
ሁለተኛው ስሜት'' የ ሆድ ብሶት'' የሚባል ስም ያለው ስሜት ተጋሪ ነው። ሃገራችን ወዴት እየሄደች እንደሆነ ህዝቡ በምናቡ ይገነዘባል። የ ዘር ፖለቲካ እና ቋንቋን መሰረት ያደረገ አከላለል ውድቀት መሆኑን ይረዳል። ይህ አደጋ ትንሽ ምክንያት ቢያገኝ ሃገሪቱን ወደ ገደል ይዞ ይሄዳል ብሎ ስላሰበ 'ሳግ' ያዘው፤ ስለ እራሱ አለቀሰ። እውነታው ይህ ነው።ከ እዚህ ውጭ ለ ፖለቲካ ትርፍ ኢህአዲግ የሚላቸው ነገሮች ሙሉ በሙሉ ትክክል አይደሉም።

የ ኢትዮዽያ ህዝብ ''ሶፍት ዌር¨'' አልተቀየረም
በ ሰሞኑ የ አቶ መለስ እረፍት የ ኢህ አዲግ ትርፍ የመሰላቸው የዋሆች ለመኖራቸው የ ኢትዮዽያ ቲቪን የሰሞኑን ፕሮግራም ያየ ይረዳል።የ ኢትዮዽያ ህዝብ ሶፍት ዌር አልተቀየረም። ሶፍት ዌሩ ኢትዮዽያዊነት  ነው።ሶፍት ዌሩ አልቦ ብሔርነት ነው። ይህን አስተሳሰብ የሚቀይር ምድራዊ ሃይል የለም።ወደፊትም አይገኝም።በ ሳምንቱ ለ አቶ መለስ እረፍት የ ኢህ አዲግ ፎረም አባለትን ጨምሮ (ለኑሮ የገቡቱ) እና ታዳጊው ወጣት ሁሉ የ ኢህ አዲግን ፖሊሲ ደጋፊ ሆኖ የወጣ አይደለም። ከ እዚህ ይልቅ ሁኔታው ያመላከተው ሁለት ነገሮች ናቸው።
የመጀመርያው አቶ መለስን ከ ኢህ አዲግ ለይቶ ነው የወጣው። እንዴት? ልትሉ ትችላላችሁ።አቶ መለስን ''ኢህ አዲግ እራሱ ሲያቆስላቸው ነው የኖረው'' የሚሉ ብዙ የ ቡና ላይ ወሬዎች አሉ። የ አቶ መለስን ስ ህተት የ አቶ መለስ ካድሪዎች'' እሱ ብሎ ነበር አልሰማ አሉት'' በሚሉ ወሬዎች ህዝቡን ሰለባ አድርገውታል። ስለ እዚህ ከህዝቡ አቶ መለስን ከ ኢህ አዲግ ለይቶ ሳጥን ውስጥ ያስገባ አለ። ይህ ለ አቶ በረከት አልገባቸውም።  ኢህ አዲግን አልደግፍም ግን በ አቶ መለስ እረፍት አዘንኩ።ሃዘኑ ግን አንድም በሁኔታው ድንገት መስማቱ(የመረጃ ማነሱን ልብ እንበል) ሃገሪቱ ምን ልት ሆን ነው የሚል ስጋት ያዘው።
ሁለተኛው ምክንያት ህዝቡ የ አልቦ ብሔር ስሜቱን በ ወንዝ እና በ መንደር ለሚያስቡ የ ኢህ አዲግ አባላት በሙሉ የሚያስተምርበት ትክክለኛ ወቅት መሆኑን ተረዳ። የ አራዳ ልጅ ሰው አክባሪ፣ ሰው አፍቃሪ ብቻ አይደለም አልቦ ብሔር መሆኑን አስመሰከረ።¨እንኳን ከ ወርቅ ህዝብ ተፈጠርኩ¨ላሉት አቶ መለስ ከ አድዋ መጣ ከ ጉለሌ  አልቦ ብሔሩ ኢትዮዽያዊ አክብሮ አስከሬን ተቀበለ።በ ነሃሴ 27 ይቀብራል።

ኢህአዲግ ከ አቶ መለስ ውጭ?
በ አቶ መለስ እረፍት የሆነው እንዲህ ነው። አቶ በረከት እና ኢህ አዲግ  በ ቲቪ ሲናገሩ ያየነው  ሁሉንም ስራ  የሰሩት አቶ መለስ ናቸው። የመንገድ መብራቱ ደሞ በ ኢህ አዲግ አደለም በ አቶ መለስ ፖሊሲ እና ስትራተጂ ነው። ሁሉም ነገር ለካ የተሰራው፣ አመራሩ ሁሉ በ አቶ መለስ ነበር። አያጣላም:: ምግብ እንድንበላ ያረጉን፤ ውሃ እንድንጠጣ ያደረጉን አቶ መለስ ናቸው። ቆዩ አያጣላን:: ለጊዜውም ቢሆን። ባጠቃላይ ኢህአዲግ በ እራሱ ምንም አይደለም አቶ መለስ ግን ሁሉም ነገር ነበሩ። ነው የተነገረው። ጥሩ።
አቶ ስየ አብርሃ ከ አቶ መለስ ጋር አብረው በረሃ የወረዱ በ ኢህ አዲግም እስከ መከላከይ ሚኒስትርነት የደረሱ አሁን የ አቶ መለስ ቀንደኛ ተቃዋሚ የሆኑ (አልቦ ብሔር  ኢትዮዽያዊነታቸውን አስቀድመው) ካለ አቶ መለስ ኢህ አዲግ ምንም ማለት አይደለም ብለው ለ አውራምባ መልቲ ሚድያ በ እዚህ ሳምንት አረጋግጠዋል። ¨
¨ አቶ መለስ ለ ህወሃት ብቻ ሳይሆን ለተቀሩት የ ኢህ አዲግ ፓርቲዎች ቀለበቱ ነበር። ካለ መለስ ኢህ አዲግ ችግር የለበትም የሚሉ ትክክል አደለም።¨ ብለዋል። ይህም ያስማማል። ኢቲቪም ህዝቡ አለ ብሎ አሳይቶናል። ለካ እነ አቶ በረከት ምንም አይሰሩም ነበር ማለት ነው? አቶ መለስ ብቻቸውን ነበር ይህን ሁሉ ስራ ሲሰሩ የከረሙት?
ስለ እዚህ ነሃሴ 27  የ ኢህ አዲግ የ ቀብር ቀን ነው ማለት ነው?
አቶ መለስ ሁሉም ነገር ከሆኑ ከ አሁን በኋላ አቶ በረከት 'ኢህ አዲግ ፖሊሲው እና ፕሮግራሙ ነው የሰራው' የሚል አረፍተነገር ለመናገር ሞራላዊ ብቃት ሊኖራቸው አይችልም።ህዝቡም (ለ አቶ መለስ ያዘነው፤ ያላዘናም አለና) በ ኢህ አዲግ ፕሮግራም የመመራት ሞራላዊ ግዴታ የለበትም። ''ለ አቶ መለስ አዘንኩ ግን አቶ መለስን የሚተካ ተቋማዊ አሰራርም ሆነ አመራር የማግኘት መብት  አለኝ'' ሊል ነው ማለት ነው  ። ባይሆን ለ አቶ መለስም ሆነ ለ ቀዳማዊ አጼ ሃይለስላሴም ሃውልት መስራት መብቱ ነው።ስለ እዚህ ከ ነሃሴ 27 የ ቀብር ስነ ስርዓት ቀጥሎ ትልቁ የ ህዝቡ ስራ በ ብሔር የተደራጀውን ኢህአዲግን በ አልቦ ብሔር መሰረት ባለው ኢትዮዽያዊ መንግስት በ ማንኛውም መንገድ መመስረት ቅድምያ የሚሰጠው የ አዲሱ አመት ስራ መሆኑን አልቦ ብሔር ሶፍት ዌሩ ይነግረዋል።
አበቃሁ።

Wednesday, August 22, 2012

ደቡብ ሱዳን ነጻ ስትወጣ ኮ/ል መንግስቱ ኃ/ማርያም ለአውስትራልያው ራድዮ SBS የተናገሩት (ኦድዮ)

ደቡብ ሱዳን ነጻ ስትወጣ  ኮ/ል መንግስቱ ኃ/ማርያም  ለአውስትራልያው ራድዮ SBS የተናገሩት።


Tuesday, August 21, 2012

የ ማስታወሻ ደብተሬ ስለ አቶ መለስ


አቶ መለስ ዜናዊ እንደ ኢሳት ቴሌቭዥን ከ አንድ ወር በፊት እንደ ኢቲቪ ደግሞ ትናንት ነሃሴ 14/2004 ዓም ከምሽቱ(5:40) አምስት ሰዓት ከ አርባ ላይ አርፈዋል።
የሚኒስትሮች ምክር ቤት መግለጫ ¨በ አቶ መለስ ዜናዊ አለጊዜው መሞት የ ኢፍድሪ መንግስ እና የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ እጅጉ ያዝናል¨  መግለጫው በመቀጠል ¨ የሃገራችን ህዝቦች የ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስቲርን መታመም ከሰሙ በኋላ በ እየእምነታቸው በጸሎት መልካም ምኞታቸውን ሲገልጹ እንደቆዩ የሚኒስትሮች ምክር ቤት እና የ ኢፍድሪ መንግስት  በከፍተኛ አድናቆት ተገንዝቧል።¨ ብሏል።

እግዚአብሄር ነፍስ ይማር። ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን እንመኛለን።

አቶ መለስ በ በጎም ሆነ በጎ ባልሆነ መልክ በ ሃገራችን ላይ ብቸኛ ተጽኖ ፈጣሪ(influential) ሰው የነበሩ ለመሆናቸው አሌ የማይባል ሃቅ ነው።

እኔ ከተናገሩዋቸው ንግግሮች ሶስት ንግግሮችን ሳያብራሩልን ማለፋቸው ወይንም በ መጽሃፋቸው ላይ ሳይገልጹልን ማለፍ አልነበረባቸውም   እላለሁ።
እነኚህ ንግግሮች አንድ ቀን ከ ስልጣን ዘመናቸው በኋላ ያስረዳሉ ብየም እጠብቅ ነበር።ምናልባት ያልታተመ መጽሃፍ ካለ አንድ ቀን ታትሞ ለማንበብ ለታሪክ ተመራማሪዎችም የመረጃ ምንጭ ይሆናል ብየ አስባለሁ።
በተለያየ ጊዜ ከተናገሩት:-

፩ ¨እንደ ግለሰብ፣ እንደ መለስ በ አንድ ጉዳይ ላይ የማስበው ሃሳብ አለ ወደ ፓርቲዪ ስመጣ እንደ ኢህአዲግ የማስበው ሃሳብ አለ።''(ለ አዲስ አመት በ አል ላይ ከተናገሩት)
የትኞቹ ይሆኑ የ ፓርቲው ሃሳቦች? የትኞቹስ ይሆኑ የ እሳቸው ሃሳቦች ግን ፓርቲው ያልተቀበላቸው?
፪ ¨ወጣት ሳለሁ ሁሉን ነገር በ አንድ ቀን ካልሆነ፣ ካልተሰራ ብዬ አስብ ነበር። አሁን በ ጉልምስና ዘመኔ ላይ ሆኘ ስመለከተው ግን የተለየ አስተያየት አለኝ። እግዚአብሄርን መፍራት፤ ቆጠብ ማለት ከወጣትነት በኋላ የሚመጣ ስሜት ነው።¨ (በ አፍሪካ ህብረት ከ አፍሪካ ለተሰበሰቡ ወጣቶች በ እንግሊዝኛ  ከተናገሩት)
፫ ¨ አንድ ነገር ስታፈርሱ እያከበራችሁ ማፍረስ አለባችሁ በ አንድ ቀን ሁሉ ካልተቀየረ ማለት የለባችሁም እያከበሩ ማፍረስ ተማሩ!''  (በሚልንየም አዳራሽ ለ ደጋፊዎቻቸው የ ፓርቲው አባላት የተናገሩት)::

ከላይ የተነገሩት ንግ ግሮች አቶ መለስን በ ሚድያ ከምናውቀው ስብዕናቸው በተለየ አንድ ያልተነገረን  ግን በ ተለያዩ ሰዎችም ይሁን ሌሎች ሃይሎች ጣልቃ የገቡበት ጉዳዮች አሉ እንዴ? እላለሁ።
ከ ሶስቱ ያልተብራሩ ንግግሮች በተጨማሪ በደንብ ያልተብራራው እራሱ አብዮታዊ ዲሞክራሲ ነው።
የ አቶ መለስ ፖለቲካዊ ፍልስፍና ''አብዮታዊ ዲሞክራሲ¨ እራሱ በደንብ የገባው ሰው ኢህአዲግ ውስጥ ያለ አይመስለኘም። ምክንያት ብዙዎቹ የ ፓርቲው ሰዎች የ እሳቸውን የ መድረክ ንግግር እየመዘዙ ከ ማስተጋባት ያለፈ የ ፖለቲካውን መሰረታዊ ፍልስፍና ስለማያስረዱ። አሁንም የ እሳቸው በበለጠ ሳያብራሩት ቢያንስ በደንብ የሚያብራራ ሰው ሳይተኩ ማረፋቸው እንደገና አሁንም ¨አብዮታዊ ዲሞክራሲ¨ላልገባን በ ሚልዮን ለምንቆጠር ¨ጭቁን ህዝቦች¨ የ ፖለቲካው ፍልስፍና በደንብ እንዲከለስ ለመጠየቅ ግድ ይለናል።
ለ አቶ መለስ እረፍተ ነፍስን፤ ለ ቤተሰቦቻቸው መጽናናትን ይስጥልን።
አበቃሁ።

Sunday, August 19, 2012

¨ጉዳያችን¨ በ አንድ አመቷ

ጉዳያችን ጡመራ መጫጫር ከጀመረች እነሆ አንድ አመቷን ደፈነች። እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ :-
  • ሰላሳ ሁለት ርዕሰ ጉዳዮች ተነስተዋል፤
  • ከ አስር ሺ ጊዜ በላይ (ከ ሰላሳ አምስት ሃገሮች በላይ ውስጥ ነዋሪ በሆኑ) አንባብያን  መከፈቱን ለማወቅ ችያለሁ፤
  • የ ጡመራው ከፋቾች ብዛት በደረጃ ኖርዌይ፣ኢትዮዽያ፣ሰሜን አሜሪካ በቀን ውስጥ ብዙ ጊዜ በመክፈት ሲጠቀሱ፤ ከ መካከለኛው ምስራቅ የ አረብ ኢምሬትስ እና እስራኤል ከ እስያ ሩስያ፤ ከ አውሮፓ ጀርመን እና እንግሊዝ፤ ከ አፍሪካ ኢትዮዽያን አስከትለው ደቡብ አፍሪካ እና ኡጋንዳ ይጠቀሳሉ።
  • አስተያየትን በተመለከተ የ ጡመራው  ከፋቾች በጣም ቁጥብ ናቸው።እስካሁን ከ ሰላሳ ሁለቱ ርዕስ ጉዳዮች አስተያየት የተሰጠው ብዛት ሰባ አራት ብቻ ነው። በእርግጥ በ ኢሜይል የሚላኩት በጣም አስፈላጊ ሃሳቦች ሆነው አግኝቻቸዋለሁ። ለምሳሌ ፎቶዪን ¨ከበድ¨ አለ የሚል ሃሳብ ከሰነዘሩልኝ ጀምሮ በቅርብ የተያያዙትን የ ¨የ ቢቢሲ ፎከስ ኦን አፍሪካን ሊንክ¨ እና የ እንግሊዝኛው  ¨ኖርዌይ ፖስት¨ ጋዜጣ ሊንክ መለጠፉን እስካሞገሱልኝ ድረስ አስተያየት ለሰጣችሁኝ እግዚአብሔር መካሪ አያሳጣብኝ እያልኩ አመሰግናለሁ። ፎቶዬን በተመለከተ በትክክልም አምኘበታለሁ እናም ቀይሬዋለሁ።በ መጪው 2005 ዓም እናንተ በ ኢ-ሜልም ጭምር በመምከር እኔ በመሞነጫጨር እንድበረታ በጸሎታችሁ አስቡኝ።
ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ

Friday, August 17, 2012

መልካም እሴቶቿ የተጎሳቆሉባት ሃገር!

  • ህብረተሰብ በተለያዩ ማህበረሰባዊ ተቋማት ውስጥ ይገኝ እንጂ የጋራ በሆኑት መልካም እሴቶቹ ላይ ግን ብዙ ባይቀልዱበት ይመርጣል።
  •  የመንግስት እና የ ሃይማኖት ተቋሞቻችን በ መልካም እሴት ጥበቃ አንጻር ስንመዝናቸው ከ አመት አመት አይደለም ከ ቀን ቀን በሚበር ፍጥነት እየወረዱ ነው።
  • እያንዳንዱ የመልካም እሴት መሸርሸር ዜና ከ ጠላ እና ጠጅ ቤቶች እስከ ሸራተን ሆቴል ውስጥ እስከሚገኘው ¨ኦፊስ ባር¨ድረስ በ ህዝቡ ዘንድ ብቻ ሳይሆን በ ውጭ ሃገር ዲፕሎማቶች ዘንድ ሁሉ ይፈተሻል::
  • ህዝብ መልካም እሴቶቼን መልሱ ብሎም በግድ ይጠይቃል። አሁንም በእዚህ አያቆምም መልካም እሴቶችን ያጎሳቆሉቱኑ ተቋማት አፍርሶ በተሻለ ለመቀየር ይወስናል።
  • በ ሃይማኖት ተቋማት ውስጥ በ ሚልዮን የ ሚቆጠር ገንዘብ የሰረቀ፤ሲበጠብጥ ሲያበጣብጥ የነበረን፤ አልተሳካም እንጂ ያለውን ጦር ሁሉ የወረወረን የሚሸልም ህብረተሰብ አለን እንዴ?
ማንኛውም ነገር መለኪያ ተቀምጦለታል።ያልተለካ ነገር መጠኑ እንዴት ይታወቃል? በጎ ስራም ሆነ ክፉ ስራ መለኪያ አለው።በስራው ቁጥር አልያም በ ጥራቱ ይለካል።ቅዱስ መጽሃፍ የ አንድ በጎ ስራ ወይንም ተግባር መለኪያው ''የ ስራ ፍሬ'' እንደሆነ ያስተምረናል።¨ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ¨ የሚለው ቃል የ ተግባር ፍሬ የ አንድ ሰው የ ስራ   መለኪያ ነው ማለት ነው።ቅዱስ መጽሃፍም የእምነት ሰውን  ካልሆነው ሰው የሚለይበት መለኪያ እያደናገረ እንዳይኖር ¨በ ፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ¨ ብሎ ፍሬ የበጎ ስራ መለኪያ መሆኑን አስቀምጦልናል።
አሁን ያለንበት ወቅት የ አዲሱ ትውልድ ከ ቀደመው ትውልድ መረከብ የጀመረበት፤ ያለፈው ትውልድ በ ዘመን እርጅናም ሆነ በ ስራ መልቀቅ ለ አዲሱ ትውልድ ቀስ በቀስ እየለቀቀ የመጣበት፤ ይህ ሂደት በ ጥሩ መሰረት ላይ ከተመሰረተ ሃገራችን የማደግ እድሏ ከፍ የሚልበት ሁኔታ መፍጠሩ የማይቀር ነው።
¨ከ ትናንት ብንዘገይ ከ ነገ እንቀድማለን¨
ትናንትን እያነሳ የሚቆዝም ህብረተሰብ የ ዛሬን ከ እጁ እንደሚጥል ሳይታለም የተፈታ ነው። እዚህ ላይ ግን ካለፉት ስ ህተቶች ተምሮ ለወደፊቱ በጎ መሰረት መጣል የሚቻለው ህብረተሰቡን  ¨የመሸለም እና የመውቀስ¨ ልምድ ያለው በማድረግ   ብቻ ይመስለኛል።
 ቀደም ባሉት መንግስታቶችም ሆነ ዛሬ እንደ ክፉ አባዜ ያልለቀቀን እና ከስር እየወጣ ያለው ታዳጊ ወጣትንም እያስተማርነው ያለነው።በጎ የሰራ ሲሸለም፤ ክፉ የሰራ ሲቀጣ አይደለም። ይህ ደግሞ ዛሬ አለንበት ከምንለው ችግር በባሰ የተደራረበ ችግር ይዞ የሚመጣ አደገኛ መርዝ ነው።
ማህበረሰባዊ ሽልማት ምንድን ነው?
ህብረተሰብ ካለፈበት ፖለቲካዊም ሆነ ምጣኔ ሃብታዊ ሂደት ዋጋ የሚሰጣቸው እሴቶች ተጠብቀው ሲያገኝ ያንን መልካሙ እሴት እንዲጠበቅ የረዳውን ወይንም መልካሙን እሴት በተግባር ያሳየውን ሁሉ ይሸልማል።ሽልማቱ በቁሳዊ ነገር አይላካ ይሆናል። በ ሞራላዊ እሴት ግን ያንበሸብሻል። የ ህብረተሰባችን መልካም እሴቶች:-
አለመዋሸት፣
አለመስረቅ፣
አለመክዳት፣
እልከኝነትን ማራቅ፣
ይቅር ባይነት፣
መተዛዘን፣
ጸረ ዘረኝነት፣
ታማኝነት፣
ወ ዘ ተ
በ ህብረተሰባችን ዘንድ ዋጋ የሚያስጡ መልካም እሴቶች ናቸው። ህብረተሰባችን ተቋማትን የሚለካበት መስፈርት በ እነኝህ መልካም እሴቶች አንጻር መሆኑ እሙን ነው። ለ ሃገር እድገት ደግሞ እነኝህ መልካም እሴቶች እጅግ አስፈላጊ ግብአቶች ናቸው። የ እነርሱ መሸርሸር የ እድገት ቁልቁልዮሽ ጉዞ ጅማሮ ብሎም  እንደ ህዝብ እና ሃገር የመቀጠል አስቸጋሪ ሁኔታዎች ከ ፊት ለፊት የመደቀን አደጋቸውም የ እዚህኑ ያህል ያጎሉታል።
ህዝብ ይመዝናል
ህዝብ የማይጨበጥ እረቂቅ ነገር አይደለም። በመንገድ ላይ ስንሄድ፤ ከ ቤት ስንገባ፤ በ ማህበራዊ ድህረ ገጾች ሁሉ የምናገኘው ምናባዊ ያልሆኑ የሚናገሩ፣የሚዳሰሱ እና የሚያዳምጡ ሰዎች ስብስብ ነው-ህዝብ።ይህ ህዝብ በ ስብስብ መልኩ ተቋማዊ መልክ ሲላበስ ህብረተሰብ ይባላል። ህብረተሰብ በተለያዩ ማህበረሰባዊ ተቋማት ውስጥ ይገኝ እንጂ የጋራ በሆኑት መልካም እሴቶቹ ላይ ግን ብዙ ባይቀልዱበት ይመርጣል። እሴቶቹን ለጠበቁለት የሚሸልመውን ያህል። ላጎሳቆሉበት ደግሞ ጥሩ አድርጎ መቅጣት ያውቅበታል።
ዲሞክራሲ ለ ህብረተሰብ የሚሰጠው እድል ይህንን ነው። በ መናገር መብትህ ታግዘህ መልካም እሴቶች ህን ያጎሳቆለብህን ውቀሰው ይላል- ዲሞክራሲ። ለ እዚህም ነጻ የ ሚድያ እድል ይሸልማል -ዲሞክራሲ።በ የትኛውም ተቋም ስር ተሸሽጎ መልካም እሴቶችህን የሚነካብህን በ ነጻ ምርጫ ምታው ይላል። አሁንም -ዲሞክራሲ።እድገትም እና ልማትም ከ እዚህ ይነሳል።
እኛን ያቆሰለን
ወደ ሃገራችን ስንመለስ መንግስት እና የ ሃይማኖት ተቋሞቻችን በ መልካም እሴት ጥበቃ አንጻር ስንመዝናቸው ከ አመት አመት አይደለም ከ ቀን ቀን በሚበር ፍጥነት እየወረዱ ነው። ይህ ነው የነገን ትውልድ ብቻ ሳይሆን የ አሁኑም ትውልድ የመኖር ህልውናውን በ ከፍተኛ አደጋ ላይ የመጣል እድል ያለው። በማስረጃ ላብራራ።
ኢትዮዽያ ለ መንግስት ስሪት አዲስ አይደለችም። በ ሺህ ለሚቆጠሩ አመታት መዋቅር ያላቸው፤ህግ እና ስርዓት የተበጀለቸው(በ ወቅቱ ይመጥናል በተባለ ደረጃ)፤ ተጠያቂነታቸው ለ ሰውም ለ እግዚያብሄርም ያደረጉ መንግስታትን በየ ዘመኑ አሳልፋለች። በ እነኚህ መንግስታት አሰራር ስርዓት ውስጥ ግን ሚስጥራዊው ዋስትና የ ህብረተሰቡን ብቻ ሳይሆን ¨ሰው¨ ተብሎ የተፈጠረ ፍጥረት ዋጋ የሚሰጣቸውን እሴቶች በ ወቅቱ ህብረተሰቡ በደረሰበት የ እድገት ደረጃን እና ስነ ልቦናዊ ንቃት በመጠነ መልክ አክብረው እና አስከብረው በመኖራቸው ነው።
መልካም እሴቶች በ አጼ ሃይለ ስላሴ እና በ ደርግ ዘመን
ባለፉት ሃምሳ አመታት ውስጥ የነበሩንን ሶስት መንግስታት ታሪኮች (የ አሁኑ ኢህአዲግን ጨምሮ) መሰረታዊ የመቀየር ባህሪያቸው የሚመነጨው ከ ህብረተሰቡ መልካም እሴት ጋር መታረቅ ሲያቅታቸው ነው። የ አጼ ሃይለ ስላሴ መንግስት አብዮቱ ከመፈንዳቱ ቀደም ብሎ ህብረተሰቡ ያነሳቸው የነበሩ ቀላል የሚመስሉ ግን ግዙፍ የሆነ የ መልካም እሴትን የማስከበር ጥያቄ እንደዋዛ ታይተው እናያቸዋለን። የወሎ ረሃብ ጉዳይ የተያዘበት አያያዝ፤ የንጉሱ የ ሰማንያኛ የልደት በዓል የተቀናጣ መሆን፤ የ ፊውዳል ባለ መሬት በጭሰኛ ገበሬው ላይ የሚያደርሰው ግፍ እና የመሳሰሉት ህዝቡ ¨በጎ እና መልካም እሴቶቼ¨ ከሚላቸው ጋር እየተጣረሱ ¨ፍት ህን፣እውነትን እና ርህራሄ¨ የተሰኙትን እሴቶች ማንም እንደማያስከብራቸውም ሆነ እንደማያከብራቸው ያረጋገጠው ህዝብ ሊያስከብራቸውም ሆነ የሚያስከብር ሊሾምላቸው እራሱ ተነሳ።አብዮቱ ፈነዳ።

ይህንኑ ጉዳይ በ ደርግ ስርዓት በ ባሰ እና በገዘፈ መንገድ እናገኘዋለን።ደርግ በመጀመርያ የ መልካም እሴት ጥሰት የጀመረው ጊዜያዊ መንግስት ነኝ ብሎ ከመጣ በኋላ በመጀመርያ ኢሰፓአኮ (የ ኢትዮዽያ ሰራተኞች አደራጅ ኮሚሽን) በመቀጠል ኢሰፓ (የ ኢትዮዽያ ሰራተኞች ፓርቲ) መች በእዚህ አበቃና ኢህድሪ (የ ኢትዮዽያ ህዝባዊ ዲሞክራሳዊ ሪፓብሊክ) ብሎ ¨አንቺው ታመጪው አንቺው ታሮጪው¨ እንዲሉ መለዮውን አውልቆ ሲቪል ሆንኩ አለ።¨እውን ደርግ አለን¨  ተብለናልና። ይህ የመስረታዊ መልካም እሴት ጥሰት ብቻ ሳይሆን በ ህብረተሰባችን ዘንድ ወንጀልነቱ ታምኖ ቅጣቱን ለመስጠት ቀን ሲታሰብለት ኢህአዲግ የሚባል ድርጅት ሲገኝ ገበሬው በተለይ ያ የተነካበትን መልካም እሴት ለማስመለስ መንገድ እየመራም፣እየተራዳም አዲስ አበባ ድረስ ይዞት ገባ።

ኢህአዲግ በ ገጠር ትግሉ ወቅት የህዝቡን ልብ ያገኘው በሌላ በምንም ሳይሆን ¨መልካም እሴትን የሚጠብቅ ነው¨ ተብሎ በ ገበሬው ዘንድ ስለታመነ ነበር። ኢህአዲግም የዛሬን አያድርገው እና ¨''ብልጠት'' ነበረበት። ሰራዊቱ በ ገጠር ያለች ቤተ ክርስቲያን ካገኘ ለጥ ብሎ በመሳለም (ደርግ በ አይሮፕላን ሲመታ በ ኢላማ ስ ህተትም ይሁን በምን  ባይታወቅም) ፤ ከ ገበሬው ቤት ተጠግቶ ¨እማዪ ይችን ልጋግር ነበር ብረት ምጣድዎን ልዋስ ዱቄት አለኝ አላስቸግርም¨ ብሎ ሰራዊቱ ሲናገር የ ገጠር እናቶቻችን ¨መሳርያ ይዞ ሞሰቡን ልገልብጥ ማለት ሲችል ¨ እያሉ እንጀራቸውንም እየጨመሩ ሰጡ።

 መልካም እሴት መጠበቅ ለትልቅ ድል ለማብቃቱ ማስረጃ ነው። ተመሳሳይ በ ኤርትራም የሆነው ይህ ነው። ከ ከተማ ታፍሶ የሚሄደው እና በ ግድ የተመለመለው ሰራዊት ሴቶችን በመድፈር ሲታማ የ ሻብያ ተዋጊዎች ግን መልካም እሴት አቃብያን ሆነው ብቅ አሉ። ¨ይህ የሆነብህ የ ደርግ ጸረ ዲሞክራሲ አሰራር ነው¨ ተብሎ ሳይሆን ለ ህዝቡ የተነገረው ¨አንተ ኢትዮዽያዊ ስላልሆንክ ነው መልካም እሴት ህን ሊያጠፉብህ መጡ¨ እየተባለ ተወሸከተለት። መልካም እሴቱን ያከበሩለት ቀዳማዊ አጼ ሃይለ ስላሴማ ከ አስመራ ወደ ምጽዋ ሲሄዱ (በ ምጽዋ የ ቅድስት ማርያምን ቤተ ክርስቲያን እና መስጊድ እንዲሰራ በ አንድ ቀን የመሰረት ድንጋይ ለመጣል ሲሄዱ) በ ፍርሃት ሳይሆን በ ፍቅር ህዝቡ ልብሱን እያወለቀ መሬት እያነጠፈ መቀበሉን በወቅቱ የ እንግሊዝ እና የ አለም የ ዜና መገናኛዎች የዘገቡት ጉዳይ ነበር።የ መልካም እሴት የመጠበቅ የ ህዝብ ክፍያ።
መልካም እሴታችን  በዘመነ ኢህአዲግ

Saturday, August 4, 2012

¨ሰማሽ አንቺ እማማ ኢትዮዽያ ቃል የ እምነት ዕዳ ነው እንጂ የ አባት የ እናት እኮ አይደለም¨

  • የ ህገ መንግስቱ ችግር ¨ ኢትዮዽያ የምትባለው ሃገር የማን ናት? ህገ መንግስቱ የ ሃገር ባለቤትነትን ለማን ስጥቷል? የሚሉትን ጥያቄዎች በ አግባቡ አለመመለሱ ነው።
  •  ¨ኢትዮዽያ የምትባል ሃገር ኢህአዲግ በስልጣን ላይ እስካለ ድረስ ብቻ የምትኖር ከሌለ ግን (ክልሎች ሁሉንም ማረግ ስለሚችሉ) ማእከላዊ መንግስት ብዙም የማያስፈልጋት ነች።¨ ለማለት ነው የፈለጉት:: የ አቦይ ስብሃት የ ገለጻ አንደምታ ለ እኔ እስከገባኝ ድረስ ።
  • ኤርትራ በብዙ የ ፖለቲካ ተንታኞች አይን ( በ አሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አይንም) የምትታየው ¨እያነባ እስክስ¨ የሚል መንግስት ያላት ምስኪን ሃገር ተደርጋ ነው።
  • የ አሜሪካ ብቻ ሳይሆን የ ፖለቲካው አለም መርህ ¨ የዘላለም ጥቅም እንጂ የዘላለም ወዳጅ የለውም¨ በሚል መርህ ላይ ይመሰረታል።
ልጅ ሆኜ በ ኢትዮዽያ ቴሌቭዥን ቅዳሜ ማታ በቀጣዩ ቀን በ አዲስ አበባ ቲያትር ቤቶች  ስለሚታየው ቴያትር ማስታወቂያ ማየት የተለመደ ነበር።ጥቁር እና ነጭ ቲቪያችን (ከለር ቲቪ በሃገራችን የተጀመረው ከ ''ኢሰፓ'' ምስረታ ጋር በ1977 ዓም መሆኑን ልብ በሉልኝ)   የምወድላት ማስታወቂያ ነበራት።''ቴዎድሮስ'' ለሚለው ቲያትር ፍቃዱ ተክለማርያም እንዲህ ሲል ልቤን ይነካዋል።¨ሰማሽ አንቺ እማማ ኢትዮዽያ ቃል የ እምነት ዕዳ ነው እንጂ የ አባት የ እናት እኮ አይደለም¨ ( አፄ ቲዎድሮስ)። ፍቃዱ ህይወት የዘራበት ይህ ታሪካዊ ተውኔት ብዙ ቁም ነገሮችን ይዟል። በዘመነ መሳፍንት ሃገራችን  ማዕከላዊ መንግስት ያልነበራት፣ መሳፍንቱ ሁሉ በያለበት አዛዥ ናዛዥ የነበረበት፣ ትንሽ ጊዜ ቢያገኝ ኖሮ ዘመነ መሳፍንት በትክክል ሃገራችን ስም ታሪኳ ጠፍቶ ትናንሽ መንግስታት የመፈጠር እድላቸው በ ሂደት የሚያሰጋበት ነበር። ይህ ደግሞ በጊዜው ከሚያንዣብበው የ አውሮፓውያን የ ቅኝ ግዛት ጥማት አንጻር እና ከ በርሊኑ ስምምነት በኋላ አስጊነቱ አሌ የማይባል ነበር። አፄ ቴዎድሮስ ግን ከ ቋራ ገስግሰው የ ጎንደርን፣የወሎን፣የጎጃምን፣የትግራይን እና የ ሸዋን የ አካባቢ ንጉሶች ሁሉ ድል አድርገው አንዲት ኢትዮዽያን መልሰው አቆሙ።
ኢትዮዽያ የምትባለው ሃገር የማን ናት?

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።