ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, June 23, 2012

ኢትዮዽያን ለማጥፋት ኦርቶዶክስን ማጥፋት -''የተሃድሶ'' ቅሰጣ

የ ኢትዮዽያ ቤተ ክርስትያን የ ኢትዮዽያን ብቻ ሳይሆን የ ዓለም አሻራ የሚታዩባት ለመሆንዋ ባዕዳንም የመሰከሩላት ነች። የ ቤተ ክርስትያን መታወክ የሃገር የጸጥታ ችግር ብቻ ሳይሆን ኢትዮዽያን እንደ ሃገር እንዳትቀጥል ለማድረግ ቁልፍ ስራ እንደሆነ የተረዱ የ ኢትዮዽያ ጠላቶች ተግተው እየሰሩበት ነው።ለእዚህም ብዙ ማስረጃ ማቅረብ ይቻላል። አንዱ ማሳያ እና አይነተኛ መሳርያ ሆኖ የቀረበው እራሱን በግልጽም ሆነ በስውር ''የ ተሃድሶ እንቅስቃሴ'' እያለ የሚጠራው አንዱ  ነው።
የቤተ ክርስትያንን መሰረተ እምነቷን ለመናድ ምዕመኗን በጥርጥር ትምህርት ለመበረዝ፣ የቤተክርስትያን በሆኑት ነገሮች ሁሉ ላይ ቸልተኛ እንዲሆን፣ቅዳሴዋን፣በማሕሌት አምላኳን ማመስገኗን እና የነበረ ስርዓቷን ቀስ በቀስ ለመናድ ተንኮል በተመላበት ትምህርት፣የ ዘፈን ቃና ባለው እና መሰረተ ዕምነትን የናደ ስንኝ በያዘ መዝሙር መሰል ''መዝሙር''  በተደራጀ መልክ ማወክ ስራዪ ብለው ይዘውታል። ከሁሉም ከሁሉም ቤተ ክርስትያንን እናድሳለን ብለው የተነሱ ወይንም ከትምህርት ማነስ እናድሳለን ላሉቱ ሳያውቁ እያገለገሉ ያሉት መሰረታዊ መለያቸው ምን ያህል ስለ ተዋህዶ ቢናገሩ ስለሚሉት ሁሉ እንደማያምኑበት በ አንድም ሆነ በሌላ በስራቸው እና በትምህርታቸው ይታወቃሉ። ''ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ'' እንዲል::

ጉዳያችን ይህ ትልቅ ሃገራዊ አንደምታ ያለው ጉዳይ በኢትዮዽያ የ ሃይማኖቱ ተከታይ ባልሆኑትም ሁሉ ላይ በተዘዋዋሪም የ እራሱ አንደምታ ስላለው  የ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታይ ያልሆኑም  ከ ሃገር ፍቅር አንጻርም ቢሆን ጉዳዩን ሊረዱት ብሎም ለሃገሪቱ የነበረ ቅርስ መጠበቅ የ እራሳቸውን ሃገራዊ ድርሻ ሊወጡ ይገባል ብላ ታምናለች።ይህ ብቻ አይደለም ለተለያየ ፖለቲካዊ ጥቅም ሲሉ ከ እዚህ አፍራሽ አስተሳሰብ ጋር በማወቅም ይሁን ባለማወቅ እያገዙ ያሉ ቆም ብለው ማሰብ ካለባቸው ጊዜው ነገ ሳይሆን ዛሬ ነው። ''ሃይማኖት የ ህዝብ ስስ ብልት ነው'' እና::

ይህንን ሃምሳ አራት ደቂቃ የፈጀ ከ ቀሲስ ዶክተር መስፍን ተገኝ ጋር'' ብስራት'' ከተሰኘ ራድዮ ጋር ያደረጉት ቃለ ምልልስ ስለ ''ተሃድሶ''ሃገራዊ  ችግር ምንነት በትክክል የሚያመላክት ይመስለኛል። ጊዜ ወስደው ያድምጡ።




ቀሲስ ዶክተር መስፍን ተገኝ
vidio source=Deje selam sep.23,2011 (''ሊያዳምጡት የሚገባ ትምህርታዊ ቃለ ምልልስ'' http://www.dejeselam.org/2011/09/blog-post_23.html)

Saturday, June 16, 2012

የአምባገነንነት ዲግሪው ስንት ነው?

ይህንን ጽሁፍ ስጽፍ በኖርዌይ ቲቪ(NRK 1)  ኦስሎ ''ቀዩ ቤት'' የኖቤል ሽልማት መቀበያ አዳራሽ በቀጥታ የሚተላለፍ ፕሮግራም የበርማዋን ዲሞክራሲ ታጋይ አዉንግ ሳንሱኪ ሃያ አመታት በፊት ተሸልማ የነበረውን የኖቤል ሽልማት ሳቢያ (እስር ቤት በመክረሟ በወቅቱ ሽልማቱን ለመውሰድም ሆነ ንግ ግር ለማድረግ ባለመቻልዋ) ንግግር ለማድረግ በዝግጅት ላይ ነበረች።
አውንግ ሳንሱኪ :-
  • ሰኔ 19/1945 እኤአ በርማ ተወለዱ፤
  •  1990 ዓም እኤአ በተደረገው ብሔራዊ ምርጫ በሊቀመንበርነት በሚመሩት ብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ ሊግ ሰማንያ ዘጠኝ ከመቶ በማሸነፍ ተመረጡ።ነገር ግን አምባገነኑ የበርማ መንግስት ቁም እስር ፈርዶባቸው ነበር እና የዲሞክራሲው ጭላንጭል ቶሎ ከሰመ፤
  • ሀምሌ 20 ፣1989 እስከ ህዳር 13 ፣2010 ሃያ አንድ አመታት ያህል በእስር ቆዩ፤
  • በእስር ላይ ሳሉ  በ1991 ዓም  ኖቤል ሽልማት፣በ1992ዓም   ህንድ ጃዋላ ኔህሩ ዓለም አቀፍ ሽልማት እና በ2007 ዓም  ካናዳ ክብር ዜግነት አግኝተዋል፤
ዛሬ ሰኔ 16/2012 እኤአ የዛሬ 20 ዓመት ማድረግ የነበረባቸውን ንግግር እያደረጉ ነው። አውንግ ሳንሱኪ አምባገነንነት ሰለባ ተምሳሌት ናቸው። አንድ ወቅት ላይ ዳኛ ቡርቱካን ሜዴቅሳ ''በትግል ህይወትዋ ሁሉ ምሳሌ የሚሆንሽ ማነው? ''ስትባል አውንግ ሳንሱኪ ማለትዋን እና በእያንዳንዱ የፈተና ቀናት የምታስታውሰው አውንግ ሳንሱኪ መሆኑን ፤ በእርሷ ላይ የደረሰውን ስታስብ ብርታት እንደምታገኝ መናገሯን አስታውሳለሁ።

  ብርቱካን ከ እስር እንደተፈታች ለ ሮይተር ጋዜጠኛ በ መኪና መስታወት ስር ስትናገር


የዚህ ጽሁፍ ዓላማ ስለ ዳኛ እና ዲሞክራሲ ታጋይ ብርቱካን ለማውሳት ሳይሆን አምባገነንነትን እና አደጋውን ምን ያህል ከገመትነው በላይ በደቀነው ችግር ላይ ትንሽ ለመሰንዘር ነው።

አምባገነንነት ምንድን ነው?
ዊኪፒድያ  አምባገነንነትን ''የ አንድ ሰው ወይንም የተወሰኑ ቡድሮች ፈላጭ ቆራጭ አስተዳደር፤ በዘመናዊ ትርጉም ደግሞ ህገመንግስት፣ለ ማህበረሰባዊ ህጎች ሁሉ የማይገዛ የመንግስት አስተዳደር''  ነው ይላል::(http://en.wikipedia.org/wiki/Dictatorship)
አምባገነንነት አስገራሚ ባህሪው   የደነገጋቸውን ህጎች ተግባራዊ የሚያደርጋቸው እራሱ የተመቹት ጊዜ ብቻ መሆኑ ነው። ኢትዮዽያ ስለ አምባገነንነት አደጋው እና ሃገር ህልውና ላይ ያዘለውን የጥፋት መዓት የምንረዳበት ደረጃ ያንስብኛል። እዚህም ይመስለኛል ሰዎች ''የባሰ አታምጣ'' የሚል ብሂል እየደጋገሙ ነገን  ማየት በተሳነ አዕምሮ መኖርን የሚመርጡት። የበርማዋ አውንግ ሳንሱኪም ሆኑ ዳኛ ብርቱካን ሜደቅሳ የባሰ አታምጣ ብለው በሙያቸው እያገለገሉ ሲጠሩዋቸው'' አቤት'' ሲልኩዋቸው ''ወዴት'' እያሉ መኖርን ሳያውቁበት ቀርተው አይደለም።የነገው አደጋ ፍንትው ብሎ ቢታያቸው እንጂ።
የአምባገነኖች የሃገር አመራር ዘይቤ አንድ እርምጃ ወደፊት ሶስት እርምጃ ወደ ኋላ
  • በ አምባገነን ስርዓት ስር የሚተዳደር ሃገር መንገድ ይሰራ ይሆናል ነገር ግን በመንገዱ ላይ የሚሔደው በፍርሃት የተሸበበ እና የተከዘ ህዝብ ነው፤
  • በ አምባገነን ስርዓት ስር የሚተዳደር ሃገር ዩንቨርሲቲ ይከፍት ይሆናል:: ነገር ግን ስለምን መመራመር፤ ስለምን ማውራት፤ወዘተ እንዳለባቸው የሚነገራቸው ብቻ ሳይሆኑ የቱን ማንበብ ፤የቱን አለማንበብ፤ እንደሚገባቸው የተወሰነላቸው ምሁራን የሞሉበት ተቋም ይሆናል፤
  • በ አምባገነን ስርዓት ስር የሚተዳደር ሃገር የተረጋጋ፣ሁሉ ነገር አልጋ በ አልጋ የሆነ ህዝቡ ከዝምታው የተነሳ ሃገሩ ሰላማዊ ነው ሊባል ይችል ይሆናል። ሰላም የሆነው ጎዳናው ነው እንጂ የህዝቡ አዕምሮ አይደለም። ሰላምም ሆነ ጦርነት  የሚፈጠረው  በሰው አዕምሮ ነው  የሚባለው ለእዚህ ነው።ምንም ያክል ልማት ቢሰራ ነገን ዋስትና ያልሰጠ ልማት እንደኖረ መቁጠር የሚከብደው ለእዚህ ነው። ለእዚህም ምሳሌ የምትሆነን ሊብያ ነች። ሊብያ ከ 1980 ዎቹ ማለቅያ ጀምሮ በ አለም ላይ የነፍስ ወከፍ ገቢያቸው ከፍተኛ ከሆኑት ሃገሮች ተርታ ትመደባለች።በ እዚህም መሰረት ከጣልያን፣ሲንጋፖር እና ደቡብ ኮርያ ጋር በተስተካከለ እና አንዳንድ ጊዜም በተሻለ ሁኔታ መሆንዋ ሲተረክላት ነበር። (http://en.wikipedia.org/wiki/Libya#Economy) የ ጋዳፊ አምባገነንነት ግን የ ህዝቡ በ ኑሮ መደላደሉ ሊያዘናጋው አልቻለም። ነጻነት፣ዲሞክራሲ፣ እንደሰው የማሰብ መብት ከሁሉ ልቀው ተነሱ። ለእዚህ ነው ዛሬም ስለ ልማት ብቻ በማውራት ሃገር ከ አምባገነንነት ሳትላቀቅ ታድጋለች ብለው ለሚናገሩ ሁሉ ማስረጃችን ከ ጓሮ አለ እና ለ አስተማማኝ እድገት ዲሞክራሲ፣የ ህግ የበላይነት እና ከ ዘረኝነት የጸዳ ፖሊሲ እና ስርዓት መቅደም አለባቸው የሚባለው።
 ለመሆኑ የ አምባገነንነት ዲግሪው ስንት ነው?
  •  የ ሰማንያ ሚልዮን ህዝብ ይወክላል ብለው ባቆሙት ምክር ቤት ውስጥ  99.6% ፐርሰንት አሸነፍኩ ማለት?
  • የትኛውም መንግስት ከ አንድ ሺህ አመት በላይ ያልደፈሩትን የዋልድባን ገዳም ደፍሮ ስኳር ፋብሪካ መገንባት እና የገዳሙን አካባቢ ወደ ከተማነት መቀየር?
  • የሰለጠነው ዓለም በነጻ የፈቀደውን የ ኢንተርኔት አገልግሎት ስካይፒን ጨምሮ ማገድ?
  • በጋዜጣም፣በኢንተርኔትም፣በቀልድም (አቤ ቶክቻውን ቀልዶች ያስቡ) አትውቀሱኝ እኔ ትክክል ነኝ ማለት?
  • በንግግር በጽሁፍ የተቃወሙትን አሸባሪ ብሎ ወደ እስር ቤት መላክ?
  • ቤልጅየምን ያህል መሬት ለ ውጭ ሃገር ባለ ሃብት ይሸጣል ማለት?
  • መምህራን የደሞዝ ጭማሪ ሲጠይቁ ድሮም ችሎታ የሌላቸው ነበሩ ማለት?
ዛሬ ሃገራችን የገጠማት ችግር አሳሳቢ የሚያደርገው የ አምባገነንነት አሰራር መስፈን ብቻ አይደለም:: የ አምባገነንነት ዲግሪው የጋለ መሆን ነው እንጂ። መቸም ይህን አባባል የሚያስተባብል ይኖራል ለማለት ይከብደኛል ምክንያቱም ይህንን ስዬ አብርሃምም፣አረጋዊ በርሔም፣ገብሩ አስራትም፣ፕሬዝዳንት ነጋሶም ያረጋገጡት ሃቅ ነው።ምናልባት የ አምባገነንነቱን ዲግሪ አለኩልንም ሌላ ጥያቄ ሊሆን ይችላል። ግን ግን ከ ስዬ አብርሃም በላይ ኢህአዲግ ነኝ ማለት ትንሽ ይከብዳል።እርሱ ቢያንስ የ አምባገነንነትን አደጋ  ነግሮናል።ዳኛ ብርቱካንም ስዬ አብርሃን በዳኛነቷ ነጻ ለቃ  ተፈትናበታለች። አውንግ ሳንሱኪ ደግሞ የ አምባገነኖችን ሰው በላነት  ለዓለም ህዝብ አሳስባለች። ጆሮ ያለው ይስማ!

ለመሆኑ የ አምባገነንነት ዲግሪው ስንት ነው?

በዛሬው የ ኦስሎ የ አውንግ ሳንሱኪ አቀባበል እና ንግግር እነሆ:-


ዛሬ 16/6/2012 ዓ.ም .እኤአ  በኦስሎ የ አውንግ ሳንሱኪ አቀባበል እና ንግግር

ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ

Thursday, June 7, 2012

''የዛሬ 21 ዓመት እንዲህ ነበር ዛሬ ግን ... ሲባል መስማት ይህ ትውልድ ከምር ሰልችቶታል።'' ትውልዱ ''የይሁዳ አንበሳ ለ ክርስቶስ የተሰጠ ስም ነው።''ልዑል ኤርምያስ ሳህለ ስላሴ

ኢቲቪ አሁንም ድረስ ዜና አንባቢው ጀርባ ያለው ማስታወቅያ ግንቦት ሃያ የሚለው መሆኑ ምን ያህል ችክ ያለ ፕሮፓጋንዳ መጠመዱን ያሳያል- ኢህአዲግ።ጀግና ከተጠራ በእርስ በርስ ጦርነት ከ ወንድሞቹ ጋር የተዋጋው ሰራዊት ይነገርባታል።ልማት ከተባለ ከ 21 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ የምትባል ሃገር ያልነበረች ይመስል'' ከ ግንቦት እስከ ግንቦት የዛሬ 21 ዓመት እንዲህ ነበር ዛሬ ግን ... እየተባለ መስማት ይህ ትውልድ ከምር ሰልችቶታል።
ሃገራችን የታሪክ ዳራ፣ስር፣መነሻ ያላት ሃገር ነች።በ ሃያ አንድ አመት መወሰን ''ከ አፍንጫ እስከ አፍ'' የማሰብ ድንክዬ አስተሳሰብ ነው። አዲሱ ትውልድን ዛሬ ማታለል አይቻልም።ዘመኑ የመረጃ ዘመን ነውና።
ልዑል ኤርምያስ ሳህለስላሴ የ አጼ ሃይለስላሴ የ ልጅ ልጅ በ አሜሪካው ኮንግረስ መጻህፍት ቤት ተገኝተው አድርገውት የነበረውን ንግግር ለ አሁኑ ትውልድ ከ 21  አመት በላይ ስለነበረችው ሃገራችን ታሪክ በሚገባ እንዲረዳ እንደሚያደርገው እገነዘባለሁ። በእዚህ አጋጣሚ አንዳንዶቻችን የምናውቃቸውን ታሪኮች አዲሱ ትውልድ በ 21 ዓመት ታሪክ ትረካ ስለተጎዳ ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ ታሪክን  ማስተላለፍ መቻል ሃላፊነት መሆኑን ልብ እንድትሉልኝ እጠይቃለሁ።
የጉዳያችን ብሎግ ጦማሪ የንጉሳዊ አስተዳደር ናፋቂ ባይሆንም እንደ እዚህ አይነት ታሪኮች (የቀደመው የ ሃገራችን የ ዘውድ ታሪክ) ከህብረተሰቡ ታሪካዊ እና ሞራላዊ ጉዳዮች ጋር የነበረው ተዛምዶ በተመለከተ  ከ ሶስት አቅጣጫዎች ሲታፈኑ ታዝቧል።
1/ በንጉሱ ስርዓት ላይ በተነሳው አብዮት የተሳተፉ የ ''ያ ትውልድ'' አባላት

 በወቅቱ የ ንጉሱ ስርዓት የነበሩበት የ ብዝበዛ አይነት፣ግራ የተጋባ አካሂያድ እና ዓለም ዓቀፋዊ ክስተቶች ሁኔታዎችን ከሚገባው በላይ ቢያፋጥኑትም ታሪክ ግን ያውም ከ ሶስት ሺህ ዓመት በላይ የ ኢትዮጵያ አካል የነበረው የዘውድ ስርዓትን ቢያንስ በቅርስነት እንዳይወሳ መጣር ተገቢ አለመሆኑን ማንም አይስተውም።ይህ ግን በ ያ ትውልድ አባላት እና ተዋናይ ዘንድ 'ክብድ' ሲላቸው ይታያል::
2/  የ ደርግ ስርዓት


 በ 1953ዓም በ እነ መንግስቱ ንዋይ ተነስቶ የነበረው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ በኋላ'' የሃገሬ ጉዳይ በጣም ስላሳሰበኝ ጻፍኩት'' ያሉት የ' ፍቅር እስከ መቃብር' መጽሃፍ ደራሲ እና ዲፕሎማት ሃዲስ አለማየሁ ''ኢትዮጵያ ምን አይነት አስተዳደር ያስፈልጋታል?'' በሚለው መጽሃፋቸው ላይ (መጽሃፉ የተጻፈው ገና የመጀመርያው የ ኢትዮጵያ አብዮት ሳይካሄድ ነበር) የደርግ መንግስት ሳይመጣ ሃገራችን ''ያሉዋት አማራጮች ሁለት ናቸው''  ።ብለዋል እነርሱም'' የ ምስራቁ አይነት አምባገነን መንግስት አልያም የ ምዕራቡ አይነት የ ንጉሳዊ ዲሞክራሲ'' መሆናቸውን ካወሱ በኋላ'' የ አምባገነን መንግስት ከመጣ አያምጣው እንጂ የህዝቡን ሃብት ለ ጆሮ ጠቢ ያባክናል፣የሃገሩን ሃብት ከልማት ይልቅ ለእርስ በርስ ውግያ ያውለዋል፣ስራው ሁሉ ስልጣን ማስጠበቅ ስለሚሆን ሃገራችን በ ዘር ፖለቲካ እንዳትገባ ያሰጋታል።ነገር ግን የ አምባገነን መንግስት በየትኛውም አለም እንደታየው ካለ ውጊያ ስልጣን ሊለቅ አይችልም ''ብለው ያስቀምጣሉ።
ደራሲ እና ዲፕሎማት ሃዲስ ዓለማየሁ ''ከሃገራችን ታሪካዊ ክስተት አንጻር የሚያስፈልጋት የመንግስት አስተዳደር ዘውዱ ለይስሙላ እንደ ሰንደቅ ዓላማ እና የ ሃገሪቱ አንድነት ተምሳሌነት ብቻ እንዲኖር አስተዳደሩ ግን በ እንግሊዝ እና በ ብዙ የ አውሮፓ ሃገራት እንዳለው ትክክለኛ ዲሞራስያዊ ምርጫ እያደረገ የምክር ቤቱንም ሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩን እንዲመርጥ ቢደረግ ይበጃል።እዚህ ላይም የህግ ማውጣቱን እና የመቆጣጠር ስራ የ ምክር ቤቱ ሆኖ ዘውዱ የቀረበለትን ማጽደቅ ብቻ ይሆናል ስራው።''የ ዘውዱን አስፈላጊነት ሃዲስ አለማየሁ ሲያስገነዝቡ'' ኢትዮዽያ ከ ክርስቶስ ልደት በፊት በታሪክ፣በእምነት እና የ አንድነት ተምሳሌት ዘውድ ወርውራ ከጣለች ትልቅ የታሪክ እና የ ህልውና ቀውስ ውስጥ እንደምትገባ'' በማሳሰብ በወቅቱ የ ማኦኢዝምም ሆነ የ ራሻን አስተሳሰብ ይዞ የተነሳውን ትውልድ ሞግተዋል።
ያሉት አልቀረም ደርግም በተነሳ በ ቀናት ውስጥ ስልሳዎቹን የ ሃገሪቱን አሻራዎች ያለፍርድ ገደለ።በ እዚህ ወቅት የተገደሉት ሰዎች ብቻ ሳይሆን ኢትዮዽያ በ አካል ነው የተገደለችው። ከሞቱት ውስጥ የ ኢንዱስትሪውን ዕቅድ የያዘ አለ፣የሃገሪቱን የ እርሻ መንገድ ሲተልም የነበረ አለ፣ የባህር ሃይልን፣የምድር ጦርን ሚስጥር እንደያዘ እንደዋዛ የቀረ አለ። ያን ጊዜ የ ኢትዮዽያ ጠላቶች እንዴት ጮቤ እረግጠው ይሆን? እንደ ሃገር የሚፈርዋት ሁሉ የፈሩት ፋይል በ ጥይት አረር ዝም ሲልላቸው። ከ እዛማ ምን አለ 'ለ ሃገሩ እንግዳ ለ ህዝቡ ባዳ' እንዲሉ ደርግ እንዳዲስ ታሪክ ሊጀምር ተነሳ
3/  የ ኢህአዲግ መንግስት

ኢህአዲግ ገና በዱር እያለ ከሚያስተላልፈው የራድዮ ፕሮግራም ውስጥ የኢትዮዽያን  ያለፉ ታሪኮች ማጥቆር አንዱ አላማው ነበር። አሜሪካን ሃገር' በዘር የሚከፋፍል ፖለቲካ አንፈልግም' ብለው በደርግ ዘመን ይቃወሙ የነበሩትን እነ ተፈራ ዋልዋ' የ ነፍጠኛው እና ያለፉት ስርዓቶች ናፋቂዎች' እያሉ ስም ይለጥፉላቸው ነበር።ይህ ብቻ አይደለም ኢህአዲግ ስልጣን ከያዘ በኋላ የ አጼ ሃይለስላሴን አስከሬን ሲወጣ ''በ አለም ዙርያ ያሉ አድናቂዎቻቸውን ጠርተን በክብር የቀብር ስነስርዓት ይከናወን ይህ ለ ሃገራችን ትልቅ ዲፕሎማሲ ነው ኢህአዲግም ያስከብረዋል እንጂ አያስነቅፈውም'' ተብሎ በተደጋጋሚ ሲነገር  ''ንጉሱ የሚቀበሩት ከ ንግስና መውረዳቸው በደርግ ከተነገረ በኋላ ስለሆነ አሁን እንደ ተራ ሰው ነው የሚታዩት'' እንደ ኢህአዲጉ አውራ አነጋገር ተብሎ ከመንግስት ባለስልጣን  አንድም ዝር ሳይል ተከወነ። አሁንም ግን በሚገባ ክብር ባለመከወኑ ወደፊት ቀን ይጠብቃል እንጂ በክብር ይከወናል የሚሉትን ሳንዘነጋ።የ እዚህ ብሎግ ጸሃፊ በወቅቱ ስለ እዚሁ የ ኢህአዲግ በ አስከሬን ላይ ሳይቀር ለያዘው ቂም'' የ ቢቢሲ ፎከስ ኦን አፍሪካ'' ፕሮግራም ከ አዲስ አበባ በዘገበው ዘገባ ላይ በተሰነዘረው አስተያየት ''ዲፕሎማሲ ያልገባው የ ንጉሱን ለ ኢትዮዽያ መልካም ገጽታ ያላቸውን ክብር ያላገናዘበ  መንግስት'' ተብሎ መቅረቡን ያስታውሳል።ይህ ብቻ አይደለም በቅርቡ በ አፍሪካ ህብረት አዲሱ ህንጻ ላይ ብዙ የ አፍሪካ ምሁራን ለምን የ አጼ ሃይለስላሴ ሃውልት እንዲሰራ ኢትዮዽያ አልጠየቀችም ሲባሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ'' 'ፓን አፍሪካን' ሃሳብ በማቀንቀን የ ጋናው ኩዋሚ ንኩማ ከ ንጉሱ ይበልጣሉ::'' በማለት የይበልጣል ያንሳል ሂሳብ ውስጥ ገቡ።በየትኛውም የ ታሪክ መለክያ ግን ''ፓን አፍሪካ'' ማለት ንጉሱ መሆናቸውን እነ ዶክተር ያቆብ ጭምር በ ምርምር ጽሁፋቸውን በማገናዘብ ለ አሜሪካ ሬድዮ ከገለጹ ገና አንድ አመት ያልሞላው ታሪክ ነው።

ይህንን ሁሉ እያሰብን ነው እንግዲህ በ ዓለም በግዙፍነቱ በሚታወቀው የ አሜሪካው ኮንግረስ ላይብረሪ ልዑል ኤርምያስ ሳህለስላሴን ንግ ግር የምናየው።እኛ የ አሁኑ ትውልዶች።እነሆ፦



   ''የይሁዳ አንበሳ ለ ክርስቶስ የተሰጠ ስም ነው።''ልዑል ኤርምያስ ሳህለ ስላሴ


ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ

Regarding copyright I could read from Congress library the following:-
With few exceptions, the Library of Congress does not own copyright in the materials in its collections and does not grant or deny permission to use the content mounted on its website. Responsibility for making an independent legal assessment of an item from the Library’s collections and for securing any necessary permissions rests with persons desiring to use the item. To the greatest extent possible, the Library attempts to provide any known rights information about its collections. Such information can be found in the “Copyright and Other Restrictions” statements on each American Memory online collection homepage. If the image is not part of the American Memory collections, contact the Library custodial division to which the image is credited. Bibliographic records and finding aids available in each custodial division include information that may assist in assessing the copyright status. Search our catalogs through the Library's Online Catalog.

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።