ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, August 31, 2013

የሰማያዊ ፓርቲ የሽብር ተግባር በፌድራል ፖሊስ ተፈፀመበት

 ዛሬ ነሐሴ 25/2005 ዓም በአዲስ አበባ አራት ኪሎ (ግንፍሌ አካባቢ) የሚገኘው  የሰማያዊ ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት የእገታ-ሽብር ተግባር እንደተፈፀመበት ተገለፀ።ፓርቲው ቀደም ብሎ ለነሐሴ 26/2005ዓም ፍፁም ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርግ ለመንግስት ከሶስት ወር በፊት ማስታወቁ ይታወቃል።ከቀናት በኃላ መንግስት ቀደም ብሎ በሰማያዊ ፓርቲ እንዲያውቀው የተደረገውን ፍፁም ሰላማዊ ሰልፍ ማስታወሻ ወደጎን በማለት ''የሃይማኖት ተቁዋማት የጋራ ጉባኤ'' የጠራው ሰልፍ ቅድሚያ እንደተሰጠው የሚገልፅ መግለጫ ዛሬ ነሐሴ 25/2005 ዓም በቀኑ የኢቲቪ ዜና ላይ አስታወቀ።በእዚሁ ዜና ላይ  የአዲስ አበባ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር በመጀመርያ የሰማያዊ ፓርቲን ፍፁም ሰላማዊ ሰልፍ መጠየቁን ''እንዳልሰሙ'' ከገለፁ በኃላ ቆይተው የተናገሩትን እረስተውት'' የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮችን አነጋግረን ነበር'' ሲሉ ተደምጠዋል። 

የአዲስ አበባ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር መግለጫውን በሰጡ በሰአታት ውስጥ ከአንድ መቶ  ያላነሱ የፓርቲው አባላት ባሉበት የሰማያዊ ፓርቲ ዋና ቢሮ ግቢውን እና በሩን ጥሰው የገቡ ከባድ መሳርያ የታጠቁ የፈድራል ፖሊስ አባላት የእገታ-ሽብር ፈፀሙ። ድርጊቱን ሽብር የሚያሰኙት ብዙ ምክንያቶች ቢኖሩም በግቢው ውስጥ የነበሩት የፓርቲው አባላት ከትጥቅ ትግል ይልቅ ፍፁም ሰላማዊ ትግል ለሀገራችን ይበጃል ያሉ ከመፈክር እና ብእር ሌላ ምንም መሳርያ የሌላቸው ንፁሃን ኢትዮጵያውያን ላይ የተፈፀመ የእገታ ተግባር በመሆኑ እና የፈድራል ፖሊስ ግቢውን ለመውረር የፍርድቤት ትእዛዝ አለመያዙ ነው።

የእዚህ አይነቱ የማሸበር ተግባር በመንግሥትነት ደረጃ ባሉ ፖሊሶች መፈፀሙ እጅግ አሳዛኝ ብቻ ሳይሆን ''ተከታታይ ትውልድ ለሰላማዊ ትግል አልታደለምን?'' የሚለውን ጥያቄ ይጭራል። ከ 1997 ዓም ወዲህ መንግስት ስምንት አመታት ሙሉ የሰላማዊ ትግልን የማክበር እና የማስከበር ልምድ ለማዳበር አለመቻሉ በእራሱ የሰላማዊ ትግል አስፈላጊነት እና አላስፈላጊነት ላይ ትልቅ እና ወሳኝ ጥያቄ መጫሩ እንደማይቀር ብዙዎች ይስማማሉ።

ምናልባትም በሰማያዊ ፓርቲ ላይ መንግስት የሚያሳየው ''አክብሮት'' ወይንም ''ንቀት'' የኢትዮጵያን የፖለቲካ የትግል አቅጣጫ ወሳኝ ደረጃ ላይ የሚያደርሰው ለመሆኑ መጠራጠር አይቻልም። ምክንያቱም ይህ ትውልድ ተመሳሳይ የእገታ-ሽብር ከተፈፀመበት ወዳልወደደው ግን ብቸኛው አማራጭ ቢሄድ ለፍርድ የሚቻኮል እንደማይኖር እርግጠኛ መሆን ይቻላል። ምርጫው አሁንም የወያኔ ባለስልጣናት ነው።ትውልዱን እያሸበሩ መኖር አልያም በቅንነት የትውልዱን ጥያቄ መስማት።


የሰማያዊ ፓርቲ የማህበራዊ መገናኛ ድህረገፅ (ፌስ ቡክ) ላይ ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ የተለቀቀው መረጃን ከእዚህ በታች ይመልከቱ።


በአዲስ አበባ የሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ አንድ ሰዓት ላይ የተለቀቀው የሰማያዊ ፓርቲ የማህበራዊ መገናኛ ድህረገፅ (ፌስ ቡክ) ማስታወቂያ እንዲህ ይነበባል -

''በአሁኑ ሰዓት የሰማያዊ ፓርቲ ቢሮ በታጠቁ ፌደራል ፖሊሶች ተከቧል
በፓርቲው ጽ/ቤት ውስጥ ወደ 100 የሚጠጉ አባላት የሚገኙ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ወደ 60 የሚሆኔ ከባድ መሳሪያ የታጠቁ የፌደራል ፖሊስ በግቢው ውስጥ ይገኛል ማንም መውጣትም ሆነ መግባት አይችልም፡፡ ያለውን ሁኔታ እየተከታተልን እንገልጽላችኋለን''

በአዲስ አበባ የሰዓት አቆጣጠር ከምሽቱ ሶስት ሰዓት ላይ የተለቀቀው የሰማያዊ ፓርቲ የማህበራዊ መገናኛ ድህረገፅ (ፌስ ቡክ) ማስታወቂያ እንዲህ ይነበባል-

''በአሁኑ ወቅት በግምት ወደ 100 የሚጠጉ የፓርቲው አመራሮች የምክርቤት አባላት እንዲሁም ደጋፊዎችና አባላት በተሽከርካሪ ተጭነው ለጊዜው ወዳልታወቀ ቦታ ተወስደዋል፡፡ የድረጅቱን ቀጣይ አቋምና እንቅስቃሴ በሂደት እናሳውቃለን''

1/ የኢሳት ሰበር ዜና 


2/ ከሽብሩ በኃላ የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ከ ኢትዮጵያ የመወያያ መድረክ ( ECADF) ጋር ያደረጉት ቃለመጠይቅ 


Friday, August 30, 2013

ሽብር ምንድነው? አሸባሪስ ማነው? ታሪካዊ የት-መጣነቱ እና በዛሬዋ ኢትዮጵያ ያለው ገፅታ (የኢሳት ልዩ ትንታኔ-ቪድዮ)

ከስር ያለው ቪድዮ ካልተከፈተልዎ ይህንን ሊንክ ይጫኑ -  http://ethsat.com/video/esat-news-analysis-30-august-2013/  




Wednesday, August 28, 2013

ኢትዮጵያውያን በእስራኤል ማሸነፋቸውን ቀጥለዋል!


በ2011 ዓም  እኤቆጣጠር  ኢትዮጵያዊቷ ሃጊት የመላዋ እስራኤል ''አይዶል'' ሙዚቃ የአመቱ አሸናፊ ሆነች።

በ 2013 ዓም እኤቆጣጠር  ኢትዮጵያዊቷ ይታይሽ የዓመቱ ''ወይዘሪት እስራኤል'' የቁንጅና ውድድር አሸናፊ ሆነች።

ዛሬ ደግሞ የ 2013  እኤቆጣጠር  የእስራኤል ታዋቂ ቴሌቭዥን ጣቢያ ያዘጋጀው ''የቢግ ብራዘርስ'' ውድድር ከጠቅላላ ተወዳዳሪዎች  ኢትዮጵያዊቷ ትሁኔ ሮቤል አሸናፊ ሆና ከ ሁለት መቶ ሺህ የአሜሪካ ዶላር በላይ አሸናፊ ሆናለች።
የትሁኔን የድል ዜና  ከእዚህ በታች ባለው ፊልም ላይ ይመልከቱ።

ኢትዮጵያዊቷ ትሁኔ የእስራኤልን ''ቢግ ብራዘርስ'' አሸናፊ መሆኗ ሲነገራት



Monday, August 26, 2013

አቶ መለስ ''የአረንጓዴ ልማት'' እና ''የልማታዊ መንግስት'' ፅንሰ ሃሳቦች አመንጪ አይደሉም



አንዳንድ ጊዜ ትምህርት ሰውን አይቀይርምን? የሚል ጥያቄ ብጠይቅ ከሞኝ እንዳትቆጥሩኝ ስጋት አለኝ።ምክንያቱም ትምህርት ሰውን ማነፁ ብቻ ሳይሆን የማመዛዘን እና ትክክለኛውን ነገር ከበቂ ማስረጃ ጋር የማቅረብ ብሎም ሃሳብን እገሌን ላስደስት ከሚል ከንቱ አስተሳሰብ የማራቅ ሁሉ ክህሎትን ያላብሳልና።አሁን ያለንበት ዘመን የመረጃ ዘመን ነው። አሁን ያለው ትውልድ ደግሞ መረጃ የማግኘት ውሱንነት ቢገጥመው መረጃን ሙሉ በሙሉ ማፈን የማይቻልበት ጊዜ ነውና ቢያንስ የተጋነነ መረጃን ከትክክለኛው ለመለየት ችግር የለበትም።

ይህንን ለማለት ያነሳሳኝ ጉዳይ በአቶ መለስ ላይ የሃገር ቤት የመገናኛ ብዙሃን እና እጅግ ጥቂት ምሁራን የሚነግሩን ፈፅሞ ከእውነታው የራቁ ጉዳዮች ናቸው። አንዳንዶቹን ጉዳዮች እንድያውም እራሳቸው አቶ መለስ በሕይወት ቢኖሩ ኖሮ የማይቀበሉት ሊሆን ይችላል።በእዚህ ፅሁፍ ላይ ላነሳው የፈለኩት ጉዳይ በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃን ደጋግሞ የሚነገረው ''አቶ መለስ የአረንጓዴ ልማት እና የልማታዊ መንግስት መርህ አመንጪ ናቸው'' የሚለውን ንግግር ነው።አቶ መለስ ግን የሁለቱም ፅንሰ ሃሳቦች አመንጪ ወይም ፈጣሪ አይደሉም።የእዚህ አይነቱ አባባል ሁለት መሰረታዊ ምክንያቶችን መነሻቸውን ያደርጋሉ።አንደኛው የአቶ መለስን ስብዕና ከሚገባው በላይ ለመካብ ከሚደረግ ጉጉት ሲሆን ሁለተኛው ግን ''ነገር ሲደጋገም ወደ መታመንነት ይቀየራል'' ከሚል አስተሳሰብ ለመረጃ የራቀው ሕዝብ አምኖ ይቀበላል ከሚል አስተሳሰብ ነው።ሆኖም ግን ማናቸውም የስብዕና ግንባታ ሥራ ሚዛናዊ ቢሆን ምን ያህል ባማረበት ነበር።

አቶ መለስ ከላይ የተጠቀሱት ሁለቱ ''ግኝት'' ተብለው የቀረቡት ''የአረንጓዴ ልማት እና የልማታዊ መንግስት መርህ'' አግኚ ሆነው ቢሆን ኖሮ እንደ ኢትዮጵያዊነት ሁላችንም ደስ ባለን ነበር።ኢቲቪ እንደሚነግረን አለመሆናቸው ግን የሚታይ ሀቅ ነው።አለማችን በልማት ዙርያ ያጠነጠኑ ጥናቶች ላይ ማተኮር ከጀመረች ሰነባብታለች።ልማት ከሚለው ፅንሰ ሃሳብ በፊት የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጡት የምጣኔ ሀብት እድገት(growth) ከቁጥር አንፃር መለካት የሚቻል ብቻ  ነበር። ይህም  የአንዲት ሀገር ማደግ የሚለካው ከአጠቃላይ አመታዊ ምርት አንፃር ብቻ ነበር።ሆኖም በተለይ ከ1970ዎቹ ወዲህ የልማት ፅንሰ ሃሳብ ብዙ ትኩረትን እየያዘ መጣ።በተለይ የሀገሮች አጠቃላይ ምርትን በማሳየት ብቻ የሀገርን እድገት አለማመላከቱ ከተረጋገጠበትመንገዶች ውስጥ አንዳድንዶቹ  አጠቃላይ ምርቱን ማን አመረተው? ምን ያክሉ ሕዝብ ከምርቱ ተጠቃሚ ነው? የእያንዳንዱ ግለሰብ የዓመት ገቢ ስንት ነው? የጤና፣የትምህርት፣የገበያ ወዘተ ዕድል የሚያገኘው ሕዝብ ስንት ነው? ሃሳብን የመግለፅ የነፃነት ደረጃ ምን ያህል ነው? ወዘተ የሚሉትን መሰረታዊ ጥያቄዎች መመለስ ያለመቻሉ እውነታ ነው።

አቶ መለስ በምክር ቤት ስብሰባዎች ላይ በአብዛኛው እድገትን የሚተረጉሙት ከአጠቃላይ ምርት አንፃር ብቻ መሆኑ እራሱ በዘመኑ የልማት ጠበብት አንፃርም ትልቅ ተግዳሮት እንዳለበት ልብ ለማለት ይቻላል።የሀገሪቱን የንግድ ዘርፍ እንደ ኢፈርት የመሳሰሉ የኢህአዲግ ድርጅቶች የአንበሳውን ድርሻ ይዘው ባለበት ምጣኔ ሀብት ውስጥ የአጠቃላይ ሃገራዊ ምርትን በማውሳት የሀገሪቱን ዜጋ አጠቃላይ እድገት እና ልማት ያሳያል ማለት በእራሱ በስህተት የተሞላ መሆኑን ለመገንዘብ ብዙም ምርምር አይጠይቅም።

በተለያየ ጊዜ በዘርፉ ባለሙያዎችም ሆነ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ምርምር ከተደረገበት በኃላ  አዳዲሶቹ የልማት ፅንሰ ሃሳቦች ወደ አለምአቀፍ መርህነት የመቀየራቸው ዕድል ከፍተኛ ነው።ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው የአንዲት ሃገርን መሻሻል በትክክል የሚለካው  የእድገት (growth) አስተሳሰብን  በልማት (development) አስተሳሰብ መቀየሩ ብቸኛ አማራጭ መሆኑን ካስተዋወቁት ውስጥ የተባበሩት መንግሥታት የልማት ፕሮግራም ድርጅት(UNDP)  አንዱ እና ዋናው ነው።የአረንጓዴ ልማት የወቅቱ የአለማችን የልማት ችግር መፍትሄ መሆኑ በተባበሩት መንግሥታት ዋና ፀሐፊ እና ሥራ አስፈፃሚ ቦርድ ደረጃ የታመነበት ግኝት ለመሆኑ የተባበሩት መንግሥታት አካባቢ ጥበቃ መርሃ ግብር (UNEP) በድህረ-ገፁ ላይ እንዲህ ይገልፀዋል-
''Designed as a timely and appropriate policy response to the economic crisis, the (Global Green New Deal)
 GGND proposal was an early output from the United Nations’ Green Economy Initiative. This initiative, coordinated by UNEP, was one of the nine Joint Crisis Initiatives undertaken by the Secretary-General of the UN and his Chief Executives Board in response to the 2008 economic and financial crisis.''www.unep.org/greeneconomy/Portals/88/documents/ger/GER_1_Introduction.pdf,page 15.

የአቶ መለስ ግኝት ነው የተባለው  ''የአረንጓዴ ልማት እና የልማታዊ መንግስት መርህ'' አቶ መለስ ስለጉዳዩ ሳያወሱ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ብዙ የለፉበት እና በመጨረሻም በአለም አቀፍ ድርጅቶችም ሆነ በከፍተኛ የምርምር ተቋማት እውቅና የተቸራቸው ሃሳቦች ናቸው። ስለእዚህ በቂ ማስረጃ ማቅረብ ከተቻለ ''አቶ መለስ የአረንጓዴ ልማት እና የልማታዊ መንግስት መርሆዎችን ይደግፉ ነበር'' ማለት ማንን ገደለ? ''የመርሆዎቹ አስገኚ እና ለአፍሪካ ያስተዋወቁ ናቸው'' ማለት ግን ገሃዱ አለም የደከመበትን ሥራ ማጣጣል አይደለም ወይ?

በመጨረሻም ለናሙናነት የአረንጓዴ ልማት እና የልማታዊ መንግስት ሃሳቦች በተባበሩት መንግሥታት አካባቢ ጥበቃ መርሃግብር (United Nations Environment Programme) ''በአረንጓዴ ልማት'' ላይ የማንቸስተር ዩንቨርስቲ ደግሞ በ''ልማታዊ መንግስት''  ምንነት እና የት-መጣነት ላይ የሰጡትን ማብራርያ ከእዚህ በታች ይመልከቱ።

የአረንጓዴ ልማትን በተመለከተ 

''የአረንጓዴ ልማት የምጣኔ ሀብት ሽግግር ደረጃዎች'' በሚል አርእስት ስር የተባበሩት መንግሥታት የአካባቢ ጥበቃ መርሃ ግብር  (United Nations Environment Programme) 2011 ሪፖርት የአረንጓዴ ልማት ፅንሰ ሃሳብ ብቸኛ የአለማችን አማራጭ የእድገት መንገድ መሆኑን ምሁራኑ ማሳሰባቸውን ያመላክታል። http://www.unep.org/greeneconomy/Portals/88/documents/ger/GER_1_Introduction.pdf, page 14

''....This recent interest in a green economy has been intensified by widespread disillusionment with our prevailing economic paradigm, emanating from the many concurrent and recent crises – particularly the recession of 2008-2009. At the same time, increasing evidence is pointing to an alternative paradigm, in which increased wealth does not lead to growing environmental risks, ecological scarcities and social disparities.
Transitioning to a green economy has sound economic and social justification. As this report demonstrates, there is a strong case for governments as well as the private sector to engage in this economic transformation. For governments, this transition would involve leveling the playing field for greener products by phasing out harmful subsidies, reforming policies and incentives, strengthening market infrastructure, introducing new market-based mechanisms, redirecting public investment, and greening public procurement. For the private sector, this transition would involve responding to these policy reforms and incentives through increased financing and investment, as well as building skills and innovation capacities to take advantage of opportunities arising from a green economy. ''

page 15  '' ....UNEP’s green economy report, Towards a Green Economy,aims to debunk several myths and misconceptions about “greening” the global economy, and provides timely and practical guidance to policy makers on what reforms they need to unlock the productive and employment potential of a green economy.Perhaps the most prevalent myth is that there is an inescapable trade-off between environmental sustainability and economic progress. There is now substantial evidence that the greening of economies neither inhibits wealth creation nor employment opportunities. To the contrary, many green sectors provide significant opportunities for investment, growth, and jobs. For this to occur, however, new enabling conditions are required to promote such investments in the transition to a green economy, which in turn calls for urgent action by policy makers.
A second myth is that a green economy is a luxury only wealthy countries can afford, or worse, a ruse to restrain development and perpetuate poverty in developing countries. Contrary to this perception, numerous examples of greening transitions can be found in the developing world, which should be replicated elsewhere. Towards a Green Economy brings some of these examples to light and highlights their scope for wider application.
UNEP’s work on the green economy raised the visibility of this concept in 2008, particularly through a call for a Global Green New Deal (GGND). The GGND recommended a package of public investments and complementary policy and pricing reforms aimed at kick-starting a transition to a green economy, while reinvigorating economies and jobs and addressing persistent poverty (Barbier 2010a). Designed as a timely and appropriate policy response to the economic crisis, the GGND proposal was an early output from the United Nations’ Green Economy Initiative. This initiative, coordinated by UNEP, was one of the nine Joint Crisis Initiatives undertaken by the Secretary-General of the UN and his Chief Executives Board in response to the 2008 economic and financial crisis.''

ልማታዊ መንግስትን በተመለከተ

''ልማታዊ መንግሥታት'' በሚል ርዕስ ስር በየካቲት 2012 በማንቸስተር ዩንቨርስቲ በሚታገዘው (ESID) የምርምር ማዕከል ''ሊትረቸር ሪቪው'' ላይ  ፅንሰ ሃሳቡ ቀደም ብሎ በተለያየ ምሁራን ሲጠና የነበረ መሆኑን ይጠቁማል።

''....One of the central debates around developmental states has focused on the controversy over how and, indeed if, states should intervene in the market, and what role the state should play in development (White and Wade 1988). Johnson (1999) recalls the hostility with which his notion of a developmental state was received by Anglo-American economists (p.34) and discusses how the Japanese experience he described was ‘inconvenient’ for both sides of the ideological cold war divide (p.49). These debates have gradually shifted to an acceptance of the significance of the states’ role, but the nature of this role continues to be argued over (Kohli 1994, p.1269). '' 


ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ



Thursday, August 22, 2013

የፆመ-ፍልሰታ መፈታት ሀዘኔ እና የሀገሬ እድገት ጉዳይ

 

ዛሬ ነሐሴ 16/2005 ዓም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክርስትያን ተከታዮች ዘንድ ፆመ ፍልሰታ የተፈታበት ቀን ነው።ይህ ፆም በሀገራችን በክረምት ወራት እንደመዋሉ ተማሪ እና መምህራን በእረፍት ላይ ያሉበት፣ ወላጆች ልጆቻቸውን ይዘው በቤተክርስቲያን የሚገኙበት ባጠቃላይ እጅግ ብዛት ያለው ምዕመን በተለይ ታዳጊ ወጣቶች እና ወጣቶችም የሚታደሙበት ነው።የፆሙ መፈታት አንዱ መታወቅያው ታድያ በቤተክርስቲያን አለምላሚ ተበለው ከሚጠሩት ምግቦች እንደ ስጋ፣እንቁላል፣ወተት የመሳሰሉት ምግቦችን ለመመገብ መቻሉ ነው።

ለመሆኑ ስንቶቻችን ምን ያህል ሕዝብ ፆሙ ሲፈታ ከላይ በተጠቀሱት ምግቦች ፆሙን በአግባቡ የመፍታት አቅም አለው? ብለን በስሌት አስበነው እናውቃለን? ሀገሪቱ እያደገች ነው በተባለበት በእዚህ ዘመን የድህነት ደረጃው ምን ላይ እንደሆነ እንቅውቀዋለን? ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ብዙ ''አንጀት የሚበሉ'' ነገሮችን በፆም ፍቺ ወቅት መመልከት የተለመደ እየሆነ መጥቷል።ሲፆም ከከረመው ክርስቲያን ስንቱ አንድ ኪሎ ስጋ የመግዛት አቅም አለው?'' ብሎ መጠየቅ ተገቢ እና ሰብአዊ ጥያቄ ነው።

አስተዋዩ መምህር እና ታዳጊ ህፃናቱ 


ከጥቂት አመታት በፊት  በአንድ በሀገራችን በሚታተም ጋዜጣ ላይ የወጣ አንድ ፅሁፍ እጅግ አስተማሪ እንደነበር አስታውሳለሁ።ጋዜጣው በአዲስ አበባ የሚገኝ አንድ የቱጃሮች እና የባለስልጣናት ልጆች የሚማሩበት ትምህርት ቤት የ አምስተኛ ክፍል ተማሪዎች በመምህራቸው አነሳሽነት ከእነርሱ የኑሮ ደረጃ በታች ስላሉት ሕፃናት እንዲማሩ በአዲስ አበባ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን አካባቢ የሚኖሩ የምስኪኖችን መንደር እንዲጎበኙ አደረገ።ከጉብኝቱ በኃላ ታድያ ተማሪዎቹ  ለመምህራቸው የተመለከቱትን እንዲፅፉ በተነገራቸው መሰረት በእንግሊዝኛ ፃፉ።እነኚሁ እድሚያቸው ከአስራ ሁለት የማይዘለው ተማሪዎች ያሉትን  ለእዚሁ ጋዜጣ ከመግቢያ ፅሁፍ ጋር ላከው።በተለይ የታዳጊ ሕፃናቱ ፅሁፍ ቀጥታ ፎቶ ተደርጎ የቀረበ ነበር እና አሳዛኝ ነበር።መምህሩ በመግቢያው ላይ ተማሪዎቹ ከጉብኝቱ ከተመለሱ በኃላ እጅግ የመንፈስ መረበሽ መመልከቱን እና በሕይወታቸው አይተውት የማያውቁት መሆኑን እንደነገሩት ከእዚህ በኃላ የተቸገሩትን ለመርዳት አባት እና እናታቸውን ይዘው መምጣት እንደሚፈልጉ እንደገለፁለት ያትታል።

ታዳጊ ሕፃናቱ ከፃፉት ውስጥ ቃል በቃል ባይሆንም የሚከተሉት አረፍተ ነገሮችን አስታውሳለሁ።

የመጀመርያዋ ታዳጊ ሕፃን- 

'' እኔ ያሳዘነኝ የሕፃን ትግስት(ስሙ ለምሳሌ የተሰጠ ነው) አኗኗር ነው። እናቷ ጠላ በመሸጥ ትተዳደራለች።ከርሷ ጋር አንድ አልጋ በተዘረጋባት ክፍል ውስጥ አምስት ሆነው ይኖራሉ።አልጋው  ቀን ቀን  ልጆቹ  እንደወንበር የሚቀመጡበት እና ማታ የቤት ስራ የሚሰሩበት ነው።አልጋው በመጋረጃ በመጋረዱ ከመጋረጃ ውጭ ያሉ ጠላ ሊጠጡ ለሚመጡ ሰዎች አይታዩም።ጠላ የሚጠጡት ሰዎች ይጮሃሉ።እናም ትግስት ከቤት ወጥታ በመንገድ መብራት ድንጋይ ላይ ቁጭ ብላ የቤት ስራዋን እንደምትሰራ ነገረችኝ።እማዬን ኪችን ያለው ወንበር ለትግስት እንድትሰጣት ነግርያታለሁ።ትግስትን እንደምደውልላት ነግርያታለሁ።የጎረበታቸውን ስልክ ወስጃለሁ።''

ሁለተኛዋ ታዳጊ ሕፃን-

''  ኃይሉ እና ወንድሞቹ ቤታቸው ትንሽዬ ነች።ምሳ የት እንደሚበሉ ኃይሉን ጠየቅሁት።እዝያው እቆምኩበት በሩ ላይ ነው ለካ። ምሳ የሚበሉት በቤታቸው በር ላይ የሚሄደው የሽንት ቤት ፍሳሽ እየሸተታቸው ነው።ይህንን ሳይ አለቀስኩ።''

ሦስተኛዋ ታዳጊ ሕፃን-
 
'' እማዬ ለእኔ ኮካ እና ኬክ የምትገዛልኝ ብር ሰላም በወር አይታው አታውቅም። ከአሁን በኃላ እማዬ ኬክ እንዳትገዛ ከገዛችም ለሰላም መጀመርያ እንድትገዛላት ነግርያታለሁ።''
ከእዚህ በላይ የተፃፉት የታዳጊ ህፃናቱ አስተያየት ቃል በቃል ለማስታወስ ባለመቻሌ እንጂ ከእዚህ በላይ በጣም በሚያሳዝኑ ቃላት የተሞሉ መሆናቸውን ግን አስታውሳለሁ።

 የምስክኑን ሕዝብ ችግር ለመረዳት ቁልቁለቱን መውረድ ይሻል


የሶስተኛው አለም የሀገራችንም ትልቁ ችግር የመረጃ ክፍተት መኖር ነው።አዲስ አበባ ውስጥ ያለውን የድህነት መጠን የህዝቡን ከኑሮ ጋር የሚያደርገውን ግብግብ የሚያውቀው ህዝቡ ብቻ ነው።ሌላው ፖሊሲ አውጭው፣የከተማው ከንቲባ፣የክፍለ ከተማ ሊቀመንበሩ፣ወዘተ ድህነትን ሊሰሙት ይችላሉ። ያለበትን ደረጃ(የድህነቱን ዲግሪ) ግን ለማወቅ እንደ እነኚህ ሕፃናት ወደተቸገሩት መንደር በአካል መግባት፣ማውራት፣መጠየቅን ይሻል።የመንግስት ባለስልጣናትም ሆኑ ቱጃር ነጋዴ ድህነትን የሚያውቀው በስም ነው።የከተማውንም ሆነ የገጠሩን የአመት የስራ ፕሮግራም የሚያወጣው ግን እርሱ ነው።አዋጁን የሚያፀድቀው ግን አሁንም እርሱ ነው። የሀገሪቱ ገንዘብ እና በጀት ቅድምያ ውስኪ ማስመጣት ላይ ይሁን ወይንስ ታላላቅ ፎቆችን በአየር መንገድ አካባቢ መገንባት ይሁን? ብሎ የሚወስነው ግን ስለድህነት ምንም መረጃ የሌለው ባለሥልጣኑ ነው።''ኢትዮጵያ አድጋለች ተመንድጋለች ምክንያቱም ከቤቴ ስመጣ በቀለበት መንገድ ላይ ነው የመጣሁት'' መሰል ንግግር የሚያደርገው ግን የሀገሪቱ ሕዝብ የመግዛት አቅሙ ወርዶ ፆም ለመፍታት አንድ ኪሎ ስጋ ሕልም እንደሆነበት የማያውቀው ምናልባት እርሱ በቤቱ በአንድ ሺህ አምስመቶ ብር(የወቅቱ የበግ ዋጋ ነው) በግ ገዝቶ አስሮ ከልጆቹ ጋር እየሳቀ እየበላ ያለው ነው።

ዛሬ ፆመ ፍልሰታ ሲፈታ ሌሊቱን  በሰዓታት፣ቀን በቅዳሴ አምላካቸውን ሲማፀኑ የነበሩት በሚልዮን ከሚቆጠሩ በተለይ ከከተማ ነዋሪዎች (የገጠር ነዋሪ በእንፃሩ ከሚያረባው ዶሮም ሆነ እንቁላል ይፈስጋል ብዬ በማሰብ) ስንቱ አንድ ኪሎ ስጋን ከ125 ብር በላይ ከፍሎ ይገዛል? ልጆች ያሉት መካከለኛ ገቢ የሚባለው (የመካከለኛ ገቢ የሚባል የህብረተሰብ ክፍል በኢትዮጵያ እየጠፋ መሆኑን ሳንዘነጋ) ስንት ኪሎ ስጋ ለስንት ልጆቹ ያዳርሳል?

በቀድሞ መንግስት ዘመን አንድ በግ በሃምሳ እና ስልሳ ብር ይገዛ የነበረበት ጊዜ ዋጋው በአስራዎቹ ውስጥ በመጨመሩ መንግስት ለመንግስት ሰራተኞች በየመስርያ ቤታቸው ለነዋሪው በማከፋፈያ ቦታዎች ከምስራቃዊው የሀገራችን ክፍል ''ዋንኬ'' የተሰኙ (አንገታቸው ጥቁር ሌላው አካላቸው ሙሉ ነጭ) በጎች በቅናሽ ሲከፋፈሉ እንደነበር በትምህርት ቤት ሕይወቴ አስታውሳለሁ።መንግስት እንደ አባት ማሰብ ህዝብ ለሚገጥመው ችግር አብሮ መፍትሄ ማፈላለግ ነበር ባህሪው ሊሆን የሚገባው።ሕዝብ ግራ ገብቶት ሲንከራተት ''የእኔ ቤት ከሞላ'' አለም ሁሉ ጠግቧል ማለት ግን ጤናማ አስተሳሰብ አይደለም።በሀገራችን የከብት እርባታም ሆነ የወተት ውጤቶች የሀገር ውስጥ ምርቶች ናቸው።ችግሩ የሚስተዋለው ስርጭት ላይ ነው።ምክንያቱም ከከተሞች በራቁ አካባቢዎች አሁንም ምርቱ በተነፃፃሪ የተሻለ ዋጋ ላይ መገኘቱ ነው።

 አናዳጁ ነገር  ማኪያቶ መዘግየቱ 

እድገት የቁሳቁስ ምርት መጨመር ወይንም የመሰረተ ልማት መስፋፋት ብቻ እንዳልሆነ የዘርፉ ባለሙያዎች አበክረው ያሳስባሉ።አድገት ሰው ላይ የሚሰራ ልማት ነው።ሰው ማለት ደግሞ በትንሹ የመኖር ዋስትና አለው የሚባለው መሰረታዊ ነገሮች ማለትም ምግብ፣መጠለያ እና ልብስ ሲሟሉለት ነው።እድገት ግን ከእነዚህ በላይ ፀጥታ፣የትምህርት ዕድል፣ገበያ ለማግኘት ያለው ዕድል፣ሕክምና ለማግኘት ያለው ዕድል ወዘተን ይለካል። የተባበሩት መንግሥታት የልማት ፕሮግራምም ሀገሮችን ለመኖርያ ምቹ የሆኑ እና ያልሆኑ ብሎ የሚለይበት መስፈርትም እነኚሁ ናቸው።ጥያቄው ግን የፖሊሲ አውጭው እና በጀት መዳቢው ባለስልጣን  የህዝቡን የድህነት መጠን ከላይ እንደተጠቀሱት  ህፃናት ተዘዋውረው ካልተመለከቱት እንዴት ከቢሮ ሆነው ለማወቅ ይችላሉ? ነው።ቢሮ ውስጥ ሁሉ ሰላም ነው።ኢትዮጵያም አድጋለች፣ሕዝቡም ተመችቶታል፣ምን ቀረ ከቢሮ ለተቀመጠ ባለስልጣን ቢያንስ የሚያናድደው ነገር አይጠፋም የህዝቡ ድህነት የኑሮ ውድነቱ አይደለም፣በእዚህ ወር የኢትዮጵያ ስታትስክስ ቢሮ ያወጣው የዋጋ ንረቱ በ 8% መጨመሩም አይደለም። በስልክ የታዘዘው ማኪያቶ መዘግየቱ ነው።ልብ ይስጠን።

አበቃሁ 

ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ  

Thursday, August 15, 2013

በኢትዮጵያ የሚድያ ታሪክ በአይነቱ ልዩ ሃገራዊ ውይይት





አቶ ሕሊና ዳኛቸው ከኢሳት አስተዳደር ለኢሳት ራድዮ  ዛሬ ነሐሴ 9/2005 ዓም እንደገለፁት ኢሳት በሰሜን አሜሪካ ቨርጂንያ፣ አርልንግተን ሸራተን ሆቴል  በአይነቱ ልዩ የሆነ የመወያያ መድረክ በመጪው ዕሁድ ነሐሴ 12/2005 ዓም ማዘጋጀቱን ገልፀዋል።

በዝጅቱ ላይ ጥሪ የተደረገላችው የፖለቲካ ድርጅቶች፣የሲቪል ማህበራት፣የሃይማኖት መሪዎች፣ታዋቂ ግለሰቦች፣የኢትዮጵያ መንግስት ተወካዮች ከውጭ እና ከሀገርውስጥ ይሳተፉበታል። እንደ አቶ ሕሊና ዳኛቸው ገለፃ ይህ መድረክ የኢትዮጵያን የፖለቲካ አቅጣጫ ለማመላከት እና መፍትሄ ለማስቀመጥ አይነተኛ ድርሻ ይኖረዋል።
 የሕዝባዊ ስብሰባው አላማ አሁን ያስፈለገበት ዋና ምክንያትን አቶ ሕሊና ሲያብራሩ ኢትዮጵያ አስጊ ደረጃ ላይ በመሆኗ መሆኑን ገልፀዋል።

'' ኢሳት የፖለቲካ ድርጅቶችን ሚና አልወሰደም ወይ? '' ለሚለው ጥያቄ ደግሞ አቶ ሕሊና ሲያብራሩ ''ኢሳት አቅዋም አይወስድም ፕላትፎርም የመፍጠር ሥራ ነው የሚያደርገው።መድረኩን መፍጠር  ብቻ ነው እንጂ የሚመሩት የፖለቲካ ፓርቲዎች ናቸው----ኢሳት እንደሚድያ የጠራው የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ብቻ አይደለም መንግሥትንም ነው'' ብለዋል።

የእዚህ አይነቱ በኢትዮጵያ የሚድያ ታሪክ የመጀመርያ የሆነውን ስብሰባ ሁሉም ኢትዮጵያዊ መንግስትም ጨምሮ በጎ ምላሽ ሰጥቶ መነጋገር የሚገባው ይመስለኛል።ኢትዮጵያ የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ፣የአንድ ብሔር ወይንም ግለሰብ ንብረት አይደለችም የሁላችንም የጋራችን ነች።ያለፈ የአምባገነንነት ዘፈን ጊዜው ተቃጥሏል።አሁን ሁሉም ያለው አማራጭ አንድ ነው።ይሄውም ከፖለቲካ ታክቲክነት በዘለለ መልክ ወደ ግልፅ ውይይት እና መፍትሄ መምጣት።እኔ  ይህ ስብሰባ ውጤታማ እንደሚሆን የሚያሳምኑኝ  ሶስት  ምክንያቶች አሉ።እነርሱም-

1/ አዲሱ የኢትዮጵያ ትውልድ ኃላፊነት የሚወስድበት ነውና 


ባለፉት አርባ አመታት በኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ላይ የነበሩ የፖለቲካ ኃይሎች የቀደሙ ስኬታቸውን እና ድክመቶችን የሚለኩበት ዛሬ እድሜ ቢጫናቸው በጎውን ልምዳቸውን በማካፈል ያለፈ ስህተታቸውን በመንቀስ እራሳቸውን የሚመለከቱበት  አይነተኛ መድረክም ነው። ኢትዮጵያ የትውልድ ሽግግር ላይ መሆኗን ከ አዲሱ የኢትዮጵያ ሚሊንየም ወዲህ የተነሱትን በወጣቶች የተገነቡ ኢትዮጵያዊ ድርጅቶችን ማየት ይቻላል።ኢሳት በራሱ የእዚህ ማሳያ ነው። ይህ ማለት አዳዲስ አስተሳሰቦች ገዢ ሆነው የመውጣታቸው ዕድል ትልቅ ነው ማለት ነው።

2/ የኢሳት ሚዛናዊ ሚድያነት የተገለፀበት ስለሆነ   


መንግስት በስብሰባው ላይ ተጋብዟል።ይህ ትልቅ እመርታ ነው።ኢሳት ሚዛናዊ የሚድያ ተቁአምነቱን አስመሰከረ ማለት ነው።ኢሳትን መንግስት በመግለጫው አያመስግን እንጂ ለኢሳት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ሃሳባቸውን ገልፀዋል።አቦይ ስብሐት፣የመንግስት መስርያ ቤት የመምርያ ኃላፊዎች፣የፖሊስ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣የጦርሃይሉ ከፍተኛ መኮንኖች፣የሃይማኖት አባቶች እነኚህ ሁሉ ከሀገር ቤት ለኢሳት ግልፅ የሆነ ሃሳባቸውን እና የመስርያቤታቸውን ሥራ ገልፀዋል።ይህ ኢሳትን ታላቅ ከበሬታ ያጎናፅፈዋል።ከበሬታው ሚዛናዊ የሆነ ሚድያ ለወደፊቷ ኢትዮጵያም ወሳኝ በሆነ መልክ መሰረት የሚጥል ነው። የኢሳት ተሳትፎም የተራራቁትን አቀራርቦ በሀገራቸው ጉዳይ እንዲወያዩ ውይይቱን የማመቻቸት ሥራ ብቻ ነውና ከእዚህ በፊት ከሚጠሩት ሃገራዊ ስብሰባዎች በአይነቱ የተለየ እና ሚዛናዊነቱን ያጎላዋል።

3/ ወቅቱ የእዚህ አይነቱን ጥሪ ብቻ የሚናፍቅ መሆኑ 


በመጪው እሁድ የሚደረገው ስብሰባ ብዙ ኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆኑ የኢትዮጵያ ወዳጆችም ለኢትዮጵያ ችግር መፍትሄ ብቸኛው መንገድ ፊት ለፊት ተቀምጦ መወያየት ብቻ መሆኑን ብዙዎቹ የፖለቲካ ፕሮግራማቸው ልዩነት የጎላ አለመሆኑ ግን አለመነጋገር የፈጠረው ችግር መሆኑን የሚያምኑበት ጊዜ ነው- ይህ ጊዜ።የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ፣ማህበራዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ችግሮች ከመቸውም ጊዜ በላይ የናሩበት፣መንግስት እራሱን ለመቆጣጠር ከሙስና እስከ ተለዋዋጭ መመርያዎች ግራ የተጋባበት፣ባለስልጣናቱ ነገን እየፈሩ ያሉበት ጊዜ ነው ይህ ጊዜ።ወጣቱ የሀገሩን  ችግር ከበቂ በላይ የተረዳበት፣ሀገሩንም ከገባችበት አዘቅት ለማውጣት ብቸኛ መፍትሄ እሱ እና እሱ
ብቻ መሆኑን የተረዳበት ጊዜ ነው-ይህ ጊዜ። በመሆኑም የስብሰባው የጥሪ ወቅት እራሱ በትክክለኛ ጊዜ ላይ ነው እና ስኬታማነቱ የጎላ ነው።

በመጨረሻ የእዚህ አይነቱ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ወደ ሕዝብ አደባባይ አውጥቶ ሃሳባቸውን መስማት እጅግ ጠቃሚ መሆኑን መዘንጋት የለብንም።ይሄውም የበረቱትን ወደ አንድ ሳጥን ገብተው በሕብረት  ሕዝብ እንዲመሩ ለማበርታት እና  ያልበረቱት ደግሞ ከፖለቲካው አለም እረፍት እንዲወስዱ ለመለየት።

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክልን

ጌታቸው

ኦስሎ

Wednesday, August 14, 2013

በግብፅ እየሆነ ያለው ለእኛ ምን ትምህርት ይሰጣል?




ከትናንት ጀምሮ ብዙዎች በግብፅ እየሆነ ያለውን በማህበራዊ ድህረ ገፆቻቸው ላይ በፎቶ የተደገፈ መረጃ እየሰጡ ነው።ሁኔታው እጅግ ዘግናኝ እና አሳዛኝም ነው።በተለይ ከጉዳዩ ጋር ምንም ተያያዥነት የሌላቸው አብያተ ክርስትያናት መቃጠል አጋጣሚን ተጠቅሞ የእረጅም ጊዜ እኩይ ዕቅድን የመፈፀም ድርጊት ነው። እኔን የሚያሳስበኝ እኛ በተወሳሰበ ፖለቲካዊ ሁኔታዎች ውስጥ ያለን ተመሳሳይ የታሪክ ክስተት ያሳለፍነው ኢትዮጵያውያን ከእዚህ ተምረን ምን እናድርግ? የሚለውን ጥያቄ መመለስ ነው ቁም ነገሩ።ከእዚህ በተረፈ ግን ለሀገራችን መፍትሄ የምንለውን ለመናገር ፈርተን ወይንም የሀገራችንን ተጨባጭ ሁኔታዎችን ሳናነሳ ስለ ግብፅ ብንናገር ምን ይሆን ፋይዳው? 



የፖለቲካ ለውጥ ከመነሻው እስከመድረሻው የሚሄድባቸው ሂደቶች እጅግ አስገራሚ እና ውጤቱም ከተጠበቀው ይልቅ ያልተጠበቀው ክስተት የበላይ መሆኑ አንዱ እና አይነተኛው ተፈጥሮው ነው።ለእዚህም የቅርብ ጊዜ ምሳሌ የሚሆነን የሰሜን አፍሪካው የለውጥ ማዕበል ነው።የለውጥ ማዕበሉ አነሳስ፣ሂደት፣ግብ እና ውጤት የሃገራቱን ተጨባጭ ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ ቢሆንም በአግባቡ የተደራጁ የፖለቲካ ፓርቲዎች ያሉባቸው እና የሌሉባቸው ሃገራት ልዩነት ግን ፍንትው ብሎ ታይቷል። የቱኒስያን እና የአልጀርያ የለውጥ ማዕበል ከሊብያ ጋር ያለው ልዩነት እና  በአንፃሩ ደግሞ የግብፅ እና የየመን ሁኔታ አሁንም ድረስ በእንጥልጥል መሆኑ ለሰሜን አፍሪካ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ቀንድ ብሎም ለኢትዮጵያ የሚኖረው ተዘዋዋሪ ተፅኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም።ቢያንስ የሁለቱ ሃገራት አለመረጋጋት በእዚሁ ከቀጠለ የአካባቢ ትናንሽ ጉልበተኞች የመፈጠራቸው አባዜ ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የጦር መሳርያ ንግድ የሚደራባቸው ሃገራት የመሆናቸው ፋይዳ ውሎ አድሮ እንደ ኢትዮጵያ ላለች ሃገር አይነተኛ ፈተና መሆኑ አይቀርም።ፈተናውም ከሃይማኖታዊ ነውጠኞች እስከ ንግድ አዋኪዎች ድረስ የሚፈጥረው ተፅኖ ቀላል አይደለም።

የአፍሪካ ቀንድን እና ቀጠናውን ስንመለከት በብዙ ፖለቲካዊ፣ምጣኔ ሃብታዊ እና ማህበራዊ ችግሮች የተወጠረ በመለስተኛ የነገሮች ክስተት ከባድ ስብአዊ ቀውስ የመድረሱ ዕድል ከፍተኛ እንደሆነ እንመለከታለን። የአሁኑ ጊዜ የአካባቢው የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊ  ኃይላት(የኢህአዲግ መንግስትም ሆነ ተቃዋሚ ኃይሎች) ነገሮችን በአንክሮ አይተው አማራጩን እና አዋጪውን የፖለቲካ መስመር የመቀየሻ ወሳኝ ጊዜ ላይ  መሆናቸውን ቢረዱት ለሀገራችን አንዱን የፈተና ወቅት የምታልፍበት ጊዜ ሆነላት ነበር።ብልህ እና ቆራጥ መሪ የሚናፈቀው የእዚህ ጊዜ ነው። ከእዚህ ባለፈ ግን ውጥረቶችን ለማርገብ በመሞከር መተኮር በሚገባው በዋናው እና እጅግ አደገኛው ሁኔታ ላይ ማትኮር ካልተቻለ ተያይዞ መጥፋት ብቸኛ ዕጣ መሆኑ የማይቀር መሆኑን መረዳት ብዙም ብልህነት አይጠይቅም።

በሰላማዊ መንገድ መንግስት መቀየር ያልታደለቸው ሀገራችን ከውጭ ያሉት ቅራኔዎች ነፀብራቅ እና በውስጥ በእራሷ እና ከቀጠናው ጋር ያሉት ቅራኔዎች ወደ አልታሰበ እና አልተፈለገ ጫፍ ኢትዮጵያን ይዘዋት እንዳይሄዱ ማሰብ የዜጎች ትልቁ ድርሻ መሆን አለበት።ለመሆኑ ውሎ አድሮ ኢትዮጵያ ላይ በተዘዋዋሪም ሆነ በቀጥታ  ተፅኖ ከሚፈጥሩት ቅራኔዎች እና ቀውሶች ውስጥ-

ከውጭ -

- በሱማሌ ያለው የአልሸባብ እንቅስቃሴ፣
- የዑጋዴን ግጭት፣
- የግብፅ ሁኔታ አለመረጋጋት እና እስካሁን ወጥ የውጭ ፖሊስዋ አለመታወቁ፣
- የአቶ ኢሳያስ ድብቅ እና ግልፅ ያልሆነ አስተዳደር በኤርትራ መኖሩ፣
- የፅንፈኛ እስልምና እንቅስቃሴ፣
- ጠንካራ ያልሆነው የደቡብ ሱዳን መንግስት ቅርፅ ገና በአግባቡ አለመለየቱ የሚሉት ጥቂቶቹ ሲሆኑ፣


ከውስጥ -


 - ኢህአዲግ ከምርጫ ጋር በተያያዘ ከህዝብ እና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የገባው ቅራኔ፣
- ኢህአዲግ ከተለያዩ ባለድርሻ የህብረተሰብ አካላት ጋር የፈጠራቸው ቅራኔዎች።(ለምሳሌ ከሙስሊሙ ህብረተስብ ጋር፣ከዋልድባ ገዳም ይዞታ ጋር ይጠቀሳሉ)፣
- የሕዝብ ብዛት እየጨመረ መሄድ፣
- የዋጋ ግሽበቱ ጭማሪ አለማቆም (ባለፈው ወር ብቻ በመንግስት ዘገባ መሰረት አጠቃላይ ግሽበቱ በ 8% መጨመሩ ይታወቃል)፣
- የሐብት ክፍፍሉ መራራቅ፣
- የስራ አጥነት መጨመር፣
- የማህበራዊ ኑሮ ቀውስ (ከቀዬው የሚፈናቀለው መብዛት፣የጎዳና ተዳዳሪ መጨመር፣ሃገሩን ጥሎ የሚሰደደው መብዛት ወዘተ) የሚሉት ከብዙ በጥቂቱ ናቸው።


ከኢህአዲግ መንግስት እና ከተቃዋሚ ኃይሎች ምን ይጠበቃል?

እነኚህ ከላይ የተመለከትናቸው ቅራኔዎች እና ቀውሶች በአግባቡ ካልተፈቱ እና ለመፍትሄነት ሁሉም ድርሻ እንዳለበት ካልተገነዘበ ነገ ሀገራችን ብለን የምንጠራት ምድር እንዳናጣ ባንመኘውም መፍራት ግን ለጥንቃቄ ይረዳል።ለሀገራችን ውስብስብ ችግር መፍትሄ ለመስጠት ተቃዋሚ መሆን ብቻ መድሃኒት አይሆንም።የመንግስትን ታላቅነት በመስበክ እና አቶ መለስ ታላቅ መሪ ነበሩ እያሉ በማስተጋባትም ሀገር አይገነባም።በሆደ ሰፊነት፣በጋራ ነጥቦች ላይ በማተኮር፣እጅግ አደገኛ የሆኑትን የሀገሪቱን ችግር ቀድሞ ለመቅረፍ በመሞከር፣ኢትዮጵያዊነትን መሰረት አድርጎ ሀገራችንን የነበረ እሷነቷን በክብር በማስቀጠል ግን በጋራ ከመጥፋት ያድናል።እዚህ ላይ ትልቁን በሃጋራችን ላይ የሚያንዣብበውን አደጋ  የተጠያቂነት  ድርሻ የሚይዘው የኢህአዲግ መንግስት መሆኑን መርሳት አይገባም።ለእዚህም ዋናው እና አቢይ ምክንያት ኢህአዲግ  በመንግሥትነት እስከተቀመጠ ድረስ ቅራኔዎችን ለመፍታትም ሆነ የፖለቲካ ኃይላትን እና የህብረተሰቡን አካላት ጥያቄ ለመመለስ የዋና ባለድርሻ አካልነቱን በመያዙ ነው።በሌላ በኩል የተቃዋሚ ኃይላትም ከኢህአዲግ ጋር የሚያደርጉት ማናቸውም አይነት የፖለቲካ ለውጥ ማ ምጫ የተፅኖ መፍጠርያ መንገዶች ማለትም ሰላማዊ ሰልፍም ሆነ  የትጥቅ ትግል የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም የማይጎዳ እና ለዘመናት ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር ለሚሹ ኃይላት የማይመች ሀገሪቱንም ወደማትነሳበት አዘቅት የማይከት መሆኑን በሚገባ ማጤን ተገቢ ነው።

ባጠቃላይ የሀገራችን ውስጣዊ የፖለቲካ ቅራኔ፣የኢህአዲግ ግትር እና ነባራዊ ሁኔታን ያላገናዘበ አሰልቺ ፖሊሲ፣የአካባቢያችን ሃገራት የፖለቲካ ንፋስ ተለዋዋጭነት፣የኢትዮጵያን የመኖር ህልውና የሚፈታተኑ እንቅስቃሴዎች መኖር (የኑሮውድነቱ፣የህዝብ ብዛት መጨመር) ስንመለከት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ለውጥ በመጣው መንገድ ቢመጣ በነበረ እሷነቷ የማስቀጠል ዋስትናውን ያሳንሰዋል።ይህ ማለት ደግሞ ኢህአዲግም ሆነ ተቃዋሚዎች በጋራ ስለሚጠሯት ሀገር ለማውራት ዕድል የማያገኙበት አስከፊ ጊዜ ይመጣል ማለት ነው።ስለዚህ ኢህአዲግ የዲሞክራሲውን መንገድ እና እውነተኛ የምርጫ ስርዓት ከልብ ባሳየ መንገድ መከወን (እውነተኛ የፖሊሲ ለውጥ ማድረግ ለምሳሌ በዋና ዋና ቁልፍ ፖለቲካዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ጉዳዮች ላይ) ፣ ነፃ የሚድያ አገልግሎት እንዲኖር ከልዩነት ይልቅ አንድነትን የሚያጠናክሩ ጉዳዮች ላይ በማተኮር ላይ መስራት ቢጀምር (ሃያ አንድ አመት ሙሉ ሲጠየቅ የነበረን ጉዳይ ካለመሰልቸት ስደግመው አንባቢ እንዳይሰለች ይቅርታ ከመጠየቅ ጋር) እና  እራሱንም ሆነ ሀገሪቱን ወደማትወጣበት አዘቅት ከመክተቱ በፊት በ2006 ዓም  በአንክሮ ቢያስበበት ለኢትዮጵያ ትልቅ ውለታ እንደዋለ ይቆጠርለት ነበር።እዚህ ላይ ላሰምርበት የምፈልገው እነኚህን ተግባራት ቀድሞ ኢህአዲግ ማድረግ ካልቻለ የለውጥ ማዕበሉ በተፈለገውም ሆነ ባልተፈለገው መንገድ መምጣቱ የግድ ነው።አሳዛኙ ግን ውጤቱ እና የመጨረሻ ግቡን በጥሩ መልኩ ለመተንበይ አለመቻሉ ነው።በትንሹ ለመተንበይ ግን የተቃዋሚዎችን አያያዝም ሆነ የመንግስትን ቅራኔ አፈታት መንገድ መመልከት በቂ ነው። ሁለቱም የሚቀራቸው መንገድ እንዳለ ይስተዋላል።ለኢህአዲግ ግን እራሱን የእውነተኛ ለውጥ ማዕበል ለማድረግ እና ሀገርንም ህዝብንም ይቅርታ ለመጠየቅ ከነገ ይልቅ ዛሬ ይቀርበዋል።2006 ዓም ምን እንሰማብሽ ይሆን?

ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ

Saturday, August 10, 2013

በኢትዮጵያ በእስልምና ስም የሚንቀሳቀስ የፅንፈኛ እንቅስቃሴ የለም?





በቂ የመወያያ መድረክ የሌለው እና የዲሞክራሲ መብቱ የታፈነ ሕዝብ በከፍተኛ የመረጃ እጥረት የመሰቃየቱ አንዱ አመላካች መንገድ እጅግ የበዙ አስተያየቶችን እንደትክክለኛ የመረጃ ምንጭ አድርጎ የመውሰድ ክፉ አባዜ ተጠቂ መሆን ነው። በተለይ  መረጃዎችን ከየት፣ለምን እና ለማን ተብሎ ተሰጠ? ከሚሉ መጠይቆች ተነስቶ ለመተንተን አቅም እንዲያዳብር የባለሙያ ትንተናዎችን በመገናኛ ብዙሃኑ ማግኘት ያልቻለ ሕዝብ በትናንሽ እና ቁርጥራጭ መረጃዎች ወደ አልተፈለገ ድምዳሜ የመድረስ አደጋው ቀላል አይደለም።

ሰሞኑን በሀገራችን የተከሰተው(ድንገተኛ ስላልሆነ ተከሰተ ማለት ባያስደፍርም) በሙስሊሙ ሕብረተሰብ ጋር ተያይዞ ከመንግስት ፌድራል  ፖሊስ ጋር የነበረው ግጭት ብዙዎች እንደመሰላቸው እና ካላቸው ፖለቲካውም ሆነ ሃይማኖታዊ አመለካከት አንፃር ሲተረጉሙት ይታያል።''ግርግር ለሌባ ይመቻል'' እንዲሉ የአንዳንድ ወገኖች ጉዳዩን አስመልክተው የሚያተኩሩበት የትኩረት አቅጣጫ በራሱ አንዳንድ እውነታዎችን እንዳይሸፍናቸው ስጋት አለኝ።

በእኔ አመለካከት የእዚህ አይነቱ ከሀገር ውስጥ የፖለቲካ አሰላለፍ፣ኢትዮጵያ ካለችበት ጅኦ-ፖለቲካዊ (አካባቢያዊ) አቀማመጥ እና ከሀገራችን መፃኢ ዕድል ጋር የራሱ ተፅኖ ያለው ጉዳይ ለጊዚያዊ ፖለቲካዊ ጥላ ተብሎ የነበሩ እውነታዎችን ማለፍ ተገቢ አይደለም።በመሆኑም የሚከተሉት እውነታዎች ከግንዛቤ መግባት ያለባቸው መሆናቸውን መረሳት ያለባቸው አይመስለኝም።

1/  አክራሪ እና ፅንፈኛ የእስልምና እንቅስቃሴ በሀገራችን አለ።


ከአክራሪ እና ፅንፈኛ የእስልምና እንቅስቃሴ እንደማንኛውም የዓለም ክፍሎች ሀገራችንም ነፃ አይደለችም። የሀገራችንን ለየት የሚያደርገው አለምአቀፉ ፅንፈኛ የእስልምና እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ ካላት ጂኦ-ፖለቲካዊ አቀማመጥ አንፃር በሀገሪቱ ሁለንተናዊ ሕይወት ውስጥ ለመንሰራፋት በአዲስ መልክ ካለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመን ጀመሮ ሲሰራ የነበረ ለመሆኑ በርካታ ማስረጃዎችን ማቅረብ ይቻላል።ይህንንም አሁን ያለውም መንግስት ሆነ  የቀደሙት ሁለት መንግሥታት የቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴም ሆነ የደርግ መንግስት ጠንቅቀው የሚያውቁት ነው።

2/ ፅንፈኛው የእስልምና እንቅስቃሴ ላለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመን በሀገራችን ፖለቲካዊ ክስተቶች ላይ እጁ ነበሩበት።


በኢትዮጵያ መንግሥታት በተቀያየሩ ቁጥር ብዙ ልዩ ፍላጎት ያላቸው (interested groups) ኃይሎች የተፅኖ እጃቸውን ለማርዘም የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም። ለእዚህም ነው አንዳንድ የመንግስታቶቻችን እርምጃዎች በሰው አይምሮ የማይታሰቡ እራሳቸው መንግሥታቱ ካለፉ በኃላም የሚገርሙ እና የሚያስደነግጡ የሚሆኑባቸው።ይሄው በወቅቱ በአግባቡ ማየት ያልቻሏቸው 'የልዩ ፍላጎት ኃይሎች' ተፅኖን ማየት የሚችሉት ከጊዜ በኃላ በመሆኑ ነው።አክራሪ እና ፅንፈኛ የእስልምና እንቅስቃሴ መኖሩን ከሁሉ በላይ የእስልምና እምነት ተከታይ ወንድሞች እና እህቶች ሂደቱን በቅርብ በእምነት ቦታዎቻቸው ያሉትን ዘገምተኛ የሂደት ለውጦች ስለሚረዱት  ቢገልፁት በጣም ያማረ ነበር። ሆኖም ግን  አሁን ላለንበት አንዳንድ የሀገራችን ሁኔታ የፅንፈኛው አክራሪ እንቅስቃሴ (በአንዳንድ የውጭ መንግሥታትም ታግዞ) ነፀብራቅ አይደለም ለማለት አያስደፍርም።

3/ ፅንፈኛው እንቅስቃሴ እንደ አለፉት ሃያ አመታት የተመቸ ጊዜ አግኝቶ አያውቅም 


ከላይ በተራ ቁጥር ሁለት ላይ እንደተገለፀው የፅንፈኛው አስተሳሰብ አራማጅ አንዳንድ የአረብ መንግሥታት በዲፕሎማሲያዊ  እና በገንዘብ ተፅኖ ያለፉትን መንግሥታትም ሆነ የአሁኑን ኢህአዲግ ላይ ተፅኖ በመፍጠር ወደ ዋናው ግብ የሚያደርሳቸውን አንዳንድ የጥርጊያ ጎዳናዎች ለመጥረግ አልቻሉም ማለት አይቻልም። በብዙዎች ዘንድ እንደሚታመነውም በሱዳን ቱጃር የግል አይሮፕላን ወደ ሀገር ውስጥ የገቡት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ የሚመሩት ኢህአዲግ ከፅንፈኛ እና አክራሪነት ጋር በተያያዘ ለሚቀርቡላቸው ጥያቄዎች ሁሉ ''የአፈጀ አመለካከት፣የድሮ ስርዓት ናፋቂዎች፣የደርግ ርዝራዥ አስተሳሰብ'' እያሉ ያጥላሏቸው ነበር። በተለይ   በጅማ፣በአጋሮ(በሻሻ)፣በኢሊባቦር፣በባሌ እና በአሩሲ አብያተ ክርስቲያናትን ሲያቃጥሉ እና የነበሩ ኢትዮጵያዊ የሙስሊም እምነት አባቶችን መስጊድ እንዳይመጡ ሲከለክሉ ሁሉ መንግስት ተገቢውን እና የማያዳግም እርምጃ በፍጥነት ሲወስድ አልታየም። በተለይ በአንዳንድ ዞኖች የድርጊቱ ፈፃሚዎች የኢህአዲግ አጋር ድርጅቶች  አመራር መሆናቸው ጉዳዩ የበለጠ እንዲደፋፈን እና የፅንፈኛ አስተሳሰቦች ስር እንዲሰዱ ጊዜ ሰጥቷል።

4/የእስልምና አክራሪ እና ፅንፈኛ ኃይሎች የስትራቴጂ(የስልት) ለውጥ 


ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው  የሀገራችን የመናገር ነፃነት መገደብ እና መረጃዎች ለፕሮፓጋንዳ ሥራ ብቻ በመንግስት የመገናኛ ብዙሃን የመለቀቃቸው ፋይዳ  እና ሕዝቡም እምነቱን በመንግስት የመገናኛ ብዙሃን ላይ ስሌለው፣ ስለአክራሪ እና ፅንፈኛው እንቅስቃሴ ትክክለኛ መረጃ በእነኚህ የመገናኛ ብዙሃን ቢሰጠውም በአግባቡ አይረዳውም።ይህ ደግሞ የእረኛውን ታሪክ የሚያስታውስ ነው።እረኛው ቤተሰቡን ለማስደገጥ  የውሸቱን ''ቀበሮ መጣብኝ!'' እያለ ይጮህ ነበር። ቤተሰቡ አንድ ሁለት ጊዜ የእውነት መስሎት ደንግጦ ወጣ ውሸቱን መሆኑን አወቀ።በሶስተኛው እረኛው የእውነት ቀበሮ መጣበት ቤተሰቡ ግን ''ልማዱ ነው ተዉት'' ብሎ ቁጭ አለ።ቀብሮው ደርሶ በጎቹን በላ። የኢቴቪ   ሂደትም የእረኛው ይመስላል። ሕዝብ ስለምን እንደፃፉ የሚያውቃቸውን ጋዜጠኞች ሁሉ ''አሸባሪ'' እያለ ሲፈርጅ ከርሞ የእውነተኛው አሸባሪ የመጣ ጊዜ እንደ እረኛው ቤተሰቦች ''ልማዱ ነው'' እንደሚባል ልብ ያለው አይመስልም።

አሁን ባለንበት ዘመን ፅንፈኛ የእስልምና ኃይሎች የስልት ለውጥ እያደረጉ መሆኑን ከአለምአቀፍ ሁኔታዎች መረዳት ይቻላል።እዚህ ላይ በእዚህ ፅሁፍ ''በፅንፈኝነት'' ለመመደብ ማስረጃ ባይኖርም በአንድወቅት ግን በእዚሁ ዘርፍ ተመድበው የነበሩት የ''ህዝቦላህ'' እና የግብፁ ''እስላማዊ ወንድማማቾች ህብረት'' ከአስር አመታት በፊት  ያደርጉት የነበረው የፅንፍ ተግባር በለዘበ እና በለሰለሰ አሰራር መቀየራቸውን ለማየት እንችላለን።ለምሳሌ ''ህዝቦላህ'' በሊባኖስ የድነብር ከተሞች ላይ መሰረቱን ከጣለ ወዲህ ለሊባኖስ ሕዝብ ብዙ ትምህርት ቤቶችን፣የበጎ አድራጎት ድርጅቶችን ውዘተ በመክፈት ከሕዝቡ ልብ ውስጥ ከመግባት አልፎ በሊባኖስ መንግስት ላይ ተፅኖ ፈጣሪ ከመሆን እና ምክርቤት ድረስ ደጋፊዎቹን የማስመረጥ ደረጃ ደርሷል።ይህም በኃይል ህዝብን ከማስገደድ በልማት ስራዎች አላማን ማሳካት እንደሚቻል ለማሳየት ያደረገው ስኬታማ ሙከራ ነው።

በሌላ በኩል የግብፁ ''እስላማዊ ውንድማማቾች ህብረት'' በግብፅ የሚታወቀው በነውፀኛ ተግባሩ እና እንዲያውም በአዲስ አበባ የእራሱን ሀገር ፕሬዝዳንት ሙባረክን ለመግደል ሙከራ በማድረግ ነው።ከጊዜ በኃላ ግን ይህ ፅንፈኛ ስልት ተቀይሮ እራሱን ዲሞክራስያዊ ፓርቲ አድርጎ ቀረበ።በግብፅ አብዮት ውስጥ አይነተኛ ተሳታፊ የነበረው ይህ ቡድን ከሙባረክ መውደቅ በኃላ ብቸኛ የተደራጀ ኃይል በመሆኑ እና በፈጠረው ተፅኖ ፕሬዝዳንት ሞሪስን ለፕሬዝዳንትነት አብቅቶ ነበር። ይህንን ቡድን ግን ከታሪኩ የምንረዳው  በፅንፈኛ እርምጃው ሲሆን ከጊዜ በኃላ ግን እጅግ ሰላማዊ እና ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ሆኖ ቀርቧል።የግብፅ ሕዝብ ግን አሁንም የጦር ሰራዊቱን ይዞ ከስልጣን አውርዶ ፕሬዝዳንት ሞሪስን በቁም እስረኝነት አስሯል።

5/ ለማጠቃለል 


ባጠቃላይ የአክራሪነት እንቅስቃሴን የእስልምና ተከታይ ኢትዮጵያውያንን እና የመንግስት የመፍትሄ አሰጣጥ ሁኔታዎችን በተመለከተ የሚከተሉት ሁኔታዎች ከግንዛቤ ማስገባት እና መረጃዎቹን ለሕዝብ በአግባቡ ማድረስ ይመለከተኛል የሚል ዜጋ ሁሉ ኃላፊነት ይመስለኛል።ይሄውም

  •  አክራሪ እና ፅንፈኛ የእስልምና እንቅስቃሴ ባለፉት መንግሥታትም ወቅት የነበረ ነገር ግን እንደ ኢህአዲግ ዘመን አመቺ ጊዜ ያላገኘ መሆኑ፣
  • መንግስት የእስልምና ተከታይ ወገኖች ያነሱትን ጥያቄ እና ሰላማዊ የመጠየቅ ሂደትን በተሻለ የመፍትሄ አሰጣጥ መንገድ አለመጠቀሙ ችግሩን የማባባስ ሚና መጫወቱ ይህም ብዙ ንፁሃን የእምነቱን ተከታዮች ወደ አላስፈላጊ አስተሳሰብ ውስጥ የሚከት መሆኑ እና


  • ጥያቄው እራሱ የስልት ለውጥ ባደረገው ፅንፈኛ እንቅስቃሴ የሙስሊሞችን ጥያቄ የመምራት ሚና እንዳይኖረው የሚያሰጉ ምልክቶች መኖራቸውን መገንዘብ የሚሉት ይጠቀሳሉ።


አበቃሁ
ጌታቸው
ኦስሎ

Thursday, August 8, 2013

ሀገር በነቀዝ ጨቅይቶ.....

ሀገር በነቀዝ ጨቅይቶ.......ነፃ አውጪው ነፃ አውጪ አጥቶ........ሰቆቃችንን እንደ ትንግርት........ባንዳ በብር ኢትዮጵያን ይሸጣል .......በተቃውሞ መተባበር ጥቅሜን ይጎዳል ብሎ----- ጆሮአችንን በቡሽ ደግመን ኢትዮጵያን አልሰማ ብለን-----ይልቅ የታሪክ አዲስ ራእይ እንይ..........ያለከፋፋይ ጠር የለን -----ስንጫወት በሕዝብ ደም-------ዲሞክራሲ በጎሳ ጦስ ዛሬም ሊታጨድ ነው መልሶ--- መክሊታችንም ባከነች የደም እንባ ስናነባ-------






በትልቋ ኢትዮጵያ ውስጥ የእስልምና ተከታዮች ወንድሞቻችን እና እህቶቻችንም አሉ።


መግቢያ 

ኢትዮጵያ ዛሬ ከሰማንያ ሚልዮን በላይ ሕዝብ ያለባት ነገ ከመቶ ሚልዮኖች በላይ የሚኖሩባት ሀገር ናት።ባለፈው ታሪካችን በባህል፣በቋን እና በሃይማኖት ተከባብረን በመኖራችን እስከዛሬዋ ቀን ድረስ በሰላም ደርሰናል። አለም የመድን ዋስትና (ኢንሹራንስ) ሳይኖረው ዕድር በመፍትሄነት አስቀምጠን የሞተው ሲቀበር እና ሃዘንተኛ ሲደገፍ ዘመናት አልፈዋል።የባንክ አሰራር ገና ሳይተዋወቅ ዕቁብ በገንዘብ መቆጠብያነት ተጠቅመንበታል። ዕድር እና ዕቁብ አገልግሎታቸው ይህ ብቻ አይደለም።በማኅበራዊ ችግሮች ዙርያ በሚነሱ አለመግባባቶችም የመፍትሄ አካል ሆኖ አገልግሏል።ግጭቶች ለእድር አባላት ቀርቦ መፍትሄ ይፈለግለታል።አቅም ያነሰው እድርተኛ እንዲደጎም ይደረጋል።ህብረተሰቡን የበጠበጠ አጉራ ዘለል ከእድር እንደሚለይ ማስጠንቀቅያ ይሰጠዋል።በጥንቱ አገረ ገዢው በዘመኑ ቀበሌ ወይንም ገበሬ ማህበር የማይፈታው የአካባቢ ችግር በዕድር መፍትሄ ያገኛል። ይህ እንግዲህ የነበርንበት የአኗኗር ዘይቤ መሆኑ ነው።

ባለንበት ዘመን በትልልቅ ከተሞች የዕድር ተቅዋም አቅም እየቀነሰ ቢመጣም በገጠሩ እና መለስተኛ ከተሞች (ከ85% በላይ ሕዝብ በ  ሚኖርበት የሀገራችን ክፍል) ግን ዕድር በሕዝቡ ኑሮ ውስጥ ተደማጭ እና ተፅኖ ፈጣሪ ነው።ዕድርን የመሳሰሉ ማህበራዊ ተማት ለሕዝቡ የአብሮነት አኗኗር  ያላቸው ፋይዳ እጅግ ትልቅ ነው። ዕድር ዘመናዊ እና ቀልጣፋ አሰራርን ይዞ ቢቻል ከመድን ዋስትና ድርጅቶች ጋር ተቀናጅቶ እስከ የጠለፋ ዋስትና አሰጣጥ ድረስ አዘምኖ ግን ማህበራዊ ትስስርን (ጊዜ፣ጉልበት እና ገንዘብን በቆጠበ መልክ) የሚያጎለብት  እንዲሆን ማድረግ  ተገቢ ነው። ኢትዮጵያ የምትገነባውም ሆነ የምትታወከው  በአራት ኪሎ ቤተመንግስት ስሜት ብቻ ሳይሆን ትንንሽ በሚመስሉ እንደ እድር ባሉት ተማት ሕልውና እና ሞት ጭምር መሆኑን  መዘንጋት አይገባም።

''የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ እንኳን እኛ ግመላችን ታውቀዋለች''

ኢትዮጵያን እድር ውስጥ ማየት ከቻልን የእስልምና ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን እየደረሰባቸው ያለው የመንግስት በትር ምን ያህል የሚያም መሆኑ ወለል ብሎ ይታየናል።በእድራችን ውስጥ እማማ ዙቤዳ ሲልኩን ተልከን አድገናል። እትዬ ፋጡማ ሲቆጡን እሺ ብለን ሰምተናል።ሃጂ ኑር ከእድሜ እና ከልምድ ሲመክሩን አዳምጠናል። እኛ ያደግንባት ኢትዮጵያ ይህች ነች። ዛሬ ሃጂ ተገልብጠው የሚ ያከብሯትን፣የሚሽቆጠቆጡላትን የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ''አጎሳቆሉት'' ብሎ ኢቲቪ ቢነግረኝ የምሰማበት ምን አይነት ሞራል ይኖረኛል? እንዴት ነው በኢትዮጵያ በጎ ዘመን ሲደሰቱ፣ኢትዮጵያ ስትከፋ ያነቡ የሰፈሬ የእድሩ ማገር የነበሩ የእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች ዛሬ የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ አዋረዱ ብሎ ኢቲቪ የሚነግረኝ? የአፋሩ ንጉስ አሊቢራ ''የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ እንኩዋን እኛ ግመላችን ታውቀዋለች'' ተብሎ ሲነገር እየሰማሁ አድጌ  ዛሬ ኢቲቪ ሌላ ታሪክ ሲያወራኝ በየትኛው ልቦናዬ ልስማው? 

ከባህር ውስጥ አንዱ ወይም ሁለቱ አሳ ቢገማ በባህር ውስጥ ያሉትን አሳዎች በሙሉ አይወክልም።

መንግስት ትልን ኢትዮጵያ ማየት ቢችል ኖሮ በቲቪ መነገር የሚገባውን ከማይገባው ለይቶ ማቅረብ በቻለ ነበር።ሆኖም ግን  ከዛሬ አስር አመት ወዲህ በአንዳንድ ቦታዎች ኢትዮጵያዊውን ሙስሊም ከኖረበት አብሮነት ስሜት ለመለየት ሙከራ እያደረጉ ያሉ የሉም ማለት አይደለም። በጅማ ዙርያ፣በአጋሮ ዙርያ፣በአሩሲ አንዳንድ ቦታዎች፣በባሌ ደቡባዊ ክፍል እና በሌሎች ከተሞች አዲስ አበባን ጨምሮ ከክርስቲያን ወንድሞቻቸው ጋር  አብረው ለዘመናት በእድር አባልነት የኖሩ የእስልምና ወንድሞች እና እህቶች እንዲሁም አባቶች እና እናቶች በፅንፈኛ ''የሙስሊም ሃይማኖት ተከታዮች'' እንግልት ደርሶባቸዋል፣ተደብድበዋል እንዲሁም ለስደት ተዳርገዋል።ኢቲቪ እና መንግስት ይህንን ያውቃሉ እንድያውም አንዳንድ ቦታዎች ለዘመናት ከኖሩበት የቡና እርሻ ተገፍተዋል።ይህ ተግባር በእስልምና ተከታዮች  ላይ ብቻ ሳይሆን በክርስቲያኖች ላይም ደርሷል። ይህ ማለት ግን እነኚህ እኩይ ተግባር ላይ የተጠመዱ ፅንፈኛ አስተሳሰብ አራማጆች ሌላውን ኢትዮጵያዊ የእስልምና ተከታይ ወንድሞች እና እህቶችን አይወክልም። ከባህር ውስጥ አንዱ ወይም ሁለቱ አሳ ቢገማ በባህር ውስጥ ያሉትን አሳዎች በሙሉ አይወክልም።

የኢህአዲግ ''አጋር'' ተብዬ ድርጅቶች የፅንፈኞች መንፈላሰሻ!

እዚህ ላይ ልብ ማለት ያለብን መንግስት ከላይ የጠቀስኩት አይነት የፅንፈኛ ሃሳቦች ሙስሊሙ ሕብረተሰብን እየረበሹ መሆኑን እያወቀ በወቅቱ ቢያንስ ከእድርም ሆነ ከማህበራዊ ኑሮ እንዲባረሩ እና እንዲገፉ የተደረጉትን ወደ ሚድያ ከማቅረብ ይልቅ ሲሸፋፍን ነበር የከረመው።ይልቁንም የእስልምና ተከታይ ወንድሞች እና እህቶች እነኚህን ፅንፈኛ አስተሳሰብ ያላቸውን እንዳይከላከሉ ትልቅ እንቅፋት የሆነባቸው እራሱ መንግስት ነበር። ምክንያቱም እነኚህ ፅንፈኛ ሃሳብ አራማጆች የተጠለሉት ''የኢህአዲግ አጋር '' በተሰኙ የጎሳ ድርጅቶች ስር ነበር። በመሆኑም በምስራቅ፣በደቡብ እና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በእነኚሁ ፅንፈኛ አካላት ለደረሱ አደጋዎች (በሙስልሙም ሆነ በክርስቲያኑ ላይ) ተገቢውን ቅጣት መንግስት ሳይሰጥ አጥፊዎቹ እንዲቀጡ የሙስሊሙ ሕብረተሰብም ጭምር መንግስትን እየተማፀነ በጥፋቱ ላይ እጃቸው እንዳለ የታወቁት የኢህአዲግ አጋር ድርጅቶች አባላት ወደ ሌላ ቦታ ተዛውረው እንዲሰሩ መደረጉ ብዙዎችን ያስቆጨ ጉዳይ እንደሆነ ይሄው አሁንም አለ።ዛሬም ሳላት ሊሰግድ መስግድ የሚገኘው ንፁሁ ሙስሊም ሳይሆን አክራሪነት የተፀናወተው በኢህአዲግ አጋር ድርጅት አባልነት ስር የተኮለኮሉ በርካታ አባላቱ ኢትዮጵያዊ ስሜቱ ያየለበትን ሙስሊም ሳይቀር ቁም ስቅሉን ማሳየታቸውን ተያይዘውታል።ስለሆነም የኢህአዲግ አጋር ተብዬ ድርጅቶች የፅንፈኛ መንፈላሰሻነታቸው እና ለወዳጃቸው ካሮት ለሚቃወማቸው ዱላ እየሰጡ  አንዳንድ የመንግስት ባለስልጣናትን ያልሆነ እርምጃ እንዲወስዱ ሲወተውቱ ይስተዋላሉ።ለምሳሌ በዛሬው የኢድ በዓል ላይ የመግቢያ ካርድ ይዘጋጅ ባዮቹ እኚሁ ''አጋር'' ተብዬዎች ውስጣቸው ፅንፈኛ ከላይ ግን ንፁሃን መስለው ለመቅረብ የሚጥሩቱ አይነተኛ ማሳያዎች ናቸው። 

ባጠቃላይ መንግስት ትልን ኢትዮጵያ በክርስትናም ሆነ በእስልምና ሃይማኖት ተከታዮች መተሳሰብ፣መፈቃቀር እና አንድነት የኖረች ስለሆነ መንግስት ለችግሮች የሚሰጠው መፍትሄ ከጠበበ አስተሳሰብ ወደ ሰፋ አስተሳሰብ መምጣት መቻል ነበረበት።በተለይ የመገናኛ ብዙሃኑ ፕሮፓጋንዳ አሰራር የዛሬዋን ትንሿን ኢትዮጵያ ሳይሆን ወደታች ህዝቡ የሚኖርበት የአኗኗር ዘይቤ እንደ እድር በመሳሰሉት የማህበራዊ ተም ውስጥም ትልን ኢትዮጵያ ማየት የሚችል መሆን ይገባዋል።ኢትዮጵያውያን ሙስሊም ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን አለአግባባ እየተገፉ እድራችን ሰላም ሊሆን አይችልም።ፅንፈኛ የእምነት አራማጆችበኢህአዲግ አጋር ድርጅትነት ስር ተጠልለው መንግስትን እያማከሩ በጎ ምክር አይገኝም።ከእድራችን አባላት ንፁህ ኢትዮጵያውያን ሙስሊም ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን የመለያ ልቦና ያድለን።

አበቃሁ 
ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ 

Wednesday, August 7, 2013

''ትምህርት ሚኒስቴር ኢትዮጵያዊ እና ወጥ የሆነ ስርዓተ-ትምህርት በመላ ሀገሪቱ እየተሰጠ እንዳልሆነ እያወቀ ለምን እንዳላየ አለፈው?''



የትምህርት ሚኒስቴር ህንፃ አዲስ አበባ 

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ  ከትምህርት ጋር በተያያዙ የሚነሱ ጉዳዮች በሁለት ጫፍ እና ጫፍ በያዙ አስተሳሰቦች የተሞሉ ናቸው። አንዱ በሀገራችን የከፍተኛ ትምህርት ሽፋን እያደገ ነው የሚለው እና ቀድሞ ወደ ዩንቨርስቲ ይገባ የነበረው የተማሪ ቁጥርን ከአሁኑ ጋር እያነፃፀረ የማቅረብ እይታ ሲሆን ይህ አመለካከት ንግስት የመገናኛ ብዙሃን ጨምሮ የሚስተጋባ ነው። ሁለተኛው አስተሳሰብ ግን ሚዛን የሚደፋ ነው። እርሱም አዎን! የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ቁጥር ጨምሯል።ነገር ግን በመረቁት ተማሪዎች ጥራት፣የስራ ብቃት እና የሉላዊው (ግሎባላይዜሽን) አለም ተወዳዳሪነት አንፃር ስናየው ገና ብዙ የሚቀሩ ስራዎች ለመኖራቸው የማይስማማ ወገን የለም።ይህ ጉዳይ በከፍተኛ ትምህርቶችም ሆነ በቀጣሪ ድርጅቶች ጥናት ብዙ የተባለት ስለሆነ ለጊዜው ስለጉዳዩ ከእዚህ የበለጠ ለማውሳት አልፈልግም። 


የዛሬው ''የትምህርታችን ነገር'' እንዳነሳው ያደረገኝ ግን የዛሬ ነሐሴ 1/2005 ዓም ምሽት  በሸገር (አዲስ አበባ) ኤፍ ኤም ራድዮ በተሰማው ዜና  ''ኢትዮጵያ ያለፈው አመትን የትምህርት ሂደት ገመገመች'' በሚለው ዜና ስር የ ኤፍ ኤም ጋዜጠኛ ለትምህርት ሚኒስትር ዴታው ያነሳው ጥያቄ መሰረታዊ እና የመንግስትን የፖሊሲ ድክመት  የሚያመላክት  ብቻ ሳይሆን ለምን? የሚል ጥያቄን ጥያቄዎች ውስጥ-የሚጭር ሆኖ ስላገኘሁት ነው። 

በመጀመርያ ወቅቱ ክረምቱ ተገባዶ አዲሱ የትምህርት ዘመን የሚጀመርበት ወር- መስከረም እየመጣ ከመሆኑ አንፃር የሸገር ኤፍ ኤም ራድዮ ዛሬ ከዜና ዘገባዎቹ ውስጥ አንዱ መሆኑ ተገቢ እና ወቅታዊ ነው።
በእዚሁ መሰረት በዜና ዘገባው ላይ ትምህርትን በተመለከተ የትምህርት ሚኒስትር ዴታ የተጠየቁት ግን ለእኔ በአግባቡ አለመመለሳቸው ከተሰሙኝ ጥያቄዎች ውስጥ-

ሀ/ መንግስት (ትምህርት ሚኒስቴር) ኢትዮጵያዊ እና ወጥ የሆነ  ስርዓተ ትምህርት በመላ ሀገሪቱ እየተሰጠ እንዳልሆነ እያወቀ ለምን እንዳላየ አለፈው?  

ለ/ በአዲሱ የትምህርት ፖሊስ መሰረት አንዳንድ የትምህርት አይነቶች  ጭራሹን ተዘግተዋል። ለምሳሌ የፍልስፍና እና የታሪክ ትምህርቶች በዲፓርትመንት ከዩንቨርስቲ መሰጠት ቀርተዋል ለምን? የሚሉ ጥያቄዎች ነበሩ።

አንዲት ሀገር ወጥ የሆነ የትምህርት ፖሊሲ የላትም ማለት ምን ማለት ነው?

ከመጀመርያው ጥያቄ (ሀ) ስንነሳ ኢትዮጵያዊ እና ወጥ የሆነ ስርዓተ-ትምህርት በመላ ሀገሪቱ ያለመሰጠቱ ምክንያት እና መንግስት ለምን ይህንን ለማስተካከል እርምጃ አይወስድም? በሚል ሃሳብ ዙርያ ያጠነጥናል። አንዲት ሀገር ወጥ የሆነ የትምህርት ፖሊሲ የላትም ማለት ምን ማለት ነው? ለእኔ የምረዳው የሚከተሉትን ማለት መሆኑን ነው።እነርሱም-

  •  በተለያዩ የሀገሪቱ ቦታዎች የሚኖሩ ዜጎች የተለያየ የትምህርት አሰጣጥ አላቸው።ይህ ማለት ስለ አንድ ነገር አሰራር በተለያየ መንገድ እንዲመለከቱ የተለያየ አመለካከት ይዘው እንዲወጡ ይደረጋሉ ማለት ነው።እነኚህ ተማሪዎች ወደ ዩንቨርሲቲ ሲመጡ ከስር ወጥ የሆነ ትምህርት ስላልያዙ በነገሮች ላይ የጋራ እና ወጥ ሃሳብ ብሎም ውሳኔ ላይ መድረስ አያስችላቸውም። ለምሳሌ በፖለቲካ፣በታሪክ፣በሀገራችን የምጣኔ ሀብት መሰረታዊ ችግሮች እና መፍትሄዎች ላይ ወዘተ የጋራ የመነሻ ግንዛቤ ስለማይኖራቸው ከመጡበት ክልል ወይም ትምህርት ቤት አልያም መምህር አስተሳሰብ ተነስተው ለነገሮች ድምዳሜ ለመስጠት ይቸኩላሉ ማለት ነው። ይህም ውሎ አድሮ ወደተሳሳተ ግንዛቤ እና ድምዳሜ ላይ ያደርሳቸዋል።

እዚህ ላይ ወጥ የሆነ እና ኢትዮጵያዊ ያልሆነ ትምህርት በሀገራችን ያለመሰጠቱ መዘዙ በዩንቨርስቲ ብቻ የሚወሰን እንዳልሆነ መገንዘብ አለብን።
  • ከዩንቨርስቲ በኃላ ወደ ስራ አለም የተሰማሩ  ነገ የሀገራችን ፖሊሲ  አውጪዎች በአንድ ጉዳይ ላይ ለመወሰን ስብሰባ ተቀምጠው የማይስማሙ እና በነገሮች ላይ የጋራ ሃሳብ ማመንጨት ያቃታቸው  የካምፓኒ ሥራ አስክያጆች፣ሚኒስትሮች፣መምህራን ወዘተ ይኖሩናል ማለት ነው። ኢትዮጵያዊ እና ወጥ ያልሆነ ትምህርት አለመስጠት ውጤቱ በአጭር አማርኛ ለመግለፅ ሃገርን በጆግራፍያዊ አቀማመጥ እና በብሄር ከመከፋፈል በከፋ መልኩ ትውልድን እንዳይታረቅ አድርጎ የመግደያ 'መርዝ' ነው።
የሸገር ኤፍ ኤም ጋዜጠኛ የጠየቀው ጥያቄ እጅግ ወሳኝ እና አንገብጋቢ ነው።የተቃዋሚ ፓርቲዎችም ከሚያነሷቸው እጅግ አንገብጋቢ ሃገራዊ ጉዳዮች ውስጥ የእዚህ አይነቶቹን የመንግስት  የትምህርት ፖሊስ ጥመቶችን (መንጋደዶችን) በወቅቱ ነቅሰው አውጥተው እንዲስተካከሉ ተፅኖ መፍጠር ይገባቸዋል።ምክንያቱም ችግሩ ጊዜ ከተሰጠው እና ትውልድን ካጣመመ  በኃላ ለመመለስ ሌላ አንድ መቶ አመት ላለመጠየቁ ምንም ዋስትና የለም። 

ዶ/ር ታዬ ወ/ሰማያት (የቀድሞ የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ሊቀመንበር) የተናገሩትን እዚህ ላይ መጥቀስ ተገቢ ነው።''ዛፍ ተጣሞ ቢያድግ ሌላ ዛፍ በመትከል  በጥቂት አመታት ታስተካክለው ይሆናል። በተሳሳተ የትምህርት ፖሊስ ምክንያት ትውልድ ተጣሞ ካደገ ግን በምን እና በስንት አመት ታስተካክለዋለህ?'' ነበር ያሉት።

የታሪክ እና የፍልስፍና የትምህርት ክፍሎች(ዲፓርትመንቶች) መዘጋት ጉዳይ 

ሁለተኛውን የጋዜጠኛውን ጥያቄ ማለትም ''ለምን የታሪክ እና የፍልስፍና ትምህርት ክፍሎች ከዩንቨርስቲ ተዘጉ?'' ለሚለው ጥያቄ እንደተባለው  የትምህርት ክፍሎቹ ከዩንቨርስቲ ውስጥ ከተባረሩ ጉዳዩን በአሳዛኝነት በማለፍ ብቻ ሳይሆን ተያያዥ ጥያቄዎችን የሚያስነሳ ለመሆኑ እማኝ እንደማይፈልግ እርግጠኛ ነኝ። ጥያቄዎቹም - 
  • ፍልስፍና የሌለው ኅብረተሰ እንዴት ማደግ ይችላል? 
  • ኢትዮጵያዊ ፍልስፍናዎቻችንን ትውልዱ እንዳይማር እና እንዳይመራመር ማድረግ ብሎም ከዩንቨርስቲ የትምህርት ክፍልነት መሰረዝ እና ተማሪዎች እንዳይማሩ ማድረግ ምን አይነት ሃገራዊ  የትምህርት ፖሊሲ ነው? 
  • ፍልስፍና የሌለው ፖለቲካ፣ፍልስፍና የሌለው የኢኮኖሚ ፖሊሲ፣ፍልስፍና የሌለው የማህበረሰብ ፖሊሲ ይዘን እስከመቼ እንኖራለን? በምን ያህል እርቀት ሀገራችንን ያስጉዛል? 

የታሪክን ትምህርት ክፍል መዘጋትን በተመለከተ ግን ጥያቄዬ አንድ እና አንድ ነው። ባለታሪክ ሀገር ኢትዮጵያ የታሪክ ተመራማሪ እና ተማሪ ከሌላት የትኛዋ ሀገር ናት ሊኖራት የሚገባትና የሚታሰብላት?

አበቃሁ 
ጌታቸው 
ኦስሎ  

Saturday, August 3, 2013

''የኢትዮጵያ ቀን'' በ ኦስሎ፣ኖርዌይ የመከበሩ ጥቅም እና ዝግጅቱን የበለጠ ለማሳመር መከናወን የሚገባቸው ተግባራት (አጭር ማስታወሻ)

በኖርዌይ የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ (ኢትዮጵያ ኮሚኒቲ) ''የኢትዮጵያ ቀን'' የተሰኘ የኢትዮጵያ ባህላዊ ምግቦች እና የቡና ማፍላት ስነ-ርአት ያካተተ መርሃ ግብር ዛሬ ሐምሌ 27፣2005 ዓም በኦስሎ ከተማ ''ግሩን ላንድ'' መናፈሻ አካሂዶ ነበር።በቅድምያ ዝግጅቱን ለማዘጋጀት ለተነሳሱት እና ለዝግጅቱ ደፋ ቀና ያሉትን ሁሉ ማመስገን ተገቢ ይመስለኛል።በመሆኑም በጎ ተግባራትን ማበርታት እና ማጎልበት ከሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚጠበቅ ኃላፊነት መስሎ ስለተሰማኝ ይህችን አጭር ማስታወሻ ለመፃፍ ወደድኩ። 


ሀ/  የመርሃብሩ ጥቅም 

 የእዚህ አይነቱ መርሃግብር  ለእኛ ለኢትዮጵያያን  የሚሰጠው ጥቅም እጅግ ከፍ ያለ ነው። ከጠቀሜታዎቹ ውስጥ ጥቂቶቹ -
1/ የኢትዮጵያውያንን ተሰሚነት በሚኖሩበት ሀገር ውስጥ በሚደረጉት ፖለቲካዊ፣ማኅበራዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ ክንውኖች ውስጥ የጎላ ሚና እንዲኖረው ያደርጋል። ይሄውም በምንኖርበት ሀገር ማኅበረሰብ ውስጥ ውሎ አድሮ የተሰሚነት እና የተፅኖ ፈጣሪነት ሚናችንን ከፍ ማድረጉ አይቀርም፣

2/ የኢትዮጵያን ባህል ማለትም አመጋገብ፣አለባበስ፣ወዘተ  በውጭው ማኅበረሰብ ዘንድ ያስተዋውቃል። ይህም የሀገራችንን ሌላውን በጎ ጎን ማለትም በባህላችን፣በታሪካችን እና በማንነታችን ዙርያ የሀገራችንን በጎ ገፅታ ለምንኖርበት ሀገር ለማሳየት ይረዳል። 

3/ በውጭ ለተወለዱ ኢትዮጵያውያን ስለሀገራቸው የበለጠ እንዲያውቁ እና ፍቅር እንዲያድርባቸው ያደርጋል።

 ለ/ በመጪው አመት ዝግጅቱን ይበልጥ ለማሳመር ምን ቢደረግ ጥሩ ነው?


''የኢትዮጵያ ቀን'' ዝግጅት ይበል የሚያሰኝ እና ለወደፊቱም ሁሉም ኢትዮጵያውያን በአግባቡ ሊሳተፉበት እና የእኔነት ስሜትን ልያጎለብቱበት የሚገባ መሆን ይኖርበታል።ለእዚህም እንዲረዳ በመጪው አመት እነኚህ ተግባራት ቢከወኑ ዝግጅቱን የበለጠ ያስውበዋል እነርሱም-
1/ ''የኢትዮጵያ ቀን'' መርሃግብር የማስታወቅያ ሥራ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እንዲሰራ ማበረታታ፣

2/ ከኦስሎ ውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም ቀኑን አስበው ቀድመው ኦስሎ እንዲመጡ ማድረግ እና የማረፍያ ቦታዎችን የኦስሎ ነዋሪዎች እንዲያግዙ ማነሳሳት፣

3/ በመላዋ ኖርዌይ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የንግድ ድርጅቶች የሚተዋወቁበት እና ስፖንሰር የሚያደርጉበት ሁኔታ ማመቻቸት፣

4/ በወጣቶች የሚዘጋጁ የተውኔት (ድራማ) መርሃግብሮችን በበዓሉ ወቅት ማቅረብ፣

5/ በዓመቱ ውስጥ በኖርዌይ ውስጥ ልዩ ልዩ ተግባራት የሰሩ ለምሳሌ በትምህርታቸው ላቅ ያለ ውጤት ያመጡ፣የኖርዌይ መገናኛ ብዙሃንን የሳበ ተግባር የሰሩ ወይንም ሀገራቸውን በተለያዩ በጎ ጎኖች ያስጠሩ ኢትዮጵያውያንን በኮሚቴ አስጠንቶ እና አወዳድሮ ለሽልማት ማብቃት እና 

6/ ለኢትዮጵያውያን እና ለኢትዮጵያ በጎ ያደረጉ ኖርወጅያናውያን የሚሸለሙበት መርሃግብር እና የመሳሰሉት ቢካተቱ ዝግጅቱን የደመቀ እንደሚያደርገው እሙን ነው።

በመጨረሻም  በኖርዌይ፣ኦስሎ የተደረገው የኢትዮጵያ ቀን ዝግጅት ጥሩ ተግባር በመሆኑ አዘጋጁ ኮሚቴ ለመጪው አመትም በበለጠ አቀራረብ እንደሚያዘጋጅ ተስፋ በማድረግ የእዚህ አይነት ዝግጅቶች  ሃይማኖት፣ትውልድ፣ወዘተ የማይለዩ ስለሆኑ ኢትዮጵያውያንን በአንድ ህብረት የማስተሳሰር እና የማስተሳሰብ ኃይላቸው ከፍተኛ ነው።በመሆኑም  ሁሉም በያገባኛል ስሜት ይሆናል የሚለውን ሃሳብ በመስጠት ያጎለብተው ጠቀሜታው ለእራሳችን፣ለልጆቻችን ከፍ ሲል ደግሞ  ለጋራ ቤታችን-ኢትዮጵያችን መሆኑ እሙን ነው።

የኢትዮጵያ ቀን አከባበር በኦስሎ ግሩንላንድ መናፈሻ ፎቶዎች ይመልከቱ። ፎቶ(ጌታቸው)












ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ 

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።