ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, October 29, 2018

የብልሁ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር) የመጀመርያ የአውሮፓ ጉዞ ለምን ወደ ፈረንሳይ ሆነ? (የጉዳያችን ሪፖርታዥ)

ጉዳያችን/Gudayachn
ጥቅምት 20/2011 ዓም (ኦክቶበር 30/2018 ዓም)


የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማርኮን(Emmanuel Macron)እና 
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር)


ኢትዮጵያዊውን ዕውቅ ዲፕሎማት የቀረፀች ፈረንሳይ! 

በ1904 ዓም በቡልጋ ከአለቃ ሀብተወልድ ካብትነህ እና ከወይዘሮ ያደግድጉ ፍልፈሉ የተወለዱት የኢትዮጵያጵያው ስመ ጥር ዲፕሎማት አክሊሉ ሀብተወልድ  አዲስ አበባ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አማርኛ ጠንቅቀው ከተማሩ በኃላ ዘመናዊ ትምህርት ለሶስት ዓመት ዳግማዊ ምንሊክ ትምህርት ቤት እንደተማሩ እና በመቀጠል ወደ ግብፅ እስክንድርያ ከተማ የሚገኘው የፈረንሳይ ሊሴ ትምህርት ቤት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ማጠናቀቃቸውን ታሪካቸው ያስረዳል።ከግብፅ  ለከፍተኛ ትምህርት ያመሩት ወደ ፈረንሳይ ታዋቂው ዩንቨርስቲ ሶቦርን (Sorbonne) ነበር ።በሶቦርን  ዩንቨርስቲ የንግድ ሕግ እና የፖለቲካ ሳይንስ ተምረው ሲጨርሱ ዘመኑ 1928 ዓም ጣልያን ኢትዮጵያን የወረረችበት ወቅት ነበር። 

የፈረንሳይ ትምህርት ውጤት ታላቁ ዲፕሎማት አክሊሉ ሀብተወልድ በፈረንሳይ ሀገር በድፕሎማትነት በመቀጠል በጀኔቭ የኢትዮጵያ ልዑካን መሪ የነበሩት የፊታውራሪ ተክለ ሐዋርያት ተከለ ማርያም ልዩ ረዳት በመሆን በጣልያን ወረራ ወቅት በያኔው የዓለም ማኅበር ፊት የነበረውን የዲፕሎማሲ ውግያ ከንጉሰ ነገስቱ ጋር በመሆን የተፋለሙ  አክሊሉ ሀብተ ወልድ የፈረንሳይ የዲፕሎማሲ ትምህርት ውጤት ናቸው።የአክሊሉ ሀብተወልድ በሃያኛው ክ/ዘመን ኢትዮጵያ በነበራት ዲፕሎማሲ አሻራ ከሱማሌ ድንበር እስከ ኤርትራ ውህደት፣ከጋምቤላ የድንበር ጉዳይ እስከ መካከለኛው ምስራቅ ውስብስብ ዓለም አቀፍ ግንኙነት እስከ የአፍሪካ ህብረት ምስረታ (የከተማ ይፍሩ ጥረት ሳይዘነጋ) የአክሊሉ ሀብተወልድ ምክር ያላረፈበት ቦታ የለም።


የብልሁ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የመጀመርያ የአውሮፓ ጉዞ ለምን ወደ ፈረንሳይ  ሆነ? 


ፈረንሳይ በዲፕሎማሲ ትምህርት ማዕከል መሆን የጀመረችው በ18ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ ነበር።ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ ሲነሳ የፈረንሳይ አስተዋፅኦ መዘንጋት አይቻልም።ስለ ዓለም አቀፍ ሕግ ሲነሳ ከአውሮፓ ተሃድሶ ጋር የሚነሳው የፈረንሳይን አስተዋፅኦ ቸል ማለት ይከብዳል።ኢትዮጵያ ከጣልያን ወረራ በፊት የትምህርት ሥርዓቷን በፈረንሳይኛ ለማድረግ የተጀመሩ ስራዎች እንደነበሩ እና ጣልያን ከኢትዮጵያ መባረር ተከትሎ ኢትዮጵያ የገቡት እንግሊዞች እና በመቀጠልም የአሜሪካ ልዕለ ኃያልነት መጉላት እንግሊዝኛ ቦታውን እንዳስለቀቀው ይነገራል። ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴም የፈረንሳይኛ ተናጋሪም ጭምር ነበሩ። የጣልያንን ወረራ ተከትሎ በጀኔቭ ለዓለም ማኅበር (አሁን የተባበሩት መንግሥታት የተሰኘው) ፊት ቀርበው አቤቱታቸውን ሲጀምሩ  '' ንግግሬን በፈረንሳይኛ ባደርገው በወደድኩ ነበር።ሆኖም ግን ሃሳቤን በሚገባ የማብራራው አማርኛ ስለሆነ በእዚሁ ንግግሬን አደርጋለሁ'' በማለት የጀመሩት ታሪካዊ ንግግርን ለአብነት መጥቀስ ይቻላል።


የዘመናችን ብልሁ መሪ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ (ዶ/ር) የመጀመርያ የአውሮፓ ጉዞ ያደረጉት ወደ ፈረንሳይ ነው።ጠቅላይ ሚኒስትሩ ታሪክ አዋቂ ናቸው።የፈረንሳይ ስረ መሠረትነት፣ታሪካዊ እና ባህላዊ ዳራ ሁሉ ሳይማርካቸው አልቀረም።ከቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ በኃላ ለፈረንሳይ የተሰጠው  ያልሞቀ እና ያልደመቀ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ፍትሓዊ አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ ልታገኝ የምትችላቸው በርካታ የቴክኖሎጂ ሽግግር እና የባሕላዊ ዕሴት አጠባበቅ ጥበቦች ሁሉ በሚገባ አለመቀሰማቸው ሳይቆጫቸው የቀረ አይመስልም። ጠቅላይ ሚኒስትር የፈረንሳይ ጉብኝታቸውን ዛሬ ጥቅምት 19፣2011 ዓም  ሲጀምሩ በሶስት መልኮች ኢትዮጵያ  ከፈረንሳይ የምታገኛቸው ጉዳዮች ላይ ማረጋገጫ ማግኘታቸውን ከፈረንሳዩ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ጎን ለጎን ሆነው በአማርኛ ለዓለም አቀፍ ሚድያ ፓሪስ ላይ በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።  እነርሱም በቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት እድሳት፣የኢትዮጵያ ጦር ማዘመን እና የቦሌ አየር መንገድን በመቶ ሚልዮን ኢሮ ወጪ ማዘመን የሚሉት ይጠቀሳሉ።


ዶ/ር አብይ ልዩ ሰው የሚይደርጋቸው አንዱ መገለጫ ዲፕሎማስን በግልብ ግንኙነት ላይ በተመሰረተ መልክ ሳይሆን የሚመሩት ታሪካዊ ግንኙነትን መሰረት አድርገው ነው።ቅድምያ የሚሰጡትን ከማይሰጡት የመለየት አቅማቸው እጅግ ድንቅ ነው።በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ሲያቀርቡ እና ሲቆጡ እንዲሁም የኢትዮጵያን ግንኙነት በእኩል ልበ ሙሉነት እና ኩሩነት ሲመሩት ያስደምማሉ።ይህ ሁሉ ደግሞ ከድንቅ ፈጠራ ጋር ታክሎበት መሆኑ ሰውየውን ግሩም ዲፕሎማት ያደርጋቸዋል።ይህ አገላለጥ ለአንዳንዶች የተጋነነ መስሏቸው ከሆነ እስካሁን ካዩት የበለጠ ወድፊት ስለሚያዩት ያኔ ይረዱታል።ስልጣን እንደያዙ በሰአታት ውስጥ  ከክልል ከተሞች ወደ ጅጅጋ የሄዱበት እና ሁሉንም የጎረቤት ሀገሮች በመጎብኘት የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲ ያረጋጉበት መንገድ መመልከት፣ ለአመታት ፈገግታ የራቃቸውን የኤርትራ መሪ አቶ ኢሳያስ ሳቅ በሳቅ ያደረጉበት የዕርቅ ሂደት፣አሜሪካንን ያህል ሃያል ሀገር ሄደው ፕሬዝዳንቱን ሳያገኙ በአስር ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖቻቸውን በአሜሪካ አደባባይ አዘምረው የዋሽንግተን ከንቲባን አስደምመው እና የኢትዮጵያን ቀን በእየዓመቱ ለማክበር ቃል እንዲገቡ አድርገው ሹልክ ብለው ዋይት ሃውስን ቁልቁል እያዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን ጳጳሳት ይዘው ወደ ሀገራቸው እብስ ያሉበት መንገድ ሁሉ ድንቅ ዲፕሎማሲ፣ድንቅ የአፈፃፀም ችሎታ ነው። ማድነቅ እና ማሞገስ ካለብን ዓብይ በሕይወት እያለ አለማድነቅ እና አለማመስገን አለመታደል ነው።ይህ ብቻ አይደለም የተባበሩት አረብ ኤምሬት ልዑል በክረምቱ ወራት ኢትዮጵያን ሲጎበኙ ከቦሌ አየር ማረፍያ የቦሌ ኢንዱስትሪ ፓርክ ሲያስጎበኙ እራሳቸው መኪናቸውን እያሽከረከሩ ያስጎበኙበት ምላሽ ልዑሉ ቀደም ብሎ ጠቅላይ ሚኒስትሩን በሀገራቸው በተመሳሳይ መንገድ እየነዱ ከወሰዷቸው በኃላ የኢትዮጵያን የሰላም ሀገርነት የገለጡበት ድንቅ እኩል ምላሽ እንደሆነ የሚናገሩ አሉ።


ዶ/ር አብይ ወደ ፈረንሳይ የመጀመርያ ጉዞ ሲያደርጉ ታሪካዊ ዳራውን እና መጪውን የፈረንሳይ አካሄድ በሚገባ አላዩትም ማለት አይቻልም። ፈረንሳይ በኢትዮጵያ ያለፈ የአርባ ዓመታት የፖለቲካ ሹክቻ ውስጥ እጇ አልተነከረም።በ1830 ዓም ከአጤ ምንሊክ አባት ከንጉስ ኃይለመለኮት ጋር ግንኙነት የጀመረችው ፈረንሳይ የዲፕሎማሲ ግንኙነት በይፋ የጀመረችው በ1897 ዓም በአፄ ምንሊክ ዘመነ መንግስት ነው።የፓርስን ከተማ ከደብረ ብርሃን ከተማ ጋር  ታሪካዊ ቁርኝት የፈጠረችው ፈረንሳይ፣ ለኢትዮጵያ ከሰባት መቶ ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያለው የመጀመርያ የባቡር  መስመር ዝርጋታ ከአዲስ አበባ እስከ ጅቡቲ የተዘረጋው ከአንድመቶ ዓመት በፊት ነበር።በአሁኑ ወቅት ከሰላሳ በላይ የፈረንሳይ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ውስጥ በሥራ ላይ መሆናቸው ሲታወቅ በአሁኑ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት ተጨማሪ ባለ ሀብቶች ወደ ኢትዮጵያ እንደሚገቡ ይጠበቃል።



ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ እና አንጌላ ሜርክል 

ይህ በእንዲህ እንዳለ የቻይና ግሎባል ኔትዎርክ አፍሪካ የተሰኘው ቴሌቭዥን ማምሻውን የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጉብኝት አስመልክቶ ሲዘግብ ፈረንሳይ ከእዚህ በፊት በመካከለኛው እና ምዕራብ አፍሪካ ላይ አተኩሮ የነበረው ዲፕሎማሲ አሁን ወደ ምስራቅ አፍሪካ መዞር የመጀመር አዝማምያ መታየቱን ገልጧል።የዜና ዘገባው እንደገለጠው ፈረንሳይ ከሩዋንዳ ጋር የነበራት ግንኙነት በመቀዛቀዙ አሁን ትኩረቷን ለኢትዮጵያ እና ኬንያ ማድረግ መጀመሯን ምልክቶች መታየታቸውን ያብራራል።በእዚሁም መሰረት የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማርኮን (Emmanuel Macron) በሳምንታት ውስጥ ኢትዮጵያን ሊጎበኙ እንደሚመጡ ዘግቧል።በዛሬው የጠቅላይ ሚኒስትር ጉብኝት ፈረንሳይ ለኢትዮጵያ የቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት እደሳ፣ከአንድ መቶ ሚልዮን ዩሮ በላይ የቦሌ ዓለም አቀፍ አይሮፕላን ለማዘመን፣የኢትዮጵያ ጦር ሰራዊት ለማዘመን ስልጠና እና ትጥቅ እና የዓለም ባንክ ከሚሰጠው በተጨማሪ በሁለትዮሽ ግንኙነት ፈረንሳይ ለኢትዮጵያ የምትሰጠው ዳጎስ ያለ ገንዘብ እንደሚኖር ተሰምቷል።እነኝህ ስጦታዎች ዝርዝር ጉዳይ የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት በኢትዮጵያ በቅርቡ በሚኖራቸው የኢትዮጵያ ጉብኝት ወቅት እልባት እንደሚያገኙ ይጠበቃል።

ከሃያ ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን የሚታደሙበት የጀርመኑ ስብሰባ 


ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ከፈርንሳይ በመቀጠል የሚጎበኙት የአውሮፓ ሀገር ጀርመን ነች።ጀርመን ከኢትዮጵያ ጋር ረጅም የዲፕሎማሲ ግንኙነት ያላት ሀገር ስትሆን ከቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዘመን ጀምሮ በቴክኒክ ትምህርት በቀዳሚነት እገዛ ከሚያደርጉ ሀገሮች ጀርመን ተቀዳሚ ነች።በቅርቡም በኢትዮጵያ የቮልስቯገን መኪና መገጣጠምያ ኢትዮጵያ ውስጥ ለመክፈት ጀርመን ፍላጎት እንዳላት የኩባንያው ኃላፊዎች በቅርቡ በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት አስታውቀዋል።


የጀርመኗ መራሂ መንግስት አንጌላ መርክል በኢትዮጵያ አሁን እየተካሄደ ላለው ለውጥ ከፍተኛ ድጋፍ ለማድረግ ፍላጎት አላት።ጀርመን ከኢንዱስትሪ ልማት በተጨማሪ በንግድ ክህሎት (ኢንተርፕረነርሽፕ) ስልጠና እንዲሁም በቤቶች ግንባታ ከፍተኛ የቴክኖሎጂ ደረጃ ላይ ትገኛለች።እነኝህን ክህሎቶች ደግሞ በ''ጂ ቲ ዜድ'' እና የግል ድርጅቶቿ ወደ ኢትዮጵያ የማስተላለፍ ስራዎች በመጠኑ ጀምራለች።ከእዚህ በተጨማሪ በጀርመን የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ያላቸውን ሙያ ለሀገራቸው እንዲያፈሱ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት አይነተኛ በር ይከፍታል።ከእዚህ ጋር ተያይዞ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የጀርመንን የቴክኒክ አቅም በጣና ሀይቅ ላይ ለተከሰተው የእንቦጭ አረም መላ ለመዘየድ የጀርመን ኩባንያዎችን ሊያነጋግሩ እንደሚችሉ ይገመታል። 


በመጨረሻም የጠቅላይ ሚንስትር የጀርመን ጉብኝት ትልቁ ቦታ የሚይዘው ከሃያ ሺህ በላይ ኢትዮያውያንን የሚያገኙበት የፍራንክፈርት ስብሰባ ነው።በእዚህ ስብሰባ ከመላው አውሮፓ የሚሰበሰቡ ኢትዮጵያውያን እንደሚገኙ ሲታወቅ በስብሰባው ላይ  በርካታ ሃገራዊ ጉዳዮች ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚነሱ እና ጠቅላይ ሚኒስትሩም ማብራርያ እንደሚሰጡ ይጠበቃል።ወደጀርመን ተጉዘው ከጠቅላይ ሚኒስትር  ጋር መገናኘት ለሚፈልጉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚያደርጉት የጋራ ስብሰባ ቀን፣ሰዓት እና የስብሰባው ስፍራ  ከእዚህ በታች ይመልከቱ።



የስብሰባ ቀን Date: 31st October 2018
የስብሰባ መጀመርያ ሰዓት Time: 13:00 (1:00pm)
የስብሰባው ቦታ እና አድራሻ  Venue: Commerzbank Arena, Morfelder Landstrasse 362, 60528 Frankfurt am Main, Germany

ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Saturday, October 27, 2018

መጽሐፈ ሄኖክ ለአውሮፓ ህዳሴ ምክንያት ነው።አሁንም በመፅሐፉ ዙርያ ከሁለት መቶ ሃምሳ የማያንሱ ሊቃውንት ጉባኤ ቫቲካን ይቀመጣሉ (ኦድዮ)

ቪድዮ 1 - መፅሐፈ ሔኖክ 
ምንጭ = ሸገር ኤፍ ኤም Sheger FM 102.1


ድዮ 2- መጽሐፈ ሄኖክ ማብራሪያ፣ ትርጉም እና ትንተና በቀሲስ ዶክተር ሐይለየሱስ አለባቸው ማኅበረ ቅዱሳን ባዘጋጀው የጥናት እና ምርምር  መርሐግብር ላይ ያቀረቡት። 

ምንጭ - ማኅበረ ቅዱሳን  ቴሌቭዥን


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Wednesday, October 24, 2018

ወደ እንግሊዝኛ የተመለሰው የደራሲና ጋዜጠኛ ሙሉቀን ተስፋው 'የጥፋት ዘመን' የተሰኘው መፅሐፍ ምረቃ በኦስሎ፣ኖርዌይ እና በዓማራ ብሔርተኝነት ዙርያ የሚነሱ ጥያቄዎች

ጉዳያችን/Gudayachn
ጥቅምት 14/2011 ዓም (ኦክቶበር 24/2018 ዓም)




መነሻ 

የኢትዮጵያ ፖለቲካ በአደገኛ መልኩ በብሔርተኝነት (በጎሳ) ፖለቲካ መናጥ የጀመረው ህወሓት መራሹ ኢህአዴግ አዲስ አበባን በ1983 ዓም ከተቆጣጠረ ጀምሮ ነው።አንዳንዶች የብሔር አደረጃጀቶች ቀደም ብለው መኖራቸውን በማንሳት የኢትዮጵያን የብሔር ፖለቲከኞች ድምፅ መሰማት የጀመረው ቀደም ብሎ እንደነበር ያወሳሉ።ሆኖም ግን የ19ኛው ክ/ዘመን እና የ20ኛው ክ/ዘመን የኢትዮጵያ የፖለቲካ፣ማኅበራዊ እና ምጣኔ ሀብታዊ አደረጃጀት እና የከተሞች መፈጠር የብሔር (የጎሳ) ፖለቲካን በእጅጉ ከማደብዘዝ አልፎ  ኢትዮጵያ ከብሄር ፖለቲካ በተለየ በሀሳቦች ዙርያ መደረጃት ወደ ርዕዮተ ዓለማዊ የአስተሳሰብ ልዕልና የደረሰች ሆና ነበር።

ጣልያን ሀገራችንን ለሁለተኛ ጊዜ በ1928 ዓም ከወረረ በኃላ እስከ 1935 ዓም በነበረው ቆይታ ኢትዮጵያን ለመከፋፈል የተጠቀመበት ብቸኛ እና ዋነኛ መንገድ ሀገሪቱን በጎሳ የመከፋፈል ሥራ ነበር።ጣልያን የመከፋፈል ሥራ ብቻ አይደለም የሰራው ከአድዋ ዘመቻ ጀምሮ እስከ ማይጨው ድረስ ለሽንፈቱ እንደ አንድ ምክንያት የሚያስበው በኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ላይ ጎልተው ይታያሉ ያላቸውን የዓማራ አካባቢ ተወላጆች የሆኑት ላይ ሌላው ሕዝብ ጥላቻ እንዲያድርበት ቅስቀሳ የማድረግ ሙከራ ነበር። ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ ይህንን የአምስት ዓመት የጣልያን መርዝ ለማምከን ከፍተኛ ሥራ ሰርተዋል።ከሥራዎቻቸው ውስጥ በሁሉም ክፍለ ሀገር ዋና ከተሞች በእኩል የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መክፈት፣ካለ ምንም ማዳላት ከሱማሌ  እስከ አፋር፣ከምፅዋ እስከ ሞያሌ የገበሬውን ልጆች ለወላጆች ቀለብ እንዲሰጥ እያደረጉ አዲስ አበባ የአዳሪ ትምህርት ቤት አስገብቶ ማስተማር እና ዘር፣ጎሳ የማይለዩ የኢንዱስትሪ ከተሞች ለምሳሌ እንደ ወንጂ ያሉትን መመስረት የሚጠቀሱ ነበሩ።

በ1967 ዓም ዘውዳዊው ስርዓት በወታደራዊ መንግስት ሲቀየር ለውጡን ተከትሎ የተነሱት ሹክቻዎች መነሻቸው ርዕዮተ ዓለማዊ እና የነበረ እና ያልነበረ መደብ በመፍጠር ዙርያ እንጂ ብሔርን መሰረት ያደረጉ አልነበሩም።አንድ መቶ ሀያ አባላት የነበሩት የደርግ ምክር ቤት ከሁሉም የኢትዮጵያ ክፍል የተውጣጡ ኢትዮጵያን ያስቀደመ  መፈክሩም ''ካለምንም ደም ኢትዮጵያ ትቅደም'' የሚል ነበር።

ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው የብሔር ፖለቲካ በተደራጀ እና መንግስታዊ ቅርፅ ይዞ የወጣው ህወሓት መራሹ የኢህአዴግ መንግስት በ1983 ዓም በሽግግር መንግስት ሲመሰረት ነው።እስከ 1997 ዓም ድረስም የብሔር ፖለቲካ እንደፈለገ በሕዝቡ ውስጥ ለመስረፅ አልቻለም።ለእዚህ ዋናው ምክንያት ደግሞ ስር መሰረት ያለው ጠንካራ ማኅበራዊ እሴት በቀላሉ ሊሸረሸር ባለመቻሉ ነበር። ሆኖም ግን ይህ ሁኔታ ከ1990ዎቹ መጨረሻ እና 21ኛው ክ/ዘመን መጀመርያ ላይ የጎሳ ፖለቲካ  የኢትዮጵያን ህልውና የሚፈታተን ጉዳይ እየሆነ መጣ።

በሀያ አንደኛው ክ/ዘመን መጀመርያ ላይ የተጠናከረ የብሔርተኝነት እንቅስቃሴዎች ከታየባቸው ውስጥ የኦሮሞ እና የዓማራ  የብሔርተኝነት እንቅስቃሴዎች ናቸው።እንቅስቃሴዎቹ  የብሔር ፖለቲካ ጠበቃ ነች ያለውን ህወሓትን እራሱን ከማነቃነቅ በላይ በእራሱ በኢህአዴግ ተበልጦ ከስልጣኑ እንዲወርድ ሆኗል።ይህ ማለት ግን የለውጥ ኃይሉ ምንም ኢትዮጵያዊነት ቀዳሚ አጀንዳው ቢሆንም አደረጃጀቱ ግን አሁንም ብሄርን ያማከለ መሆኑ ይታወቃል።

የጥፋት ዘመን የተሰኘው መፅሐፍ በዓማራ ብሔርተኘንት ላይ አዲስ መነቃቃት ፈጥሯል።


ይህ በእንዲህ እያለ ነው የጋዜጠኛ እና ደራሲ ሙሉ ቀን 'የጥፋት ዘመን' የተሰኘው መፅሐፍ በሀገር ውስጥ እና በውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዘንድ መነበብ ጀመረ።መፅሐፉ ከወልቃይት የማንነት ጥያቄ ጋር እና በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ''ዓማራ'' ናችሁ በመባል የተፈናቀሉት ኢትዮጵያውያን ጉዳይ ጋር ተያይዞ ከፍተኛ የብሔርተኝነት ስሜት ተቀጣጠለ።በሌላ በኩል በኦሮምያ ከነበረው ሕዝባዊ አመፅ ጋር በተያያዘ በህወሓት የሚታዘዙ ወታደሮች ግድያ አንፃር በኢትዮጵያ የብሔር ፖለቲካ መቀጣጠሉ እንደ አንድ ስልት ብቻ ሳይሆን ከምር የእራሱ የሆነ አስፈሪ ቅርፅ ያዘ።ህወሓትም ትግራይ ላይ ለመቆየትም ሆነ ሕዝቡን በሰብዓዊ ጋሻነት ለመጠቀም  የብሔር ፖለቲካን ማስፋፋት ብቻ ሳይሆን የምዕራብ ትግራይ ነዋሪ አዛውንቶች እና አሮጊቶች በሽሬ ከተማ ክላሽ ጠብመንዣ እያስያዘ ያስፎክር ጀመር።

በዓማራ አንፃር የሚነሳው የብሔርተኝነት ጥያቄ አስመልክቶ ደራሲ እና ጋዜጠኛ ሙሉቀን ጨምሮ የዓማራ ብሔራዊ ንቅናቄ የሚሉት አንድ ጉዳይ አለ።ይሄውም የሕልውና ጉዳይ ስለሆነ የብሔርተኝነት እንቅስቃሴው አስፈላጊ ሆነ  የሚል ነው።እዚህ ላይ ጋዜጠኛ ሙሉቀን ''የጥፋት ዘመን'' በተሰኘው መፅሐፍ ላይ ያቀረባቸው  ዓማራ በመሆናቸው ብቻ በግፍ የተገደሉ፣የተሰደዱ እና አካላቸውን ያጡ ኢትዮጵያውያን ታሪክ እጅግ ልብ የሚነካ እንደ ኢትዮጵያዊነትም የተፈፀመው ጉዳይ አሳፋሪ ነው።ይህ ማለት በመጠን ይለያይ እንጂ የእልቂት ድግስ በኦሮሞ፣ኮንሶ፣ራያ፣ጋምቤላ እና ሱማሌ ሁሉ ተፈፅሟል።የአንዱ ከአንዱ የሚከፋበትን መንገድ ለመግለጥ በርካታ ምክንያቶች መዘርዘር ይቻል ይሆናል።

የብሔር ፖለቲካ መለጎምያ ካልተበጀለት  መጨረሻውን የሚያውቀው የለም።

አሁን ጥያቄው አንድ ነው።ይሄውም መቼ ነው ኢትዮጵያ ያለፈ የቂም ቁስል እያመረቀዘ ከሚጎዳት አዙሪት የምትወጣው?  የሚለው ነው።ብዙዎች የዓማራ እንቅስቃሴ ከሌሎች የብሔር እንቅስቃሴዎች የተሻለ የሚያደርጉበት ዋናው ምክንያት ኢትዮጵያዊነት ላይ ጥያቄ የማያነሳ ብቻ ሳይሆን  የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማን ብቻ የሚጠቀም መሆኑ ነው።ይህ ማለት ግን በብሄር ፖለቲካ ዙርያ አደገኛ ግብ ላይ ጥያቄ ዛሬም የለም ማለት አይደልም።ከጥያቀዎቹ ውስጥ አንዱ ዛሬ እንደዋዛ የተጀመረ የጎሳ ፖለቲካ ነገ ለልጆቻችን ብቻ አይደለም አሁን ላሉት አመራሮችም ለመመለስ ቢያስቡም እራሳቸውን በጠላትነት የሚያስፈርጃቸው መሆኑን ባሳብን ጊዜ ሁሉ ነገር በጊዜ መጠናቀቅ እንዳለበት አመላካች ነው።የብሔር ፖለቲካ ሲጀመር ብዙ ሰው ይከተለው እንጂ ወደ መደምደምያው ላይ በእኛ እና በእነርሱ  መካከል ያለ ልዩነት እንዳይፈጥር ያሳስባል።ይህንን ከህወሓት እና ከኦነግ መረዳት ይቻላል።ህወሓት በትግራይ ተማሪዎች ማኅበር አዲስ አበባ ላይ የተጠነሰሰው የብሔር ፖለቲካ ትግራይ ገበሬ ላይ ሲደፋ ሕዝቡን ህወሓት ከጠበቀው በላይ ብሄርተኛ አድርጎ ያወጣዋል ብሎ አልገመተ ይሆናል።አልያም ሲያስቡት በፈለጉት ደረጃ ሲደርሱ መልሰው የምያበርዱት መስሏቸው ይሆናል።ሆኖም ግን ይህ ሊሆን አልቻለም።የብሔር ፖለቲካ ክፋቱ በፈለጉ ጊዜ ልመልስህ ብለው ቢያስቡም የሚያመልጥበት ጊዜ አለ።የብሔር ፖለቲካ መለጎምያ ካልተበጀለት  መጨረሻውን የሚያውቀው የለም። ሀገር ይዞ ወዴት እንደሚያደርስ ለመገመትም ከባድ ነው።

በመጪው ቅዳሜ፣ጥቅምት 17፣2011 ዓም ( ጥቅምት 27፣2018 ዓም) በኦስሎ ከቀኑ 14.30 ጀምሮ በALNAFETGATA 2 (አንደኛ ፎቅ)   የሚመረቀው የጋዜጠኛ እና ደራሲ ሙሉቀን ''የጥፋት ዘመን '' የተሰኘው መፅሐፍ  የእንግሊዝኛ  ትርጉም ''The Amhara Holocaust'' አማርኛ ለማይናገረው የውጭው ዓለም እና በውጭ ለተወለዱ ኢትዮጵያውያን የጎሳ ፖለቲካ የደረሰበትን እጅግ አደገኛ ደረጃ አመላካች ነው።

በመጨረሻም ከእዚህ በፊት በአማርኛ የታተመውን  የመፅሐፉን ይዘት ተከትሎ ወንጀሉን የፈፀሙ ግለሰቦች ዛሬም ኢትዮጵያ ውስጥ እና በውጭ የመኖራቸውን ያህል ተከታታይ የማጣራት ሥራ አከናውኖ ዓለም አቀፍ እና የሀገር ውስጥ የእስር ትእዛዝ እንዲወጣ በማድረግ ድርጊቱ ለትውልድ አስተማሪ እንዲሆን መደረግ አለበት የሚሉ የመኖራቸውን ያህል፣ ያለፈ ቂምን ትቶ የወደፊቱ ላይ ማተኮር  የሚሉ ኢትዮጵያውያንም አሉ።የሚናፈቀው አሁንም ግን ኢትዮጵያዊነት የነገሰባት፣እኩል ተጠቃሚነት በሕግ የተደነገባት ሀገር ማየት መሆኑን ሁሉንም ያስማማል።


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Monday, October 22, 2018

የኢትዮጵያ ትረስት ፈንድ በይፋ ስራውን ጀመረ! (የሁለት ደቂቃ ማስታወቂያ) Ethiopian Diaspora Trust Fund (EDTF) officially Launches! (2 minutes video adv.)

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ አህመድ በክረምቱ የምክር ቤት ዓመታዊ ሪፖርት እና የ20111 ዓም በጀት ዕቅድ ሲያቀርቡ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በቀን አንድ ዶላር በሀገር ቤት ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የልማት ፕሮጀክቶች እንዲሰጡ በጠየቁት መሰረት ዓለም አቀፍ የፈንዱ አስተባባሪዎች ተሹመው ኮሚቴው በእንቅስቃሴ ላይ መሆኑ ይታወቃል።ዛሬ ሰኞ፣ጥቅምት 12፣2012 ዓም የትረስት ፈንዱ በኦፊሴል ስራውን መጀመሩ ለማወቅ ተችሏል።የትረስት ፈንዱ ድረ ገፅ https://www.ethiopiatrustfund.org/ ሲሆን ይህንን ገፅ በመክፈት በቀጥታ መርዳት ይቻላል።የትረስት ፈንዱ የመጀመርያ ማስታወቂያ ቪድዮ ከስር ይመልከቱ።


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Is Ethiopia East Africa’s emerging giant? CNBC Africa talks with the new generation of Ethiopia

Video source = 


Published on Oct 17, 2018

ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Wednesday, October 17, 2018

በአቡነ ሕርያቆስ የተፃፈው ''ፍኖተ ቤተ ክህነት ወቤተ መንግስት'' የተሰኘው መፅሐፍ ቅዳሜ አዲስ አበባ ላይ ይመረቃል (ጉዳያችን ዜና)


ጉዳያችን / Gudayachn Exclusive
ጥቅምት 8/2011 ዓም (ኦክቶበር 18/2018 ዓም)

መቀመጫቸውን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አውሮፓ አህጉረ ስብከት በኖርዌይ፣ኦስሎ መካነ ቅዱሳን የቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አድርገው፣ የአቡነ ኤልያስ ረዳት ጳጳስ እና የደብሩ አስተዳዳሪ በመሆን በማገልገል ላይ የሚገኙት አቡነ ሕርያቆስ የፃፉት ''ፍኖተ ቤተ ክህነት ወቤተ መንግስት'' የተሰኘው አዲስ መፅሐፍ በመጪው ቅዳሜ ጥቅምት 10፣2011 ዓም አዲስ አበባ አራት ኪሎ በሚገኘው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አዳራሽ ከቀኑ 8ከ 30 ጀምሮ እንደሚመረቅ ለማወቅ ተችሏል።የመፅሐፉ አዘጋጅ እና ፀሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ በአሁነ ሰዓት ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ አዲስ አበባ የሚገኙ መሆኑ የታወቀ ሲሆን  በመፅሐፋቸው ምረቃ ላይ መፅሐፉን አስመልክቶ ማብራርያ እንደሚሰጡም ለማወቅ ተችሏል።በአሁኑ ወቅት የመፅሐፉ ሕትመት ጥቂት ስለሆነ  በምረቃው ስነ ስርዓት ላይ ቀድመው የመጡ ብቻ መፅሐፉን ለመግዛት የሚችሉ መሆኑ ተሰምቷል።

በእዚሁ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ ከውጭ ሀገር የተለያዩ አህጉረ ስብከቶች እና ከሀገር ቤትም ከተለያዩ ሀገረ ስብከቶች በመጪው ሰኞ ጥቅምት 12/2011 ዓም በሚጀመረው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ላይ ለመገኘት ወ\ደ አዲስ አበባ ከሄዱት ብፁዓን አባቶች ውስጥ አቡነ ኤልያስን ጨምሮ ሌሎች የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት፣የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ መምህራን እና ደራስያንም ጭምር  የሚታደሙበት የመፅሐፍ ምረቃ መርሐ ግብር እንደሚሆን  ለማወቅ ተችሏል።

በመሆኑም በሀገር ቤት የሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታዮችም ሆኑ ኢትዮጵያውያን በሙሉ  በምረቃው ስነ ስርዓት ላይ እንዲገኙ ተጋብዘዋል።

''ፍኖተ ቤተ ክህነት ወቤተ መንግስት'' የተሰኘው  መፅሐፍ  ይዘት በተመለከተ በመጠኑ የተጠቀሰበትን ፅሁፍ ለማንበብ ይህንን  ይጫኑ። 
ገብርኤል ኃያል 



ጉዳያችን GUDAYACHN 

 www.gudayachn.com

Monday, October 15, 2018

የአዲስ አበባ ወጣቶችን በጅምላ ያሳፈሱ ስውር የፖሊስ አመራሮች፣ከጀርባ የሚገፉ ፅንፈኛ ጎሰኞች ተለይተው ለፍርድ ይቅረቡ! (ጉዳያችን)

ጉዳያችን/ Gudayachn
ጥቅምት 6/2011 ዓም  (ኦክቶበር 16/2018 ዓም)
  • ማን ነህ? ከየት መጣህ? የማያውቀው የአዲስ አበባ ወጣት አዲስ አበባን በጎጥ መስፈርት መለካትን ተቃወመ።ተቃውሞው መደረጉ በጎጥ ስም በሚስጥር የተደራጁ እና በፖሊስ መዋቅር ውስጥ የተሰገሰጉ እና ከባህር ማዶ የመጡ የመንግስት ሆቴል ተቀላቢዎችን አደናገጠ።
  • ወጣቶቹን ከይቅርታ ጋር ፍቱልን! ያሰሩት የጎሳ አድናቂዎች ለፍርድ ይቅረቡ! 
  • የዶ/ር ዓብይ መንግስትም በፍጥነት በፖሊስ ውስጥ የተሰገሰጉ ፀረ ኢትዮጵያ አላማ የሚያራምዱ ''የጭቃ ውስጥ እሾሆችን'' መንጥሮ ማውጣት አለበት::
በቅርቡ በቡራዩ እራሳቸውን የቄሮ እንቅስቃሴ እና የኦነግ ደጋፊ መሆናቸውን የሚናገሩ ወጣቶች የቡራዩ ዙርያ ነዋሪዎችን በስለት ጨምሮ በርካቶች በምሽት ተጠቅተዋል።ከአስር ሺህ በላይ የሚሆኑ ነዋሪዎች ተፈናቅለዋል (የተፈናቀሉት ከከፍተኛ የስነ ልቦና ችግር ጋር መመለሳቸው ተነግሯል)።ይህ ድርጊት ኢትዮጵያውያንን ከሀገር ውስጥ እስከ ውጭ ድረስ ልብ የነካ ሃዘን አሳድሯል።ይህንን ድርጊት የፈፀሙት እነማን እንደሆኑ በቡድንም ሆነ በድርጅት ወይንም በግለሰብ ደረጃ የምርመራው ውጤት እስካሁን አልተገለጠም።ለምን? ከስድስት መቶ በላይ በቡራዩ ዙርያ ጥቃት የፈፀሙ እና የተሳተፉ ታስረዋል የሚል ዘገባ ፖሊስ ሰጥቷል።ሆኖም ምርመራው የድርጊቱን ፈፃሚዎች ማንነት አልተገለጠም።ይህ በእንዲህ እያለ ነው የአዲስ አበባ ወጣቶች ፍትህ ለአዲስ አበባ በሚል በመስቀል አደባባይ  ሰልፍ የወጡት።
 
ፎቶ =የአዲስ አበባ ወጣት ከአዲስ አበባ ውጭ ለመጡ የኦነግ ደጋፊዎች ምግብ በነፃ ሲያድል

በአዲስ አበባ የቡራዩን ጥቃት ተከትሎ በተደረገው ተቃውሞ ሰልፍ ላይ ጎሳ የለሹ የአዲስ አበባ ነዋሪ፣ማን ነህ? ከየት መጣህ? የማያውቀው የአዲስ አበባ ወጣት አዲስ አበባን በጎጥ መስፈርት መለካትን ተቃወመ።ተቃውሞው መደረጉ በጎጥ ስም በሚስጥር የተደራጁ እና በፖሊስ መዋቅር ውስጥ የተሰገሰጉ እና ከባህር ማዶ የመጡ የመንግስት ሆቴል ተቀላቢዎችን አደናገጠ።በመሆኑም ሰልፉ ከተጠናቀቀ በኃላ የአዲስ አበባን ወጣት ማፈስ ተያያዙት።አፈሳው የተከናወነው ሰልፉ ካበቀ ሰዓታት በኃላ በምሽት ሲሆን ቀጣይ አፈሳው ሰልፉ ካበቃ ከቀናት በኃላ ሁሉ ነበር።

እስካሁን ፖሊስ ባመነው መሰረት ከአንድ ሺህ ሁለት መቶ በላይ ወጣቶች መታፈሳቸው የተሰማ ሲሆን  የፈድራል ፖሊስ እና የአዲስ አበባ ፖሊስ የሰጠው መግለጫ እርስ በርሱ የሚጋጭ ነው።አንድ ጊዜ ከሽሻ ቤት ያፈሱ መሆናቸውን ሲናገሩ፣በሌላ በኩል ደግሞ ስልጠና ለመስጠት ነው የሚል መግለጫ በመስጠት የሚሉት የጠፋቸው ስውር የጎሳ ፖለቲካ አራማጅ የሕግ አስከባሪዎች የሌለ ሕግ ሊያስተምሩን ሲዳዳቸው ተስተውሏል። ይህ ብቻ አይደለም።የቡራዩ ግጭት ፈፃሚዎች ለፍርድ ይቅረቡ።የሚል ጥያቄ እንደሚነሳ የፈሩት የጎጥ አራማጆች ወጣቶቹን ወደ ጦላይ ማሰልጠኛ ወስደው አጎሯቸው።አንድ ሰው በፖሊስ ከተያዘ ፍርድ ቤት ቀርቦ ወንጀሉ ሊነገረው ይገባል።በአዲስ አበባ ወጣቶች ላይ የተፈፀመው ግን ታፍሰው ስልጠና መስጠትም ሆነ እንዲያርም መብት ባልተሰጠው ፖሊስ በእራሱ መብት ጦላይ አጉሮ ከቤተሰብ ነጥሎ እያሰቃየ መሆኑ ነው የከፋው ወንጀል።

ይህ ሁሉ ሲሆን በየትኛውም የሕግ አግባብ ድርጊቱ ህገ ወጥ መሆኑን የሚያውቀው የአቃቢ ሕግም ሆነ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ አንዳች እርምጃ አለመውሰዳቸው  ከፍተኛ ቁጣ በአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ከተሞችም ቀስቅሷል።አሁን ወጣቶቹን መፍታት ብቻ አይደለም።ይህንን በህገወጥ መንገድ ወጣቶቹን በማጎር ተግባር ላይ የተሳተፉ በሙሉ  ምርመራ ተደርጎባቸው ለፍርድ መቅረብ አለባቸው።ለተግባራዊነቱም ሁሉም ኢትዮጵያዊ በአንድነት መቆም አለበት።የዶ/ር ዓብይ መንግስትም በፍጥነት በፖሊስ ውስጥ የተሰገሰጉ ፀረ ኢትዮጵያ አላማ የሚያራምዱ ''የጭቃ ውስጥ እሾሆችን'' መንጥሮ ማውጣት አለበት።ከእዚህ በተጨማሪ ለሃያ ሰባት ዓመታት የአዲስ አበባ ሕዝብ የተነፈገውን የአዲስ አበባ ፖሊስ ቢሮ ለከተማው መስተዳደር የመመልስ መልካም ጅምር ተፋጥኖ ሕዝብ የራሱን ፀጥታ በራሱ እንዲጠብቅ መደረግ አለበት።አዲስ አበባ ሞግዚት ሰልችቷታል።ከእዚህ በፊት የነበረ የአዲስ አበባ ዝምታ በጎሳ ለሚራኮት ግጭት ላለመወገን እንጂ በኢትዮጵያዊነት መንፈስ ማንም ጋር የሌለ አንድነት እና ተጋድሎ አዲስ አበቤ ውስጥ ከልዩ ፈጠራ ጋር እንዳለ አለመዘንጋት ጥሩ ነው። አሁንም ጊዜው አልረፈደም።ወጣቶቹን ከይቅርታ ጋር ፍቱልን! ያሰሩት የጎሳ አድናቂዎች ለፍርድ ይቅረቡ! ዶ/ር ዓብይ ይህንን ያደርጋሉ ብለን እናምናለን።

ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴ ''አዲስ አበባ ቤቴ'' 


ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com

Monday, October 8, 2018

በኖርዌይ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያ ኤምባሲ በአይነቱ ልዩ ስብሰባ ጠራ።ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ከሁለት ሳምንት በኃላ ወደ አውሮፓ ይመጣሉ (ጉዳያችን ዜና)

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር  ዋና መስርያ ቤት 
ጉዳያችን/ Gudayachn
መስከረም 28/2010 ዓም (ኦክቶበር 8/2018 ዓም)

የለውጡ ነፋስ ወደ አውሮጳ እየደረሰ ነው

በኢትዮጵያ በ2010 ዓም አጋማሽ በኃላ በተፈጠረው የለውጥ ነፋስ ወደ አውሮፓ እየደረሰ ነው።ላለፉት ሀያ ስምንት ዓመታት በኢትዮጵያ ጉዳይ ግንባር ቀደም በመሆን የኢትዮጵያን ጉዳይ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ከብራሰልስ እስከ ለንደን፣ከጀኔቭ እስከ ኦስሎ ድምፁን  ከማሰማት አልፎ በተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮች ተሳትፎ ሲያደርግ የነበረው በአውሮጳ የሚኖረው ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ በቅርቡ በሀገራችን በተከሰተው ለውጥ ደስተኛ መሆኑን ባደረጋቸው ሰልፎች እና ሕዝባዊ ስብሰባዎች መግለጡ ይታወሳል።

አሁን ደግሞ የመደመር እና የሀገራዊ አንድነት ሂደት አካል የሆነው ከኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ጋር የፊት ለፊት ስብሰባዎች ከኢትዮጵያዊው ማኅበረሰብ ጋር መደረግ ተጀምሯል።በእዚህም መሰረት በመጪው ቅዳሜ ጥቅምት 3/2011 ዓም (ኦክቶበር 13/2018 ዓም) መቀመጫውን ስቶኮልም ያደረገው በኖርዲክ ሀገሮች የኢትዮጵያ ኤምባሲ በኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ  ኢትዮጵያውያንን ጠርቷል።ኤምባሲው ለኢትዮጵያውያን ጥሪ ያደረገው በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ (ኮምዩንቲ) በኖርዌይ በኩል ሲሆን ኮሚኒቲው መልዕክቱን በቫይበር ለአባላት ማሳወቁን ለማወቅ ተችሏል።

በብዙ ሀገሮች ላለፉት ሀያ ስምንት ዓመታት ያህል በኢትዮጵያዊው ማኅበረሰብ እና በኢትዮጵያ ኤምባሲዎች እና ቆንስላዎች መካከል የነበረው የደፈረሰ ግንኙነት እንደነበረ ሁሉ በኖርዌይም ተመሳሳይ ገፅታ ነበረው። ስለሆነም የመጪው ቅዳሜ ስብሰባ ልዩ የሚያደርገው ኢትዮጵያዊው በእኔነት መልክ የሚገኝበት የለውጥ ሂደቱን መደገፉን የምገልጥበት ብቻ ሳይሆን ከአሁን በኃላ ኤምባሲው የአገልጋይነት፣ኢትዮጵያዊውን ካለምንም ማዳላት የሚወክልበት  መድረክ እንዲሆን ሀሳቡን የሚገልጥበት እና ለሀገሩ ሰላም፣የዲሞክራሲያዊ ሽግግር እና መዋለ ንዋይ ማፍሰስ ላይ ሁሉ የሚኖረውን ሚና የሚያጎላበት አንዱ እና አይነተኛ መድረክ እንደሚሆን ይጠበቃል።የእዚህ አይነት መድረክ ከረጅም ጊዜ በኃላ የሚደረግ የጋራ ስብሰባ ከመሆኑ አንፃር ከፍተኛ ትዕግስት፣ጨዋነት እና ኃላፊነት በተሰማው መንገድ የኤምባሲው ልዑክም ሆነ  የስብሰባው ተሳታፊ በጋራ ሊያካህዱት ይገባል።




በቅዳሜው የኦስሎ ስብሰባ ላይ በኖርዲክ ሀገሮች የኢትዮጵያ አምባሳደር ፕሮፌሰር መርጋ በቃና እንደሚገኙ ተሰምቷል።ፕሮፌሰር መርጋ በቃና በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የእንስሳት ሕክምና ፋክልቲ ዲን፣ በአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የባህል አካዳሚ የቦርድ አባል፣ የብሔራዊ የእንስሳት ሕክምና ኢንስቲትዩት የቦርድ አባል እና የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው አገልግለዋል።ፕሮፌሰር መርጋ ከአማርኛ፣እንግሊዝኛ  እና ኦሮምኛ   በተጨማሪ ስፓኒሽ እና የፖርቹጋል ቋንቋ እንደሚናገሩ በተለይ የስፓኒሽ ችሎታቸው ከፍተኛ እንደሆነ ይነገራል። በመጪው ቅዳሜ ጥቅምት 3/2011 ዓም (ኦክቶበር 13/2018 ዓም) ኦስሎ የሚደረገው ስብሰባ አድራሻ  Norges Idrettshogslole, Sognsveien 220, 0863 Oslo ሲሆን ሰዓቱ  ከቀትር በኃላ  ከ14 - 18 ባለው ጊዜ ውስጥ ነው።

በሌላ በኩል እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ኦክቶበር 31/2018 ዓም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ አህመድ ወደ ጀርመን እንደሚመጡ ለማወቅ ተችሏል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጀርመን ጉብኝታቸው ከጀርመኗ ቻንስለር  ወ/ሮ አንጌላ ሜርክል እና ሌሎች ከፍተኛ የጀርመን ባለስልጣናት እና በተለይ ከአውሮፓ ከተለያዩ ከተሞች የሚመጡ ኢትዮጵያውያን ጋር ይገናኛሉ።በእዚሁም መሰረት በጀርመን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከመላው አውሮፓ ወደ  ጀርመን በመሄድ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለማግኘት ለሚመጡ ቀድመው መመዝገብ እንዲችሉ  የኦን ላይን የመመዝገብያ ገፅ አዘጋጅቷል።

በመሆኑም ወደጀርመን ተጉዘው ከጠቅላይ ሚኒስትር  ጋር መገናኘት ለሚፈልጉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚያደርጉት የጋራ ስብሰባ ቀን፣ሰዓት እና የስብሰባው ስፍራ እና የመመዝገብያ ሊንክ ከእዚህ በታች ይመልከቱ።


የስብሰባ ቀን Date: 31st October 2018
የስብሰባ መጀመርያ ሰዓት Time: 13:00 (1:00pm)
የስብሰባው ቦታ እና አድራሻ Venue: Commerzbank Arena, Morfelder Landstrasse 362, 60528 Frankfurt am Main, Germany
በስብሰባው ላይ ለመገኘት ለመመዝገብ ይህንን ይጫኑ። ሆኖም ግን አለመመዝገብ በህዝባዊ ስብሰባ ላይ ከመገኘት የሚያግድ ጉዳይ አይደለም። የአውሮፓ ማዕከል በሆነችው ጀርመን ኢትዮጵያውያን በብዛት እንደሚገኙ ይጠበቃል።
ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ የተገጠመ ድንቅ ግጥም በገጣሚት ሳባ መኩርያ የግጥም ስብስብ ምረቃ ላይ የቀረበ ድንቅ ግጥም (ቪድዮ) 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

Tuesday, October 2, 2018

በአቡነ ሕርያቆስ የተፃፈ ''ፍኖተ ቤተ ክህነት ወቤተ መንግስት'' የተሰኘ አዲስ መፅሐፍ በቀናት ውስጥ ገበያ ላይ ይውላል (ጉዳያችን ልዩ ዜና)

ጉዳያችን / Gudayachn (Exclusive)
መስከረም 23/2010 ዓም 

የመፅሐፉ የፊት እና የጀርባ ሽፋን  

 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የአውሮፓ እና አፍሪካ አህጉረ ስብከት ረዳት ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የተፃፈ ''ፍኖተ ቤተ ክህነት ወቤተ መንግስት'' የተሰኘ አዲስ መፅሐፍ በቀናት ውስጥ ገበያ ላይ ይውላል።ይህ በዓይነቱም ሆነ በስፋቱ ልዩ የሆነ መፅሐፍ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ምዕመናን ብቻ ሳይሆን  የቤተ ክርስቲያኒቱ አባላት ያልሆኑም ሊረዱት በሚችሉት መልክ የቀረበ ነው።  መፅሐፉ: -


  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንን ከክህነት ስርዓት እስከ ሲኖዶስ ስርዓት እና ሌሎች ስርዓቶቿን  በሚገባ የሚያብራራ እና ለማጣቀሻ የሚጠቀሙበት መድበል ነው 
  • በቅርብ ዘመናት (በዘመነ ኢህአዴግ ጨምሮ) ቤተ ክርስቲያን ያለፈችባቸውን ውጣ ውረዶች ከተጨባጭ ማስረጃዎች ጋር ያሳያል፣
  • ቤተ ክርስቲያን በሃይማኖት ቀሳጮች እና በውጭ ኃይሎች የደረሰባትን ፈተና በተለይ ከዘመናችን ሉላዊነት ጋር  አዛምዶ ያመለክታል፣ለመጪው ዘመንም ምን ማድረግ እንዳለባት መንገድ ያሳያል፣
  • ቤተ ክርስቲያን ስትጎዳ የእስልምና እምነትም አብሮ ለምን ማልቀስ እንዳለበት በምክንያት ያመላክታል፣
  • ቤተ ክርስቲያን አስተዳደሯን በስልታዊ እቅድ እና በበጀት መመራት እንዳለባት ከዝርዝር አሰራር እና ናሙና ጋር  ለማንም አገልጋይ በሚገባ መልኩ የዘመኑ ጥበብ ከደረሰበት አንፃር ያብራራል፣
  • ቤተ ክርስቲያን እና መንግስት ምን አይነት ግንኙነት መያዝ እንዳለባቸው ያሳያል፣
  • በቅርብ በፍጥነት ቤተ ክርስቲያን ካልተገበረቻቸው የምመጡባትን አደጋዎች ይጠቁማል፣
  • ቤተ ክርስቲያን በአይቲ ቴክኖሎጂ በቶሎ መራመድ መቻል እንዳለባት በዝርዝር ያሳያል፣
  • ቅዱስ ሲኖዶስ ለእነኝህ ሁሉ ለውጦች ያለበትን ኃላፊነት በሚገባ ያብራራል።\
ይህ ከአራትመቶ ገፆችን በA5 መጠን የቀረበ ዳጎስ ያለ መፅሐፍ አለማንበብ ብዙ ያሳጣል።መፅሐፉ በጣም ጥቂት ኮፒዎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ኦስሎ ቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለ ኃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በሚገኝባት የኖርዌይ ዋና ከተማ ኦስሎ ላይ ይታተማል።በሀገር ቤት በምእመናን ጥያቄ መሰረት  በተጨማሪ ወደፊት ይታተማል።መፅሐፉን ለማግኘት የምትችሉበትን መንገድ ቤተ ክርስቲያን በድረ ገፅ ላይ ታወጣለች አያምልጣችሁ።
 የአቡነ ሕርያቆስ ሲመተ ጵጵስና አስመልክቶ በጉዳያችን ላይ ብፁዕነታቸው ያላቸውን አገልግሎት እና በሀገር ቤት የተማሩባቸው፣ያገለገሉባቸው ሀገሮች እና አህጉረ ስብከቶች የያዘ ሙሉ መረጃ ጉዳያችን ላይ መውጣቱ ይታወቃል።ዝርዝሩን ለማንበብ ይህንን ይጫኑ።


ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

Monday, October 1, 2018

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች የጋራ ጉባዔ እና የኢትዮጵያ አንድነት ዕድሎቹና ፈተናዎቹ

ጉዳያችን GUDAYACHN
መስከረም 21/2011 ዓም (ኦክቶበር 1/2018)
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ 


መነሻ 
የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) የአመሰራረቱ ሒደት ለተመለከተ በህወሓት ሞግዚትነት የተቀመረ እንደነበር በቀላሉ መረዳት ይችላል።በድርጅት አቅም ቀደም ብሎ የእራሱ የመሰረት ታሪክ የነበረው ከኢሕአፓ (ከኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ) ከሰባ ያላነሱ አባላቱን ይዞ በሰሜን ጎንደር እና ሰሜን ወሎ የተመሰረተው በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ ይመራ የነበረው ኢህዴን (የኢትዮጵያ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ) በኃላ ብአዴን (ብሔረ አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ) ስሙን ወደ ብአዴን እንዲቀይር የተደረገው አዲስ አበባ ከገባ በኃላ ነበር።ሌሎቹ ኦህዴድ (ኦሮሞ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ድርጅት) እና ደህዴን (ደቡብ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ) አመሰራረታቸው በፖለቲካ ቤተ ሙከራ ውስጥ እንደተቀመመ የፖለቲካ ድርጅት በህወሓት አድራጊ ፈጣሪነት ነበር።ለምሳሌ ኦህዴድ የቀድሞ ሰራዊት ውስጥ የነበሩ ዝቅተኛ መኮንኖችን ህወሓት ሰብስቦ የመኮንኖች ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ በማለት ከሰበሰበ በኃላ ቀጥሎ እንደ አባዱላ ያሉትን ሰብስቦ ኦህዴድ መሆናቸው ተነገራቸው።

የኦህዴድ እና የደህዴን የምስረታ ታሪክ ላይ እስካሁን ትክክለኛ የአመሰራረቱን ታሪክ እራሱ ህወሓትም እየረሳው የአመሰራረት ታሪክ ተፅፎ አላለቀም እያሉ የሚቀልዱ አሉ። ህወሓት በተፈጥሮው የዕለት ችግሩን የሚፈታ ከሆነ ነገ የቱንም ያህል ችግር እንደ ሀገርም ሆነ እራሱ ላይ ይፍጠር ጉዳዩ አይደለም።የጊዜውን ችግር  ለማቅለል በጊዜያዊ መፍትሄ የታጠረው ህወሓት አሁን ላይ የዘለቄታ ሀገራዊ ርዕይ ማጣት ዋጋ እንዴት እንደሚያስከፍል የሚጎነጭበት ሰዓት አሁን ደርሷል።እንደ ቤተ ሙከራ የፈጠራቸው ኦህደድ እና ከሀገራዊ ድርጅት ወደ ክልል ድርጅት ያወረደው ብአዴን በአዲሱ ትውልድ እየተተኩ እራሳቸውን አጠናክረው ወደ ፓርቲነት ተቀይረው መጥተዋል።

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ጉባኤዎች

ከመስከረም ወር ሁለተኛ አጋማሽ ጀምሮ እስከያዝነው ሳምንት መጀመርያ ድረስ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ጉባኤዎቻቸውን አካሂደዋል።እነኝህ ጉባኤዎች በኢህአዴግ ታሪክ ያልታዩ አዳዲስ ክስተቶች ታይተዋል።ከክስተቶቹ ውስጥ ሶስቱ ድርጅቶቹ የራሳቸውን ጉባኤ ካለህወሓት ተፅኖ ማካሄድ መቻላቸው፣ ድርጅቶቹ ህወሓት ያወጣላቸውን ስም አሽቀንጥረው በፓርቲ ደረጃ መደራጀታቸው እና የቆዩ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቶቻቸውን ማስወጣታቸው ተጠቃሽ ናቸው።

በእዚህም መሰረት ኦህደድ ወደ ኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) ሲሰኝ፣ብአዴን በበኩል የአማራ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ተብሏል።የድርጅቶቹ ስም መቀየር ብቻ ሳይሆን ጎሳ ተኮር ላይ ብቻ አጠንጥኖ አባላትን የማሰባሰብ እና በፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ የማሳተፍ ተግባርን ወደ በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ሁሉም ብሔር ተወላጆች በአባልነት ለማቀፍ እና ለማሳተፍ ዕድል የሚሰጥ እንደሆነ ይነገራል።ይህ ማለት ኦሮሞ እና አማራ ክልል ሲባል የህዝብ የዘር መሰረትን ከመምዘዝ በክልሉ የሚኖር ማንኛውም ሕዝብ የሚያቅፍ ነው የሚል አንደምታ ይዟል።ዝርዝሩ የአዲሶቹ ፓርቲዎች መተዳደርያ እና የፖለቲካ እና ምጣኔ ሐብታዊ ፕሮግራሞች ገና ለሕዝብ ይፋ አልሆኑም።ሌላው የእየራሳቸው አዳዲስ ፕሮግራም ያወጣሉ ወይንስ አያወጡም? የሚለው እራሱን የቻለ ጥያቄ ነው።በመጪው ሮብ መስከረም 23/2010 ዓም የሚከፈተው  የኢህአዴግ ስብሰባ የኢትዮጵያ አንድነት ዕድሎች እና ፈተናዎች አንዱ አመላካች ጉባኤ የመሆን ዕድል አለው።

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች የጋራ ጉባኤ እና  የኢትዮጵያ አንድነት ዕድሎች እና ፈተናዎች

አሁን ባለንበት የኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ላይ ተዋናይ ኢህአዴግ ብቻ እንዳልሆነ ግልጥ ነው።የኢትዮጵያ አንድነት ጥያቄ አሁን ላይ ቆመንም አንዱ እና ወሳኙ ጥያቄ ሆኖ የቀረበ አጀንዳ ነው።ላለፉት 27 ዓመታት አንድነት የሚለው ቃል በጎሳ ፖለቲካ በታሹ ድርጅቶች ሁሉ የነፍጠኛው ሀሳብ ነው እየተባለ በእጅጉ እንዲጎሳቆል ተደርጎ ኖሯል።የሀገር አንድነት መሸርሸር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በበለጠ የኢትዮጵያ ሕዝብ በተሻለ ይረዳዋል።ምክንያቱም ሕዝብ አንድነት በማጣት ሳብያ የሚመጣው የሰላም መደፍረስ እና የህዝብ እልቂት እንዲሁም ስደት  የመጀመርያ ተጎጂ ሕዝብ ነው።የኢትዮጵያ ሕዝብ በዶ/ር አብይ፣አቶ ገዱ እና የለማ ቡድን እየተቀነቀነ ያለውን ለውጥ የደገፈው የኢትዮጵያ አንድነትን የበለጠ የሚያጠናክር እና የበታኝ ኃይሎችን አቅም የሚያሳንስ በመሆኑ ነው።

የመስከረም 23ቱ የኢህአዴግ ጉባኤ ሊኖሩበት ከሚችሉት ስራዎች ውስጥ አንዱ እራሱ ኢህአዴግ የሚለው ስም  የመቀየር መሆኑ ይገመታል።ምክንያቱም ንቅናቄ እና ድርጅት የሚሉ ስሞች አሁን ፓርቲ ሆነው መጥተዋል።ስለሆነም አብዮታዊ ግንባር የሚለው ትርክት ያበቃለት ይመስላል።አሁን ከእነኝህ እና ከሌሎች ርዕዮተ ዓለማዊ ጉዳዮች ጋር ተደማምሮ ኢህአዴግ ሊቀጥል አይችልም።ስለሆነም ይህ ጉባኤ አንድ አይነት መልክ ይዞ መምጣቱ አይቀርም።ለኢትዮጵያ አንድነት ግን ይዞ የሚመጣው ዕድልም ሆነ ፈተና አለ።ዕድሉ ኢህአዴግ የአዴፓ እና የኦዴፓ መንገድ የደቡብ ሕዝብ፣የአፋር እና የሱማሌ ክልል በሚገባ ደግፈው እንዲቆሙ ማድረግ እስከተቻለ ድረስ ለሃያ ሰባት ዓመታት ሲሰበክ የኖረው የልዩነት ፕሮፓጋንዳ ቀስ በቀስ በማከም የህዝቡን አንድነት በማጉላት ኢትዮጵያን ወደተሻለ የአንድነት ደረጃ የማድረስ ዕድል በጣም አለ። ከእዚህ እሳቤ ዙርያ ደግሞ የደህንነቱም ሆነ የጦር ሰራዊቱ ድጋፍ እንደሚኖር ይታሰባል። ምክንያቱም እስካሁን ባሉት ለውጦች ሁለቱም አካሎች በግልጥ ጣልቃ የገቡበት መንገድ የለም።

ከእዚህ በተጨማሪ ህወሓት በውስጡም ሆነ የትግራይ ሕዝብ እንደ አንድ ማኅበረሰብ የለውጡን ሂደት በሚገባ ተመልክተው የህወሓት የመለያየት፣የማጋጨት እና የዝርፍያ ፖለቲካ እንደማያዋጣ የተገነዘቡ ኃይሎች አሁን በብዙ ወንጀል የሚፈለጉትን አቶ ጌታቸው አሰፋ የመረጠውን የህወሓት ቡድን ተቃውሞ የሚወጣበት ወቅት እሩቅ አይሆንም።ይህ ለአንዳንዶች ሕልም የሚመስላቸው እውነታ ግን ሀገር እየተረጋጋ ሲመጣ ሕዝብ የበለጠ የፀጥታ ዋስትናው ሲረጋገጥ የሚከሰት ክስተት ነው። ይህ ሂደት በትግራይ ብቻ ሳይሆን በኦሮምያ ውስጥ ያሉ የፅንፍ ፖለቲካ አራማጆችን ሁሉ ከፅንፈኛ መሪዎቻቸው የመለየት አቅሙ ትልቅ ነው።ስለሆነም የኢትዮጵያ አንድነት የማረጋጋት እና ወደ ሀገራዊ ህብረት የመምጣት እድላችን ከጨመረ መንግስት አስፈላጊ የዲሞክራሲ አካላትን በተፈለገው የጥራት እና የሞራል ልዕልና ደረጃ ለማደራጀት ጊዜ የሚያገኝበት ሊሆን ይችላል።ከእነኝህ የዲሞክራሲ አካላት ውስጥ የምርጫ ኮሚሽን ተጠቃሽ ነው።

በሌላ በኩል የኢሕአዴግ ስብሰባ ምንም አይነት ያለመስማማት ወይንም ነገሮችን ኃላፊነት በተሰማው መንገድ ባለመውሰድ መንገድ ህወሓት ለመግፋት ካሰበ ህወሓት ፈፅሞ የሚገለልበት ሁኔታ ይፈጠራል።ለጊዜውም ቢሆን በኢትዮጵያ አንድነት ላይ የሚያጠላው ጥላ የለም ብሎ ማለት አይቻልም።ይህ ይዞ የሚመጣው ጥሩ ያልሆነ አዝማምያ ይኖራል።ለእዚህ ደግሞ የትግራይ ማኅበረሰብ እና ሊህቃኑ በጥብቅ ሊያስቡበት ይገባል።ህወሓት እንደ ጠፍ ከብት የሚመራቸው መሆን የለባቸው።ይህም በእራሱ ለህወሓት አዲስ ተቃውሞ ከራሱም ሆነ ከህዝብ ማስተናገዱ አይቀርም።በሁኔታው ህወሓት ግርግር የፈጠረ መስሎ ሊሰማው ይችላል።ውጤቱ ግን ህወሓት ከኤርትራም ሳይቀር አጣብቂኝ ውስጥ የሚገባበት ሁኔታ ነው የሚፈጠረው።በአሁኑ ሰዓት የኤርትራ ህዝብም ከአመታት በኃላ የተሻሻለለት የዋጋ ንረት መልሶ እንዳይመጣ ስጋት አለ።ከእዚህ በተጨማሪ ህወሓት ለማፈንገጥ ቢሞክር ከፈተኛ የምጣኔ  ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ ክስረትም ህወሓት እንደሚገጥመው ያውቃል።ስለሆነም በኢህአዴግ ስብሰባ ህወሓት ሁለት መንገዶች ሊከተል ይችላል።

ህወሓት፣ከኦሮሞ ፅንፈኛ ኃይሎች ጋር  በኢህአዴግ ጉባኤ ላይ ሊፈፅማቸው  የሚችላቸው  ሁለት ሴራዎች

አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ህወሓት ከመቼውም ጊዜ በላይ ሀገራዊ አቅሙ በተረጋጋች ኢትዮጵያ ውስጥ መፈፀም የማይችልበት ደረጃ ደርሷል።ያሉት ሁለት ብቸኛ አማራጮች ውስጥ: -

 አንዱ  የተተራመሰች ኢትዮጵያ ውስጥ የለውጥ ኃይሉ ያለውን ድጋፍ ማሳጣት እና ሕዝብ በመንግስት ላይ መተማመን እንዳይፈጥር ማድረግ በእዚህም ሳብያ ሕዝብ ትልቁ ጥያቄው የፀጥታ ጉዳይ እንዲሆን አድርጎ ማስጨነቅ እና ለአምባገነን አገዛዝ ምቹ እንዲሆን ማድረግ ነው።በእዚህ ሂደት ከጦር ሰራዊቱ አፍቃሪ ህወሓት የሆኑትን ወደ ፍፁም አምባገነን አገዛዝ እንዲመጡ ማድረግ እና በውጤቱ የበለጠ ሀብት መዝረፍ አንዱ መንገድ ነው። ይህንን የማተራመስ ሥራ ለማገዝ ፅንፈኛ የኦሮሞ ድርጅቶችን እና አክቲቪስቶች የተለያየ የመለያያ አጀንዳዎች እንዲያነሱ በገንዘብ መደለል ነው።የሰሞኑ የአዲስ አበባ ባለቤትነት ጉዳይ ማጮህ የተፈለገበት ምክንያት ለማንም ይበጃል ወይንም ወቅታዊ ነው ተብሎ ሳይሆን በጥቅም የተገዛ አጀንዳ ስለሆነ ነው።በእርግጥ የማተራመሱ አጀንዳ እና ማዕከላዊ መንግስት በፅንፈኛ ኃይል የመቀየር ሃሳብ የህወሓት ብቻ አይደለም።አንዳንድ በኦሮሞ ስም የሚንቀሳቀሱ ፅንፈኛ የኦሮሞ ኃይሎችም የትርምሱ ተጠቃሚ የሚሆኑ ስለሚመስላቸው ህወሓት የሚሰጣቸውን ትንንሽ አጀንዳዎች ማራገብ ስራዬ ተብሎ ተይዟል።

ሁለተኛው ሴራ ህውሓት ሊጠቀምበት የሚፈገው የኢህአዴግን ስብሰባ ባለመስማማት እና አጀንዳው ለረጅም ጊዜ እንዲቆይ በማድረግ ኢህአዴግ ሀገር ሊመራ እንዳልቻለ ማሳየት እና የለውጥ ኃይሉን የማዳከም ሥራ መስራት ነው።በተለይ አጀንዳዎቹን በማርዘም የሚደረገው ሂደት ሌሎች ስራዎች እንዳይሰሩ በማድረግ እንደ ሀገር የማዳከም ሥራ ሊሰራ ይቻላል።

ባጠቃላይ መስከረም 23 የሚከፈተው የኢህአዴግ ጉባኤ በለውጡ ሂደት ላይ ዋና ተዋናይ የሆኑት የዶ/ር አብይ፣የአቶ ገዱ እና አቶ ለማ ቡድን ታላቅ ሃገራዊ ኃላፊነት እንደወደቀባቸው የሚታይበት ሌላው ወሳኝ ጊዜ ነው።ሀገር ከህወሓት እና ከፅንፈኛ የኦሮሞ እንቅስቃሴ የበለጠች መሆኗን የለውጡ ኃይል የሚያሳይበት ወቅት ነው።ህወሓትም ሆነ የኦሮሞ የነውጥ ኃይሎች በኢትዮጵያዊነት ላይ ግልጥ የሆነ ሰይፍ መዘው መምጣታቸው በይቅርታ የሚታለፍበት ወቅት አይደለም። ይህ ከሆነ ዋጋ ያስከፍላል።ለድርድር የማይቀርቡት የሀገር ደህንነት፣ፀጥታ እና ቀጣይነት በከፍተኛ ደረጃ የሚጠበቁ መሆናቸው በቃልም ሆነ በተግባራዊ እርምጃ ሁሉም እንዲያውቀው ማድረግ አስፈላጊ ነው።በእርግጥ ህወሓት እቅድ 'ለ' ያለውን ለማሳካት በእዚህ ስብሰባ በቶሎ የተስማማ መስሎ ጉባኤው ቶሎ እንዲያልቅ ሊስማማ ይችላል።ይህም ቢሆን ግን ወንጀለኞችን በትክክል ለፍርድ የማቅረብ ሥራ መፋጠን አለበት።በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ሕዝብ በንቃት እና በትጋት የለውጡ ሂደት እንዲቀጥል ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት መቆም አለበት።


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።