ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, October 1, 2018

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች የጋራ ጉባዔ እና የኢትዮጵያ አንድነት ዕድሎቹና ፈተናዎቹ

ጉዳያችን GUDAYACHN
መስከረም 21/2011 ዓም (ኦክቶበር 1/2018)
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ 


መነሻ 
የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) የአመሰራረቱ ሒደት ለተመለከተ በህወሓት ሞግዚትነት የተቀመረ እንደነበር በቀላሉ መረዳት ይችላል።በድርጅት አቅም ቀደም ብሎ የእራሱ የመሰረት ታሪክ የነበረው ከኢሕአፓ (ከኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ) ከሰባ ያላነሱ አባላቱን ይዞ በሰሜን ጎንደር እና ሰሜን ወሎ የተመሰረተው በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ ይመራ የነበረው ኢህዴን (የኢትዮጵያ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ) በኃላ ብአዴን (ብሔረ አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ) ስሙን ወደ ብአዴን እንዲቀይር የተደረገው አዲስ አበባ ከገባ በኃላ ነበር።ሌሎቹ ኦህዴድ (ኦሮሞ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ድርጅት) እና ደህዴን (ደቡብ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ) አመሰራረታቸው በፖለቲካ ቤተ ሙከራ ውስጥ እንደተቀመመ የፖለቲካ ድርጅት በህወሓት አድራጊ ፈጣሪነት ነበር።ለምሳሌ ኦህዴድ የቀድሞ ሰራዊት ውስጥ የነበሩ ዝቅተኛ መኮንኖችን ህወሓት ሰብስቦ የመኮንኖች ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ በማለት ከሰበሰበ በኃላ ቀጥሎ እንደ አባዱላ ያሉትን ሰብስቦ ኦህዴድ መሆናቸው ተነገራቸው።

የኦህዴድ እና የደህዴን የምስረታ ታሪክ ላይ እስካሁን ትክክለኛ የአመሰራረቱን ታሪክ እራሱ ህወሓትም እየረሳው የአመሰራረት ታሪክ ተፅፎ አላለቀም እያሉ የሚቀልዱ አሉ። ህወሓት በተፈጥሮው የዕለት ችግሩን የሚፈታ ከሆነ ነገ የቱንም ያህል ችግር እንደ ሀገርም ሆነ እራሱ ላይ ይፍጠር ጉዳዩ አይደለም።የጊዜውን ችግር  ለማቅለል በጊዜያዊ መፍትሄ የታጠረው ህወሓት አሁን ላይ የዘለቄታ ሀገራዊ ርዕይ ማጣት ዋጋ እንዴት እንደሚያስከፍል የሚጎነጭበት ሰዓት አሁን ደርሷል።እንደ ቤተ ሙከራ የፈጠራቸው ኦህደድ እና ከሀገራዊ ድርጅት ወደ ክልል ድርጅት ያወረደው ብአዴን በአዲሱ ትውልድ እየተተኩ እራሳቸውን አጠናክረው ወደ ፓርቲነት ተቀይረው መጥተዋል።

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ጉባኤዎች

ከመስከረም ወር ሁለተኛ አጋማሽ ጀምሮ እስከያዝነው ሳምንት መጀመርያ ድረስ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ጉባኤዎቻቸውን አካሂደዋል።እነኝህ ጉባኤዎች በኢህአዴግ ታሪክ ያልታዩ አዳዲስ ክስተቶች ታይተዋል።ከክስተቶቹ ውስጥ ሶስቱ ድርጅቶቹ የራሳቸውን ጉባኤ ካለህወሓት ተፅኖ ማካሄድ መቻላቸው፣ ድርጅቶቹ ህወሓት ያወጣላቸውን ስም አሽቀንጥረው በፓርቲ ደረጃ መደራጀታቸው እና የቆዩ የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላቶቻቸውን ማስወጣታቸው ተጠቃሽ ናቸው።

በእዚህም መሰረት ኦህደድ ወደ ኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) ሲሰኝ፣ብአዴን በበኩል የአማራ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ተብሏል።የድርጅቶቹ ስም መቀየር ብቻ ሳይሆን ጎሳ ተኮር ላይ ብቻ አጠንጥኖ አባላትን የማሰባሰብ እና በፖለቲካ እንቅስቃሴ ላይ የማሳተፍ ተግባርን ወደ በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ሁሉም ብሔር ተወላጆች በአባልነት ለማቀፍ እና ለማሳተፍ ዕድል የሚሰጥ እንደሆነ ይነገራል።ይህ ማለት ኦሮሞ እና አማራ ክልል ሲባል የህዝብ የዘር መሰረትን ከመምዘዝ በክልሉ የሚኖር ማንኛውም ሕዝብ የሚያቅፍ ነው የሚል አንደምታ ይዟል።ዝርዝሩ የአዲሶቹ ፓርቲዎች መተዳደርያ እና የፖለቲካ እና ምጣኔ ሐብታዊ ፕሮግራሞች ገና ለሕዝብ ይፋ አልሆኑም።ሌላው የእየራሳቸው አዳዲስ ፕሮግራም ያወጣሉ ወይንስ አያወጡም? የሚለው እራሱን የቻለ ጥያቄ ነው።በመጪው ሮብ መስከረም 23/2010 ዓም የሚከፈተው  የኢህአዴግ ስብሰባ የኢትዮጵያ አንድነት ዕድሎች እና ፈተናዎች አንዱ አመላካች ጉባኤ የመሆን ዕድል አለው።

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች የጋራ ጉባኤ እና  የኢትዮጵያ አንድነት ዕድሎች እና ፈተናዎች

አሁን ባለንበት የኢትዮጵያ የፖለቲካ መድረክ ላይ ተዋናይ ኢህአዴግ ብቻ እንዳልሆነ ግልጥ ነው።የኢትዮጵያ አንድነት ጥያቄ አሁን ላይ ቆመንም አንዱ እና ወሳኙ ጥያቄ ሆኖ የቀረበ አጀንዳ ነው።ላለፉት 27 ዓመታት አንድነት የሚለው ቃል በጎሳ ፖለቲካ በታሹ ድርጅቶች ሁሉ የነፍጠኛው ሀሳብ ነው እየተባለ በእጅጉ እንዲጎሳቆል ተደርጎ ኖሯል።የሀገር አንድነት መሸርሸር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በበለጠ የኢትዮጵያ ሕዝብ በተሻለ ይረዳዋል።ምክንያቱም ሕዝብ አንድነት በማጣት ሳብያ የሚመጣው የሰላም መደፍረስ እና የህዝብ እልቂት እንዲሁም ስደት  የመጀመርያ ተጎጂ ሕዝብ ነው።የኢትዮጵያ ሕዝብ በዶ/ር አብይ፣አቶ ገዱ እና የለማ ቡድን እየተቀነቀነ ያለውን ለውጥ የደገፈው የኢትዮጵያ አንድነትን የበለጠ የሚያጠናክር እና የበታኝ ኃይሎችን አቅም የሚያሳንስ በመሆኑ ነው።

የመስከረም 23ቱ የኢህአዴግ ጉባኤ ሊኖሩበት ከሚችሉት ስራዎች ውስጥ አንዱ እራሱ ኢህአዴግ የሚለው ስም  የመቀየር መሆኑ ይገመታል።ምክንያቱም ንቅናቄ እና ድርጅት የሚሉ ስሞች አሁን ፓርቲ ሆነው መጥተዋል።ስለሆነም አብዮታዊ ግንባር የሚለው ትርክት ያበቃለት ይመስላል።አሁን ከእነኝህ እና ከሌሎች ርዕዮተ ዓለማዊ ጉዳዮች ጋር ተደማምሮ ኢህአዴግ ሊቀጥል አይችልም።ስለሆነም ይህ ጉባኤ አንድ አይነት መልክ ይዞ መምጣቱ አይቀርም።ለኢትዮጵያ አንድነት ግን ይዞ የሚመጣው ዕድልም ሆነ ፈተና አለ።ዕድሉ ኢህአዴግ የአዴፓ እና የኦዴፓ መንገድ የደቡብ ሕዝብ፣የአፋር እና የሱማሌ ክልል በሚገባ ደግፈው እንዲቆሙ ማድረግ እስከተቻለ ድረስ ለሃያ ሰባት ዓመታት ሲሰበክ የኖረው የልዩነት ፕሮፓጋንዳ ቀስ በቀስ በማከም የህዝቡን አንድነት በማጉላት ኢትዮጵያን ወደተሻለ የአንድነት ደረጃ የማድረስ ዕድል በጣም አለ። ከእዚህ እሳቤ ዙርያ ደግሞ የደህንነቱም ሆነ የጦር ሰራዊቱ ድጋፍ እንደሚኖር ይታሰባል። ምክንያቱም እስካሁን ባሉት ለውጦች ሁለቱም አካሎች በግልጥ ጣልቃ የገቡበት መንገድ የለም።

ከእዚህ በተጨማሪ ህወሓት በውስጡም ሆነ የትግራይ ሕዝብ እንደ አንድ ማኅበረሰብ የለውጡን ሂደት በሚገባ ተመልክተው የህወሓት የመለያየት፣የማጋጨት እና የዝርፍያ ፖለቲካ እንደማያዋጣ የተገነዘቡ ኃይሎች አሁን በብዙ ወንጀል የሚፈለጉትን አቶ ጌታቸው አሰፋ የመረጠውን የህወሓት ቡድን ተቃውሞ የሚወጣበት ወቅት እሩቅ አይሆንም።ይህ ለአንዳንዶች ሕልም የሚመስላቸው እውነታ ግን ሀገር እየተረጋጋ ሲመጣ ሕዝብ የበለጠ የፀጥታ ዋስትናው ሲረጋገጥ የሚከሰት ክስተት ነው። ይህ ሂደት በትግራይ ብቻ ሳይሆን በኦሮምያ ውስጥ ያሉ የፅንፍ ፖለቲካ አራማጆችን ሁሉ ከፅንፈኛ መሪዎቻቸው የመለየት አቅሙ ትልቅ ነው።ስለሆነም የኢትዮጵያ አንድነት የማረጋጋት እና ወደ ሀገራዊ ህብረት የመምጣት እድላችን ከጨመረ መንግስት አስፈላጊ የዲሞክራሲ አካላትን በተፈለገው የጥራት እና የሞራል ልዕልና ደረጃ ለማደራጀት ጊዜ የሚያገኝበት ሊሆን ይችላል።ከእነኝህ የዲሞክራሲ አካላት ውስጥ የምርጫ ኮሚሽን ተጠቃሽ ነው።

በሌላ በኩል የኢሕአዴግ ስብሰባ ምንም አይነት ያለመስማማት ወይንም ነገሮችን ኃላፊነት በተሰማው መንገድ ባለመውሰድ መንገድ ህወሓት ለመግፋት ካሰበ ህወሓት ፈፅሞ የሚገለልበት ሁኔታ ይፈጠራል።ለጊዜውም ቢሆን በኢትዮጵያ አንድነት ላይ የሚያጠላው ጥላ የለም ብሎ ማለት አይቻልም።ይህ ይዞ የሚመጣው ጥሩ ያልሆነ አዝማምያ ይኖራል።ለእዚህ ደግሞ የትግራይ ማኅበረሰብ እና ሊህቃኑ በጥብቅ ሊያስቡበት ይገባል።ህወሓት እንደ ጠፍ ከብት የሚመራቸው መሆን የለባቸው።ይህም በእራሱ ለህወሓት አዲስ ተቃውሞ ከራሱም ሆነ ከህዝብ ማስተናገዱ አይቀርም።በሁኔታው ህወሓት ግርግር የፈጠረ መስሎ ሊሰማው ይችላል።ውጤቱ ግን ህወሓት ከኤርትራም ሳይቀር አጣብቂኝ ውስጥ የሚገባበት ሁኔታ ነው የሚፈጠረው።በአሁኑ ሰዓት የኤርትራ ህዝብም ከአመታት በኃላ የተሻሻለለት የዋጋ ንረት መልሶ እንዳይመጣ ስጋት አለ።ከእዚህ በተጨማሪ ህወሓት ለማፈንገጥ ቢሞክር ከፈተኛ የምጣኔ  ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ ክስረትም ህወሓት እንደሚገጥመው ያውቃል።ስለሆነም በኢህአዴግ ስብሰባ ህወሓት ሁለት መንገዶች ሊከተል ይችላል።

ህወሓት፣ከኦሮሞ ፅንፈኛ ኃይሎች ጋር  በኢህአዴግ ጉባኤ ላይ ሊፈፅማቸው  የሚችላቸው  ሁለት ሴራዎች

አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ህወሓት ከመቼውም ጊዜ በላይ ሀገራዊ አቅሙ በተረጋጋች ኢትዮጵያ ውስጥ መፈፀም የማይችልበት ደረጃ ደርሷል።ያሉት ሁለት ብቸኛ አማራጮች ውስጥ: -

 አንዱ  የተተራመሰች ኢትዮጵያ ውስጥ የለውጥ ኃይሉ ያለውን ድጋፍ ማሳጣት እና ሕዝብ በመንግስት ላይ መተማመን እንዳይፈጥር ማድረግ በእዚህም ሳብያ ሕዝብ ትልቁ ጥያቄው የፀጥታ ጉዳይ እንዲሆን አድርጎ ማስጨነቅ እና ለአምባገነን አገዛዝ ምቹ እንዲሆን ማድረግ ነው።በእዚህ ሂደት ከጦር ሰራዊቱ አፍቃሪ ህወሓት የሆኑትን ወደ ፍፁም አምባገነን አገዛዝ እንዲመጡ ማድረግ እና በውጤቱ የበለጠ ሀብት መዝረፍ አንዱ መንገድ ነው። ይህንን የማተራመስ ሥራ ለማገዝ ፅንፈኛ የኦሮሞ ድርጅቶችን እና አክቲቪስቶች የተለያየ የመለያያ አጀንዳዎች እንዲያነሱ በገንዘብ መደለል ነው።የሰሞኑ የአዲስ አበባ ባለቤትነት ጉዳይ ማጮህ የተፈለገበት ምክንያት ለማንም ይበጃል ወይንም ወቅታዊ ነው ተብሎ ሳይሆን በጥቅም የተገዛ አጀንዳ ስለሆነ ነው።በእርግጥ የማተራመሱ አጀንዳ እና ማዕከላዊ መንግስት በፅንፈኛ ኃይል የመቀየር ሃሳብ የህወሓት ብቻ አይደለም።አንዳንድ በኦሮሞ ስም የሚንቀሳቀሱ ፅንፈኛ የኦሮሞ ኃይሎችም የትርምሱ ተጠቃሚ የሚሆኑ ስለሚመስላቸው ህወሓት የሚሰጣቸውን ትንንሽ አጀንዳዎች ማራገብ ስራዬ ተብሎ ተይዟል።

ሁለተኛው ሴራ ህውሓት ሊጠቀምበት የሚፈገው የኢህአዴግን ስብሰባ ባለመስማማት እና አጀንዳው ለረጅም ጊዜ እንዲቆይ በማድረግ ኢህአዴግ ሀገር ሊመራ እንዳልቻለ ማሳየት እና የለውጥ ኃይሉን የማዳከም ሥራ መስራት ነው።በተለይ አጀንዳዎቹን በማርዘም የሚደረገው ሂደት ሌሎች ስራዎች እንዳይሰሩ በማድረግ እንደ ሀገር የማዳከም ሥራ ሊሰራ ይቻላል።

ባጠቃላይ መስከረም 23 የሚከፈተው የኢህአዴግ ጉባኤ በለውጡ ሂደት ላይ ዋና ተዋናይ የሆኑት የዶ/ር አብይ፣የአቶ ገዱ እና አቶ ለማ ቡድን ታላቅ ሃገራዊ ኃላፊነት እንደወደቀባቸው የሚታይበት ሌላው ወሳኝ ጊዜ ነው።ሀገር ከህወሓት እና ከፅንፈኛ የኦሮሞ እንቅስቃሴ የበለጠች መሆኗን የለውጡ ኃይል የሚያሳይበት ወቅት ነው።ህወሓትም ሆነ የኦሮሞ የነውጥ ኃይሎች በኢትዮጵያዊነት ላይ ግልጥ የሆነ ሰይፍ መዘው መምጣታቸው በይቅርታ የሚታለፍበት ወቅት አይደለም። ይህ ከሆነ ዋጋ ያስከፍላል።ለድርድር የማይቀርቡት የሀገር ደህንነት፣ፀጥታ እና ቀጣይነት በከፍተኛ ደረጃ የሚጠበቁ መሆናቸው በቃልም ሆነ በተግባራዊ እርምጃ ሁሉም እንዲያውቀው ማድረግ አስፈላጊ ነው።በእርግጥ ህወሓት እቅድ 'ለ' ያለውን ለማሳካት በእዚህ ስብሰባ በቶሎ የተስማማ መስሎ ጉባኤው ቶሎ እንዲያልቅ ሊስማማ ይችላል።ይህም ቢሆን ግን ወንጀለኞችን በትክክል ለፍርድ የማቅረብ ሥራ መፋጠን አለበት።በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ሕዝብ በንቃት እና በትጋት የለውጡ ሂደት እንዲቀጥል ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት መቆም አለበት።


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...