ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, October 31, 2015

የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ ድምፃቸውን አጥፍተው የሚገቡበት አግባብ ስውሩ የህወሓት አመራር በጀርባ በር በኢትዮጵያ ጉዳዮች ላይ የመደራደሩ ማሳያ ነው።

ፎቶ ከ''የኔታ ትዩብ''


የጉዳያችን ማስታወሻ

የስርዓቱ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ድንግዝግዝ፣ሙስና-ገዝ እና ጥቂቶች በውስጥ ስብሰባ እንደፈለጉ የሚገለባብጡት ነው።በአደባባይ ባለስልጣናቱ የሚናገሩት እና በውስጥ መስመር የሚሰሩት ፈፅሞ አይገናኝም።ይህ ደግሞ በድንግዝግዝ፣ወጥነት እና አቅጣጫ የሌለው አሰራር እና ለአገር ጥቅም ሳይሆን ለጥቂቶች ብልፅግና የሚዋትት ስርዓት መለያ ነጥቦች ናቸው።በኢትዮጵያ በስልጣን ላይ ያለው አምባገነን ስርዓት ምን እንደሚያቅድ፣የት ለመድረስ እንደሚያስብ እና ወጥ የሆነ ፖሊሲው ምንድነው? ብሎ ለማወቅ በጎሳ ላይ የተመሰረተ የምጣኔ ሀብት፣ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ መሰረቱን ከመናገር ውጭ ወጥ የሆነ ስዕሉን ለማግኘት ለባዕዳንም አስቸጋሪ ሆኗል።በመሆኑም በሚናገራቸው ነገሮች ከማመን ይልቅ ሊያደርግ የሚያስበው ይህንን ነው ብሎ መተንበዩ አዋጪ ነው።

ለእዚህም አመላካቾቹ ሁለት  ነጥቦች ናቸው። እነርሱም 

1/ የአገሪቱን ፖለቲካዊ፣ማጣኔ ሃብታዊ እና ወታደራዊ መዘውር የሚያሽከረክረው ህወሃት ዋናው አመራር እራሱን ከቤተ መንግስት ጀርባ ሆኖ አቶ ኃይለማርያም እና መሰሎቻቸውን ከማዘዝ በቀር ወደ አደባባይ ወጥቶ ጋዜጣዊም ሆነ ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ አለመታየቱ እና 

2/ ከፊት እንዲሰለፉ የተደረጉት እና  የእራሳቸው ሃሳብ የማይናገሩቱ  እነ አቶ ኃይለማርያም ነገር አሳመርን እያሉ ''ከመምህሩ ደቀመዝሙሩ'' እንዲሉ የበለጠ ታማኝነታቸውን ለማፅናት የሚሉት ከሚፈፀመው ጋር አለመገናኘቱ የሚሉት ናቸው።

ኢትዮጵያን ለመጎብኘት የሚሄድ አንድ የውጭ አገር ባለስልጣን ሁለት አይነት ባለስልጣናት እንዳሉ ጠንቅቆ ያውቃል።እነርሱም የይስሙላ እና ዋናው ባለስልጣን የሚባሉ ናቸው።በምጣኔ ሀብት ጥናት እውነተኛ (real) የሚሉት እና ''እውነተኛ'' ያልሆነው (nominal) የተሰኙ ሁለት አፈራረጆች እንዳሉ ሁሉ ባዕዳኑም ከባለስልጣናት ጋር የሚኖራቸውን ቀጠሮ  ኤምባሲዎቻቸውን ''እውነተኛው ነው ወይንስ የይምሰሉ ባለስልጣን ነው?'' ( Is he nominal or real?) እያሉ መጠየቅ ይዘዋል።አቶ ኃይለማርያም ከይምሰል ውስጥ የሚመደቡ ሲሆኑ የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ደግሞ ከዋናው ፖሊሲ ዘዋሪው ውስጥ ይመደባሉ።


የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ ድምፃቸውን አጥፍተው እየገቡ ነው

በኢትዮጵያ የአደባባይ መግለጫዎች እና ከበሩ ጀርባ የሚሰሩ ስራዎች የመለያየት አይነተኛ ማሳያዎች ውስጥ አንዱ የግል ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ ያለበት አግባብ ነው።የይምሰሉ የባለስልጣናት ቡድን በአደባባይ የውጭ ባንኮችን ወደ አገር ቤት ለማስገባት በቅድምያ የአገር ውስጥ ባንኮች መጠንከር አለባቸው ይላል።የውስጥ አመራሩ ደግሞ የግል ባንኮች ከገቢያቸው እስከ 27% ድረስ ለአባይ ቦንድ መግዛት አለባቸው እያለ የባንኮቹን አቅም ያዳክማል። የአደባባዩ አመራር ዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅቶች መብራት እና ስልክ ሽጡ ሲሉን አልተቀበልናቸውም ይላል።የውስጥ አመራሩ ግን በመብራት ሥራ ላይ የግል ባለሀብት መግባት ይችላል ይል እና እራሱ ያደራጀውን የግል ባለ ሀብት ቦታውን እንዲይዝ በጎን ይፈቅዳል።


የእዚህ አይነቱ አሰራር ኢትዮጵያ በምን ያህል ደረጃ ለባእዳን እንደተሸጠች ለመለካት በማያዳግት ደረጃ አደጋ ላይ መሆናችንን አመላካች ነው።ከእዚህ ጋር ተያይዞ የግል አለማቀፍ የገንዘብ ተቋማት ወደ ኢትዮጵያ መግባት በእራሱ ጉዳት ወይንም ጥቅም አለው ብሎ ለመናገር የእራሱ የሆነ የተለያየ አቅጣጫዎችን እና የሌሎች አፍሪካ አገራትን ተሞክሮ አንስቶ መተንተን ስለሚጠይቅ በእርሱ ላይ ሃሳብ ለመስጠት ሌላ ጊዜ መመለሱ ይሻላል።ሆኖም ግን ኢትዮጵያ በአደባባይ ለሕዝቧ፣በአገር ውስጥ ላሉ የግል የገንዘብ ተቋማት እና ለዓለም አቀፍ ማሕበረሰብ ከፊት በተሰለፉ ፖሊስ አውጭ ባልሆኑት ባለስልጣናት እንዲናገሩ የሚደረገው እና በውስጥ መስመር ህወሃት የሚሰራው ሥራ መለያየቱን በትክክል መመልከት ጠቃሚ ነው።


በኢትዮጵያ የብሔራዊ ባንክ በውጭ ባንኮች ላይ ያለው ፖሊሲ መቀየሩ በአደባባይ ሳይታወጅ እና በውጭ ያሉ ባንኮችም ፖሊሲው ግራ እንዳጋባቸው በውስጥ መስመር እየገቡ ከህወሃት ጋር በልዩ መስመር እየተደራደሩ አዲስ አበባ ላይ ቢሮ የከፈቱ የውጭ ባንኮች ቁጥር በርክቷል።ቢሮ ሲከፈት ደግሞ ሁለት ስራዎችን ለመስራት ይረዳል።አንዱየተከማቸ ገንዘባቸውን ለማበደር የሚደረጉ  የውስጥ ድርድሮችን እና ባለስልጣናትን የማግባባት ሥራ ያቀላጥፉበታል።ሌላው ደግሞ ወደፊት ወደ ኢትዮጵያ ገበያ ሲገቡ እንዴት የአገር ውስጥ ባንኮችን አሸንፈው ገበያውን እንደሚቆጣጠሩ ያጠኑበታል።ከእዚህ በተረፈ በተለያየ መንገድ ከአገር የሚወጣ የውጭ ምንዛሪ 'እኛጋር አስቀምጡ' ብለው ከባለስልጣናት ጋር ምንም አይነት ድርድር እንደማያደርጉ ተስፋ እናድርጋለን።

በነገራችን ላይ አሁን አዲስ አበባ ላይ ቢሮ እየከፈቱ የሚገኙት ባንኮች ብለን የምናነሳቸው አህጉር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ የልማት ባንኮች ማለትም የአፍሪካ ልማት ባንክ፣የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ እና የመሳሰሉትን አይጠቀልልም።እነኝህ በየትኛውም የዓለም ክፍል ቢሮ የሚኖራቸው እና በንግድ ባንክ ደረጃ የሚሰሩ ስራዎች ውስጥ የማይገቡ የልማት ባንኮች ናቸው።አሁን የምንነጋገረው በኢትዮጵያ ያሉትን የግል ባንኮች ሥራ ጋር ተመሳሳይ ሥራ ያላቸው ባንኮች ግልፅ ባልሆነ መንገድ የመግባታቸው አግባብ ላይ ነው።እዚህ ላይ ቀደም ብዬ እንደጠቀስኩት የፖሊሲ ለውጥ ኖሮ የኢትዮጵያ ህዝብም ጥቅምና ጉዳቱ ተነግሮት፣የአገር ውስጥ ባንኮችም በግልፅ ተነግሯቸው እና ብሔራዊ ባንክ ግልፅ የሆነ መመሪያ እና ፖሊሲ አውጥቶ የሚገቡ ቢሆን ለአገር ጉዳት ያለው አይመስለኝም።በእርግጥ ከኢትዮጵያ አንፃር የእራሱ የሆነ ጥናት የሚያስፈልገው ቢሆንም።እስካሁን በሌሎች አፍሪካ አገራት የታየው ተሞክሮ ብዙ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ክስተቶች ተስተውለውበታል።ባጭሩ ግን አሁንም ሊሰመርበት እና አደገኛ አገባብ ያለው ያለ አንዳች መመርያ እና ፖሊሲ ወይንም ድብቅ ስምምነት  እየተስማሙ ቢሮ ስለሚከፍቱት ባንኮች ጉዳይ ነው።

በመጨረሻም እስከ ያዝነው ዓመት ድረስ ብቻ ድምፃቸውን አጥፍተው አዲስ አበባ ላይ ቢሮ የከፈቱ እና የብሔራዊ ባንክ በየትኛው ፖሊሲ ቢሮ እንዲከፍቱ እንደፈቀደ ግልፅ ያልሆኑት የውጭ ዓለም አቀፍ ባንኮች ዝርዝር አይተን ፅሁፌን ልደምድም። እዚህ ላይ ከተዘረዘሩት በላይ ሊኖሩ እንደሚችሉ ይገመታል።እዚህ ላይ ባንኮቹ በአገር ውስጥ ቢሮ መክፈታቸውን የምንሰማው በውጭ አገር ከሚወጡ ዜናዎች እና አልፎ አልፎ የአገር ውስጥ ጋዜጦች የሚያወጡት ዜና ላይ እንጂ የመንግስት የዜና አውታሮች ለጉዳዩ እንግዳ መሆናቸው በእራሱ አነጋጋሪ ነው።
እስከያዝነው ወር ጥቅምት/2008 ዓም ድረስ በአዲስ አበባ ቢሮ የከፈቱ ዓለም አቀፍ ባንኮች ዝርዝር : -
1/  የቱርክ መንግስት ባንክ ''ዚራት ባንክ''  በቀጣዮቹ ሁለት ወራት ውስጥ ቢሮ የሚከፍት፣

2/ የእንግሊዙ እና ደቡብ አፍሪካ መሰረቱን ያደረገው ''ስታንዳርድ ባንክ'' በአዲስ አበባ ቢሮ የከፈተ፣

3/ የጀርመኑ ግዙፉ ''ኮሜርዝ ባንክ'' በአዲስ አበባ ቢሮ የከፈተ እና

4/ ግዙፉ የአሜሪካ ባንክ ''ሲቲ ባንክ''  በአዲስ አበባ ቢሮ የከፈተ የሚሉት ይጠቀሳሉ።


ባጠቃላይ የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ጉዳት ወይንም ጥቅም  አለው ብሎ ለመደምደም ማጥናት የሚጠይቅ ቢሆንም በአገር ውስጥ ያሉ የግል ባንኮች አድገው ድንበር ተሻጋሪ ቢያንስ አፍሪካ ከተሞች ላይ የመድረስ አቅማቸው እንዲጎለብት መንግስት ምን አደረገ? ብሎ መጠየቅ ግን ተገቢ ነው።ባንኮች የአንድ ምጣኔ ሀብት ዋና አነሳቃሽ ሞተሮች ናቸው።የመንግስት ጥበቃ እና እንክብካቤ ይሻሉ።በተቃራኒው በኢትዮጵያ ግን ከባእዳን የተሰጠ ተልኮ እስኪመስል ድረስ በተለያዩ መመሪያዎች እንዲታነቁ ተደርገዋል።እዚህ ላይ በግድ የተጫነባቸው እና በግል ባንኮች ማኅበር ጭምር ክፉኛ የተተቸው የአባይ ቦንድ ግዥ ግዳጅን መጥቀስ ይቻላል።ባንኮቹ እንዲገዙ በግድ የተነገራቸው የአባይ ቦንድ ግዥ ከአቅማቸው በላይ እንደሆነ እና ተወዳዳሪነታቸውን በእጅጉ እንደሚጎዳው ቢገልፁም ሰሚ አላገኙም።

ጉዳያችን GUDAYACHN
ጥቅምት 20/2008 ዓም (Oct.31,2015)
www.gudayachn.com 

Thursday, October 29, 2015

ኢትዮጵያ ሕዝባቸውን በመረጃ መረብ (ኢንተርኔት) ሃሳቡን እንዳይገልፅ ካገዱ አምስት ቀንደኛ አገሮች ውስጥ ተመደበች። (ሙሉ ሪፖርቱን ይመልከቱ)




  •  ከአፍሪካ ቀዳሚ የመረጃ አፋኝ መንግስት ያላት ተብላለች። ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ጋዜጠኞችን በማሰር ከአምስቱ አገራት ውስጥ ተመድባለች።
  • ''Ethiopia is among the world’s top five jailers of journalists''
የሁለተኛው ዓለም ጦርነት እንደተጀመረ እንደ አውሮፓውያን አቆታጣጠር በ1941 ዓም ኒውዮርክ ላይ የተመሰረተው ''ፍሪደም ሃውስ'' በየአመቱ የዓለም አገራትን የሰብአዊ መብት እና በተለይ በኢንተርኔት ላይ ያላቸውን ሃሳብን የመግለፅ የመፍቀድ ደረጃ እያጠና ሪፖርት ያቀርባል።የዘንድሮ አመት ተመሳሳይ ሪፖርትንም በእዚህ ሳምንት አቅርቧል።

በዘንድሮው ሪፖርት ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ህዝቦቻቸውን መረጃ እንዳያገኙ ከሚያፍኑት አምስት ቀንደኛ አገራት ውስጥ ሲመድባት ከአፍሪካ በቀዳሚነት ይስቀምጣታል።ይህ ምን ማለት ነው? ብለን ለመተንተን ብንነሳ ብዙ ነገር ማለት መሆኑን እንረዳለን።በ21ኛው ክ/ዘመን የምትገኝ አገር ኢትዮጵያ መረጃ ሕዝቧን ነፍጋ ምን ያህል ወደኃላ እየቀረች ማሰብ በራሱ በቂ ነው።በርካታ የአፍሪካ አገሮች በገጠር የሚገኙ ትምህርት ቤቶቻቸውን በመረጃ መረብ አስተሳስረው ትምህርት ማሰራጨት በጀመሩበት ዘመን አንድ የስርዓቱን ድምፅ እንደ ገደል ማሚቱ የሚያስተጋቡ ጋዜጦች እና አንድ ቴሌቭዥን ለ92 ሚልዮን ሕዝብ የተወረወረላት ኢትዮጵያ በመረጃ መረብ (ኢንተርኔት) ሃሳባቸውን በነፃነት የማይገልጡባት አገር ሆናለች ኢትዮጵያ።

ሁኔታው በእዚሁ ከቀጠለ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመቱ በራሱ ይዘገንናል።ይህ ማለት ወጣቶቿ ያላቸውን አዲስ ሃሳብ ለህዝባቸው የሚገልጡበት መንገድ የለም ማለት ነው።በድፍረት ሃሳባቸውን ለመግለፅ ለመፃፍ ቢነሱ ደግሞ ለእስር ይዳረጋሉ። የዞን 9 ጦማርያን የደረሰባቸውን ማሰቡ ብቻ በቂ ነው። አዎን! መረጃ ሲታፈን እውቀት ይጠፋል፣እውቀት ሲሞት አገር ይሞታል፣አገር ሲሞት አላዋቂ ይገዛዋል።

የ''ፍሪደም ሃውስ'' ሙሉ ሪፖርትን ከእዚህ በታች ያለውን ማስፈንጠርያ ተጭነው ያንብቡት።
  

ጉዳያችን GUDAYACHN
www.gudayachn.com  

Monday, October 26, 2015

ሰበር ዜና - የሳውዲ አረብያ ንጉሳዊ ቤተሰብ ልዑል ሁለት ቶን (2 ሺህ ኪሎ ግራም) አደገኛ አደንዛዥ እፅ ጭነው ተያዙ Saudi prince arrested on private plane with 2 tons of drugs - reports

FILE PHOTO © Jaime Saldarriaga / Reuters


የሊባኖስ የፀጥታ ኃይሎች ዛሬ ሰኞ ጥቅምት 15/2008 ዓም የሳውዲ አረብያ ንጉሳዊ ቤተሰብ ልዑል አብዱል ሞሸን ቢን አልዋሊድ ሁለት ቶን አደንዛዥ እፅ በግል አይሮፕላናቸው እንደጫኑ በቁጥጥር ስር አውለዋቸዋል።በቤሩት ራፊቅ  ሐሪሪ ዓለም አቀፍ አየር ማረፍያ ላይ የተያዙት ልዑል አደንዛዥ እፁን ወደ ሳውዲ አረብያ ይዘው ለመብረር ዝግጅት ላይ እንደነበሩ መገለፁን የሩስያ ቴሌቭዥን ''ሩስያ ቱዴይ'' (አርቲ) የሊባኖስ ዜና ምንጮችን ጠቅሶ ገልጧል።''አል ማያድን'' የተሰኘው  የሊባኖስ ቴሌቭዥን ዘገባ ደግሞ ሁለት ቶን አደንዛዥ እፅ በ40 ጥቅል የታሸገ እንደነበር ይገልፃል።

የሩስያው ቴሌቭዥን የኢራኑን የ24 ሰዓት የእንግሊዝኛ ቴሌቭዥን ''ፕሬስ ቲቪ'' በመካከለኛው ምስራቅ የሚደረጉ ጦርነቶች ባብዛኛው በአደንዛዥ እፅ ንግድ እንደሚደጎሙ መጥቀሱን በመግለፅ ዘገባውን ይደመድማል።

ኢትዮጵያ ከሳውዲ አረብያ መንግስት ጋር የሚያቀርርባት ጉዳዮች እየበዙ ነው።በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሳውዲ ከርመው ነው የመጡት።ኢትዮጵያ ውስጥ ከመንግስት ቀጥሎ ከፍተኛ የሰው ኃይል ቀጥሮ የሚገኘው ሚድሮክ ኩባንያ ባለቤት ከሳውዲ ልዑላውያን ቤተሰቦች ጋር ጥብቅ የንግድ ሽርክና እንዳላቸው ይታወቃል። በሌላ በኩል ደግሞ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ሴት ኢትዮጵያውያን ምንም አይነት የጤና እና የደህንነት ዋስትና በሌለበት አካባቢያዊ ሁኔታ ጉልበታቸውን የሚገብሩባት አገር ነች ሳውዲ አረብያ።

በነገራችን ላይ የሳውዲው ልዑል 2 ሺህ ኪሎ ግራም (1 ቶን 1ሺህ ኪሎ ነው) አደገኛ ናርኮቲክ የተሰኘውን አደንዛዥ እፅ መያዛቸው ቀዳሚ የዓለም አስገራሚ ዜና ቢሆንም ከሳውዲ አረብያ ጋር የተለያየ የጥቅም ግንኙነት ያላቸው የምዕራቡ የዜና አውታሮችን ጨምሮ እንደማያናፍሱት ይጠረጠራል።የሆነው ሆኖ ግን ጉዳዩ የሳውዲ አረብያን ልዑላውያን ቤተሰብ ጨምሮ በርካታ ባለሃብቶቻቸውን ሌላ የሀብት ምንጭ ያመላከተ ዜና ለመሆኑ አያጠራጥርም።

ምንጭ - ሩስያ ቱዴይ (አር ቲ)

ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG
ጥቅምት 15/2008 ዓም  (ኦክቶበር 26/2015)

Friday, October 23, 2015

''ጉዳያችን'' ጡመራ ከጡመራነት ወደ ድረ-ገፅነት ጉዞ እና ያለፉት አራት አመታት ሂደት አጭር ዳሰሳ



ጉዳያችን ጡመራ ባለፉት አራት አመታት ውስጥ ብዙ ጉዳዮችን ለማንሳት ሞክራለች።ባለፈው ነሐሴ/ 2007 ዓም ጡመራዋ ሙሉ አራት ዓመት ሞላት።ሆኖም ግን ገና በአራት አመቷ፣አራት አመታትን አሳለፍኩ  ብላ ግርግር ለመፍጠር አትደፍርም።ምክንያቱም በድፍረት እና በቁጭት ለመፃፍ ልሞክር እንጂ ብዙ የሚቀሩ እና በሚፈለገው የይዘት እና የጥራት ደረጃ ለአንባብያን እየቀረበ እንዳልሆነ ይሰማኛል።ሆኖም አብሻቂው የአገራችን ፖለቲካ ጤነኛንም ናላ የማዞር አቅም አለው እና ይዘት ላይ ለማተኮር ጊዜ የማይገኝበት ወቅት ነበር።በእዛ ላይ በውጭ አገር ሲኖር ስራው፣ትምህርቱ፣ማኅበራዊ ኑሮው ሁሉ በእራሱ ሌላ የቤት ሥራ ነው።ሆኖም ግን በቀጣዩ ጊዜዎች  ከብሽሽቅ ፖለቲካ የዘለሉ እና የበሰሉ ጉዳዮችን ለማትኮር እሞክራለሁ።ይህ ማለት ግን ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ተጠርንፋ የተያዘችበት የጎጥ እና የአምባገነንነት ስርዓትን ስህተቶች እየነቀሱ ማቅረብ ችላ የሚባል ጉዳይ ነው ለማለት አይደለም።

ጉዳያችን ባለፉት አራት አመታት ውስጥ  ከ500 በላይ በሆኑ በአብዛኛው በአገራችን ኢትዮጵያ ጉዳይ እና ተያያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ላይ አተኩራ ለአንባብያን አቅርባለች።በእዚህም ወደ ግማሽ ሚልዮን የተጠጋ ጊዜ ከሰሜን አሜሪካ እስከ ኢንዶኔዣ፣ከደቡብ አፍሪካ እስከ ሩስያ የሚደርሱ አንባቢዎች ጎብኝተዋታል። እዚህ ላይ በኢትዮጵያ የሚኖሩ አንባቢዎች ቁጥር ከሰሜን አሜሪካ ቀጥሎ የሚቀመጥ ነው።ይህም ከሁሉ በተሻለ  ያስደስታል።ምክንያቱም በመረጃ እጥረት የሚሰቃየው የአገር ልጅ መረጃ ማግኘቱ በእራሱ አንድ እርካታ ነው።

በመጀመርያ ጡመራውን ለመጀመር ያነሳሱኝ ሁለት ጉዳዮች -አንደኛው፣በድረ-ገፆች ላይ የሚታዩት ሊተኮርባቸው የሚገቡት ማለትም ሊጎሉ (መጉላት) የሚገባቸው ጉዳዮች በአግባቡ አለመጉላታቸው እና ለአንዳንዶች እንደ ግንዛቤ ልካቸው ዝቅ አድርገው ሲመለከቱት በመመልከቴ ሲሆን ሁለተኛው፣ አሁን በስልጣን ላይ የሚገኘው ስርዓት በቀጣይ አመታት ከቀደመው የከፋ ተግባር እንደሚፈፅም በማመኔ ነበር።በእዚህም አንዳንዶች የአገራችንን ፖለቲካ ከሚመለከቱበት የቸል ባይነት አስተያየት ወደ ያገባኛል ስሜት እንደመጡ አጫውተውኛል።ይህ ማለት በጭፍን ስርዓቱን የሚደግፉቱ በምን ያህል ደረጃ እንደሚናደዱብኝ አይገባኝም ማለት አይደለም።ይህ ግን ከቁብ የሚቆጠር አይደለም።ምክንያቱም ጊዜዬን ወስጄ በጡመራው ላይ የሚወጡ ጉዳዮች ሁሉ የማምንባቸው፣ምክንያታዊ እና በማስረጃ የተደገፉ መሆናቸውን እረዳለሁ።ከእዚህ በላይ ፅሁፎቹ  ከጭፍን ጥላቻ አለመሆናቸውን እና ዘመን ተሻግረውም ቢጠየቁ የማያሳፍሩ ባለማስረጃ እንደሆኑ ለእራሴ ለመመለስ እሞክራለሁ።የስርዓቱ ጭፍን ደጋፊዎችም አንድ ቀን አይናቸው እንደሚገለጥ እና ችግሩ የሁላችንም እና በጭፍን የሚደግፉትም ችግር መሆኑን የሚረዱበት ቀን እሩቅ እንደማይሆን ተስፋ አለኝ።

ባለፉት አራት አመታት ውስጥ የኢትዮጵያ የሆኑ ጉዳዮች እንዲነሱ እና ትኩረት እንዲያገኙ ለማድረግ የተሞከረባቸው ሆኖም ግን የተሳኩም ያልተሳኩም ነበሩ።አንዳንዶቹ ጉዳዮች ቢነሱም ትኩረት ሳያገኙ ማለፋቸው የሚቆጩኝ አሉ።ለምሳሌ የኔልሰን ማንዴላን ሕይወት የታደጉት የሻምበል ጉታ ዲንቃ ዜና ለመጀመርያ ጊዜ በሸገር እንደተላለፈ ዜናውን ከሌሎች ድረ-ገፆች በቀዳሚነት በጉዳያችን ላይ ወጥቶ ነበር።በወቅቱም የፃፍኩት  ኔልሰን ማንዴላ በሕይወት እያሉ ሻምበል ጉታ በቶሎ ደቡብ አፍሪካ ቢሄዱ የዓለም ቁጥር አንድ ዜና ይሆናል ኢትዮጵያንም ያስጠራል። የሚል ሃሳብ ነበር።ሻምበል ጉታ የፖሊስ ሰራዊት አባል እንደመሆናቸው መጠን ለኢትዮጵያ ፖሊስ ትልቅ ዝናም ነበር።በሙዚየሙ የሚያስቀምጠው  ፎቶ በኖረው እና የአፍሪካ ፖሊስነታችን በታየ ነበር።''ነበር ለካ እንዲህ ቅርብ ነው'' እንዳሉት ይህ ሳይሆን ቀርቶ ማንዴላ አረፉ።ማንዴላ ሲያርፉ ሻምበል ጉታ እንዲሄዱ (ያውም በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን አስተባብረው) ተደረገ።ይህ እንግዲህ ከሚቆጨኝ ውስጥ ሲሆን ሌሎች በርካታ ጉዳዮች ግን ግንዛቤ ሲሰጣቸው እና ሲሰጡ ተመልክቻለሁ።ይህ ማለት ግን ካለምንም ማጋነን ብዙ የሚቀሩ ስራዎች እንዳሉ ከመገንዘብ ጋር ነው።እዚህ ላይ መጥቀስ የምፈልገው የተነሱት ጉዳዮች ጡመራውን ጠቅሰው በድረ-ገፃቸው ላይ የሚያትሙ በርካታ ድረ-ገፆች እና ጡመራዎችን ሳላመሰግን አላልፍም።ይህም አስፈላጊ ጉዳዮች በበለጠ ጎልተው እንዲታዩ እና በሁሉም ዘንድ ትኩረት እንዲያገኙ ለማድረግ በመቻላቸው ነው።አንዳንዶች ደግሞ በጉዳያችን ላይ ፅሁፉ በወጣ በሰአታት ውስጥ የእራሳቸው አስመስለው ስለጥፉት ታይቷል።ይህ እንግዲህ ሌላው ጉድለት ነው።

ባጠቃላይ  ከእዚህ በፊት የነበረው የጉዳያችን አካሄድ አገራዊ ጉዳዮች ትኩረት እንዲያገኙ ማድረግ እና ቢያንስ በእኔ ትውልድ ያለውን ኢትዮጵያዊ ነባራዊ እውነታዎችን እንዲገነዘብ ማድረግ ነበር።ለእዚህም ሲባል የጉዳያችን ያልሆኑ ነገር ግን በሌሎች የተፃፉም ሆኑ የተቀረፁ የድምፅ እና ተንቀሳቃሽ ምስሎች መጉላት ስላለባቸው ምንጫቸውን እየጠቀስኩ በጡመራዬ ላይ ለማስተናገድ ሞክርያለሁ።ገፁን በተለያዩ አርእስቶች መከፋፈል እና ፅሁፎቹን በእየዘርፋቸው የማሰናዳት ሥራ መሰራት ያለበት መሆኑን እረዳለሁ።ሌላው ገፁ የእንግሊዝኛ ገፅ እንዲኖረው ማድረግ ቀጣይ ስራዎች ናቸው።

በመጨረሻም ጉዳያችንን  ከጡመራ ወደ ድረ-ገፅነት የማሳደጉ ሂደትን እነሆ በአራተኛ አመቷ ተከናውኗል።ይህ ማለት በቀጥታ www.gudayachn.com በመጫን መክፈት ይቻላል ማለት ነው።ከእዚህ በተጨማሪ ጉግል ላይ gudayachn ብሎ በመፃፍ ብቻ መክፈት ሌላው አማራጭ ነው። ድረ-ገፁ አስተማሪ፣የመረጃ ምንጭ፣ በኢትዮጵያ እና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ በእውቀት ላይ ተመስርቶ ያተኮረ  ለማድረግ ዋናው ግብ ነው።ለእዚህም ብዙ ቅን አእምሮዎች ያስፈልጋሉ እና ሃሳባችሁን ከመስጠት አትቦዝኑ።እስከ አሁን ድረስ በማበረታታት፣ሃሳብ በመስጠትም ሆነ 'እንዲህ በማለቱ ምን ይሆን ይሆን?' እያላችሁ ለተጨነቃችሁ ሁሉ ምስጋናዬ ከፍ ያለ ነው። ከሁሉም በላይ ግን ''ማሰብን  የሚሰጥ አምላክ ነው'' እና ይህንን እንዳስብ፣እንድጀምረው እና እንድቀጥል የፈቀደልኝ ልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ይግባው።ጉዳያችን በድረ-ገፅነት ትቀጥላለች።


ጉዳያችን GUDAYACHN
ጥቅምት 12/2008 ዓም (Oct.23/2015)
www.gudayachn.com  

Thursday, October 15, 2015

የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን ESAT: Ethiopian Satellite Television

ኢሳትን ሁሉም ሊደግፈው ይገባል!
የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን 
ESAT: Ethiopian Satellite Television non-profit organisation embraces the diversity of people.
ESAT is the first independent Ethiopian Satellite Television service and Radio Station who broadcast to Ethiopia and the rest of the world.

ቪድዮ:- ከኢሳት ዩትዩብ


ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG

Monday, October 12, 2015

''ስደት፣ክርስትናና ኢትዮጵያዊነት'' በሚል ርዕስ ልዩ መርሃ ግብር በኦስሎ፣ኖርዌይ ቀረበ፣''ኅዳገ ተዋሕዶ'' የተሰኘች ልዩ መፅሔት ተመርቃለች የመፅሄቷን ይዘት ይዘናል።(ጉዳያችን ልዩ ጥንቅር)



ኅዳገ ተዋሕዶ ሽፋን እና የውስጥ ማውጫ 

በኖርዌይ፣ኦስሎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የቅዱስ ገብርኤልና አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ''ስደት ክርስትናና ኢትዮጵያዊነት'' በሚል ርዕስ ያዘጋጀው መርሐ ግብር ብዙ ምዕመናንና ኖርዌጅያን እንግዶች በተገኙበት ቅዳሜ መስከረም 22 ቀን 2008 ዓ/ም (03/10/2015)  በደማቅ ሁኔታ በኦስሎ፣ማየሽቷ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ የቅዱስ ገብርኤልና አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ተካሄደ::ከመርሃ ግብሮቹ ውስጥ የሚከተሉት ይገኙበታል።እነርሱም፣
  • ሰቆቃወ ጴጥሮስ የሚለው የሎሬንት ፀጋዬ ገ/መድህን መነባንብ  ''እመቤቴ ምነው ኢትዮጵያን ጨቀንሽባት'' የሚለው ክፍል በአርቲስት እንዳለ በቃል ቀርቦ አድናቆትን አትርፏል፣
  • ግጥም በገጣሚት አፎምያ ተደርሶ መድረክ ላይ ቀርቧል፣
  • የሐዲስ አለማየሁ ልብ ወለድ መፅሐፍ ፍቅር እስከ መቃብርን ወደ ኖርወጅኛ የተረጎሙት ዶ/ር ረዱልፍ ሞልቨር ( D/R Redulf Molvær) ከመፅሃፋቸው ጋር መድረክ ላይ ቀርበው ስለመፅሐፉ ማብራርያ ሰጥተዋል፣
  • ''ኅዳገ ተዋሕዶ'' የተሰኘ መፅሄት ልዩ እትም ተመርቋል።መፅሄቱ ካካተታቸው ቁምነገሮች ውስጥ ስለ ቤተክርስቲያኒቱ መሰረተ-እምነት፣የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ባጭሩ፣ስለ ሕፃናት  አስተዳደግ፣የኢትዮጵያውያን የዘመን አቆጣጠር ከአውሮፓውያን የተለየበት ምክንያት፣የምእመናን ድርሻ በቤተ ክርስቲያን ምን መሆን አለበት፣የተሐድሶ እንቅስቃሴ  ምንነት፣ስልት እና እንቅስቃሴ፣ እና የአማርኛ እና ግዕዝ  መንታ ሆሄያት አፃፃፍ የሚገልፅ ልዩ ጥናታዊ ፅሁፍ እና ሌሎች ጠቃሚ አርስቶችን ይዟል፣
  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በትምህርት፣ ሕግ፣ ማኅበራዊ ሕይወት፣አገር አስተዳደር፣ነፃነት፣እና ጤና እንክብካቤ ዘርፍ ያደረገችው አስተዋፅኦ የሚገልፅ በስላይድ የተደገፈ ገለፃ ቀርቧል፣
  • የኢትዮጵያ ታሪክ ከጥንት እስከ ዛሬ  የሚገልፅ ገለፃ ቀርቧል፣
  • ከምእመናን ምን ይጠበቃል በሚል አርእስት ስር አሁንም በስላይድ የቀረበ አስተማሪ ገለፃ ቀርቧል፣
  • አስተማሪ እና ሁሉንም ያስደመመ ድራማ ታይቷል።

ህዳገ ተዋሕዶ በይፋ በመላከ ብስራት ቆሞስ አባ ሀብተየሱስ ስትመረቅ (ፎቶ ጉዳያችን)

ህዳገ ተዋሕዶ መፅሄት  በውስጧ የያዘችው ፅሁፎች ማውጫ 

በመቀጠልም ለተጋበዙት ኖርዌጅያን እንግዶች  የእንኳን ደህና መጣችህ መልእክት ካስተላለፈ በኋላ የቤተ ክርስቲያናችንን ታሪክና መሠረተ ክርስትና ባጭሩ ለኖርዌይ እንግዶች ገለፃ ተሰጥቷል። ከተጋባዥ እንግዶች ለመጀመሪያ ጊዜ “ፍቅር እስከ መቃብር” የሚለውን የታዋቂው የሀዲስ ዓለማየሁ መጽሐፍ ወደ ኖርዌጅያን የተረጎሙት ዶ/ር ረዱልፍ ሞልቫር  ስለ ኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ጥራት የመጽሐፉን ገጸ ባህርያት ፊታውራሪ መሸሻ፣በዛብህ፣ጉዱ ካሳ፣ሰብለ ወንጌልን በመጥቀስ አብራርተዋል:: በተለይ የመጨረሻውን የሰብለ ወንጌል፣በዛብህ እና ጉዱ ካሳ መገናኘት እና ሞት እንዲሁም የሰብለ ወንጌልን በምንኩስና ሕይወት ሆና የበዛብህን መቃብር ለጉዱ ካሳ ስታሳይ የሚገልጠው ክፍልን ሲያነሱ እንባ ሲተናነቃቸው ከንግግራቸው መቆራረጥ ይታወቅ ነበር።

“ፍቅር እስከ መቃብር” የሚለውን የታዋቂው የሀዲስ ዓለማየሁ መጽሐፍ ወደ ኖርዌጅያን የተረጎሙት  ኖርዌጅያዊው ዶ/ር ረዱልፍ ሞልቫር ስለ መፅሃፉ ሲናገሩ (ፎቶ ጉዳያችን)

በማስከተለም  በኖርዌይ ኦስሎ ዩኒቨርስቲ የህክምና ፕሮፌሰር የሆኑት ፕሮፌሰር ጉናር አክሰል ብዩነ  ለብዙ ጊዜ በሥራ ምክንያት ኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታ የሀገራችን ባህል ምን እንደሚመስል ለመረዳት እንደቻሉ በሰፊው አብራርተዋል:: እንዲሁም ጥንታዊቷ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እምቅ ሀብትና ታሪክ እንዳላት መስክረዋል::ዝግጅቱ የበለጠ እንዲያምር ያደረጉት ሌላው እንግዳ  ጥርት ያለ አማርኛ ተናጋሪ የሆኑትና ለምእመኑ ባቀረቡት የእራሳቸው ድርሰት በሆነ አማርኛ ግጥም ተደጋጋሚ ጭብጨባ የተቸራቸው ሚስተር ሸል ኡስትቢ ነበሩ:: በሚናገሩት አማርኛ ምእመኑን ከማስደመማቸው በተጨማሪ ብዙ እድሜአቸውን ያሳለፉባትን ኢትዮጵያን የማንነታቸው አንዱ ገጽታ እንደሆነ በስሜት አስረድተዋል:: በተለይ እዚህ ሀገር ተወልደው ያደጉም ሆነ በማደጎነት የመጡ ሕጻናት ቅይጥ ባህሪ ይዘው እንደሚያድጉ ይህም ጥሩና መጥፎ ገጽታ ሊኖረው እንደሚችል አስረድተዋል:: ነገር ግን ባህላቸውን መርሳት እንደሌሌባቸውና ወላጆችም ማስተማር እንዳለባቸው መክረዋል:: 

ሚስተር ሸል ኡስትቢ ስደት እና ማንነት ዙርያ ገለፃ ሲያደርጉ (ፎቶ ህንፃ አሰሪ ኮሚቴ ፌስ ቡክ ገፅ)

ከሁሉም የምእመኑን ልብ የነካው ሚስተር ሸል ኡስትቢ በስደት የምንኖረውን ኢትዮጵያዊያንን ሲያፃናኑ ''አውቃለሁ እዚህ ሀገር ስትመጡ ማልቀሳችሁ አይቀርም።ብቸኝነት ከአገር መለየት በእራሱ ያሳዝናል ግን አይዟችሁ'' ብለው ሲናገሩ ነበር።

የደብሩ ታዳጊ ወጣት መዘምራን በፀናፅል  ያሬዳዊ ዜማ ሲያቀርቡ (ፎቶ ህንፃ አሰሪ ኮሚቴ ፌስ ቡክ ገፅ)

የመዘምራኑ ያሬዳዊ ዜማ - 
''እግዚአብሔር ሀበነ ልሳነ ጥበብ፣ከመናእምር ሕጋ ለቤተ ክርስትያን'' የሚል ሲሆን ትርጉሙም ''እግዚአብሔር ሆይ የቤተ ክርስትያንን ሕግ እናውቅ ዘንድ ዕውቀትን ስጠን'' ማለት ነው። 

ሌላው ለዝግጅቱ ልዩ ድምቀት ሰጥቶት የነበረው በአርቲስት ሶስና ግዛው ደራሲነት እና የመድረክ ዝግጅት የቀረበው ተውኔት (ድራማ) ነበር።ተውኔቱ በአንድ ስደት በወጣ አባወራ እና በቤተሰቡ ዙርያ የደረሰውን ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን  ሲሆን ብዙ ምእመናን ከታሪኩ ጠቃሚ ምክር በዘለለ በአሳዛኝ የቤተሰቡ ሁኔታ ሲያለቅሱ ተስተውለዋል።

በመጨረሻም መርሃ ግብሩ  በጸሎት ከመጠናቀቁ በፊት የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ብስራት ቆሞስ አባ ሀብተ ኢየሱስ ለገሠ የዕለቱን ዝግጀት በተመለከተ ማጠቃለያ መልእክት አስተላልፈዋል:: በመልዕክታቸውም መርሐ ግብሩ እጅግ አስተማሪ እንደነበር ገልፀው የእዚህ ዓይነት መርሐ ግብሮች በቀጣይነት መዘጋጀት እንዳለባቸው አባታዊ ምክራቸውን ሰጥተዋል::

ማሳሰቢያ - ከእዚህ በላይ የተገኘው ጥንቅር ከሕንፃ አሰሪው ኮሚቴ ፌስ ቡክ  እና ጉዳያችን በአካል ካጠናቀረችው ነው።



ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG
ጥቅምት 2/2008 ዓም (ኦክቶበር 13/2015)

Friday, October 9, 2015

በፖላንድ፣ዋርሶ የተደረገው 19ኛው የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ሪፖርት The 19th International Conference of Ethiopian Studies (Warsaw 24-28 August, 2015)



ከነሐሴ 24-28/2015 እኤአ በፖላንድ፣ዋርሶ የተደረገው 19ኛው የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ 
ተሳታፊዎች።ፎቶ ከጀርመን ድምፅ ራድዮ አማርኛው አገልግሎት የተገኘ

ከ60 ዓመት በላይ የሆነዉ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ የሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ትኩረት ነፍገውታል።አለም ስለእኛ ሲያጠና እኛ ለምን ዝም እንደምንል እንቆቅልሽ ነው።ቀደም ተብሎ በእዚሁ ጡመራ ላይ ጉባኤው ከመከፈቱ በፊት በወጣው ፅሁፍ ላይ አስራ ዘጠነኛው የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ...በሚል ርዕስ ስር እንደተገለፀው ይህ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ከመደረጉ በፊት እና ጉባኤው ከተደረገ በኃላ የነበሩትን ክንውኖች የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ከ24 ዓመታት በፊት በልዩ ዘገባ ያቀርብ የነበረ መሆኑን እና በተለይ በጉባዔው ላይ የተሳተፉት ምሁራን ሰፊ ጋዜጣዊ መግለጫ ይሰጡ እንደነበር ተገልጧል።ይህም በአገር ቤት ላለው ወጣት ስለ አገሩ የበለጠ እንዲረዳ እንደሚያደርገው ይታወቃል።

ይህ ሁኔታ ግን በዘመነ ኢህአዴግ/ሀውሃት ቀርቷል።ስለጉባዔው የመንግስቱ መገናኛ ብዙሃን አይተነፍሱም።የዓለም ምሁራን ስለ ኢትዮጵያ ጥናት ለማድረግ ሲሰበስቡ የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን እና በመንግሥትነት የተሰየመው አካል ከፍተኛ ልዑክ አይልክም።ከእዚህ ይልቅ በዩንቨርስቲ ያሉ ወጣት ምሁራን በከፍተኛ ውጣ ውረድ በጉባዔው ላይ ለመሳተፍ ይሞክራሉ።ዘንድሮም ከኢትዮጵያ ዩንቨርስቲዎች ወደ 100 የሚጠጉ ምሁራን ሲገኙ በጠቅላላው ከመላው ዓለም 476 ምሁራን መሳተፋቸውን ለማወቅ ተችሏል።ኢትዮጵያ በስንቱ ትበደላለች? መቼ ይሆን የኢትዮጵያን በጎ ነገር የሚያጎላ መንግስት የሚኖረን? ከ1953 ዓም ጀምሮ በእየሶስት ዓመቱ  የሚደረገው ይህ ጉባዔ በርካታ ጥናቶች በተለያዩ ምሁራን ቀርቧል።እነኝህ ጥናቶች ለሕዝብ ለምን ይፋ አይደረጉም? የጥናቶቹ አቅራቢዎች ጋር ሰፊ ውይይት ማድረግ እና ሃሳባቸውን ለሕዝብ የማስተዋወቅ ሥራ ለምን አይሰራም? የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የኢትዮጵያ የሚል ስም ይዞ በኢትዮጵያ ስም የሚደረጉ ታላቅ የጥናት ጉባዔን ለምን እንዳላየ አለፈው? ብዙ ጥያቄ ይጭራል። በተለይ የእዚህ አይነቱ በርካታ ክርክሮችን ሊፈጥር የሚችሉ ሃሳቦች የሚነሱበት የምርምር ጉዳይ ባለቤት ሳይኖረው ወይንም በአግባቡ መያዝ ሳይቻል ከቀረ ሌሎች ስለ እራሳችን እንዲናገሩ የምንተወው ሜዳ እንዳይሆንም ያሰጋል።  
ከዋርሶ ዩንቨርሲቲ ድረ-ገፅ የተገኘ ጉባኤውን አስመልክቶ የወጣ ፖስተር 

=====\\\\\\\\\\\==========\\\\\\\\\\\=======\\\\\\\\\\\\==============\\\\\\\\\\\\\=========

ከእዚህ በታች ያለው ፅሁፍ ከጀርመን ድምፅ የአማርኛው አገልግሎት መስከረም 24/2015 ዓም እ ኤ አቆጣጠር ጉባኤውን አስመልክቶ አዜብ ታደሰ እና አርያም ተክሌ ተዘጋጅቶ የቀረበው ሪፖርት ነው

መስከረም 24/2015 ዓም እ ኤ አቆጣጠር
አዜብ ታደሰ እና አርያም ተክሌ 
የጀርመን ድምፅ የአማርኛው አገልግሎት

የጥንታዊ ቅርሶችና ታሪክ ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያ ከረጅም ጊዜ አንስቶ የታሪክ የቅርስ ተመራማሪዎችን ትኩረት እንደሳበች ናት።ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ለሚካሄዱት የተለያዩ ጥናቶች ግብዓትነት ትልቅ አስተዋፅኦን ማድረጉም ይታወቃል። ለዚህም ከ60 ዓመት በላይ የሆነዉ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ተጠቃሽ ነዉ። ስለጉባዔዉ ፋይዳ ኢትዮጵያዉያንና አንድ ጀርመናዊ የጉባዔዉን ተሳታፊን አነጋግረንናል።

የመጀመርያዉ ኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ በጎርጎሪዮሳዊ 1959 ዓ,ም ነዉ የተካሄደዉ። በየሶስት ዓመት አንድ ጊዜ የሚደረገዉ ይህ ጉባዔ አንድ ጊዜ ኢትዮጵያ ዉስጥ ሁለት ጊዜ ከኢትዮጵያ ዉጭ በመፈራረቅ ነዉ ትኩረታቸዉን በኢትዮጵያ ባህል፤ ታሪክ፤ ቅርስ፤ ቋንቋ ላይ ያደረጉ የምሑራን ጥናታዊ ጽሑፎች የሚቀርቡበት። በፖላንድ መዲና ላይ ለአምስት ቀናት የተካሄደዉ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ምን ዓይነት መልክ ነበረዉ ? በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ የጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ዶክተር አህመድ ሀሰን፤« ይህ ጉባዔ ታሪክን ብቻ ሳይሆን የሚጠናዉ፤ በዚህ ጉባዔ ሥነ-ሕዝብ ይጠናል የቋንቋና ፤ ማኅበረሰባዊ ሳይንስ፤ ሥነ-ቋንቋ በሙሉ የሚቀርብበትና አዳዲስ ሃሳቦች የሚፈልቁበት ነዉ ። ከነዚህ ሃሳቦች ደግሞ ትምህርት የሚገኝበት የእዉቀት አድማስ የሚሰፋበት ነዉ። እኔ ስብሰባዉን ከሚከፍቱት ሰዎች አንዱም ነበርኩ። በመክፈቻ ንግግሪ ያወሳሁት የጉባዔዉን ታሪክ ነዉ። 

ጉባዔዉ ለመጀመርያ ጎዜ በጎርጎረሳዊ 1959 ዓ,ም ሮም ላይ ተካሄደ ከዝያ በ1972 ዓ,ም ማንችስተር ብሪታንያ ፤ 3 ተኛዉ በ1966 አዲስ አበባ፤ በ 1972 ሮም ኢጣልያ፤ በ 1977 ዓ,ም ኒስ፤ ፈረንሳይ፤ በ1978 ዓ,ም ቺካጎ፤ ዩኤስ አሜሪካ ፤ በ1980፤ ቴላቪብ ፤ እስራኤል፤ በ1982 ዓ,ም ፈረንሳይ፤ በ1991 አዲስ አበባ፤ በ1994 ሚቺገን፤ ዩኤስ አሜሪካ፤ በ1977ዓ,ም ኪዮቶ ጃፓን፤ 2000 ዓ,ም አዲስ አበባ፤ በ2003 ሃንቡርግ፤ ጀርመን ፤ በ2007 ኖርዊ፤ በ2009 ዓ,ም አዲስ አበባ ፤ በ2012 ዓ,ም ድሪደዋ ፤ በ2015 ዓ,ም ዋርሶ ፖላንድ ላይ ነዉ የተካሄደዉ። ይህ ሲሆን ትልቁ ነገር የኢትዮጵያ ጥናት ጉባዔ ምስራቅ አዉሮጳ ላይ፤ በሩስያሞስኮ፤ ዋርሶ ፖላንድ፤ ላይ ሲካሄድ ምስራቁን ከምዕራቡ አደበላልቆ ብዙ ቦታዎችን የሚሸፍን የሕዝብን ትኩረት የሳበ ባህል ነዉ ያለን። በዚህ ጉዳይ እኛም የምንኮራዉ በታሪካችን በማንነታችን በባህላችን ነዉ። እነዚህ ጉባዔዎች የኢትዮጵያ ምስክር ናቸዉ።» 

በዋርሶ በተካሄደዉ ኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ወደ 476 ጉባዔተኞች ተገኝተዉበታ። በዚህ ጉባዔ የሚደንቀዉ ነገር ከኢትዮጵያ ተሳፍረዉ የመጡ ከ 100 በላይ ምሑራን ተሳታፊዎች እንደነበሩ ዶክተር አህመድ ሀሰን ተናግረዋል።

« በፖላንዱ ጉባዔ ኢትዮጵያ ዉስጥ ያሉ ዩንቨርስቲዎችን አሰባስበናል። የክልል ዩንቨርስቲዎች በጣም በሚያስደስት ሁኔታ ለምሁራኖቻቸዉ ገንዘብ እየሸፈኑ ወደ ጉባዔዉ ልከዋቸዋል። የምርምሩ አጀንዳ ዘርፈ ብዙ ነዉ። ችግር ፈቺ ምርምሮች ያሉበት ነዉ። የሚገርመዉ በዚህ ጉባዔ በርካታ ኢትዮጵያዉያን ከኢትዮጵያ ዉጭ ሲሳፉ ለመጀመርያ ነበር። ኢትዮጵያዉያን መምህራን በከፍተኛ ቁጥር ታይተዋል። ከመቶ በላይ ነበሩ።»

በጀርመን መዲና ነዋሪ የሆነዉ የአፍሪቃ ጉዳይ ተመራማሪ እና አማረኛ ቋንቋ ተናጋሪዉ ጀርመናዊ ዶክተር አንድሪያስ ቬተር እስካሁን በተደረጉት በአብዛኞቹ ኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ተካፋይ ነበር። በጉባዔዉ ላይ ስለኢትዮጵያ መንዙማ የጥናት ጽሑፋቸዉን አቅርበዋል። ዘንድሮ ዋርሶ ላይ የተደረገዉ ይህ ጉባዔ፤ ከዚህ ቀደም ከተካሄዱት በምን ይለያል፤ ለሚለዉ ጥቃቄ ዶ/ር አንድርያስ ቬተር

«የሚለየዉ ቦታዉ አዲስ በመሆኑ ነዉ። ከሶስት ዓመት በፊት ጉባዔዉ የተካሄደዉ ድሪደዋ ላይ ነበር። ብዙ ልዩነት አልታየኝም። ጉባዔዉ ከድሮ ጊዜ ልዩነቱ አሁን ኢትዮጵያዉስጥ ብዙ ዩንቨርስቲዎች ስላሉ የኢትዮጵያ ምሁራን የኢትዮጵያ ተመራማሪዎች እየበዙ መምጣታቸዉ ነዉ። ቀደም ሲል በሀገር ደረጃ ሲታይ አብዛኛዉ የጉባዔ ተሳታፊ የሚመጣዉ ከጀርመን ነበር። አሁን ግን ከኢትዮጵያ የመጡ ተሳታፊ ምሑራን ነበሩ አብዛኞቹ። እንደዉም በገንዘብ ችግር ምክንያት ብዙዎች መምጣት አልቻሉም።»

ሌላዉ የጉባዔዉ ተሳታፊ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ረዳት ፕሮፊሰር አህመድ ዘካርያ ናቸዉ። አህመድ ዘካርያ በጉባዔዉ ላይ ስለ ኢትዮጵያ መንዙማ የጥናት ጽሑፋቸዉን ካቀረቡት ጥቂት ምሑራን መካከል አንዱም ነበሩ።

« በአጠቃላይ ስብሰባዉ በጣም ጥሩ ነበር። በዚህ ጉባዔ ስለ ኢትዮጵያ መንዙማ ብዙ የጥናት ጽሑፎች ቀርበዋል። በአጠቃላይ ስለ መንዙማ ይዘት ፤ ስለ ወሎ መንዙማ፤ ስለ ሀረር መንዙማ፤ ስለ ሙዚቃዊ ይዘቱ፤ ስለ ያዘዉ ሥነ- ጽሑፍ የተለያዩ የጥናት ወረቀቶች ቀርበዋል። በኢትዮጵያ ያለዉን የመንዙማ ዓይነቶች ለመዳሰስ ተሞክሮአል። አሁንም ግን አጠቃላይ ነዉ ማለት አይቻልም። ምክንያቱም መንዙማ አፋሮች፤ ሶማሌዎች፤ ኦሮሞዎችም ጋር አለ። የመንዙማ ዓይነቶች በጣም ብዙ ናቸዉ።

እስከ ዛሬ በስርዓቱ ስላላጠናናቸዉ አፍ ሞልቶ መናገር ግን አይቻልም። አሁን በይዘት ያሉት ግን በብዛት በካሴት ገበያም ላይ ያሉት፤ የኦሮምኛ እና የአማርኛ መንዙማዎች ናቸዉ። እነዚህ ሥራዎች ወደ ሕዝቡ ቀርበዋል፤ ምሑራን ይዘቶቻቸዉን እየተነተኑ የሚጽፉት ለጥናት ምርምር ግብዓት እየሆነ ነዉ በግለሰብ ደረጃም የእያንዳንዱን እየነቀሱም የሚያጠኑ ምሑራንም አሉ። ከዛ ዉጭ ያለዉን የሚያጠኑ አሉ። የአቀራረቡ ይዘት በጣም የተለያየ ነበር። ከዚህ በፊት አዲስ አበባም ላይ አንድ ዓለማቀፍ የመንዙማ ጉባዔ አካሂደን ነበር። ይህ ዋርሶ ላይ የተደረገዉ ጉባዔ ለመንዙማ ዓለማቀፍ ጥናት መድረክ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑ ነዉ። ከዚህም ሌላ በተከታታይ ስለመንዙማ የጥናት ዝግጅቶች ይኖሩናል። የእዉቀት አድማሳችን በየጊዜዉ እየሰፋ የማወዳደርያም ነገር እያደረግነዉ ነዉ። የኢትዮጵያ መንዙማ ከዓለም አቀፍ መንዙማ እንዲሁም ከኦርቶዶክስ ዝማሬ ጋር ያለዉን ልዩነት እና ቅርበት የሚጠናበት ጊዜ ነዉ። በተለይ የሙዚቃ ቅኝት ጥናት ምሑራን የበለጠ ዘርፉን ያሰፉታል ብዩ ተስፋ አደርጋለሁ።» 

ዶክተር አንድርያስ ቬተር በአፍሪቃ ቋንቋዎች ሙዚቃ እና ባህል ዙርያ በርካታ የምርምር ስራዎችን አድርጎአል። ኢትዮጵያዉያንም ከጫፍ እስከ ጫፍ ዞር ጎብኝቶአታል፤ አጥንቷታልም። የአዝማሪን ሥራ ለጀርመናዉያን ብሎም በዓለም አቀፍ መድረክ ለማስተዋወቅ ጥረት ካደረጉት ምሁራን ዉስጥ አንዱም ነዉ። ንጹህ ጀርመናዊ ነዉ። የኢትዮጽያን ባህላዊ ምግቦች እጅግ ይወዳል። ከባህላዊ ምግብ ሌላ የበዛወርቅ ትዝታ የዚነት ሙሃባ ዜማ፤ የኤፍሪም ሙዚቃ እጅግ እንደሚያዝናዉ ከዚህ ቀደም አጫዉቶናል። ኢትዮጽያን ስለሚወድ ቋንቋዋን አጥንቶ ባህልዋን ለምዶ እዚህ በሃገሩ በጀርመን በመዲና በርሊን በሚገኘዉ እዉቁ የሁን ቦልት ዪንቨርስቲ በአፍሪቃ በተለይ ደግሞ በኢትዮጽያ የአማረኛ እና በመጥፋት ላይ ባለዉ የአርጎባ ቋንቋ ላይ ጥናት ያደርጋል። በዋርሶ ጉባዔ ላይ በኢትዮጵያ የሥነ-ልሳናዊ ጥናትና መንዙማ ላይ የሰራዉን ጥናት እንዳቀበ ነግሮናል።

እንደ አህመድ ዘካርያ ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያን ጥናት በተመለከተ በአብዛኛዉ ብዕራባዉያን ምሑራን ነበር የሚሳተፉበት ያሉት ባለፉት ጥቂት ዓመታት ጀምሮ ግን በርካታ ኢትዮጵያዉያን ተመራማሪዎች በተለያዩ ዘርፎች የኢትዮጵያን ጉዳይ በጥልቅ እያጠኑ መሆን ተናግረዋል።

ኢትዮጵያን እናጥናት እያሉ ታሪክዋን ባህሉዋን ማኅበረሰቡን ወንዝ ሸንተረሯን የሚያጠኑ የሚመረምሩ አያሌ የዓለም ምሁራን የሚፈልጔት ብቸኛ ሃገር ናት ሲሉ የኢትዮጵያ የጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ዶክተር አህመድ ሀሰን ገልፀዋል።



ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG
መስከረም 28/2008 ዓም (ኦክቶበር 9/2015)

Thursday, October 8, 2015

ያጣነው ነፃነታችንን ብቻ አይደለም አገራችንንም ጭምር እንጂ።ኮ/ል ባጫ፣ጋዜጠኛ ሙሉጌታ እና አምባሳደር ዘውዴ አገሩን ባልተነጠቀ ሕዝብ መሃከል አርፈው ቢሆን ኖሮ (የጉዳያችን አጭር ማስታወሻ)


አገር የሰንደቅ አላማ በምሰሶ ላይ በነፋስ የመወዛወዙ ፋይዳ ብቻ አይደለም።አገር የይስሙላ ምክር ቤት ለምን እንደተሰበሰቡ እና ምን እንደሚሰሩ በማያውቁ ሰዎች ሞልቶ የካሜራ ጋጋታ ከፊታቸው ማርመስመስ አይደለም።

አዎን! ኢትዮጵያውያን በእዚች ሰአት አገራቸውን  በባንዳ እና ለገንዘብ ባደሩ የጊዜው ገዢዎች መነጠቃችንን ለማወቅ ብዙ መመራመር አያስፈልገንም።አገራችንን ያልተነጠቅን ቢሆን ኖሮማ ከሁለት ሚልዮን በላይ ስደተኛ በመላው ዓለም ተበትኖ አይገኝም ነበር።አገራችንን ያልተነጠቅን ቢሆን ኖሮማ ከአፍሪካ የተማረ የሰው ኃይሏን በማሰደድ ቀዳሚ ሀገር መሆናችንን የጎረቤታችን የሱዳን ጋዜጣ አይነግረንም ነበር።አገራችንን ያልተነጠቅን ቢሆን ኖሮ እህቶቻችን የአረብ ሀገር ዘመናዊ ባርነት ባልተዳረጉ ነበር። አገራችንን ያልተነጠቅን ቢሆን ኖሮ ከአፍሪካውያን አቅም ስደተኛ ተብለን መኖርያ የምንለምን አንሆንም ነበር።አገራችንን ያልተነጠቅን ቢሆን ኖሮማ ከመቶሺህ  በላይ ኢትዮጵያውያን ሕፃናት በኢትዮጵያ ከተሞች የጎዳና ተዳዳሪ ሆነው በእየቆሻሻው ላይ የተደፋ ፍርፋሪ ለቀማ ባልተዳረጉ ነበር።አገራችንን ያልተቀማን ቢሆን ኖሮማ በእየዓመቱ ሕፃናት ከእናት አባታቸው ጉያ እየተነጠቁ ለባእዳን በማደጎነት እየተላኩ የዶላር መሰብሰብያ ባልሆኑ ነበር።

አዎን! ያጣነው ነፃነታችንን ብቻ አይደለም አገራችንንም ጭምር ነው።

ነፃነታችንን እና አገራችንን የነጠቁን እና አምባገነንነትን አጥፍተን እኩልነት እናሰፍናለን ብለው ስልጣን ላይ ሲወጡ የከዱን ከሃዲዎች የክህደታቸውን ዳር ለእራሳቸው ደጋፊዎች ግራ እስከሚያጋባ ድረስ ኢትዮጵያን የባእዳን የረከሰ ባህል መፈንጫ፣አንጡራ ሀብቷን በሰንሰለት ለተሳሰሩት ባንዳ  እያከፋፈሉ የድሃ ድሃ አድርገው የእነርሱን ኪስ እየሞሉ ይሄው ሁለት አስርተ አመታት አለፉ።ሕዝቡን የማደህየታቸው ማሳያ ዛሬ በልቶ ለማደር ምን ያህል ፈታኝ ተግባር እንደሆነ መመልከት በእራሱ በቂ ነው።የአገልግሎት ሰጪ ድርጅቶች አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየወረደ አሳፋሪ ደረጃ ደርሷል። መብራት ከአዲስ አበባ አንስታችሁ በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል በማንኛውም ጊዜ ይጠፋል።ይልቁንም አንዳንድ ቦታዎች ላይ የእዚህ ፅሁፍ አቅራቢ እንዳለው መረጃ ካለምንም ማጋነን እስከ ሶስት ቀናት ጠፍቶ የሚመጣበት ለእዚህም ሕዝብ ይቅርታ የማይጠየቅባት አገር ነች ኢትዮጵያ።ከሃያ አመታት በፊት መብራት ኃይል በእዚህ አይነት ደረጃ አገልግሎቱን ቀልዶበት አያውቅም ነበር።ከሃያ አመታት በፊት በደርግ ዘመን መብራት ከመጥፋቱ ከ72 ሰዓት በፊት መጥፋቱን በራድዮ እና ቴሌቭዥን ይነገር ነበር። ዛሬ በ21ኛው ክ/ዘመን የደንበኛ ፅንሰ ሃሳብን አፈር ድሜ ያስገቡ የአገራችን እና የነፃነታችን ነጣቂዎች  ለሱዳን እና ለጅቡቲ መብራት እያደሉ ኢትዮጵያን እንድትጨልም ፈርደው እነርሱ ጀነሬተር እያስመጡ ይቸበችቡልን ገቡ። 

ኮ/ል ባጫ ሁንዴ፣ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ እና አምባሳደር ዘውዴ ረታ ነፃነቱን እና አገሩን ባልተነጠቀ ሕዝብ መሃከል አርፈው ቢሆን ኖሮ 


ሰሞኑን ለኢትዮጵያ በጎ የሰሩ ሶስት የታሪክ ፈርጦች ከእዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።እነርሱም ኮ/ል ባጫ ሁንዴ፣ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ እና አምባሳደር ዘውዴ ረታ ናቸው።ኮ/ል ባጫ ሁንዴ ኢትዮጵያ ከዚያድባሬዋ ሱማሌ በ1969 ዓም በተሰነዘረባት ጥቃት በኢትዮጵያ አየር ኃይል በጀት አብራሪነት በጀግንነት ጀብዱ የሰሩ እና ዛሬ በነፃነት እና ካለምንም የታሪክ ጠባሳ አንገታችንን ቀና አድርገን እንድንሄድ ያደረጉን ኩሩ ኢትዮጵያዊ ናቸው።ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ ቀደም ብለው በማስታወቂያ መስርያ ቤት ቀጥለው የመጀመርያው የነፃ ፕሬስ ፈር ቀዳጅ ሆነው በተለይ ''ሰው ማለት ሰው የሆነ ነው ሰው የጠፋለት'' እንደሚባለው ለኢትዮጵያ የሚናገር ሰው በሌለበት ፈር ቀደው መናገርን፣መፃፍን እና የመፃፍ ኃይል ምን ያህል አምባገነኖችን እንደሚያንቀጠቅጥ ያሳዩ፣አሁን ላሉት ወጣት ጋዜጠኞች መንገድ እና ወኔ ያስተማሩ፣ከእዚህም ሁሉ በላይ እስከ ሕይወታቸው ፍፃሜ ድረስ ስለ ኢትዮጵያ ሲናገሩ ያለፉ የብእር አርበኛ ናቸው።አምባሳደር ዘውዴ ረታ በቀዳማዊ አፄ ኃይለስላሴ ዘመን በኢትዮጵያ ራድዮ እና ቴሌቭዥን በጋዜጠኝነት፣በማስታወቂያ ሚኒስትር ምክትል ሚኒስትርነት፣በምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ደረጃ አገራቸውን አገልግለዋል።አምባሳደር ዘውዴ ለመጪው ትውልድ ለምርምርም የሚረዱ ''የኤርትራ ጉዳይ''፣''ተፈሪ መኮንን ረዥሙ የስልጣን ጉዞ''፣''የቀዳማዊ ኃ/ስላሴ መንግስት'' የተባሉ መፃህፍቶቻቸው ለትውልድ የተሰሩ ቅርሶች ናቸው።

ወደ ፅሁፌ ዋና ነጥብ ልመለስ።ኮ/ል ባጫ ሁንዴ፣ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ሉሌ እና አምባሳደር ዘውዴ ረታ ነፃነቱን እና አገሩን ባልተነጠቀ ሕዝብ መሃከል አርፈው ቢሆን ኖሮ የእረፍታቸው ዜና ለኢትዮጵያ እንዴት ይነገር ነበር? ብለን እናስብ።የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን በድንገት መርሃ ግብሩን ያቆምና በሰበር ዜናነት የ1969 ዓም የኢትዮጵያ እና የሱማልያ ጦርነትን እያሳየ ኮ/ል ባጫን ፎቶ እያሳየ እረፍታቸውን ባረዳን ነበር።ቀብራቸውንም  በታላቅ ወታደራዊ ሰልፍ እና ከትውልድ ቦታቸው ግንጪ፣ወለጋ በመጡ ፈረሰኞች ከፊት እየመሩ እና የአዲስ አበባ ሕዝብ አጅቦ ቀብራቸው በተፈፀመ ነበር።ጀግና እና ለሀገሩ የሰራ ሲከበር የተመለከተ ወጣት እንደ ጀግናው ለመሆን ይመኛልና የእዚህ አይነት ቀብር በእራሱ ጀግና ወልዶ ያድር ነበር።አገራችንን ተነጥቀን ባይሆን ኖሮ የኢትዮጵያ አየር ኃይል በቀብሩ ስርዓት ላይ በአዲስ አበባ ሰማዮች ላይ እየተስገመገመ ሲበር ይታይ ነበር።አገር እና ነፃነትን ባንነጠቅ ኖሮ የኢትዮጵያ አየር ኃይል በሚገነባው ሙዚየም ውስጥ የኮ/ል ባጫ እና ሌሎች ጀግና የአየር ኃይሉ ባለ ገድሎች ታሪክ ተዘርዝሮ ለሕዝብ በታየ ነበር።አገር እና ነፃነታችንን ተነጥቀን ባይሆን ኖሮ ጋዜጠኛ ሙሉጌታ እና አምባሳደር ዘውዴ እንዲህ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን 50ኛ አመቱ ዋዜማ ላይ ሆኖ የቀደሙትን የሚያስብበት ትልቅ አጋጣሚ በሆነለት ነበር።በተለይ አምባሳደር ዘውዴ ከማስታወቂያ ሚኒስቴር ባለፈ የሰሩበት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አንጋፋው ዲፕሎማት በማረፋቸው ሃዘናችንን እንገልፃለን ብሎ መግለጫ ያወጣ ነበር።

ባጠቃላይ ነፃነታችንን ብቻ ሳይሆን አገራችንንም ጭምር መነጠቃችንን ለማጤን ከላይ የተጠቀሱትን የኢትዮጵያ ውድ ልጆች ከእዚህ ዓለም በሞት መለየት በስልጣን ላይ ያሉት አሁን በኢትዮጵያ ሕዝብ የሚነግዱት አምባገነን ገዢዎች እንዳልሰሙ ዝም የሚሉት ለምን እንደሆነ ይገባን ይሆን? ኮ/ል ባጫ ሁንዴን የዚያድባሬ ቴሌቭዥን ጣቢያ እንዲያመሰግናቸው እና ማረፋቸውን በሃዘን እንዲዘግብ አይጠብቅም።የዛሬዋ የኢትዮጵያ ቴሌቭዥንም ተመሳሳይ ሥራ ሰራ።ስለ አምባሳደር ዘውዴ ረታ ታላላቅ ስራዎች በማመስገን እና እረፍታቸውን በሃዘን እንዲዘግቡ ኢትዮጵያን እንደ አገር የሚጠሉ አገራት የዜና አውታሮች እንዲናገሩ አይጠበቅም።ይልቁንም ጀግኖቹ ኮ/ል ባጫ እና ጋዜጠኛ ሙሉጌታ ቀብራቸው በሚወዷት አገራቸው አፈር ላይ ሳይሆን በምድረ አሜሪካ ሆነ።ቀብራቸውን ጨምሮ የማለፋቸው ዜና ግን በኢትዮጵያ ስም በተሰየመ መንግስት እና የቴሌቭዥን ጣቢያ ላይ እንደ አንድ አገር ወዳዶች ቀርቶ በውጭ አገር በጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ዜና የሚሰጠውን ሽፋን አለማግኘቱ  ግን እየቆየ የሚያንገበግበንን አንድ  ጉዳይን ያስረግጥልናል።ይሄውም ያጣነው ነፃነታችንን ብቻ ሳይሆን አገራችንንም ጭምር መሆኑን።


ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG
ጥቅምት 27/2008 ዓም (ኦክቶበር 8/2015)

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።