ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, October 9, 2015

በፖላንድ፣ዋርሶ የተደረገው 19ኛው የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ሪፖርት The 19th International Conference of Ethiopian Studies (Warsaw 24-28 August, 2015)



ከነሐሴ 24-28/2015 እኤአ በፖላንድ፣ዋርሶ የተደረገው 19ኛው የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ 
ተሳታፊዎች።ፎቶ ከጀርመን ድምፅ ራድዮ አማርኛው አገልግሎት የተገኘ

ከ60 ዓመት በላይ የሆነዉ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ የሀገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ትኩረት ነፍገውታል።አለም ስለእኛ ሲያጠና እኛ ለምን ዝም እንደምንል እንቆቅልሽ ነው።ቀደም ተብሎ በእዚሁ ጡመራ ላይ ጉባኤው ከመከፈቱ በፊት በወጣው ፅሁፍ ላይ አስራ ዘጠነኛው የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ...በሚል ርዕስ ስር እንደተገለፀው ይህ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ከመደረጉ በፊት እና ጉባኤው ከተደረገ በኃላ የነበሩትን ክንውኖች የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ከ24 ዓመታት በፊት በልዩ ዘገባ ያቀርብ የነበረ መሆኑን እና በተለይ በጉባዔው ላይ የተሳተፉት ምሁራን ሰፊ ጋዜጣዊ መግለጫ ይሰጡ እንደነበር ተገልጧል።ይህም በአገር ቤት ላለው ወጣት ስለ አገሩ የበለጠ እንዲረዳ እንደሚያደርገው ይታወቃል።

ይህ ሁኔታ ግን በዘመነ ኢህአዴግ/ሀውሃት ቀርቷል።ስለጉባዔው የመንግስቱ መገናኛ ብዙሃን አይተነፍሱም።የዓለም ምሁራን ስለ ኢትዮጵያ ጥናት ለማድረግ ሲሰበስቡ የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን እና በመንግሥትነት የተሰየመው አካል ከፍተኛ ልዑክ አይልክም።ከእዚህ ይልቅ በዩንቨርስቲ ያሉ ወጣት ምሁራን በከፍተኛ ውጣ ውረድ በጉባዔው ላይ ለመሳተፍ ይሞክራሉ።ዘንድሮም ከኢትዮጵያ ዩንቨርስቲዎች ወደ 100 የሚጠጉ ምሁራን ሲገኙ በጠቅላላው ከመላው ዓለም 476 ምሁራን መሳተፋቸውን ለማወቅ ተችሏል።ኢትዮጵያ በስንቱ ትበደላለች? መቼ ይሆን የኢትዮጵያን በጎ ነገር የሚያጎላ መንግስት የሚኖረን? ከ1953 ዓም ጀምሮ በእየሶስት ዓመቱ  የሚደረገው ይህ ጉባዔ በርካታ ጥናቶች በተለያዩ ምሁራን ቀርቧል።እነኝህ ጥናቶች ለሕዝብ ለምን ይፋ አይደረጉም? የጥናቶቹ አቅራቢዎች ጋር ሰፊ ውይይት ማድረግ እና ሃሳባቸውን ለሕዝብ የማስተዋወቅ ሥራ ለምን አይሰራም? የኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የኢትዮጵያ የሚል ስም ይዞ በኢትዮጵያ ስም የሚደረጉ ታላቅ የጥናት ጉባዔን ለምን እንዳላየ አለፈው? ብዙ ጥያቄ ይጭራል። በተለይ የእዚህ አይነቱ በርካታ ክርክሮችን ሊፈጥር የሚችሉ ሃሳቦች የሚነሱበት የምርምር ጉዳይ ባለቤት ሳይኖረው ወይንም በአግባቡ መያዝ ሳይቻል ከቀረ ሌሎች ስለ እራሳችን እንዲናገሩ የምንተወው ሜዳ እንዳይሆንም ያሰጋል።  
ከዋርሶ ዩንቨርሲቲ ድረ-ገፅ የተገኘ ጉባኤውን አስመልክቶ የወጣ ፖስተር 

=====\\\\\\\\\\\==========\\\\\\\\\\\=======\\\\\\\\\\\\==============\\\\\\\\\\\\\=========

ከእዚህ በታች ያለው ፅሁፍ ከጀርመን ድምፅ የአማርኛው አገልግሎት መስከረም 24/2015 ዓም እ ኤ አቆጣጠር ጉባኤውን አስመልክቶ አዜብ ታደሰ እና አርያም ተክሌ ተዘጋጅቶ የቀረበው ሪፖርት ነው

መስከረም 24/2015 ዓም እ ኤ አቆጣጠር
አዜብ ታደሰ እና አርያም ተክሌ 
የጀርመን ድምፅ የአማርኛው አገልግሎት

የጥንታዊ ቅርሶችና ታሪክ ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያ ከረጅም ጊዜ አንስቶ የታሪክ የቅርስ ተመራማሪዎችን ትኩረት እንደሳበች ናት።ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ለሚካሄዱት የተለያዩ ጥናቶች ግብዓትነት ትልቅ አስተዋፅኦን ማድረጉም ይታወቃል። ለዚህም ከ60 ዓመት በላይ የሆነዉ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ተጠቃሽ ነዉ። ስለጉባዔዉ ፋይዳ ኢትዮጵያዉያንና አንድ ጀርመናዊ የጉባዔዉን ተሳታፊን አነጋግረንናል።

የመጀመርያዉ ኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ በጎርጎሪዮሳዊ 1959 ዓ,ም ነዉ የተካሄደዉ። በየሶስት ዓመት አንድ ጊዜ የሚደረገዉ ይህ ጉባዔ አንድ ጊዜ ኢትዮጵያ ዉስጥ ሁለት ጊዜ ከኢትዮጵያ ዉጭ በመፈራረቅ ነዉ ትኩረታቸዉን በኢትዮጵያ ባህል፤ ታሪክ፤ ቅርስ፤ ቋንቋ ላይ ያደረጉ የምሑራን ጥናታዊ ጽሑፎች የሚቀርቡበት። በፖላንድ መዲና ላይ ለአምስት ቀናት የተካሄደዉ የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ምን ዓይነት መልክ ነበረዉ ? በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ የጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ዶክተር አህመድ ሀሰን፤« ይህ ጉባዔ ታሪክን ብቻ ሳይሆን የሚጠናዉ፤ በዚህ ጉባዔ ሥነ-ሕዝብ ይጠናል የቋንቋና ፤ ማኅበረሰባዊ ሳይንስ፤ ሥነ-ቋንቋ በሙሉ የሚቀርብበትና አዳዲስ ሃሳቦች የሚፈልቁበት ነዉ ። ከነዚህ ሃሳቦች ደግሞ ትምህርት የሚገኝበት የእዉቀት አድማስ የሚሰፋበት ነዉ። እኔ ስብሰባዉን ከሚከፍቱት ሰዎች አንዱም ነበርኩ። በመክፈቻ ንግግሪ ያወሳሁት የጉባዔዉን ታሪክ ነዉ። 

ጉባዔዉ ለመጀመርያ ጎዜ በጎርጎረሳዊ 1959 ዓ,ም ሮም ላይ ተካሄደ ከዝያ በ1972 ዓ,ም ማንችስተር ብሪታንያ ፤ 3 ተኛዉ በ1966 አዲስ አበባ፤ በ 1972 ሮም ኢጣልያ፤ በ 1977 ዓ,ም ኒስ፤ ፈረንሳይ፤ በ1978 ዓ,ም ቺካጎ፤ ዩኤስ አሜሪካ ፤ በ1980፤ ቴላቪብ ፤ እስራኤል፤ በ1982 ዓ,ም ፈረንሳይ፤ በ1991 አዲስ አበባ፤ በ1994 ሚቺገን፤ ዩኤስ አሜሪካ፤ በ1977ዓ,ም ኪዮቶ ጃፓን፤ 2000 ዓ,ም አዲስ አበባ፤ በ2003 ሃንቡርግ፤ ጀርመን ፤ በ2007 ኖርዊ፤ በ2009 ዓ,ም አዲስ አበባ ፤ በ2012 ዓ,ም ድሪደዋ ፤ በ2015 ዓ,ም ዋርሶ ፖላንድ ላይ ነዉ የተካሄደዉ። ይህ ሲሆን ትልቁ ነገር የኢትዮጵያ ጥናት ጉባዔ ምስራቅ አዉሮጳ ላይ፤ በሩስያሞስኮ፤ ዋርሶ ፖላንድ፤ ላይ ሲካሄድ ምስራቁን ከምዕራቡ አደበላልቆ ብዙ ቦታዎችን የሚሸፍን የሕዝብን ትኩረት የሳበ ባህል ነዉ ያለን። በዚህ ጉዳይ እኛም የምንኮራዉ በታሪካችን በማንነታችን በባህላችን ነዉ። እነዚህ ጉባዔዎች የኢትዮጵያ ምስክር ናቸዉ።» 

በዋርሶ በተካሄደዉ ኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ወደ 476 ጉባዔተኞች ተገኝተዉበታ። በዚህ ጉባዔ የሚደንቀዉ ነገር ከኢትዮጵያ ተሳፍረዉ የመጡ ከ 100 በላይ ምሑራን ተሳታፊዎች እንደነበሩ ዶክተር አህመድ ሀሰን ተናግረዋል።

« በፖላንዱ ጉባዔ ኢትዮጵያ ዉስጥ ያሉ ዩንቨርስቲዎችን አሰባስበናል። የክልል ዩንቨርስቲዎች በጣም በሚያስደስት ሁኔታ ለምሁራኖቻቸዉ ገንዘብ እየሸፈኑ ወደ ጉባዔዉ ልከዋቸዋል። የምርምሩ አጀንዳ ዘርፈ ብዙ ነዉ። ችግር ፈቺ ምርምሮች ያሉበት ነዉ። የሚገርመዉ በዚህ ጉባዔ በርካታ ኢትዮጵያዉያን ከኢትዮጵያ ዉጭ ሲሳፉ ለመጀመርያ ነበር። ኢትዮጵያዉያን መምህራን በከፍተኛ ቁጥር ታይተዋል። ከመቶ በላይ ነበሩ።»

በጀርመን መዲና ነዋሪ የሆነዉ የአፍሪቃ ጉዳይ ተመራማሪ እና አማረኛ ቋንቋ ተናጋሪዉ ጀርመናዊ ዶክተር አንድሪያስ ቬተር እስካሁን በተደረጉት በአብዛኞቹ ኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔ ተካፋይ ነበር። በጉባዔዉ ላይ ስለኢትዮጵያ መንዙማ የጥናት ጽሑፋቸዉን አቅርበዋል። ዘንድሮ ዋርሶ ላይ የተደረገዉ ይህ ጉባዔ፤ ከዚህ ቀደም ከተካሄዱት በምን ይለያል፤ ለሚለዉ ጥቃቄ ዶ/ር አንድርያስ ቬተር

«የሚለየዉ ቦታዉ አዲስ በመሆኑ ነዉ። ከሶስት ዓመት በፊት ጉባዔዉ የተካሄደዉ ድሪደዋ ላይ ነበር። ብዙ ልዩነት አልታየኝም። ጉባዔዉ ከድሮ ጊዜ ልዩነቱ አሁን ኢትዮጵያዉስጥ ብዙ ዩንቨርስቲዎች ስላሉ የኢትዮጵያ ምሁራን የኢትዮጵያ ተመራማሪዎች እየበዙ መምጣታቸዉ ነዉ። ቀደም ሲል በሀገር ደረጃ ሲታይ አብዛኛዉ የጉባዔ ተሳታፊ የሚመጣዉ ከጀርመን ነበር። አሁን ግን ከኢትዮጵያ የመጡ ተሳታፊ ምሑራን ነበሩ አብዛኞቹ። እንደዉም በገንዘብ ችግር ምክንያት ብዙዎች መምጣት አልቻሉም።»

ሌላዉ የጉባዔዉ ተሳታፊ በኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ረዳት ፕሮፊሰር አህመድ ዘካርያ ናቸዉ። አህመድ ዘካርያ በጉባዔዉ ላይ ስለ ኢትዮጵያ መንዙማ የጥናት ጽሑፋቸዉን ካቀረቡት ጥቂት ምሑራን መካከል አንዱም ነበሩ።

« በአጠቃላይ ስብሰባዉ በጣም ጥሩ ነበር። በዚህ ጉባዔ ስለ ኢትዮጵያ መንዙማ ብዙ የጥናት ጽሑፎች ቀርበዋል። በአጠቃላይ ስለ መንዙማ ይዘት ፤ ስለ ወሎ መንዙማ፤ ስለ ሀረር መንዙማ፤ ስለ ሙዚቃዊ ይዘቱ፤ ስለ ያዘዉ ሥነ- ጽሑፍ የተለያዩ የጥናት ወረቀቶች ቀርበዋል። በኢትዮጵያ ያለዉን የመንዙማ ዓይነቶች ለመዳሰስ ተሞክሮአል። አሁንም ግን አጠቃላይ ነዉ ማለት አይቻልም። ምክንያቱም መንዙማ አፋሮች፤ ሶማሌዎች፤ ኦሮሞዎችም ጋር አለ። የመንዙማ ዓይነቶች በጣም ብዙ ናቸዉ።

እስከ ዛሬ በስርዓቱ ስላላጠናናቸዉ አፍ ሞልቶ መናገር ግን አይቻልም። አሁን በይዘት ያሉት ግን በብዛት በካሴት ገበያም ላይ ያሉት፤ የኦሮምኛ እና የአማርኛ መንዙማዎች ናቸዉ። እነዚህ ሥራዎች ወደ ሕዝቡ ቀርበዋል፤ ምሑራን ይዘቶቻቸዉን እየተነተኑ የሚጽፉት ለጥናት ምርምር ግብዓት እየሆነ ነዉ በግለሰብ ደረጃም የእያንዳንዱን እየነቀሱም የሚያጠኑ ምሑራንም አሉ። ከዛ ዉጭ ያለዉን የሚያጠኑ አሉ። የአቀራረቡ ይዘት በጣም የተለያየ ነበር። ከዚህ በፊት አዲስ አበባም ላይ አንድ ዓለማቀፍ የመንዙማ ጉባዔ አካሂደን ነበር። ይህ ዋርሶ ላይ የተደረገዉ ጉባዔ ለመንዙማ ዓለማቀፍ ጥናት መድረክ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑ ነዉ። ከዚህም ሌላ በተከታታይ ስለመንዙማ የጥናት ዝግጅቶች ይኖሩናል። የእዉቀት አድማሳችን በየጊዜዉ እየሰፋ የማወዳደርያም ነገር እያደረግነዉ ነዉ። የኢትዮጵያ መንዙማ ከዓለም አቀፍ መንዙማ እንዲሁም ከኦርቶዶክስ ዝማሬ ጋር ያለዉን ልዩነት እና ቅርበት የሚጠናበት ጊዜ ነዉ። በተለይ የሙዚቃ ቅኝት ጥናት ምሑራን የበለጠ ዘርፉን ያሰፉታል ብዩ ተስፋ አደርጋለሁ።» 

ዶክተር አንድርያስ ቬተር በአፍሪቃ ቋንቋዎች ሙዚቃ እና ባህል ዙርያ በርካታ የምርምር ስራዎችን አድርጎአል። ኢትዮጵያዉያንም ከጫፍ እስከ ጫፍ ዞር ጎብኝቶአታል፤ አጥንቷታልም። የአዝማሪን ሥራ ለጀርመናዉያን ብሎም በዓለም አቀፍ መድረክ ለማስተዋወቅ ጥረት ካደረጉት ምሁራን ዉስጥ አንዱም ነዉ። ንጹህ ጀርመናዊ ነዉ። የኢትዮጽያን ባህላዊ ምግቦች እጅግ ይወዳል። ከባህላዊ ምግብ ሌላ የበዛወርቅ ትዝታ የዚነት ሙሃባ ዜማ፤ የኤፍሪም ሙዚቃ እጅግ እንደሚያዝናዉ ከዚህ ቀደም አጫዉቶናል። ኢትዮጽያን ስለሚወድ ቋንቋዋን አጥንቶ ባህልዋን ለምዶ እዚህ በሃገሩ በጀርመን በመዲና በርሊን በሚገኘዉ እዉቁ የሁን ቦልት ዪንቨርስቲ በአፍሪቃ በተለይ ደግሞ በኢትዮጽያ የአማረኛ እና በመጥፋት ላይ ባለዉ የአርጎባ ቋንቋ ላይ ጥናት ያደርጋል። በዋርሶ ጉባዔ ላይ በኢትዮጵያ የሥነ-ልሳናዊ ጥናትና መንዙማ ላይ የሰራዉን ጥናት እንዳቀበ ነግሮናል።

እንደ አህመድ ዘካርያ ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያን ጥናት በተመለከተ በአብዛኛዉ ብዕራባዉያን ምሑራን ነበር የሚሳተፉበት ያሉት ባለፉት ጥቂት ዓመታት ጀምሮ ግን በርካታ ኢትዮጵያዉያን ተመራማሪዎች በተለያዩ ዘርፎች የኢትዮጵያን ጉዳይ በጥልቅ እያጠኑ መሆን ተናግረዋል።

ኢትዮጵያን እናጥናት እያሉ ታሪክዋን ባህሉዋን ማኅበረሰቡን ወንዝ ሸንተረሯን የሚያጠኑ የሚመረምሩ አያሌ የዓለም ምሁራን የሚፈልጔት ብቸኛ ሃገር ናት ሲሉ የኢትዮጵያ የጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ዶክተር አህመድ ሀሰን ገልፀዋል።



ጉዳያችን GUDAYACHN BLOG
መስከረም 28/2008 ዓም (ኦክቶበር 9/2015)

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።