ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, March 16, 2012

የ ኤርትራ ጉዳይ ና የ ሃያ አንደኛው ክ/ዘመን ልጆች አስተሳሰብ


በ ካርታ ጫወጣ ጎበዝ አደለሁም። ግን ጆከር የተባለች ካርታ መኖሯን አውቃለሁ።ጆከር ካርታ በ ሁሉም ቦታ ስለምትገባ በ ካርታ ጫወታ ጆከር የደረሰው ሰው የማሸነፍ እድል ስላለው ፊቱ በ ፈገግታ ይሞላል።
  የ አትዮጵያ ና የ ኤርትራ  ጉዳይን መሪዎቻችን   የ ፖለቲካ መጫወቻ ''ጆከር''  ካርድ  ካደረጉት  ቆዩ።  ፕሬዝዳንት ኢሳያስም ሆኑ ጠቅላይ ሚ/ር  መለስ ይችን ''ጆከር'' የተባለችውን የ ካርታ ካርድ በየሀገራቸው ይጫወቱበታል። በስልጣን ላይ ለመቆየት ይችን የ ኢትዮጵያ ና ኤርትራ ካርድ ትመዘዛለች፣ትርገበግባለች፣ትውለበለባለች፣በ ንግግር ላይ ጣል ትደረጋለች፣አስፈላጊ ሲሆን ደሞ ወደ ፋይል ክፍል ትገባና ስትጠራ የ አራዳ ልጅ  ''ከች በ ኮረኮንች'' አንደሚለው ''አንደገና ጆከር አንደገና'' ተብላ ትመዘዛለች።

የ ሃያአንደኛው ክፍለ ዘመን ልጆች  አዲሱ አስተሳሰብ

በ ሃያኛው ክ/ዘመን አጋማሽ የተነሳ የ ኤርትራ ጉዳይ ይሄው  እስከ ትናንትና ምሽት ድረስ ካርዱ እየተመዘዘ በሰው ሕይወት መቀለዱ ቀጥሏል። ይህን ችግር የፈጠረው ትውልድ ወደድንም ጠላንም እያለፈ ነው። በእናታቸው  ከ እንደርታ (ትግራይ) የሚወለዱት ፕሬዝዳንት  ኢሳያስም ሆኑ በ እናታቸው ከ ዓዲቇላ(ኤርትራ) የሚወለዱት ጠቅላይ ሚ/ር መለስ ዜናዊ ለምን የ ጆከሯን ካርታ በየጊዜው  እየመዘዙ ሕዝቡን እንደምያሰቃዩት የሁሉም ሰው ያልተፈታ እንቆቅልሽ ነው ።
አንድ ነገር ግን መገንዘብ ይቻላል ከመቸውም ጊዜ በበለጠ ህዝቡ የ ፖለቲከኞችን ልፈፋ ወደጎን ትቶ ነገሮችን የምያጠናበት ጊዜ ላይ መድረሱን ማንም ልብ ያለው ያለ አይመስልም። ኢሳያስም ሆኑ መለስ ካለ አንዳች ''ሃይ'' ባይ በ ፈለጉት መንገድ ላለፉት ሃያ አመታት የመሩት ሀገር ዛሬ ላይ ሲመለከቱት ብዙ ታሪካዊ ስህተቶች መኖራቸውን አፋቸው ባይናገረው ህሊናቸው ይፈርደዋል።ሁለቱም  ባለፉት ሃያ አመታት በታሪክ ታይቶ ያልታወቀ ስደተኛ በመላው ዓለም ማፍራታቸው  ቢያንስ  ለ ህዝቡ ያልሰሩት አልያም ያጎደሉት  ብዙ ሥራ መኖሩን ካልነገራቸው ጉድ  ነው።
አዎን! በ አልፈው ታሪካችን በጎ ዘመን የመኖሩን ያህል የ ፈተና ዘመን አልነበርም ማለት አይቻልም። ግን ቀይ ሽብር  አስመራ ላይ ሲሰማ አዲስ አበባም  በተመሳሳይ መንገድ ትታመስ ነበር። በየዘመኑ የነበሩ ፈተናዎች   በታሪክ አጋጣሚዎች የ ጦርነት አውድማ ያልሆኑ ቦታዎች ቢኖሩም መከራው ግን ያልጎበኘው ቤት አለ ማለት  ይከብዳል። ከዚህ ሁሉ በላይ ግን አንድ ደስ የሚል ሁሉንም የሚያስማማ ነጥብ አለ ። ይሄውም   እንደ ሕዝብ ተነስቶ  ሕዝብ በ ሕዝብ ላይ የሰራው በደል አለ ማለት ታሪካዊ ሂደቱን ና ክስተቱን አለማጠን ብቻ ነው ሳይሆን ተራ የ ፖለቲካ ፕሮፓጋንዳ ከመሆን የሚያልፍ አለመሆኑን ሁሉም መረዳቱ ነው። አሁን ቆም ብሎ የሚያስብ ትውልድ  ይመጣ ዘንድ መስራት አስፈላጊ ነው። ብዙዎች የተዘጋ ታሪክ የሚመስላቸው ግን ፖለቲካ፣ምጣኔ ሃብታዊ ትስስር፣ባህል፣ሃይማኖት፣ጆግራፍያዊ አቀማመጥ ወዘተ የ ሕዝቡን ችግር ከ ኢሳያሳዊ  ና መለሳዊ የ መለያየት ፖሊሲ በዘለለ ማሰብን የግድ ይላል።





የ ኤርትራ ጉዳይ'' እግሩ ሀገርቤት ይሁን እንጂ እራሱ ከ ውጭ ነው ''
የ ኤርትራ ጉዳይ'' እግሩ ሀገርቤት ይሁን እንጂ እራሱ ከ ውጭ ነው '' ያሉት አንድ የታሪክ ምሁር አይረሱኝም። ጣልያን ኤርትራን በ አስራዘጠነኛው ክ/ዘመን ማጠናቀቅያ ላይ በ ኃይል ከያዘች ጀምሮም ሆነ በፊት ሰሜናዊውን የ ሀገራችንን ክፍል ኦቶማን ቱርኮች ለመቆጣጠር ያላደረጉት ጥረት የለም ። ''የ ኤርትራ ጉዳይ በ ቀዳማዊ ኃይለሰላሴ ዘመን'' በተባለ ትልቅ ጥራዝ መፅሐፋቸው አምባሳደር ዘውደ ረታ ''ኤርትራን ከ አትዮጵያ ጋር አንድትኖር ከፈቀድንላት ሞተናታላ!'' በሚል ስሜት በ ተባበሩት መንግሥታት ቢሮ በየኮርደሩ በ ወቅቱ የ ኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስቴር በነበሩት አክሊሉ ሃብተወልድ  ላይ ከ ብዙ የ አረብ ሃገራት ይዛት የነበረ መሆኑን ፅፈውልናል።ይህም ''የ ኤርትራ ጉዳይ እራሱ ከ ውጭ'' የሚለውን አመላካች ጉዳይ ነው።
የ ሃያ ዓመት ትውልድ ካለፈው ክስተት የተማረበት ና ስለወደፊቱ ማሰብ የጀመረበት ወቅት ላይ መሆኑን ለማወቅ የ ቴዲ አፍሮን ''ዳህላክ ላይ ነው ቤቴ'' የሚለውን ዘፈን መስማት የግድ አይልም።  ባለፈው የካቲት ወር ላይ የ ኢትዮጵያ ና ኤርትራ ወዳጅነት ፎረም (Ethiopian and Eritrean frend ship forum) በ አሜሪካ ሳንጆሴ ካሊፎርንያ ውስጥ የ እራት መርሃግብር አዘጋጅቶ ነበር።http://ethiopianunitydiasporaforum.com/news/san-jose-hosts-ethio-eritrean-friendship-dinner/  ይህ ጅምር ነው።የ ሃያ አንደኛው ክ/ዘመን ልጆች ሥራ ይህ መሆን አለበት። የ ሃያንደኛው ክ/ዘመን ልጆች አዲስ ሃሳብ፣አዲስ መንገድ ግን አባቶቻቸው የኖሩበትን የ ፍቅር ጎዳና ተመልክተው መራመድ ይጠበቅባቸዋል። ሁል ጊዜ ''ቆራጡ መሪያችን'' ''አስተዋዩ መሪያችን'' እያልን ችግራችን እየመዘመዘ ሲፈጀን ምንም እንዳልሆን ብንተወው ለልጆቻችን ሌላ መከራ ከማቆየት በቀር ትርፍና ኪሳራውን የሚካፈለው ይሄው አዲሱ ትውልድ ነው።
አዲሱ ትውልድ የነገውን ታሪክ መስራት ነው እንጂ ያለፈው ታሪክ ላይ የሚያመጣው አዲስ ነገር ሊኖር አይችልም። ምክንያቱም ያለፈው ታሪክ መሰረታዊ እውነታዎችን ይዞ ይቀጥላል። ከእነዚህ  እውነታዎች ውስጥ -
  • ኢትዮጵያ የ ኢሳያስም ሆነ የ መለስ  እናት መሆኗን በ ህሊና ሁለቱም አይስቱትም ። ነገር ግን መከራዋን ከማብዛት በጎ በጎውን ማሰብ ቢጀምሩና የእናታቸውን ሃዘን ባያንሩባት ብሎ የሚያስብ ትውልድ መምጣቱን ፣
  • በታሪክ ቢያንስ አክሱም ላይ፣በ ሃይማኖት ቢያንስ በ ዘጠኙ ቅዱሳን ስደት፣በ ፀረ ኮሎንያሊዝም  ቢያንስ በ አብርሃምና ሞገስ የጀግንነት  ሥራ፣በ ባህል አመጋገብ ቢያንስ አሁንም በአንጀራና ወጥ--- ምን ቀረ ሁሉ ኢትዮጵያውነትን ማሳየቱ፣
  • እስከዛሬ ለተሰሩት ታሪካዊ ስህተቶች ጠያቂ ትውልድ የሚነሳ መሆኑን ካወቅን ለጊዜው ይበቃናል።
''ቆራጡ መሪያችን'' የት አደረሱን?
የ ፖለቲካም ሆነ የ ታሪክ ሀሁ አውቃለሁ የሚል ሰው ስለወደፊቱ ከ ራስ ካሳ እስከ ራስ ዱመራ (የ አሁኗ ኤርትራ) ሊከሰቱ የሚችለውን ነገር  መገመት ይቻላል ብዬ አስባለሁ።ይህን የ ግምት ክስተት የምፅፈው መዓት ለማውራት ሳይሆን በአካባቢው ላይ ባለፉት የ ዓለም ታሪኮች ከተከሰተው ና አሁን ከሚመስለው ነገር አንፃር መሆኑ ልብ ይባልልኝ።በ ቅርቡ በ አረቡ ዓለም የተነሳው ማአበል አዳዲስ ግን የመንግስታቸው ፕሮግራም ና ቅርፅ ያልታወቁ መንግስታትን ወደ ስልጣን አምጥቷል። ለምሳሌ ግብፅ በምንም አይነት በ አባይ ላይ ያላትን የመቆጣጠር ፍላጎት በ ቀጥታ ኢትዮጵያን በመውረር ለማከናወን የ ጆግራፊካል አቀማመቶች ይገድቧታል።ስለዚህ በመጀመርያ ኤርትራን መራመጃ ማድረግዋ ወይንም የ አክራሪ  እስልምናን በ ፖለቲካ አካህያድ ብቻ ሳይሆን ከ እምነቱ ና እስትንፋሱ ጋር የተዋሃደው መንግስት አስመራ ላይ  ማስቀመጥ የመጀመርያ ስራዋ ሊሆን እንደሚችል አልገመታችሁ ከሆነ አሁን ገምቱ። የ እዚህ አይነቱ ሂደት ደግሞ የ ሃይማኖት ችግርም ይዞ የሚመጣ ብቻ ሳይሆን በ ኢትዮጵያም ላይ የሚያስከትለው የራሱ ጥላ መኖሩ አይካድም።ያን ጊዜ ኤርትራውያን ወንድሞቻችን ና እሕቶቻችን ሌላ ችግራቸውን ከ ኢትዮጵያ በተለየ  የምፈታላቸው እንደማይኖር ማንም አይስተውም።ለዚህም ነው ሃያላኑ ሀገሮች የ አካባቢውን የ ኃይል ሚዛን  ከ ሰማንያ ሚልዮን በላይ የ ሕዝብ ብዛት በያዘችው ኢትዮጵያ አንፃር የሚመዝኑት መሆኑን ለ አፍታም መዘንጋት የለለብንም። ዛሬ አዲሱ ትውልድ የሚጀምረው በጎ  ጅማሮ ከላይ የተጠቀሰው ክፉ ጊዜ አይምጣ አንጂ ከመጣ በዝያን  ጊዜ ውስጥ ዛሬ የሚጀመሩት የ ህብረት ግንኙነቶችች  ታሪክ ይቀይራሉና ችላ ማለት አይገባም። ከዚህ ባለፈ ግን ''ቆራጡ መሪያችን'' እያሉ በ ''ቆራጡ መሪ ''አስተሳሰብ ከመሄድ ወጣ ያለ ግን ደግሞ የነገውን ክስተት፣ያለፈውን ታሪክ  ያገናዘበ ከ ግለሰቦች ቁጣ ይልቅ የ ተከታታይ ትውልድን ፍላጎት የሚያረካ  ሃሳብ ማምጣት አስፈላጊ ጊዜ ላይ ነን።
ይችን አነስተኛ ማስታወሻ ከማቆሜ በፊት የ አዲሱ ትውልድ አስተሳሰብ በ ዩቱዩብ እንዴት እንደተገለፀ በ እዚህ ቪድዮ ላይ ይመልከቱ::
ዩቱብ የተገኘ :- source.-http://www.youtube.com/watch?feature=player_embedded&v=hHd6ZImz5Dc&wl_token=Nmu5v7JHAIGaHl98BCaOW0H85iR8MTMzMjAwMzU4NUAxMzMxOTE3MTg1&wl_id=hHd6ZImz5Dc



ዩቱብ የተገኘ :- source.-http://www.youtube.com/watch?feature=player_embedded&v=hHd6ZImz5Dc&wl_token=Nmu5v7JHAIGaHl98BCaOW0H85iR8MTMzMjAwMzU4NUAxMzMxOTE3MTg1&wl_id=hHd6ZImz5Dc

አበቃሁ
ጌታቸው
ኦስሎ



3 comments:

Anonymous said...

IT IS GREAT OBSERVATION.THAT IS THE WAY EVERY BODY SHOULD UNDERSTAND SUCH CASES.THANK YOU KEEP IT UP.

selamawit said...

i think every body must read it.i share to all my friends.please others do also the same.

Anonymous said...

konjo tshuf I like it A M E S E G N A L E H U!!

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።