ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, July 3, 2018

የሆለታ ገነት የጦር አካዳሚን ስም ማን ሰወረው?

ጉዳያችን/Gudayachn
ሰኔ 26/2010 ዓም (ጁላይ 4/2018 እኤአ)

ሆለታ እና የጦር አካዳሚዋ

ከአዲስ አበባ ስላሳ አምስት ኪሎሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው የሆለታ ገነት ከተማ ከአዲስ አበባ ባልተናነሰ ታሪካዊ መነሻ አላት።በ1903 ዓም የመጀመርያው በውሃ ኃይል የሚሰራ ወፍጮ የተተከለባት ታሪካዊ ከተማ መሆኗን የታሪክ ምሁሩ ሪቻርድ ፓንክረስ ፅፈውላታል።የከተማው ስም ሆለታ (ኦለታ) ሲባል ገነት የሚለውን ስም የሰጧት ግን አፄ ምንሊክ እንደነበሩና  ከቦታው ማራኪነት የተነሳ እንደነበር ታሪኩን የሚያውቁ ይናገራሉ።አፄ ምንሊክ ቤተ መንግስታቸውን አዲስ ዓለም እና ሆለታ ላይ እንደሰሩ ይታወቃል።ቤተ መንግስታቸው ጋር ተያይዞም አሁን ማሰልጠኛው ባለበት ግቢ የኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን ትገኛለች።
ሆለታ ገነት ጦር የምትገኘው የኪዳነ ምህረት ታቦት በጦር ሰራዊቱ ታጅባ ወደ ጥምቀተ ባህር ስትሸኝ።

የሆለታ ገነት ጦር አካዳሚ በ1928 ዓም በቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ ስም በአምስት የስዊድን መኮንኖች አሰልጣኞች እገዛ ስራውን ጀመረ።ሆኖም ግን ወድያው የፋሽሽት ጣልያን ሀገራችንን መውረር የጦር ማሰልጠኛው በአግባቡ ስራውን ማከናወን አቃተው።በወቅቱ ስልጠና ይከታተሉ የነበሩ ሰልጣኞች የመጀመርያ ዘመናዊ ጦር ሰልጣኝ ስለነበሩ ብርቅ ተዋጊዎች ነበሩ።ከማሰልጠኛው ውስጥ የነበሩ ሰልጣኞችም ሆኑ ስልጠናውን ያጠናቀቁ የጥቁር አንበሳ ጦር በሚል አዲስ የአርበኞች እንቅስቃሴ በተለይ በምዕራብ ኢትዮጵያ ጀመሩ።
የጥቁር አንበሳ ጦር በፋሽሽት ጣልያን ወረራ ወቅት  በአርበኝነት የተሳተፉ የሆለታ ገነት ጦር ምሩቃን እና በውጭ የተማሩ ጥቂት ኢትዮጵያውያን የመሰረቱት ፀረ ፋሽሽት እንቅስቃሴ በጣልያን ላይ ዘመናዊ የጦር ውጊያ በማሳየት ብቻ ሳይሆን በጥንታዊ መንገድ ለሚዋጋው የኢትዮጵያ ገበሬ አርበኛ ዘመናዊ ውግያ ስልትን በማስተማር የጥቁር አንበሳ ጦር ያደረገው አስተዋፅኦ ቀላል አልነበረም።የጦር አካዳሚው ተመልሶ የተመሰረተው ጣልያን ከሀገራችን ተባርራ ንጉሰ ነገስቱ ተመልሰው ከመጡ በኃላ በ1935 ዓም ነበር።የጥቁር አንበሳ የጦር አካዳሚ ሆለታ ገነት ጦር አካዳሚ የሚል ስያሜ ያገኘው ደርግ ወደ ስልጣን ከመጣ በኃላ ነበር።

የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት ስም ማን ሰወረው?

የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት በአፍሪካ አንጋፋው በዓለማችንም ከሁለተኛ  ዓለም ጦርነት በፊት ከተመሰረቱ ጥቂት የጦር ትምህርት ቤቶች ውስጥ አንዱ ነው። ይህ ለሀገራችን የጦር ሰራዊት ታሪክ አንዱ እና አይነተኛ ቅርስም ነው።ይህ የጦር ትምህርት ቤት በዘመነ ህወሓት/ኢህአዴግ በ1990 ዓም ከሕግ ውጭ በሆነ መንገድ ለግማሽ ክፍለ ዘመን የሆለታ ገነት ጦር አካዳሚን ስም  አቶ መለስ ደምስሰው ሐየሎም አርአያ የጦር ማሰልጠኛ አሉት።ጉዳዩ በወቅቱ ከፍተኛ ተቃውሞ በተለይ ከጦር ትምህርት ቤቱ ከተመረቁ የቀድሞ ሰራዊት አባላት ቢነገርም ሰሚ አላገኘም።


ለማጠቃለል ማንንም መንግስት ለሚያደንቀው የጦር ሰው በስሙ ማሰልጠኛ መሰየም መብቱ ነው ብለን የምንናገር እንኖራለን።ሆኖም ግን ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ በአፍሪካም ሆነ በኢትዮጵያ ዝነኛ ማሰልጠኛን ታሪካዊ መሰረት በምንድ መልኩ በአንድ ሰው ስም መሰየም ፈፅሞ ተቀባይነት የለውም።የሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት የህዝብ፣የሀገር ከፍ ሲል ደግሞ የአፍሪካም ነው።ቀድሞ የነበረው ስም የግለሰብ ስም አይደለም።አሁንም ስሙ በክብር ሊመለስለት ይገባል።አቶ መለስ ለሐየሎም አዲስ ማሰልጠኛ ከፍተው መሰየም መብት ነበራቸው።ከጣልያን ፋሽሽት ጀምሮ ገድል የሰራ ታላቅ አፍሪካዊ የጦር አካዳሚን ታሪካዊ ዳራ በሚያጠፋ መልኩ ስሙን መቀየራቸው ግን ወንጀል ነው። አሁንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዓብይ ይህንን የስም ጉዳይ እንዲስተካከል ማድረግ አለባቸው።የሆለታ ከተማ ልጆችስ ለምንድን ነው ይህንኑ የሚጠይቅ የማኅበራዊ ሚድያ ጥያቄ የማትጀምሩት። ሆለታ ገነት ጦር ትምህርት ቤት ስምሽን ማን ሰወረው?

ጥቁር አንበሳ በድምፃዊ አብዱ ኪያር 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments: