ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, September 3, 2013

የህፃኑ ጥሪ - (እስክንድር ነጋን እና ሌሎች በግፍ የታሠሩ የህሊና እሥረኞችን ለማሰብ የተጻፈ! ግጥም በአንዱአለም በቀለ 2005ዓም)



በረንዳ ቢወጣ - እጉዋዳ ቢገባ፣
ቢጣራ ቢጣራ - አስሬ ቢል ባባ፣
እናቱን ቢያስጨንቅ - ፊቱ ተጥቦ በ'ንባ፣
ውስጧ ቢተራመስ - የሷም ሆድ ቢባባ፣
መልስ ግን የላትም - ታውቀዋለችና፣
ለጊዜው አይመጣም ...
እውነትን ፍለጋ - ትግል ላይ ነው ባባ።


ውጣ ችላው እንጂ - እሷስ ምን ታድርገው፣
ቀን ዘሞባት እንጂ - እሷስ መቼ ፈቅዳው፣
ምን ብላ ትዋሸው - እነደምን ታባብለው፣
ያን ቆሻሻ ታሪክ - ምን ብላ ትንገረው!፣
......................እንዴት ትተርከው!፣
ቢሆንም ታሪክ ነው - ይወቀው ይረዳው፣
ፈርድ የሚሰጥበት - የነገ ሥራው ነው፣
......................ብላ እያየችው፣
"ባክህ ማሙሽዬ - ነገሩ እንዲህ ነው፣
ቆየ 'ኮ ከረመ - ቤታችን ወህኒ ነው፣
አንተን የወለድኩህ - እትብትህም ያለው፣
ባታውቀውም ቅሉ - እስር ቤት እኮ ነው!፣
አባትህም ባባ - እዛችው ቦታ ነው፣
ርቆ አልሄደም - እዛው እቤቱ ነው፣
ከሞቀ ኑሮው - አብርሮ ያመጣው፣
የሃገሩ ነገር - የወገን ፍቅር ነው፣
...............እናም እዚሁ ነው፣
እዚሁ ሀገሩ - እዚሁ እስር ቤት ነው፤
ታገስ ማሙሽዬ - ታሪኩ ብዙ ነው፤
በአምላክ ቸርነት - በነፃ ተፈጥረው፣
እንዳንተው ማሙሽን - ጨቅላቸውን ትተው፣
ታስረው የሚኖሩ - ብዙ አባቶች ናቸው፤
ኦልባና ና አንዱዓለም - ፍትህ የራቃቸው፣
በቀለ ና ውብሸት - እውነት የጠማቸው፣
መቁጠር የሚታክት - ብዙ ዜጎች ናቸው፤
ይገባሃል ማሙሽ - ሁሉም እስር ቤት ነው!፤
አይዞህ ማሙሽዬ - አባትህ ጎበዝ ነው፣
ለኛም ለእነሱም - ለሁላችን ሲል ነው፤
ከኔ በፊት ሀገር - ወገኔ ብሎ ነው፣
እኔንም አንተንም - ታስሮ ሊያስፈታ ነው፤
ሀገርን ከ'ስር ቤት - እስር ቤትን ካገር...
......................ታስሮ ሊለይ ነው።
ደግሞም ማሙሽዬ - ሌላም ሚስጥር አለው፣
ምናልባት አባትህ - ቢመረጥ እኮ ነው!፣
ከሌላው ለይቶ - ምሳሌ ሊያረገው፣
እሱን ሻማ አርጎት - ለሌላ ሊያበራው፣
በሱ ወህኒ መውረድ - ሌላውን ሊያስፈታው፣
ለዛም 'ኮ ይሆናል - ጨለማ የጣለው!፣
እንዴ ማሙሽዬ.......................!
የፈጣሪ ሥራ - ረቂቅ እኮ ነው!፣
እቺን የኛ ዓለም - ከጥፋት ያዳነው፣
የኛን ክፉ ሥራ - በደሙ ያጠበው፣
ያ የዓለም ጌታ - ሁሉን ያደረገው፣
እከብቶች ማደሪያ - በረት ተወልዶ ነው!።
የጥቁርን ውርደት - መንግሎ የጣለው፣
ማንዴላ ሃገሩን - ባ'ለም ከፍ ያረገው፣
ሃያ ሰባት ዓመት - ታሥሮ ተገርፎ ነው!።''

ብላ ስታወራው - ይሰቀጥጣታል፣
ይሄ ጨቅላ ህጻን - እንዴት ይገባዋል!፣
ሃገርን ከእሥር ቤት....................
እሥር ቤትን ካገር - እንዴት የለየዋል?፣
ቢሆንም ግን ቅሉ - ማሙሽ ያስተውላል፣
አባቱን ሊያይ ሲሄድ - ፖሊስ ይቆጣዋል፣
ከእቅፉ እንዳይቆይ - በብረት ተከቧል፣
ባባ ወጥቶ አይመጣ - በግረ ሙቅ ታሥሯል፣
እንዴት አያስጨንቅ..................!
ሁሉም ታሥሮ እያየ - ምኑን ይለየዋል!፣
ያባት ፍቅር ሳያይ - ሃገር እንዴት ያውቃል!?
በምን መመዘኛ..........................
ሃገር ተረካቢ - ተተኪ ይባላል?፣
እሥር ቤት ነው ሃገር - ምኑን ይረከባል!፣
እንኳን ለዚህ ጨቅላ - እኛም ቸግሮናል፣
እንኳን ለመናገር - መስማት ወንጀል ሆኗል፣
በገዛ ጣታችን - መጻፍ ያስጠይቃል፣
ዓይናችንም ላየው - አንቀጽ የጠቀሳል፣
በነፃ ተፈጥረን - ሆኖ አለመታደል፣
ዳግመኛ ነጻነት - ከሰው ይለመናል!፤
እንቆቅልሽ ነገር - እርግጥ ነው ይጨንቃል፣
ለዚህ ህፃን ጨቅላ - ለምን ይተረካል?!
ማሙሽ ግን ብልህ ነው - ተችሮት ማስተዋል፣
ሁሉንም ታዝቧል - ጠልቆ ተረድቶታል፣
መዝለል መቦረቁን - የልጅ ወጉን ትቷል፣
ይወጣል ይገባል - እናቱን ያያታል፣
እንደሰውነቱ - እውነት ይፈልጋል፣
ችላ ባትመልስም - ማሙሽ ይጠይቃል፣

''ማማ ምን ይሻላል?
እኔም ባባን ሳክል - ፖሊስ ይወስደኛል?፣
ጨለማ ክፍል ውስጥ - ይቆልፉብኛል?፣
ሰው እነዳላናግር - ይከለክሉኛል?፣
ቆይ ደሞ ማማዬ'' - ይላል ይቀጥላል፣
''ለወገኑ ሲል ነው - ያሰሩት ብለሻል፣
ይሄ ሁሉ ሥቃይ - ላገር ነው ብለሻል፣
እሱ እንዲህ ሲሆን - ወገኑ ግን የታል!?
ስሚኝ ባክሽ እናት.......................!
እንደዚህ ናት ሃገር - እኔም የማድግባት?፣''
ግን ለምን ወለድሽኝ - ምን ይሰራልኛል፣
ይላል ይገረማል - እናቱን ያያታል፣

መልስ ያጣ ጥያቄ - ምን መልስ ይኖራታል!፣
እናት ታለቅሳለች - እሱም ይጠይቃል፣
ህፃኑ ይጣራል - የአባት የወገን ያገር ያለህ ይላል፣
ላባቱ ያልሆነ - ሀገር ያስፈራዋል፣
ያቅበጠብጠዋል - ይጣራል ይጮሃል!፣
የተኛችሁ ንቁ - የነቃችሁ በረቱ አንድ ሁኑ ይለናል፣
ማሙሽ እውነቱን ነው - በጣም ያስጨንቃል፣
መውለድ እስኪያስፈራ - መጪው ያሳስበል፣
ሀገር ለማቆየት - ተተኪ ለማብቀል፣
ከዚም ጫፍ ከዚያም ጫፍ - አርቆ ማስተዋል፣
ከራስ በዘለለ - ማሰብ ያስፈልጋል፣
ደጋግሞ ደጋግሞ - መጨነቅ ይገባል፣
የህፃኑ ጥሪ - - - -ምላሽ ይፈልጋል።


No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...