ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, September 13, 2013

ትኩስ ዜና ስለ ዘመን ተሻጋሪው አየርመንገዳችን


ኢትዮጵያ ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ከገነባቻቸው ተቋማት ውስጥ በውጤታማነቱ የሚጠቀሰው አንዱ እና ጉልሁ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው።የኢትዮጵያ አየር መንገድ በየዘመኑ ሀገራችን ከሚገጥማት ፖለቲካዊ ፈተናዎችን የሚወጣበት የእራሱ የሆነ ''የጥሩ ነጋዴ ክህሎት'' ማዳበሩን የሚናገሩ አሉ።ለእዚህ አይነቱ ክህሎት ያላበሰው አይነተኛ ምክንያት ደግሞ  የረጅም ጊዜ ልምድ ያዳበሩ ሰራተኞቹ ድርጅቱን በጡረታ አልያም ለሌላ ድርጅት በተሻለ ደሞዝ ትተው ቢሄዱምካሉበት ሀገር ሆነው ማኔጅመንቱን በምክር ከማገልገላቸውም በላይ የእኔነት ስሜት (belongingness) በሌሎች ላይ በማሳደር የሚፈጥሩት በጎ ተፅኖ ተጠቃሽ ነው።


የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰራተኞች ከድርጅቱ በጡረታም ሆነ የተሻለ ሥራ አግኝተው ከወጡም በኃላ ጠንካራ በሆኑት ማኅበራቱ ለምሳሌ በገንዘብ ቁጠባ እና ብድር ማኅበር፣በጡረተኞች ማህበር፣የአብራሪዎች ማኅበር በመሳስሉት መንገድ ድርጅቱ የሚያገኝበት መንገድ አለው።ይህም እንደ አንዳንድ መስርያቤቶች ሰራተኞች ጡረታ ሲወጡ ድርጅቱን በሩቅ ተመልካች እንዳይሆኑ ባለማድረጉ ለአብነት ተጠቃሽ ነው።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በያዝነው ሳምንት መጀመርያ ላይ መሰረቱን አሜሪካ፣ካሊፎርንያ  ያደረገው Airline Passenger Experience Association (APEX) በተሰኘ ድርጅት ተሸላሚ ሆኗል።

ይሄው በመላው አለም በአየር መንገድ ለሚጠቀሙ መንገደኞች ምቾት የሚሰራው ድርጅት  በአለም ዙርያ በአየር መንገድ ለሚጠቀሙ መንገደኞች በቀጥታ በሚጠይቀው መጠይቅ በሚልዮን የሚቆጠሩ  መንገደኞች የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምርጫቸው መሆኑን እንደገለፁለት አሳውቆ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ''የ 2013 በአፍሪካ በደንበኞች የበለጠ ተመራጭነት'' ሽልማት አሸናፊ መሆኑን ገልጧል።ዜናውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ  እና ''All africa.com'' መስከረም 2/2006 ዓም በድህረ ገፃቸው ላይ ዘግበውታል።

በሌላ በኩል  ''ሰላምታ'' የተሰኘው የኢትዮጵያ አየርመንገድ መፅሄት በዓለም ላይ ካሉት የበረራ መፅሄቶች ውስጥ ከአምስቱ ምርጦች ውስጥ መደመሩ እና ለሽልማት መብቃቱ ሌላው ተጨማሪ  የዜናው አካል ነበር።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከብዙ ድርጅቶች ብዙ ሽልማቶችን ተቀብሏል።እንደዚህ በቀጥታ በሚልዮን የሚቆጠሩ ደንበኞች ሲመርጡት መመረጡን ደግሞ ገለልተኛ የሆነ ድርጅት ሲያረጋግጥ ሀገርኛ ደስታ ነው።ለዘመን ተሻጋሪው አየር መንገዳችን መልካም አዲስ ዘመን።

ጌታቸው በቀለ 
ኦስሎ