ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, August 27, 2021

የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ልጅን በመድፍ

በመድፍ የወደመው ቤት 

ከትግራይ መሬት የበቀሉት በንፁሃን ደም የሰከሩት የደብረፅዮን እና ጌታቸው ረዳ ጀሌዎች ከሰሞኑ በአማራ እና የአፋር ክልል በሚኖረው ኢትዮጵያዊ ላይ የፈፀሙት ግፍ ተፅፎ አያበቃም።ለአቅመ ሔዋን ያልደረሱ ሴቶች ተደፍረዋል፣ የገበሬዎች ንብረት ከተጋገረ እንጀራ እና ሊጥ እስከ የቁም ከብት ተዘርፏል።ከእዚህ ሁሉ በላይ አዛውንት እና አሮጊቶች መሬት ለመሬት እየተጎተቱ ተገድለዋል።እንደ መርሳ ባሉ ቦታዎች ደግሞ ሕዝቡን እየሰበሰቡ ያልታወቀ መርፌ ወግተውታል።ይህንን ሁሉ ሲያደርጉ ነገ የአፀፋ ምላሽ የሌለው መስሏቸዋል።

በአፋር የሽብርተኛው ህወሓት የጅምላ ግድያ የሚዘገንን ነበር።በመጠለያ ውስጥ ያሉ 107 ሕፃናት ጨምሮ ከ200 በላይ ሕዝብ በአንድ ላይ ነው የፈጇቸው።አንዲት የአፋር እናት ለኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ጋዜጠኛ ሲናገሩ -

 ''በአፋር ታሪክ በሙሉ እንዲህ ዓይነት ግፍ በማንም መንግስትም ሆነ ጠላት ተፈፅሞብን  አያውቅም።እስካሁን የተዋጉት ወንዶቻችን  ናቸው።አሁን ግን አንዲትም ሴት ከቤት አንቀመጥም  እርጉዝ አትቀርም ስንዋጋ'' በማለት ገልጠዋል።በአፋር የተፈፀመው ግፍ የሞቱትን ለመቅበር መቃብር የሚቆፍሩትን ሁሉ ላይ ነበር።

ቢቢሲ አማርኛ እኤአ ሐምሌ 23/2021 ዓም በአፋር ሽብርተኛው ህወሓት የፈፀመውን ግፍ አስመልክቶ በሰራው ዜና ላይ እንዲህ የሚል ይገኝበታል - 
''ከአፋር የደረሱን በርካታ ምንጮች እንደሚሉት የህወሓት አማጺ ኃይሎች በአፋር ክልል በርካታ ንጹሐንን ገድለዋል። ንብረቶችንም ዘርፈዋል። ቤቶችን በእሳት አቃጥለዋል። ይህም በያሎ እና በአውራ የተከሰተ ነው።ያሎ ከሚባለው የአፋር አካባቢ ሸሽቶ ያመለጠ አንድ ነዋሪ እንደተናገረው ሰዎች የተገደሉት የቀብር ሥነ ሥርዓት እየታደሙ በነበረበት ሰዓት ነውበማኅበራዊ ትስስር መድረክ እየተጋራ የሚገኝ አንድ ተንቀሳቃሽ ምስል ይህንኑ የሚያጠናክር ነው።አንድ የአፋር ነዋሪ አጠገቡ የአማርኛ አስተርጓሚ እየተናገረ የሚከተለውን ሲል በተንቀሳቃሽ ምሥሉ ላይ ይታያል፡- "ለ20 ሟቾች መቃብር በመቆፈር ላይ ነበርን። እየተጠጉን ሲመጡ ይህን ጨርቅ ከፍ አድርጌ አሳየኋቸው፤ ንጹሐን ነዋሪዎች እንደሆንን እንዲረዱ ነበር። ነገር ግን ከመሀላቸው አንዱ ተኩስ ከፈተብን።" ቢቢሲ አማርኛ እኤአ ሐምሌ 23/2021 ዓም

ፋሺሽታዊው የሽብርተኛው ህወሓት ጀሌ በአፋር ሕዝብ ላይ ከፈፀመው አውሬያዊ ተግባር ሌላ አጋምሳ ቆቦ የሚገኝ አንድ ሙሉ መንደር ሆን ተብሎ እንዲወድም መደረጉ ሌላው ዘግናኝ ተግባር ነው።

የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ልጅን በመድፍ 

ጦርነት የራሱ ሕግ አለው።በጦር ሜዳ ከወታደር ጋር ልትዋጋ ትችላለህ።ቤታቸው ያሉ ገበሬዎች ቤት ገብቶ መረሸን ግን ከውስጥ የወጣ የጥላቻ ጥቀርሻ ነው።አማራ በመሆናቸው ብቻ መግደል አለብን የሚል ተልዕኮ ይዘው በንፁሃን ደም ታጥበው ተመልሰው ትግራይ ይገባሉ ወይ? ነው።በእዚህ ወንጀል ውስጥ ያሉ የጊዜ ጉዳይ እንጂ ለፍርድ መቅረብ ወይንም በገቡበት መውጫ አጥቶ መያዝ አይቀርም።

ባሳለፍነው ሳምንት ውስጥ የደብረታቦር ከተማ የደብረ ታቦርን ዓመታዊ በዓል ለማክበር ዝግጅት ላይ ነበረች። በክምር ድንጋት እና ጋይንት ላይ  ሾልኮ የገባው የሽብርተኛው የህወሓት ጀሌ ገበሬው ላይ እየተኮሰ እህሉን ብቻ ሳይሆን ከብቱን በጥይት አረር እየገደለ መሆኑ ተሰምቷል።በእዚህ መሃል የደብረ ታቦርን ከተማ ለመያዝ ጀሌው ጥረቱ አልተሳካም።ለእዚህም ዋናው ምክንያት ደግሞ የደብረ ታቦር ከተማ እና የአካባቢው ወጣት ከጎራደ እስከ የነፍስ ወከፍ ክላሽ ይዞ ወጥቶ ከደብረ ታቦር ከተማ ወጥቶ ሰርጎ የገባውን ከማሳደድ አልፎ አያሌዎችን ማርኮ ደብረታቦር ከተማ አሰልፎ ለሕዝብ አሳየ።ይህን ተከትሎ የደብረ ታቦር እለት ወደ ከተማው የሚገኙ ሁለት አብያተ ክርስትያናት እና ሆስፒታል ላይ ከባድ መሳርያ እና መድፍ ተተኮሰ።

ከተተኮሱት ውስጥ ሦስቱ የታለሙት አንዱ ለደብረ ታቦር መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን፣ሁለተኛው አሁንም በከተማው ለምትገኘው እናቲቱ ማርያም የታለመ እና ሦስተኛው ደግሞ ሆስፒታሉን ለማውደም የተተኮሱ ነበር።ሲተኮሱ ደግሞ ማንምም የአማራ ተወላጅ በመግደላቸው ብቻ እንደ ስኬት የተቆጠረ ነው።ይህ ደግሞ በድንገት የተፈፀመ አይደለም።ሆን ተብሎ ታቅዶ እና ከላይ የሽብርተኛው አመራሮች በተላለፈ ትዕዛዝ ጭምር ለመሆኑ መሪዎቹ ቀደም ብለው ሲናገሩት የነበረው ''ከአማራ ጋር ሂሳብ እናወራርዳለን'' የሚለው ንግግር ማስረጃ ነው። 

ወ/ሮ ታደላ ነጋ የደብረታቦር ነዋሪ ነች። ታደላ ኑሮዋ ከደብረታቦር መድሃኔ ዓለም ስር ነው።ቤቷ ውስጥ የደብረ ታቦር ዕለት ታደላ ቤት የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ልጅ፣ወላጅ እናቷ፣ ሁለት እህቶቿ፣አንድ ወንድሟ እና ግቢው ውስጥ የተከራዩ እንደወንድም የምታያቸው ሁለት ተከራዮች ነበሩ።የህወሓት ከባድ መሳርያ የደብረ ታቦር መድኃኔዓለም ለበዓል የተሰበሰበውን ሕዝብ ለመፍጀት ታልሞ ያረፈው ወ/ሮ ታደላ ነጋ ቤት ላይ ነበር።ወ/ሮ ታደላ የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ልጇን፣እናቷ፣ሁለት እህቶቿ እና አንድ ወንድሟ ወድያው ሕይወታቸው ተቀጠፈ። እንደወንድም የምታያቸው ተከራዮችም እንዲሁ ከቆሰሉ በኃላ ሕይወታቸው አለፈ።

ሁለተኛው ከባድ መሳርያ የደብረታቦር እናቲቱ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለፍልሰታ ጾም እና ለደብረ ታቦር በዓል የተሰበሰበውን ሕዝብ ለመፍጀት ያለመ ነበር።ሆኖም ግን ጥይቱ ያረፈው ከቤተ ክርስቲያኑ ጎን ይኖር የነበረ ነዋሪ ጣርያ ላይ ነበር።ግለሰቡ አጋጣሚ ወደ ቤተ ክርስቲያን ለመሄድ ከቤቱ ወጥቶ የቤቱን ቁልፍ ከውጭ እየቆለፈ እያለ መሳርያው ቤቱ ላይ ሲያርፍ ቆርቆሮው ተሰንጥቆ እግሩ ላይ አረፈ ቆስሎ ወደቀ።ወደ ሆስፒታል ተወሰደ።ሕይወቱ ግን ወደ ቤተ ክርስቲያን ለመሄድ በመውጣቱ ተረፈ እንጂ ከቤት ውስጥ ቢሆን  ሟች ነበር። ሶስተኛው ከባድ መሳርያ የተተኮሰው የደብረታቦር ሆስፒታልን ለማውደም ታቅዶ የተተኮሰ ነበር።ሆኖም ይሄኛውም ሆስፒታሉንም ሆነ የማንንም ቤት ሳይነካ ሜዳ ላይ ወደቀ። 

ለማጠቃለል ይህ የፋሺሽቶቹ የትግራይ ህወሓት አረመኔያዊ ታሪኮቹ ውስጥ የሚከተብ ነው።የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ሕፃን በመድፍ የተገደለበት ታሪክ። ጀሌው የተኮሰው የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ህፃንን ለመግደል ብቻ ሳይሆን እርጉዝም ከተገኘች እንደሚገድል የተኮሱት እና ያስተኮሱት ያውቃሉ።አበባ እንዳልበተኑ ይረዳሉ።ዓላማቸው ለደብረ ታቦር የተሰበሰበው ሕዝብ በጅምላ እንዲያልቅ እና የደብረታቦር ከተማ በአምቡላንስ ስትታመስ ማየት ነበር። ከአንድ ቤተሰብ እስከ ስድስት ሰዎች መሞታቸው አንዱ እና አሳዛኙ ሁኔታ ቢሆንም በጅምላ ሺዎች ንፁሃንን ለመግደል ያቀዱት ዕቅድ ግን አልተሳካም።ለእዚህም የእግዚአብሔር ጥበቃ ከሕዝቡ አልተለይም።ገዳዮች ግን በሕሊናቸው ንፁሃንን ገድለው ጨርሰዋል።የእዚህ ዓይነቱ የአውሬነት ተግባር ነገ ከተጠቃው ሕዝብ ምን ዓይነት ምላሽ እንደሚያሰጥ ሲታሰብ ግን ያስፈራል።የተዘረፈው ተዘርፎ ቁጭ ይላል ወይ? የግፍ አገዳደሉስ ለከት ማጣት በአማራው ላይ ያለው የጥላቻ ጥግ በሽብርተኛው ህወሓት አንፃር እንዲህ የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ልጅን በመድፍ በመግደል ሲገለጥ በዘመናችን ሰማን። 
==============///=============== 
==========================
ማስታወቂያ /Advertisement 
===============================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።