ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, May 7, 2020

የዓባይን ግድብ ጉዳይ ተከትሎ ኢትዮጵያ በመጪው ወራት ሊገጥማት የሚችሉትን ተግዳሮቶች ለመወጣት የውስጥ አንድነቷን እና ፀጥታዋን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መጠበቅ አለባት።


ጉዳያችን ልዩ አጭር ዘገባ
================
ሚያዝያ 29/2012 ዓም 
(ጉዳያችን ድረ ገፅ፣ፌስ ቡክ እና ቴሌግራም ላይ የተለጠፈ)
================
- ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ለግብፅ እና ሱዳን ደብዳቤ ልከዋል፣
- ግብፅ ለፀጥታው ምክር ቤት የላከችው ደብዳቤ ዋና ይዘት፣
- ሱዳን ከአሜሪካ የምትፈልገው ዋና ጉዳይ 
===================
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ለሱዳን እና ለግብፅ ኢትዮጵያ የዓባይ ውሃን ለመሙላት ባወጣችው የጊዜ ሰሌዳ እና በሂደቱ ላይ ሁለቱ አገሮች እንዲስማሙ እና የኢትዮጵያን አዲስ ዕቅድ (ፕሮፖዛል) በደብዳቤ ልከው እንደነበር የግብፁ አልሃራም በድረ ገፁ ማምሻውን ገልጧል።ደብዳቤው የተላከው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ሚያዝያ 10/2020 ዓም ሲሆን በጉዳዩ ላይ ግብፅ ባለመስማማቷ ግንቦት 1/2020 እኤአ ለተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክርቤት ይህንኑ ደብዳቤ ያስገባችው አቤቱታ ይህንኑ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ደብዳቤ የሚቃወም አንቀፅ እንዳለበት ያትታል።

እንደጋዜጣው አባባል የኢትዮጵያን አዲሱን ፕሮፖዛል ሱዳንም እንዳልተቀበለች የሚገልጥ ዓረፍተነገር ግብፅ ለተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክርቤት በላከችው ደብዳቤ ላይ ጠቅሳለች።የሱዳን መቃወም ወይንም ሱዳን ኦፊሻል ምላሽ ለኢትዮጵያ መስጠት አለመስጠቷን ጉዳያችን አላረጋገጠችም።የግብፅ ሚድያዎች በዓባይ ግድብ ዙርያ በርካታ የሐሰት ዜናዎችን በመንዛት ብዙ ጊዜ ይወቀሳሉ።

የግብፅ ለተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክርቤት የላከችው ባለ 17 ገፅ ደብዳቤ በዋናነት ''ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ሕግን አላከበረችም ግዴታዋን ትወጣ'' የሚል እና የውሃ ሙሊቱ ግብፅ ሳታውቀው እንዳይፈፀም የሚጠይቅ ነው።የኢትዮጵያ ውሃ፣መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶ/ር ኢንጅነር ስለሺ ኢትዮጵያ ውሃውን መሙላት በያዝነው ክረምት እንደምትጀምር እና ይህንን  ከማድረግ ምንም የሚያግዳት እንደሌለ መግለጣቸው ይታወሳል።በሌላ በኩል የግብፁ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር  ሳመህ ሹክሪ ከእስቶንያው አቻቸው ጋር በስልክ መወያያታቸውን አልሃራም ዘግቧል።የኢትዮጵያ መንገናኛ ብዙሃንም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገዱ አንዳርጋቸው ከኢስቶንያ አቻቸው ጋር መወያየታቸውን በቅርቡ ዘግበው ነበር። ኢስቶንያ የወቅቱ የፀጥታው ምክር ቤት አባል ነች።

ይህ በእንዲህ እያለ ሱዳን ከሃያ ዓመታት በኃላ ለመጀመርያ ጊዜ ከአሜሪካን ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቷን በማደስ ላይ እንደሆነች እና አምባሳደሯን ዋሽንግተን ላይ መሰየሟ ተሰምቷል።የአሜሪካው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር  ፖምፕዎ ትናንት ተጠይቀው በቅርቡም አሜሪካ አምባሳደሯን ወደ ካርቱም እንደምትልክ ለእዚህም እየሰራች መሆኗን ገልጠዋል።የሱዳን ዋነኛ እና ቀጣዩ ከአሜሪካ የምትፈልገው ሱዳንን ከአሸባሪ መዝገብ ውስጥ እንድትሰርዛት ነው።

ግብፅ በአባይ ጉዳይ ሱዳን ኢትዮጵያን እንድትቃወም  የማትፈነቅለው ድንጋይ የለም።የሱዳን የውስጥ ጉዳይ ከመግባት እና የምትፈልገውን መንግስት ለመመስረት ከመጣር እስከ መለማመጥ የሚደርስ ሥራ ላይ ነች።በቅርቡ ሁለት የወታደራዊ አይሮፕላኖች  ለኮሮና ወረርሽ የሚረዱ መርጃ የህክምና ቁሳቁስ ይዘው ከካይሮ ወደ ካርቱም በረዋል።

የዓባይን ግድብ ጉዳይ ተከትሎ ኢትዮጵያ በመጪው ወራት ሊገጥማት የሚችሉትን ተግዳሮቶች ለመወጣት የውስጥ አንድነቷን እና ፀጥታዋን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መጠበቅ አለባት።ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ ከሳምንት በፊት በምክር ቤት ባደረጉት ማብራርያ ላይ ''ኢትዮጵያ ልትወረር በምትችልበት በእዚህ ጊዜ''   የሚሉ ቃላት ከመጠቀማቸውም በላይ በዛሬው ዕለት በሰጡት መግለጫ ላይም የአገር ሉዓላዊነት ጥቃት ሊደርስ የሚችልበት ሁኔታ እንዳለ ጠቁመዋል።

ይህ በእንዲህ እያለ ነው አንዳንድ ተቃዋሚዎች በድርድር መንግስት ይመስረት የሚል አጀንዳ እያራገቡ ያሉት።ዛሬ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በሰጡት መግለጫ ይህ ፈፅሞ እንደማይሆን እና መንግስት ከሕገ መንግስቱ እና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ ውጪ የሚሄዱትን እንደማይታገስ እና ለእዚህም በቂ ዝግጅት ማድረጉን ገልጠዋል።

በምርጫው መራዘሙ ላይ ከተስማሙት ዋና ዋና የተቃዋሚ ኃይሎች ውስጥ  ኢዜማ፣ እናት ፓርቲ እና አብን ተጠቃሽ ናቸው።ኢትዮጵያውያን ይህ ወቅት በታኝ  ኃይሎችን ተጋፍጠው እና የውስጥ አንድነታቸውን አጠንክረው ኢትዮጵያን ወደተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር የሚነሱበት ወሳኝ ጊዜ መሆኑን ከመቼውም ጊዜ በላይ መረዳት አለባቸው።

ጉዳያችን ዩቱብ ሰብስክራይብ ያድርጉ 



ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments: