ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, May 13, 2020

ኢትዮጵያ ተደፍራለች! አለመቆጣት የመታመም ምልክትም ነው።

ከእዚህ በታች ያለውን የእንግሊዝኛ መልዕክት በተለይ በትዊተር እና ሌሎች የማኅበራዊ ሚድያዎች ያሰራጩ።ተፅኖ የማትፈጥር ቃል በምድር ላይ እንደሌለች ይመኑ።
Here are the two messages of Gudayachn to Egypt and the USA stands regarding the Grand Ethiopian Renaissance Dam. 
>> If Egypt tries to provoke Ethiopia in any military action, it will lose the Nile as a whole
forever.
>> If the USA supports Egyptians' injustice and unfair stand in case of the Grand Ethiopian Renaissance Dam, America will lose her Africa base forever.

ሰው የሚያስደስተው ነገር ሲኖር ይደሰታል።የሚያስቆጣው ጉዳይ ላይ ይቆጣል።ከእዚህ በተቃራኒ የሚሆን ሰው የጤንነቱ ትክክለኛነት ያጠራጥራል።በሚያስቆጣው ጉዳይ አለመቆጣት ጉዳዩን በደንብ አለመረዳት  የህመም ምልክት ነው።

ግብፅ በዓባይ ግድብ ዙርያ እያለች ያለው በሚገባ የገባን አይመስልም።ግብፅ እያለች ያለችው በቤትህ ውስጥ ለምትቀዳው አንድ ኩባያ ውሃ እኔ መፍቀድ አለብኝ ነው።ኢትዮጵያ ግድቡን የምትጠቀመው የኤሌክትሪክ ማመንጫ ተርባይነሩን አሽከርክሮ እንዲያልፍ ብቻ ነው።ይህንንም ግብፆች እንዲረዱት ለዓመታት የህዝብ ዲፕሎማሲ ልዑክ ከመላክ ጀምሮ በውይይት ሱዳንን ጨምሮ በቅርቡም አሜሪካ ባለችበት ተወያየች።አሁንም ግን ግብፅ እየፎከረች ነው።

ዛሬ ብቻ የግብፁ አልሃራም ጋዜጣ በግድቡ ዙርያ ሁለት የፉከራ ፅሁፍ አውጥቷል።አንዱ ርዕሱ ''የግብፅን የሕይወት መስመር መከላከል'' ይላል ሁለተኛው ፅሁፍ ደግሞ ''የሕዳሴው ግድብ የጫወታው ፍፃሜ'' ይላል።ይህ ሁሉ ፉከራ ኢትዮጵያ ውስጥ ስላለ ውሃ ነው።ይህ ድንበር ጥሶ ወታደር የማዝመት ያህል ነው።አንዳንዴ ኢትዮጵያውያን በጣም በበዛ ደረጃ ሳይታወቀን ''ፍትሃዊ'' የሆንን እየመሰለን የራሳችን ውሃ ላይ ግብፅ፣ሱዳን እና አሜሪካ እያወሩ መሆኑን ሁሉ  ሳያስቆጣን መቅረቱ በራሱ አደጋ አለው።እያወራሁ ያለሁት ስለ ተራው የእኔ ብጤ ሰው ነው።ተራው ሕዝብ በደንብ ሊሰማው ይገባል።ሊቆጣ ይገባል።ሙከራው ካላናደደን፣ነገ በተግባር ሲመጣም አንቆጣም።መቆጣት ጤነኛነት ነው።

ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሚድያዎች፣የኪነጥበብ ባለሙያዎች እና ባለስልጣናት ሁሉ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚገባው ደረጃ እንዲቆጣ ማድረግ አለባቸው።አለመቆጣት በራሱ ህመም ነው።በተለይ ሚድያዎች እና የኪነጥበብ ሰዎች ለይምሰል ከሚመስል አባባል  ወጥተው ተጨባጭ ማስረጃ የሚያሳይ ደረጃውን የጠበቀ ፕሮግራም በማዘጋጀት ህዝቡ እንዲቆጣ ማድረግ መቻል አለባቸው።ይህ የቁጣ ስነ ልቦና መድረስ ያለበት ደረጃ መድረስ አለበት። ከሚፈለገው የቁጣ ስሜት በትንሹ ካነሰ በራሱ አደጋ ነው።አሁንም መቆጣት የጤነኛነት ምልክትም መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።አለመቆጣት እና የድፍረቱን ልክ አለመረዳቱ በራሱ ግዙፍ አደጋ አለው።ግብፆች የህዝቡን የቁጣ መጠን አይለኩም ማለት አይቻልም።

ስለሆነም ኢትዮጵያውያን በሚገባ እንዲቆጡ ማድረግ ያስፈልጋል።የኢትዮጵያን የተፈጥሮ ሀብት ለመቀራመት የሚፈልጉ ኃይሎች የህዝቡን የመቆጣት ልክ ይለኩታል።ስለሆነም በቤትህ በብርጭቆ የተቀዳ ውሃ ከሌላ ቦታ የመጣ ሰው ውሃውን የምትጠጣው እኔ ስፈቅድልህ ነው ስትባል እንዴት መቆጣት አለመቻልህ የጤና አለመሆኑን እራስን መጠየቅ ይገባል።ይህንን ጥያቄ ጋዜጠኛውም የኪነጥበብ ሰውም መረዳት አለበት።ስሜት የሚኮረኩሩ እና የባለቤትነት ስሜቱን የሚያስረግጡ ዝግጅቶች ከምድያዎች ያስፈልጋል።መንግስት በዲፕሎማሲው የግለት ልክ ከብዙ መረጃዎች አንፃር ሊሄድበት ይችላል።ግለቱ ከመንግስት መምጣት ያለበት የግብፅ የቀይ መስመር ደረጃ ይኖራል።ለግብፅ ሚድያፉከራ ሁሉ የኢትዮጵያ መንግስት መልስ መስጠት የለበትም።ሕዝብ ግን መቆጣቱ ለግብፃውያን በደንብ መታየት አለበት። ለግብፃውያን ሲባል ብቻ አይደለም፣የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህ ጉዳይ ካላመመው እና በሚገባው መልክ ካላስቆጣው በራሱ ብዙ ነገር ማለት ነው።መታመም አንዱ ሆኖ ማለት ነው።

ባጠቃላይ የውሃው ሙሌት እስኪረጋገጥ ሕዝብ በግብፅ ጉዳይ መቆጣቱን በሚገባ ማሳየት አለበት።ቁጣው ከሚገለጥበት መንገድ አንዱ ከማኅበራዊ ሚድያም ኢትዮጵያውያን ጉዳዩ በደንብ እንዲረዱት ቅስቀሳ ማድረግ ነው። እዚህ ላይ ጉዳዩን የማያውቅ ማን አለ? የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል።እኔ የምለው ግን በሚገባ ደረጃ ሕዝብ ቁጣው መታየት አለበት።መናደድ አለበት ነው።ይህ በራሱ ከግድቡ ሥራ ጋር አብሮ የሚሄድ የስነ ልቦና ልእልና መገለጫ መሆኑ ሊገባን ያስፈልጋል።በተለይ፣ በተለይ በየትኛውም ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን  በትውተር እና ሌሎች የማኅበራዊ ሚድያዎች የኢትዮጵያ በውሃዋ የመጠቀም ፍትሃዊ መብት ላይ ያተኮሩ እጅግ ኃይለኛ ቃላትን የያዙ መልዕክት ያላቸው  ነገር ግን ከስድብ እና ከወረዱ ቃላት የፀዱ ዓረፍተ ነገሮች ማሰራጨት ያስፈልጋል።

February 28, 2020 Al Jazeera report on Ethiopian Grand Renaissance Dam 


ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments: