ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, March 19, 2022

የአቡነ ማትያስ ንግግር ግልጽ የሆነ ፖለቲካዊ ተልዕኮ እንጂ ሃይማኖታዊ አይደለም። ''እውነት አርነት ያወጣችኋል'' የሚለው ቃል ተዘቅዝቆ ተጻፈ።ህወሃትም ለማለት ያልደፈረውን ማለታቸው ደግሞ አስተዛዛቢ ነው።



👉አቡነ ማትያስ ''ትግሬዎችን ከምድር ገጽ ለማጥፋት ተብሎ የተጀመረ ጦርነት'' ያሉት የትኛው ኢትዮጵያዊ የትግራይ ተወላጅን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ሲዘምት ተመለከቱ? 
👉120 ሺህ ሰራዊትስ ትግራይ ገብቶ 120 ሺህ ሴቶች ለመድፈሩ ማስረጃቸው ምንድነው? 
👉ህወሃትም 120 ሺህ ሴቶች በትግራይ ተደፈሩ በማለት ወደ ትግራይ ለህግ ማስከበር ከዘመተው የመከላከያ ሰራዊት ቁጥር በላይ ሴቶች ተደፈሩ የሚል ዘገባ ሲያወጣ አልተሰማም።

===============
ጉዳያችን/Gudayachn
===============
ከአምስት ዓመታት በፊት አቡነ ማትያስን የሸገር ኤፍኤም ራድዮ ቀርበው ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ የተለያዩ ጥያቄዎች አቅርባላቸው ነበር። 
''የሙስናው ጉዳይ በቤተክህነት በሰፊው ይነሳል።እርስዎ ይህንን ለመቅረፍ ምን እርምጃ መወሰድ አለበት ይላሉ?''
አቡነ ማትያስ በወቅቱ የሰጡት መልስ አስደንጋጭ ነበር። ''ሙስናው ከባድ ነው።እንዲህ በቀላል የሚፈታ አይደለም።እኔ ይቻላል ብዬ አላስብም'' ነበር መልሳቸው። 
''እና አይቻልም እያሉኝ ነው አባታችን?'' መዓዛ ደግማ ጠየቀች
ጋዜጠኛ መዓዛ ቀጠለች  ''የግል ጉዳዮች ላይ ልጠይቅዎት። አባታችን ያነባሉ? ምን ጊዜ ያነባሉ?'' 
አቡነ ማትያስ ቀጠሉ '' አዬ ማንበብ፣ድሮ ነበር እንጂ አሁን ምን ማንበብ አለ።አንዴ ያንዱን ጉዳይ ሌላ ጊዜ የሌላውን ጉዳይ እና ስሞታ ስንሰማ ነው የምንውለው'' ነበር የአቡነ ማትያስ ምላሽ። 

ይህ በመረጃም ሆነ በማስረጃ ያልተደገፈ ሂደት ትናንት በትግራይ ሚድያ ቀርበው ''ትግሬዎችን ከምድር ገጽ ለማጥፋት ተብሎ የተጀመረ ጦርነት'' እና ''120ሺህ ሴቶች ተደፈሩ'' ሌላም ለመናገር የሚከብዱ ዓረፍተነገሮች ከአቡነ ማትያስ ሰምተናል።ቃላቶቻቸው ለትግራይ ሕዝብ በራሱ አደገኛ ንግግሮች ናቸው።አቡነ ማትያስ በትግራይ ሚድያ ላይ ከላይ የጠቀሱትን እና ሌሎች ህዝብ የሚያጋጩ ንግግሮችን መነሻ ያደረጉት በቅርቡ በቤኒሻንጉል ክልል በአንድ ግለሰብ ላይ የተፈጸመ ግድያን በመጥቀስ ነው።ይህ ግድያ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ያወገዘው ብቻ ሳይሆን ጉዳዩን መንግስትም አውግዞ መግለጫ ከመስጠት አልፎ ይፈጸሙትን ለፍርድ እንደሚያቀርብ ገልጧል። 

የቢኒሻንጉል ግድያ በህወሃት መንደር የሰርግና ምላሽ ያህል ነበር የተወሰደው።ከትግራይ ክልል ውጪ የሚኖረውን የትግራይን ህዝብ የእገሌ ህዝብ ሊበላህ ነው፣ሊፈጅህ ነው እያሉ የሰሩት ፕሮፓጋንዳ ሁሉ አልሰራ ብሎ።ህዝቡ ይልቁን እያስፈጀው ያለው እራሱ ህወሃት መሆኑን ሲያውቅ ህወሃት የሚቆጣጠረውን ቦታ እየተወ ወደ ሰሜን ወሎ መሰደድ መጀመሩ የሰሞኑ ዜና ነበር።ህወሃቶች ይህንን ስደት ለመዋሸት ሞክረው ነበር።ለቪኦኤ አማርኛው የተናገሩት የቀድሞ የመቀሌ ዩንቨርስቲ ፕሬዝዳንት እና አሁን ህወሃትን ወክለው የሚናገሩት ሰው የትግራይ ህዝብ ህወሃትን እየተወ መምጣቱን ሊክዱ ሞክረዋል። ህዝቡ ግን በሺዎች እየሆነ በህወሃት ቁጥጥር ስር ያለውን ቦት እየተወ እየተሰደደ ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ነው የቤኒሻንጉል ግድያ ቪድዮ በተለቀቀ ምሽት የትግራይ ሚድያ ስታሊን ''ቪድዮውን ለእያንዳንዱ የህወሃት ታጣቂ በቶሎ እንዲሰራጭ ይደረግ ይህ በቶሎ እንዲሰራ ይደረግ '' የሚል ንግግር ከህወሃት እንደመመርያ የወረደ ህዝብ ከህዝብ የሚያጋጭ እና የትግራይን ህዝብ የሚያስደነብር ርዕስ ማግኘቱን የገለጠው። ይህ በቀጣይ ቀናት ህወሃት ይህንኑ የቤኒሻንጉል የአንድ ሰው ግድያ አስመልክቶ የትግራይ ህዝብ ላይ ሁሉ የታወጀ ጦርነት አስመስሎ መግለጫ አወጣ።ይህ ማለት በህወሃት መዋቅር ስር ያሉ ሁሉ የፕሮፓጋንዳ ማሽኖች የትግራይን ህዝብ ለማስደንበር እንዲጠቀሙበት ትዕዛዝ ወረደላቸው። ከእዚህ ሁሉ በኋላ አቡነ ማትያስም በትግራይ ሚድያ ቀርበው  ''ትግሬዎችን ከምድር ገጽ ለማጥፋት ተብሎ የተጀመረ ጦርነት'' እና ''120ሺህ ሴቶች ተደፈሩ'' ብለው ተናገሩ።በነገራችን ላይ ህወሃትም 120 ሺህ ሴቶች በትግራይ ተደፈሩ በማለት ወደ ትግራይ ለህግ ማስከበር ከዘመተው የመከላከያ ሰራዊት ቁጥር በላይ ሴቶች ተደፈሩ የሚል ዘገባ ሲያወጣ አልተሰማም።እንደ አቡነ ማትያስ አባባል 120 ሺህ የትግራይ ሴቶች ተደፈሩ ያሉት ሆስፒታል የሄዱትን ብቻ እንደሆነ አቅርበዋል።

አቡነ ማትያስ በጭና ተክለሃይማኖት በህወሃት ሰራዊት ካህናት በቤተክርስቲያን መታረዳቸውን፣የካህናት ሚስቶች መደፈራቸውን፣እናቶች በልጆቻቸው ፊት መደፈራቸውን፣በቤተመቅደስ ውስጥ የህወሃት ጀሌ ከብት ማረዱን፣ታቦታት መዘረፋቸውን፣ንዋየቅድሳት እና ቅርሶች ተሰርቀው በዓለም አደባባይ እየተቸበቸበ መሆኑን ሲቃወሙ አልታዩም።ከእዚህ በተጨማሪ ከላሊበላ እስከ ሰሜን ሸዋ ካህናት ከህዝቡ ጋር ከመኖርያቸው ሲፈናቀሉ፣በአፋር በአንድ ቀን ከአንድ መቶ 12 በላይ ህጻናት በህወሃት ሲጨፈጨፉ ምንም ዓይነት መግለጫ አልሰጡም።

የአቡነ ማትያስ ንግግር ፖለቲካዊ እንጂ ሃይማኖታዊ አይደለም።በቤኒሻንጉል የደረሰው ማንንም ኢትዮጵያዊ አሳዝኗል።ድርጊቱ ኢትዮጵያውያንን ለማጋጨት የተፈጸመ ድርጊት እንደሆነ ግልጥ ነው። ድርጊቱን ማውገዝ አንድ ነገር ነው።''ትግሬዎችን ከምድረገጽ ለማጥፋት'' የተደረገ ነው ብሎ በመሃል ሃገር ለሚኖሩ የትግራይ ተወላጆች ላይ ህወሃት ለብዙ ጊዜ ሞክሮ ያልተሳካለትን አጀንዳ ለመፍጠር መሞከር ሌላ ጉዳይ ነው።ይህ አካሄድ ምን ያህል ሃላፊነት የማይሰማ አካሄድ እንደሆነ እራሱ የትግራይ ህዝብ ይታዘባል።በእዚህ ጊዜ አቡነ ማትያስ እንዴት የሁሉም አባት ሆነው ቢያገለግሉ ለሁሉም እኩል አባትነታቸውን ቢያሳዩ ምን ያህል የትግራይ ህዝብ ይደሰት እንደነበረ ብዙ መመራመር አይፈልግም።አሁን ግን በፖለቲካዊ ተልዕኮ ባዘሉ ንግግሮች ብቻ ሳይሆን ማስረጃ በሌለባቸው እንደ 120 ሺህ ሴቶች ተደፈሩ የውሸት ዜና ሁላችንም ከማዘን በላይ አፍረናል። ''እውነት አርነት ያወጣችኋል'' የሚለው ቃል ተዘቅዝቆ ተጻፈ።
==================///============


 

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...