ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, November 29, 2021

ሽብርተኛው ህወሓት ኤርትራን ለመውረር ቀጣዩ ዕቅድ ሊሆን የሚችልባቸው አራት ምክንያቶች።



  • አሜሪካ አዲስ አበባን ብታጣ አስመራን ለማግኘት እና አሻንጉሊት መንግስት ለመመስረት ጥረት እንደምታደርግ ማስላት ተገቢ ነው። 
==============
ጉዳያችን / Gudayachn
==============

የትግራይን ሕዝብ እንደ ማገዶ እንጨት ከአርባ ዓመት በላይ በጫረው ጦርነት ማግዶታል።በ2010 ዓም በኢትዮጵያ የተጀመረውን የለውጥ ሂደት አልቀበልም ብሎ በጥቅምት 24/2013 ዓም በሰሜን ዕዝ ላይ በፈፀመው ግድያ ሳብያ ላለፈው አንድ ዓመት በትንሹ ከ45 ሺህ በላይ የትግራይ ወጣት እና ጎልማሳ በአማራ እና አፋር ክልል በጫረው ጦርነት ማግዶታል።በእዚህ የመማገድ ሂደት ላይ ከውጭ ሆነው በለው እያሉ የራሳቸውን ኑሮ የሚኖሩ በሀገር ቤትም በገንዘብ እና በቁሳቁስ እልቂቱን የሚያስፈፅሙ ሁሉ እጅ አለበት።እነኝህ ሁሉ ህወሓት በኢትዮጵያውያን ደም ሲነከር አብረው አናካሪ እና የወንጀሉ ተባባሪዎች ናቸው።

አሁን ህወሓት ከአፋር ሙሉ በሙሉ ተጠራራርጎ ሲወጣ በአማራ ክልል ደግሞ ባለፉት ሦስት ቀናት ብቻ ከ15 ሺህ በላይ ሰራዊቱ ተመቷል።በመሆኑም የሽንፈት ፅዋውን ተጎንጭቶ ከአማራ ክልል ሙሉ በሙሉ እንደሚወጣ ምንም ጥርጥር የለውም። ወደ ትግራይ ሲመለስ ግን ከ100 ሺህ በላይ እናት እና አባቶች ለሞቱባቸው ልጆቻቸው ገና ለቅሶ መቀመጥ ይጠብቃቸዋል።ለእዛውም በትክክሉ የመርዶ ስነ ስርዓቱ ከተደረገ ነው።

አሁን የሽብርተኛው ህወሓት ቀጣይ የጦርነት ዕቅድ ወደ አስመራ አይደለም ብሎ ለማሰብ አይቻልም።ይህንን አባባል ብዙዎች ሊሆን አይችልም ብለው የሚሉት ኤርትራ የብሔራዊ ውትድርና አገልግሎት ያልቆመባት ሀገር ከመሆኗ አንፃር እና ሰራውቷም ከህወሓት ሰራዊት ጋር ያለው ንፅፅር ስለማይገናኝ ነው ብለው ይናገራሉ።።

ሽብርተኛው ህወሓት ኤርትራን ለመውረር ቀጣዩ ዕቅድ ሊሆን የሚችልባቸው አራት ምክንያቶች።

1) ህወሓት ቀጣይ ጦርነት ከሌለ መኖር አይችልም።

ጦርነት ለህወሓት የህልውናው ጉዳይ ነው። የትግራይ ሕዝብ ሰላም ካገኘ የሞቱት ልጆቹን ብቻ ሳይሆን  መብቱንም ይጠይቃል።ይህ ብቻ አይደለም አሁን ባለው ሁኔታ ህወሓት በኢኮኖሚም የትግራይን ሕዝብ ለማስተዳደር ቁመና የለውም።መሰረተ ልማቶቹን በጦርነቱ ከማውደሙም በላይ የሰው ኃይሉን በውግያው ሙትና ቁስለኛ አድርጎታል።
ስለሆነም ከአማራ እና አፋር ተባሮ እንደወጣ ሌላ ጦርነት ከአስመራ ጋር ፈጥሮ በውግያ የትግራይን ሕዝብ መወጠር ለህልውናው ወሳኝ ነው።ሌላው ቀርቶ ወደ አፋር እና አማራ ዘመታችሁ ግን ሕዝብ ከማስጨረስ በላይ ምን አገኛችሁ? ብሎ ስለሚጠይቃቸው ሌላ ጦርነት በመጫር ኤርትራ ወረረችን በማለት ወደ ጦርነቱ መግባቱ አይቀርም።

2) ለአሜሪካ ተላላኪ በመሆኑ 

ሁለተኛው ምክንያት አሜሪካም ሆነች ምዕራባውያን በምስራቅ አፍሪካ ያላቸው አንዱ የትኩረት አቅጣጫ የቀይ ባህር እና ኤርትራ መሆናቸው ነው።የግብፅ ዋና ፍላጎትም  በቀይባሕር በኩል የባህር መውጫ የማግኘት መንገዷን ሁሉ መዝጋት ነው።ይህ ደግሞ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ያደረጉት እርቅ እና ኢትዮጵያ የራሷን የባህር ኃይል እያደራጀች መሆኗ ሁሉ አልተፈለገም።ለግብፅ ኢትዮጵያ አደገኛ የምትሆንባት በኤርትራም ሆነ በቀይባሕር በኩል ከቀረበች መሆኑን ትረዳለች።ይህም ለሚፈጠሩ ግጭቶች ሁሉ ኢትዮጵያ በአጭር ሚሳኤል ወይንም በአየር ኃይል የማጥቃት ዕድሏ ይጨምራል።ስለሆነም ኢትዮጵያ ከኤርትራም ሆነ ከቀይ ባህር መራቅ አለባት።

ግብፅ ብቻ ሳትሆንም እስራኤልም ሆነች ሳውዳረብያ ኤርትራ ኢትዮጵያን ወደ ቀይ ባህር እየሳበች ማምጣቷ የኤርትራ ቀይባሕርን ከመቶ ሚልዮን የኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር አብራ በማስከበር የምራባውያንንም ሆነ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮችን የማያስቀርብ ሁኔታ እንደሚፈጠር ግልጥ ነው። 

ስለሆነም አሜሪካም ሆነች የመካከለኛው ምሥራቅ ሀገሮች የኤርትራን መንግስት በቀጥታ መውረር ባይችሉ አሁን ያላቸው ብቸኛ አምራጭ ህወሓትን እንደፈረስ በመጋለብ የአስመራ መንግስትን መቀየር እና ለአሜሪካ ታዛዥ የሆነ መንግስት መትከል ነው።አሜሪካ አዲስ አበባን ብታጣ አስመራን ለማግኘት እና አሻንጉሊት መንግስት ለመመስረት ጥረት እንደምታደርግ ማስላት ተገቢ ነው። በእዚህም በምስራቅ አፍሪካ የሚበጠብጥ አንድ መንግስት አስመራ ላይ በማስቀመጥ ለህወሓት ጉልበት በመስጠት ኢትዮጵያም ላይ ሆነ ቀይ ባህር ላይ ያላትን አቅም ለማሳየት አንዱ እና ቀሪው ሂሳቧ የማይሆንበት ምክንያት የለም።

3) ህወሓት የደረሰበትን ኪሳራ አስመራን በመውረር ድጎማ ከአሜሪካ ከመቀበል እና የትግራይ ሕዝብ ተበቀልኩልህ ከማለት ሌላ አማራጭ ስለሌለው።

ህወሓት በጋራ ትብብር የጋራ እድገት ይመጣል የሚል ስሌት ከውልደቱ ድረስ አልተማረም።ህወሓት የሚያውቀው ሲመቸው ማጥፋት፣ሳይመቸው የሚታረቅ መስሎ አጎንብሶ መቆየት እና አድፍጦ ማጥፋት ነው።በእዚህ መሰረት አስመራን ማጥፋት የህወሓት እቅድ ነው። ልክ በኮምቦልቻ እና ደሴ እንዳደረገው ኤርትራን ማውደም እና አሻንጉሊት መንግስት በአሜሪካ እርዳታ መመስረት  የአሁኑ እቅዱ አይደለም ማለት አይቻልም።በእዚህም አሜሪካ ለሩስያ ዩክሬንን፣ለቻይና ታይዋንን እንደ የጉሮሮ አጥንት ተሰንቅረው ለአሜሪካ ታዛዥ መንግሥታት እየተውተረተሩም እንዲቆሙ እንደምትደግፈው ሁሉ ለኢትዮጵያ ለምስራቅ አፍሪካ እና ለመላው አፍሪካ  አንድ ታዛዥ መንግስት አስመራ እና መቀሌ ላይ መመስረት ዕቅዷ ነው።

4) ህወሓት በጅቡቲም ሆነ በሱዳን መውጫውን ለማግኘት ቢሞክርም ስላልተሳካለት።

ሽብርተኛው ህወሓት በሱዳን በኩል ያለው መውጫ የማይቻል መሆኑን ካወቀ በኃላ ያለ የሌለ ኃይሉን አሰባስቦ የጅቡቲ አዲስ አበባን መንገድ ቆርጦ ለመደራደር እና ጊዜ ለመግዛት ይህ ባይሆን ወደ አዲስ አበባ ለመግባት በምዕራባውያን የሳተላይት መረጃ ድጋፍ እና የፕሮፓጋንዳ ሽፋን ሁሉ ቢደገፍም አሁን ባለው ሁኔታ ይህ እንደማይቻል ግልጥ ሆኖለታል። ስለሆነም ድሮም በተሳሳተ ስሌት እና የኢትዮጵያ ሕዝብ አይነሳም በሚል ተስፋ ወደ ወሎ አስገብቶ ያስፈጀውን ያህል ሕዝብ ወደ አስመራ አዝምቶ ቢሆን ኖሮ አስመራ ሶስቴ ሰርጾ የመጣበት ነበር የምትል ደካማ ምክር ከምዕራባውያንም በኩል ተሰንዝሮ እንደነበር ተሰምቷል።ስለሆነም ለመውጫ ቀላል መንገድ የሚያገኘው አስመራ ላይ ለህወሓት እና አሜሪካ ታዛዥ የሆነ መንግስት ሲመሰረት በመሆኑ ህወሓት ወደ አስመራ አትተኩስም ብሎ  ማሰብ አይቻልም።

ባጠቃላይ የህወሓት ቀጣይ ዕቅድ የሚሆነው ወደ አስመራ የኤርትራ ተቃዋሚዎች ናቸው እኔ የለሁበትም በሚል ጦርነቱን ጭራ አስመራ ላይ መሰል መንግስት ማስቀመጥ ብቸኛ ቀሪ መንገዷ ነው።ለእዚህ ደግሞ የአሜሪካ ከፍተኛ እገዛ አይኖርም ማለት አይቻልም።ይህም በመካከለኛው ምስራቅ ያለው የሀገሮቹ ክፍፍል (በየመን የታየው ዓይነት) መ  ኖሩ የአፍሪካ ቀንድንም ላይ ጥላ አይኖረውም ማለት አይቻልም።በተለይ የኤርትራ ተቃዋሚዎች ናቸው ብላ ህወሓት የምትልካቸው ከአቶ ኢሳያስ ጋር ሲዋጉ የአሜሪካ ሚና የሚሆነው በኤርትራ የውስጥ ጉዳይ ማንም አይግባ በማለት ኢትዮጵያ እንዳታግዝ ''የሽፋን ተኩስ ''ልትሰጥ ትችላለች።ይህ ሁሉ ከመሆኑ እና ከመታሰቡ በፊት  እራሱ ህወሓት ከስሩ ተነቅሎ መጥፋቱ ወሳኝ ነው።

===================////=============== 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።