ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, October 4, 2021

ከዛሬው የመንግስት ምስረታ ኢትዮጵያ መጪ ተስፋዋ ከፍ ያለ መሆኑን የምንለካባቸው አምስቱ መመዘኛዎች

=============
ጉዳያችን/Gudayachn
==============
  • ከእዚህ አጭር ፅሁፍ ስር ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በመስቀል አደባባይ ዛሬ ያደረጉት ሙሉ ንግግር ያገኛሉ።

ኢትዮጵያ ዛሬ የአዲስ መንግስት ምስረታ አካሂዳለች።የኢትዮጵያ ተወካዮች ምክር ቤት እና ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥምር ስብሰባ ተከፍቷል።ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ተመርጠዋል።የፌዴሬሽንም ሆነ የተወካዮች ምክር ቤቶች አፈጉባኤዎቻቸው መርጠዋል።በእዚህ መሰረት የተወካዮች ምክር ቤት አቶ ታደሰ ጫፎ ሲመረጡ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ደግሞ በቅርቡ የአማራ ክልል ፕሬዝዳንትነት የለቀቁት አቶ አገኘሁ ተሻገር ተመረዋል።አቶ አገኘሁ ተሻገርም በማስከተል የሕገ መንግስት ትሩጉም  ቋሚ አባላት ለምክር ቤት አስቀርበው አፀድቀዋል።

በመቀጠል የተወካዮች ምክር ቤት እና ፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥምር ስብሰባ በክብርት ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ተከፍቷል።ከቀትር በኃላ በመስቀል አደባባይ በብዙ ሺህ የሚቆጠር ሕዝብ፣የኬንያ፣ዩጋንዳ፣ሱማልያ፣ጅቡቲ፣ደቡብ ሱዳን፣ሴኔጋል፣ናይጀርያ መሪዎች በተገኙበት የጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ በዓለ ሲመት እና የአዲስ መንግስት ምስረታ ይፋ ሆኗል።በዝግጅቱ ላይ አዲስ የተመረጠው የተወካዮች ምክር ቤት አባላትን ጨምሮ ከፍተኛ የምንግስት ባለስልጣናት እና ወታደራዊ ባለስልጣናት የታደሙበት ሲሆን በቀጥታ በሁሉም የኢትዮጵያ ቴሌቪዥኖች ተላልፏል።በዛሬው ዕለት ምሽት ለአፍሪካውያን ፕሬዝዳንቶች የራት ግብዣ በብሔራዊ ቤተ መንግስት እንደሚደረግ ለማወቅ ተችሏል።

ከዛሬው የመንግስት ምስረታ ኢትዮጵያ መጪ ተስፋዋ ከፍ ያለ መሆኑን  የምንለካባቸው አምስቱ መመዘኛዎች

 የአሁኑ የመንግስት አመሰራረት ከቀደሙት የራሱ የሆነ ልዩነት አለው።የመጀመርያው እና ዋናው የምርጫ ቦርድ የተሻለ ነፃነት የነበረው እና የጎላ የተባለ ችግር ያልታየበት መሆኑ ሲሆን ሁለተኛው ከ40 ሚልዮን የሚሆነው መራጭ በነፃነት የመረጠበት ምርጫ መሆኑን ነው።ከእዚህ በተለየ በጣም ጥቂት በሆኑ ቦታዎች የነበረው የምርጫ ጣብያዎች ችግሮች ለማረም የምርጫ ቦርድ ምርጫዎቹ አወዛጋቢ በሆኑ ቦታዎች የነበረውን ምርጫ ሰርዞ እንደገና እስከማድረግ ደርሶ ነበር። 

የአዲሱ መንግስት ለኢትዮጵያ የሚያመጣው ተስፋ ለመለካት አምስት መመዘኛዎች አስፈላጊ ናቸው።እነርሱም 
  
  • ልማትን የማምጣት አቅም፣
  • ዲሞክራሲ የማስፈን እና ባሕል እንዲሆን መስራት፣
  • ሃገራዊ አንድነት ማጠናከር፣ 
  • ህገመንግስታዊ ማሻሻያ ይፋ ማድረግ እና 
  • አካባቢያዊ እና ዓለም አቀፍ ተፅኖ ፈጣሪነት ማሳደግ የሚሉት ናቸው።
ከእነኝህ ቁልፍ ጉዳዮች አንፃር አዲሱ መንግስት ከተወካዮች ምክር ቤት ጀምሮ እስከ የካቢኔ አባላት እና ታች ያለውን ሰራተኛ እና የህዝብ አገልጋይ ድረስ በተሻለ አቅም እንደሚያደራጅ እና በእዚህም መሰረት ልማትን፣ዲሞክራሲ፣ሃገራዊ አንድነት፣ህገመንስታዊ ማሻሻያ እና አካባቢያዊና ዓለም አቀፍ ተሰሚነት እና ተፅኖ ፈጣሪነትን እንደሚያሳድግ ይጠበቃል። በልማት የህዝብ ኑሮ ይሻሻላል፣በዲሞክራሲ ባሕል መሆን ሰላም ይረጋገጣል፣በሀገራዊ አንድነት መጠናከር ትልቅ አቅም ይፈጠራል፣በሕገ መንግስት ማሻሻያ አደገኛ የሕገ መንግስቱ አንቀፆች ይወገዳሉ፣የአካባቢ እና ዓለም አቀፋዊ ተፅኖ ፈጣሪነትን በማሳደግ የገበያ ተደራሽነትን ማስፋት ይቻላል።

ባጠቃላይ ኢትዮጵያ ወደ አዲስ ምዕራፍ የምትሻገርበት ወሳኝ ጊዜ ላይ ደርሳለች።ሁሉንም በበቂ ደረጃ አከናውና ለተሻለ ደረጃ እንደምትደርስ ምንም ጥርጥር የለውም። ለእዚህም ርዕይ ያነገቡት ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይም ሆኑ ሌሎች አመራሮች በቅንነት እና በትጋት ሕዝብ እንደሚመሩ ትልቅ ተስፋ ተጥሎባቸዋል። ለኢትዮጵያ መልካሙን ሁሉ እንመኛለን።

ከእዚህ በታች የዓለም የሰላም ሎሬት እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዶር ዓቢይ አህመድ በበዓለ ሲመታቸው መርሃግብር ላይ በመስቀል አደባባይ ያደረጉት ንግግር ይመልከቱ።


No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።