ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, November 5, 2013

''የአፍሪካ ሚድያ ፎረም'' በሚል በእነ ሚሚ ስብሃቱ የሚዘጋጀው ጉባኤ በኢትዮጵያ የሚድያ ነፃነት ላይ ከመሳለቅ እኩል ሆኖብኛል።ለመሆኑ እኛ ከአፍሪካውያን ጋር ስንነፃፀር የት ላይ ነን?

አዲስ ዘመን ጋዜጣን ሳስበው ነፃነት ናፈቀኝ

ዛሬ ዛሬ ጋዜጦችን በኢንተርኔት ማንበብ የተለመደ ነው።የበለፀጉት ሃገራትን ትተን የአፍሪካዎቹ ለምሳሌ የዩጋንዳው ''ኒው ቪዥን'' የኬንያው ''ዴይሊ ኔሽን'' ዕለታዊ ጋዜጦች በሕዝቡ ዘንድ እንደ ማለዳ ቡና ከጉልት ቸርቻሪ እስከ ከፍተኛ የናጠጠ ሃብታም ነጋዴ ሳያነባቸው አይውሉም።ጋዜጦቹ ይዘዋቸው የሚወጡት እትሞች ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል የሚመለከቱ እና የመፃፍ መብትን በተሻለ ደረጃ ይንፀባረቅባቸዋል።ስርጭታቸው በታተሙበት ዕለት እስከ ታች ገጠር ከተሞች ድረስ የመድረስ አቅም አላቸው።

ለምሳሌ የኬንያው ''ዴይሊ ኔሽን'' በቀን ከእሩብ ሚልዮን ቅጂ በላይ ሸጦ ያድራል።የዩጋንዳው ዕለታዊ ጋዜጣ ''ዘ ኒው ቪዥን'' እንዲሁ እጅግ ተናፋቂ ጋዜጣ ነው።መቼ ነግቶ አንብቤው ባዩ ብዙ ነው።ጋዜጣው  በአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች  ጭምር ሳይቀር ሁል ጊዜ እንዲያነቡት እና በዕለቱ ትምህርት ቤት የሚያቀርቡት የቤት ሥራ እንዲሰሩ ይታዘዛሉ።ታድያ ማታ አባት እቤት እስኪገባ እና ጋዜጣውን ይዞ እስኪመጣ መጠበቅ የልጆች ሥራ ነው።ማታ ላይ የሚጠጣ አባት ያለው ልጁ የቤት ስራውን ባለመስራቱ ይታወቃል።''ኒው ቪዥን'' የመንግስት ድርሻ ከሃምሳ ፐርሰንት በላይ ያለበት ጋዜጣ ነው(በቅርቡ ፐርሰንቱ ለውጥ ሊኖረው ይችላል)።

እነኚህ ሁለት የቅርብ እና የሩቅ ጎረቤቶቻችን ህዝባቸው የማንበብ ባህሉ እንዲያድግ ደረጃቸውን የጠበቁ ጋዜጦች አሏቸው።

የእኔው አዲስ ዘመን 

ዕለታዊ ጋዜጣ አዲስ ዘመን በ 1935 ዓም ስራውን ሲጀምር ሃገራቱ ቅኝ ተገዢዎች ነበሩ።ዛሬ ዕለታዊ ጋዜጦቻቸው በሀገር ውስጥ የተከበሩ እና የህዝቡን የዕለት ከዕለት  ሕይወት የሚዳስሱ ብቻ ሳይሆኑ ከየትኛውም የዓለም ጥግ በኢንተርኔት በቀጥታ ይነበባሉ።የመፃፍ ነፃነት እና የጋዜጠኝነት መብት የታገተባት ሀገር ኢትዮጵያ አዲስ ዘመንን ይዘን ከአራት ኪሎ ብርሃንና ሰላም አለፍ ሲል ጨረታ እና የግምሩክ ማስታወቅያ የሚከታተሉ የመርካቶ ነጋዴዎች ያውም ሥራ እና እንጀራ ሆኖባቸው ይገዛሉ።

አዲስ ዘመን ጋዜጣ በገበያ ላይ 70 ዓመታትን አሳልፏል።ባለፉት አርባ ዓመታት ውስጥ ከሚያወጣቸው ፅሁፎች ይልቅ በንጉሡ ዘመን የሚያወጣቸው ፅሁፎች በሕዝብ ዘንድ የመነጋገርያ አጀንዳዎች የመሆን ዕድል ነበረባቸው።የሚያሳዝነው ነገር በንጉሡ ዘመን ስልጣን ጠቅልሎ መያዝ የተለመደበት እና እስከ 1960ዎቹ ድረስ የነበረ  የአገዛዝ ዘይቤ ነበር እንበል።በደርግ ዘመንም ሶሻሊስታዊ የአምባገነነት አስተዳደር የአንዳንድ የዓለማችን ክፍል ፋሽንም ነበር እንበል። ዛሬ መላው ዓለም በመረጃ መረብ በተገናኘበት፣የተነገረው ብቻ ሳይሆን የተነጠሰው በሚታወቅበት ዘመን  የሀገራችን የፕሬስ ነፃነት ይህንን ያህል የሚያሸማቅቅ መሆኑ ምን ያህል ድንቁርና በሕዝባችን ላይ እንደጣለ ያመላክተናል።

ሕዝብ የማንበብ ባህሉ እንዲዳብር እንደ አዲስ ዘመን ያሉትን ጋዜጦች በዘመናዊ መልክ ማደራጀት እና ለሕዝብ እንዲደርሱ ከመንግስት የፕሮፓጋንዳ መሳርያነት ማውጣት ብሎም የመፃፍ መብትን መልቀቅ ሲገባ ዛሬም ድረስ   በነፃ የመፃፍ መብት መነፈጋችን እጅግ ያስቆጫል።የአዲስ ዘመን ጋዜጣ  በ 1960ዎቹ ላይ ይፈለግ የነበረውን ያህል ዛሬ ከነመኖሩም እንዲረሳ መሆኑ የብዙ ችግሮቻችን አመላካች አንዱ መንገድ ነው።እርግጠኛ ነኝ እራሱ አዲስ ዘመን ጋዜጣን አሁን ባላስታውሳችሁ ብዙዎቻችሁ እረስታችሁታል።ግን ቀን ጥሎት እንጂ አዲስ ዘመን የተባለ ዕለታዊ ጋዜጣ 70ኛ ልደት በአሉን አክብሮ ወደ 71ኛው እያዘገመ ነው።

የአዲስ ዘመን ጋዜጣን ጉስቁልና ስናጤነው እና የቅርብ ጎረቤት ኬንያ እና ዩጋንዳ ያሉበትን የማንበብ ባህል መዳበር እና ለመፃፍ ነፃነታቸው ምን ያህል ዋጋ እንደሚሰጡ ስናስብ ምን ያህል በነፃነት እጦት እየማቀቅን እንደሆነ ይቆጠቁጠናል።አይደለም ጋዜጣ ብሎጎችን እኮ አሳዶ የሚዘጋ መንግስት ያለን ነን- እኛ ኢትዮጵያውያን።በእዚህ ደረጃ ህዝብ የመፃፍ እና የመናገር ነፃነት አጣ ማለት ምን ማለት ነው? አዎን!ይህ ማለት ሲመነዘር ብዙ ብዙ ይወጣዋል።

ከምንዛሬው ውስጥ ትውልድ አዲስ ነገር እንዳይፈጥር መሸበብ፣ሙስና ሕዝብ አናት ላይ ሲፈነጭ ዝም እንድንል፣በሕዝብ ስም መንግስት የተበደረው ገንዘብ እንደፈለገ ለግለሰቦች የግል ኪስ ማድለብያ ሲሆን ፈርተን እንድናቀረቅር፣የተሳሳተ የትምህርት ፖሊሲ ትውልድ ሲገድል ለመናገር እንዳይቻል ወዘተ መጥቀስ ይቻላል።በነፃነት ለመፃፍ መታገድ እንዲህ ትውልድንም ሀገርንም ይገድላል።የኢትዮጵያን አሳዛኝ የሚያደርገው መንግስት በእራስህ መንገድ ቀጥል ለሕዝባችን በገንዘባችን የሻማ ጭላንጭል እንሆናለን ብለው የተነሱ የግል ጋዜጦችን ለምሳሌ አዲስ ነገር፣ወዘተ እያዋከበ አዘጋጆቹን በዘመኑ ፋሽን ስድብ እየለጠፈ ከገበያም ከሀገርም እንዲሰደዱ ማድረጉ ነው።የመፃፍ ነፃነት ማጣት ምንዛሬው ብዙ ነው። ምንዛሬውን ዘርዝረን ስንጨርስ አስከፊው የወደቅንበት ጭቃ ያዳለጠን ዳጥ ወለል ብሎ ይታየናል። ውድ የሆነው ነፃነትም እጅግ ይናፍቀናል።አዎን አዲስ ዘመን ጋዜጣን ሳስበው ነፃነት ናፈቀኝ።

ጥቅምት 23/2006 ዓም
ጌታቸው በቀለ
ኦስሎ

1 comment:

Anonymous said...

i am very proud with your article always your admire. I LIKE ALL YOUR ARTICLS . please keep it up bro.

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...