ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, September 22, 2014

ኢትዮጵያ ያለባት የብድር መጠን 400,000,000,000 (አራት መቶ ቢልዮን ብር)ወይንም 20,000,000,000 (ሀያ ቢልዮን ዶላር ደርሷል) (Gudayachn update)

የታዳጊ ሀገሮች ወደ ውጭ የሚወጣው የገንዘብ ፍሰት እ ኤ አ ከ2001-2010 ዓም (የካርታውን ምንጭ ለማግኘት ይህንን ይጫኑ 

በሀገር ስም መበደር ትንሽ ለባቡር፣ለመንገድ እና ለፎቅ መስርያ ማዋል፣ ከተማውን ሞቅ ማድረግ፣ የድሆችን ቤት እያፈረሱ ከከተማ ማራቅ እና   የቀረውን አብዛኛውን በብድር የተገኘ ገንዘብ ግን በሙስና ለግል ጥቅም ማዋል አልያም በውጭ ባንኮች በግል ስም ማስቀመጥ።በመጨረሻም የብድር ዕዳውን ለልጅ ልጅ ማቆየት።ኢትዮጵያ ያለባት የብድር መጠን  400,000,000,000 (አራት መቶ ቢልዮን ብር)ወይንም 20,000,000,000 (ሀያ ቢልዮን ዶላር ደርሷል)።

አስገራሚው ነገር የብድር ስምምነቶችን ማፅደቅ ያለበት የሀገሪቱ ምክርቤት ሲሆን በአሁኑ ትውልድ እና በመጪው ትውልድ ስም እየተበደረ ያለው መንግስት በይስሙላ ምክርቤቱ የሚያፀድቀው ለፎርማሊቲ መሆኑ ነው።
የኢትዮጵያ ቴሌቭዥንም ሆነ ባለስልጣናት ኢትዮጵያ ብድር ስታገኝ እንደ ትልቅ ስኬት እየተኩራሩ ነው የሚነግሩን።በመሰረቱ አንዲት ሀገር ከሀገር ውስጥ ምርቷ እና ከውጭ ንግድ ገንዘብ አግኝታ ልማት ስትሰራ እንጂ ተበድራ ለትውልድ በምታቆየው የብድር ዕዳ  ''ልማት ተሰራ'' ብላ መኩራራት አትችልም።ምክንያቱም በብድር የመጣው መዋለ ንዋይ በራሱ አትራፊ መሆኑ የሚታየው ከአመታት በኃላ ያውም ብዙ ነገሮች ባሉበት የመሆናቸው ዕድል ከተፈጠረ በመሆኑ ነው።
የዶላር በብር አንፃር ያሳየው የምንዛሪ እድገት (ከጉግል የገንዘብ ምንዛሪ መረጃ የተገኘ)

ዛሬ አንድ ሰው ተበድሮ ጥሩ ሊለብስ፣ሊንቆጠቆጥ ይችላል።ነጥቡ ግን ተበድሮ ነው? ወይስ ሰርቶ ነው ያማረበት ነው? የአዲስ አበባን የባቡሩ ዝርጋታ ጉዳይ ስናስብ እንዲህም እናስባለን።በአሁኑ ትውልድ እና በመጪው ትውልድ ስም ተበድረን ''እኔ ከሞትኩ '' በሚል መርህ ይመርብን? ወይንስ ማማራችንን በልክ አድርገን ሰርተን ለማግኘት ጥረን በሀገር ምርት እና በውጭ ንግድ በምናገኘው ሀብት  ሀገራችንን እናሳድግ? ይህ ነው የሀገር መሪዎች ፈታኝ ጥያቄ።የእኛን የከፋ የሚያደርገው ተበድረንም አብዛኛው ከሀገር በህገወጥ መንገድ መመዝበሩን መስማታችን ነው።

ኢትዮጵያ ከፍተኛ ባለስልጣናት በለየለት የገንዘብ ዘረፋ ላይ መሰማራታቸውን እራሱ መንግስትም ያመነው ጉዳይ ነው።አንዳንድ ባለሥልጣናቱንም ዘብጥያ ማውረዱ ይታወቃል።ሆኖም የኢትዮጵያ አንጡራ ሃብት በቢልዮን የሚቆጠር ዶላር አሁንም እየተመነዘረ መውጣቱ የዓለም ዓቀፍ ጥናቶች አመላክተዋል።የሚገርመው ነገር ግን እንደተጠበቀው የሙስና ዘመቻ ሲባል የነበረው የውሃ ሽታ ሆኖ መቅረቱ ነው።አሁን የሙስና ኮሚሽን መኖሩን የሚያስታውሱት ምናልባት በለጋሃር በኩል ሲያልፉ ህንፃውን ከተመለከቱ ብቻ ነው።

ጥቂቶች በናጠጡበት፣ ሙስና ከሃይማኖት ድርጅት እስከ ቁንጮ ባለስልጣናት የተካኑበት ተግባር ነው። ጉዳዩ የበለጠ የእያንዳንዱን ሰው ትኩረት የሚሻ መሆኑን የምንረዳው ሀገሪቱ በገፍ ከውጭ ከሚቀርበው እርዳታ በተጨማሪ በከፍተኛ መጠን እየገባችበት ያለው የብድር ዕዳ ነው።በአግባቡ በፓርላማ የማይመከርባቸው፣ ፓርላማ ላይም ቢነሳ ሁሉም አጨብጭቦ የሚወጣበት ፓርላማ ከመሆኑ አንፃር ብድሩን የሚያፀድቀው አካል ምን ያህል ኃላፊነት እየተሰማው ነው? የሚለው ሌላው አጠያያቂ ጉዳይ ነው።ዕዳው ለልጅ ልጅ የሚቀመጥ እየተቀመጠልን መሆኑን አለመዘንጋት ጠቃሚ ነው።

የኢትዮጵያ የገንዘብ እና ኤኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ድረ-ገፅ እንደሚያመለክተው በ 2001 እና በ 2005 ዓም መካከል ባሉት ዓመታት ብቻ  የኢትዮጵያ የውጭ ብድር በ 156 % ማደጉን ያሳያል።ይሄውም በ 2001 ዓም 4.35 ቢልዮን የነበረው ብድር በአምስት ዓመታት ውስጥ ወደ 11.17 ቢልዮን ዶላር መመንደጉን ያሳያል።ባጠቃላይ የቅሌት መዝገባችን ወደ 16.11 ቢልዮን ዶላር ደርሷል። አብዛኞቹ በመንግስት የሚሰሩ ፕሮጀክቶች ዋና ምንጫቸው የውጭ ብድር ነው።ብድር አትራፊ ለሆኑ አዋጭ ፕሮጀክቶች ከሆነ ሙሉ በሙሉ አይወቀስም ነገር ግን ተበድሮ ለሙስና እና ለጥቂቶች ኪስ ማድለብያ ሲሆን ወንጀሉን ያከብደዋል።

 ሚያዝያ 2/2006 ዓም የ ገንዘብ እና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር ባቀረበው የአምስት ዓመት ትራንስፎርሜሽን ክንውን ላይ ከተባለው ግብ ኢትዮጵያ መድረስ አለመቻሏን አምኗል። የምክር ቤቱ ብቸኛ ተቃዋሚ አቶ ግርማ ''ቀድሞውንም ዕቅዱ በአግባቡ ያልታሰበበት ለመሆኑ አሁን ላለበት ውጤት መብቃቱ በራሱ ምስክር ነው'' ብለዋል።

የኢትዮጵያ ምጣኔ ሃብት ከፖሊሲ ችግር በተጨማሪ ቅጥ ያጡ የኢህአዲግ ባለስልጣናት ሙስና ዋነኛው ምክንያት ለመሆኑ አያጠራጥርም። ከእነርሱ ጋር አብረው የሚዘርፉ ግን ሀገሪቱ አድጋለች እያሉ ሪፖርት ለማውጣት የሚሽቀዳደሙ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችን እዚህ ላይ መዘንጋት አይገባም።

 ከላይ መግስት እራሱ  ያመነውን የብድር መጠን ካወሳን ቀጥለን ለሙስናው ማስረጃ ባለፈው ዓመት ግንቦት ላይ መሰረቱን ዋሽግተን ላይ ያደረገው ''ግሎባል ፋይናንስ እንተግርቲ'' ከኢትዮጵያ  ባለፉት አስር ዓመታት ውስጥ በሕገ ወጥ መንገድ 16.5 ቢልዮን ዶላር ከሀገር ወጣ ይላል።(Ethiopia lost 16.5 Billion to illegal smuggling of cash out of the country in 10 years) ለትውልድ ከሚቀመጥ ብድር ላይ ከተሞች ሲብለጨለጩ እናይ ይሆናል።ግን ሀገሪቱ ከተበደረችው መጠን አንፃር እየተሰራ ነው ወይ? ስንል ትልቅ ጥያቄ ይጭራል። ጥያቄውን ይህንን ያህል ብድር የተበደረች ሀገር ዋና ከተማዋ ነዋሪ ከ25% በላይ የሚሆነው ውኃ ማግኘት አልቻለችም ይህም ቁጥሩ ወደ አንድ ሚልዮን የሚጠጋ ሕዝብ ነው።

ጉዳያችን
መስከረም 12/2007 ዓም (ሴፕቴምበር 22/2014)

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።