ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Friday, July 25, 2014

የኢህአዲግ/ወያኔ ባለስልጣናት አልቻሉም እንጂ በሕሊናቸው ገድለዋታል።በእግዚአብሔር ቸርነት እና ለእውነት በቆመው ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ህሊና ግን ማርያም ተርፋለች።

ማርያም ይህላ ኢብራሂም 

የ 27 ዓመት ወጣት ነች።ሁለት ልጆች አሏት።አንዱ ልጇ የተወለደው በሱዳን እስር ቤት ውስጥ ነው።በእስር ቤት የተወለደው ልጇን ከወለደች በኃላ ለመጨረሻ ጊዜ እንደምታገኘው አውቃለች።ከወሊድ በኃላ በሞት እንድትቀጣ የሱዳን ፍርድ ቤት ወስኖባታል።የሰራችው ወንጀል የለም።ወንጀል ተብሎ የተቆጠረባት ክርስቲያን መሆኗ እና እምነቷን ወደ እስልምና አለመቀየሯ ብቻ ነበር።ማርያም ይህላ ኢብራሂም ትባላለች።አባቷ ሱዳናው እናቷ  ኢትዮጵያዊት እና የኦርቶዶክስ ክርስቲያን ኃይማኖት ተከታይ ነች።ይህ ብቻ አይደለም።ያገባችው ባለቤቷም ክርስቲያን ነው። 

የሱዳን ፍርድ ቤት በማርያም ላይ የፈፀመው ፍርደ ገምድል እና ፅንፈኛ ብይን መላው ዓለምን አሳዘነ።ሆኖም ግን የሱዳን ፍርድ ቤት ግን ግንቦት 15/2014 ዓም እ ኤ አ የወሰነውን የሞት ፍርድ ከመለወጥ ይልቅ የማርያም ልጅ መውለድን ብቻ እንደሚጠብቅ በቀጣዩ ቀን ግን ግድያውን እንደሚፈፅም ደጋግሞ ገለፀ።

ማርያም በደረሰባት የፍርድ ገምድል ውሳኔ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣የኖርዌይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትርን ጨምሮ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን፣አብያተ ክርስቲያናትን፣ከፍተኛ የዓለማችን ባለስልጣናት እና የመገናኛ ብዙሃን ድምፃቸውን አሰሙ።ማርያም እናቷ የተወለደችባት፣ ከሱዳን ጎረቤት የምትገኘው እና ከአርባ ሚልዮን በላይ የሚሆን ክርስቲያን የሚኖርባት ሀገር ላይ በመሪነት የተቀመጡ የኢህአዲግ/ወያኔ ባለስልጣናት ግን ቃል አለመተነፈሳቸው አሳዛኝ ብቻ ሳይሆን አሰቃቂ ጭካኔ ነው።ጉዳዩ ዓለም አቀፍ ጉዳይ ከመሆኑ አንፃር የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አንዳችም አይነት መግለጫ አልሰጠም።
ማርያም ሮም ስትደርስ የኢጣልያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ስቀበሏት 

ኢትዮጵያውያን በአረብ ሃገራት ክብራቸው ተዋርዶ እና በቀላል ዲፕሎማስያዊ ንግግሮች ሊፈቱ የሚችሉ ችግሮቻቸው እንደ ዋዛ በኢህአዲግ/ወያኔ ባለስልጣናት ሳይፈፀሙ በመቅረታቸው ሺዎች ኢትዮጵያውያን ለመከራ ተዳርገው ተመልክተናል።
ዶ/ር ቴዎድሮስን እዚህ ጋር በስም መጥቀሱም ተገቢ ነው።የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንዲት ኢትዮጵያዊት ክርስቲያን በመሆኗ ብቻ የሞት ፍርድ ሲፈረድባት እና መላው ዓለም ስለ ዕምነት መብት እና ለምስኪኗ ኢትዮጵያዊት ሲሟገት የተቃውሞ መግለጫ  ለማውጣት ካልቻለ ስራው ምን ሊሆን ነው? ዶ/ር ቴዎድሮስ መቼም  ዛሬም ''በሳውዳረብያ ላይ ተመጣጣኝ እርምጃ እንወስዳለን'' እያሉ እንደቀለዱት ቀልድ ዛሬም በማርያም ላይም ቀለዱባት ብለን እንገምት ይሆን?

ማርያም በፅናቷ፣በእግዚአብሔር ቸርነት እና በመላው ዓለም ተፅኖ ትናንት ሐምሌ 17/2006 ዓም  ከሞት ፍርዱ ድና ጣልያን ገብታለች።ቢሆንልን ማርያም ከሮም ይልቅ መጀመርያ ወደ እናቷ ሀገር  ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ነበረባት።ኢትዮጵያ ግን በኢህአዲግ/ወያኔ ስር ነች።ኢህአዲግ/ወያኔ ደግሞ  መሬት ለመሸጥ እና ሀገር ለመቸብቸብ እንጂ ለሀገር እና ለወገን  የሚፈይድ ሥራ ለመስራት  ያልታደለ መንግስት የነገሰባት ሀገር ነች።

ማርያም ሮም ስትገባ የኢህአዲግ/ወያኔ ባለስልጣናት ችላ እንዳሏት አለመሆኗን አሳይታለች።የጣልያኑ  ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፈደሪካ ሞሃረን አይሮፕላኗ ውስጥ ገብተው ተቀበሏት።ይህ ብቻ አይደለም ለክብሯ እንድታርፍ የተደረገው ሮም በሚገኘው ክላምፕኖ በተሰኘው ወታደራዊ የአየር ማረፍያ ነበር።የሮም የካቶሊክ ቤ/ክርስቲያን ርዕሰ ሊቀ ጳጳስ ፖፕ ፍራንሲስ ጋርም ተገናኝታለች።ሮም ጥቂት ቀናት ትቆያለች።ስለ ማርያም ዓለም ሲጮህላት አንዳች ያልተነፈሱት የኢህአዲግ/ወያኔ ባለስልጣናት ግን አልቻሉም እንጂ በሕሊናቸው ገድለዋታል።በእነርሱ አሰራር ማርያም ዛሬ ሞታለች።ብዙዎች ኢትዮጵያውያን በአረብ ሃገራት ለሚደርስባቸው ግፍ የኢህአዲግ/ወያኔ ባለስልጣናት ምንም አይነት ዲፕሎማስያዊ ሥራ ለመስራት አይፈልጉም ሲባል ቀልድ አለመሆኑን ማሳያ ነች ማርያም።ማርያም በኢህአዲግ/ወያኔ ህሊና ተገድላለች።በእግዚአብሔር ቸርነት እና ለእውነት በቆመው ዓለም አቀፉ  ማሕበረሰብ ህሊና ግን ማርያም ተርፋለች።

ጉዳያችን 
ሐምሌ 18/2006 ዓም (ጁላይ 25/2014)

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።