ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, April 26, 2022

በዩክሬን ግጭት ሳቢያ ዘንድሮ የዓለም ምጣኔ 3.6 በመቶ ብቻ ያድጋል።የኢትዮጵያ ግን ዘንድሮ 3.8 በመቶ ሲያድግ በመጪው ዓመት ደግሞ በ 5.7 በመቶ ያድጋል ሲል አይኤምኤፍ አስታወቀ።

The Ethiopian economy will grow by 3.6% in 2022. By next year it will go up to 5.7% - IMF

በየሁለት ዓመቱ በሚያወጣው የዓለም ኢኮኖሚ ምልከታ ሪፖርት የኢትዮጵያን የአገር ውስጥ ምርት ዕድገት (ጂዲፒ) ትንበያ ሳያካትት ያለፈው የዓለም የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ)፣ በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የሚያንሰራራበት ዕድል መኖሩን አስታወቀ፡፡

አይኤምኤፍ የሩሲያና የዩክሬይን ጦርነት የዓለምን ኢኮኖሚያዊ ማገገም ወደኋላ እንደሚመልሰው ባብራራበት አዲሱ ሪፖርት፣ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እ.ኤ.አ በ2022 3.8 በመቶ ያድጋል ሲል ተንብዮ፣ በመጪው ዓመት ደግሞ ይህ ቁጥር ወደ 5.7 በመቶ ከፍ ይላል ብሏል፡፡ 

በጥቅምት ወር ይፋ ተድርጎ በነበረው የድርጅቱ ትንበያ ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ አፍጋኒስታን፣ ሊባኖስ፣ ሊቢያና ሶሪያ የተያዘውን የአውሮፓውያን ዓመት ጨምሮ ለቀጣይ አምስት ዓመታት ባለው ጊዜ ውስጥ የሚኖራቸውን አጠቃላይ አገራዊ ምርት ዕድገት መተንበይ አለመቻሉን አስታውቆ ነበር።

ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ አገሮች ኢኮኖሚ በዋናነት የኮሮና ወረርሽኝ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከመከሰቱ ጋር ተያይዞ በተፈጠረው የኢኮኖሚ ቀውስ ሳቢያ፣ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ዕድገት ማሽቆልቆል እንደሚገጥማቸው መተንበዩ አይዘነጋም፡፡ ኢትዮጵያ በትንበያው ያልተካተተችው በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ሳቢያ አገራዊ የምርት ዕድገት ሒደቱን ማመላከት አዳጋች ሆኖ በመገኘቱ እንደሆነ መግለጹ ይታወሳል፡፡

ባለፈው ሳምንት ይፋ በተደረገው ሪፖርት መሰረት በኢትዮጵያ ያለው የዋጋ ንረት እኤአ በ2021 ከነበረበት  26.8% ወደ 34.5% እንደሚያድግ የተተነበየ ሲሆን፣ነገር ግን ይህ አኃዝ እ.ኤ.አ በ2023 ወደ 30.5 በመቶ ዝቅ የማለት ዕድል አለው ተብሏል፡፡

የሩሲያና የዩክሬይን ጦርነት የዓለም ምጣኔ ሀብትንእኤአ 2021 ከነበረው 6.1%  ዕድገት 2022 ወደ 3.6% ሊያወርደው እንደሚችል በሪፖርቱ ተመላክቷል። ይህ ደግሞ ጦርነቱ የውጪ ንግድ እንቅስቃሴዎችን በማስተጓጎል፣ የነዳጅና የምግብ ዋጋ ንረት በማስከተሉ እንደሆነ ሪፖርቱ ያሳያል፡፡

ከሰሃራ በታች የሚገኙት ነዳጅ አቅራቢ አገሮች በአማካይ 3.4 በመቶ እንደሚያድጉ የተተነበየ ሲሆን፣ መካከለኛ ገቢ እንዳለቸው የሚነገርላቸው የአፍሪካ አገሮች ደግሞ በአማካይ 3.3 በመቶ እንደሚያድጉ ይጠበቃል፡፡

ዝቅተኛ ኢኮኖሚ አላቸው የተባሉት አገሮች በአማካይ ሊያድጉ ይችላሉ የተባለበት አኃዝ 4.8 በመቶ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ 6.4 በመቶ፣ ኬንያ 5.7 በመቶ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ታንዛኒያና ኡጋንዳ እንደ ቅደም ተከተላቸው ከ4.7 አስከ 4.9 በመቶ የሚመዘገብ ዕድገት እንደሚስመዘግቡ ሲጠበቅ፣ ኢትዮጵያ ደግሞ 3.8 በመቶ እንደምታድግ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ዕድገት የዝቅተኛ ገቢ አላቸው ተብሎ ከተቀመጡት የአፍሪካ አገሮች ዝቅ ብሎ ቢገኝም፣ የነዳጅ ላኪ አገሮች ዝርዝር ውስጥ ከሚገኙት ናይጄሪያ፣ አንጎላና ጋቦን፣ እንዲሁም መካከለኛ ገቢ ካላቸው እንደ ደቡብ አፍሪካና ዛምቢያ ከመሳሰሉ አገሮች ብልጫ እንዳለው የአይኤምኤፍ ሪፖርት ትንበያ ያሳያል፡፡

የተራዘመ ጦርነት፣ ድርቅና ሰፊ የፀጥታ ችግር ውስጥ እንደምትገኝ በሚገለጸው ኢትዮጵያ ትንበያው ተስፋ የሚያሰንቅ ቢሆንም፣ አገሪቱ ብዙ ሥራዎች ማከናወን እንደሚገባት አመላካች እንደሆነ ሪፖርቱን የተመለከቱ የኢኮኖሚ ባለሙያዎች አስታውቀዋል፡፡

የኢኮኖሚ ባለሙያው አቶ ዋሲሁን በላይ በሪፖርቱ ላይ ባቀረቡት አጭር ጽሑፍ እንዳመለከቱት፣ዓለም በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት ተዳክሞ የነበረውን ኢኮኖሚ እንዲያገግም የማድረግ ደረጃ ላይ ደርሶ ነበር፡፡ነገር ግን የሩስያና የዩክሬይን ጦርነት ነገሮችን ለውጦታል ብለዋል፡፡

አይኤምኤፍ ለኢትዮጵያ የዕድገት ትንበያ የሠራው የተጀመሩ ሥራዎችን፣ እንዲሁም ሪፖርቶችን መሠረት አደርጎ ነው የሚለውን ከግንዛቤ እንደወሰደ ይታመናል ያሉት የኢኮኖሚ ባለሙያው፣ በተጨማሪም በአገሪቱ ውስጥ የግብርና ምርታማነት እንደሚያድግ፣ የውጪ ንግድ አማራጮች እንደሚሰፉ፣ ለዓለም ገበያ ክፍት መሆን  የጀመሩት ሥራዎችና የህዳሴ ግድብ የኃይል ምንጭ ጅማሮ ከግምት ውስጥ የገቡ ጉዳዮች ይሆናሉ የሚል እምነት እንዳለቸው አቶ ዋሲሁን ጠቁመዋል፡፡

የዜናው ምንጭ ሪፖርተር ጋዜጣ ሚያዝያ 24፣2022 ዓም እኤአ ዕትም ነው።

https://ethiopianreporter.com/article/25300

====================/////=========

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...