Monday, May 22, 2023

መንግስት ከዲፕሎማሲያዊ መፋዘዝ ይውጣ! የአረብ ሊግ በአባይ ግድብ አንጻር የወሰነውን የጸብጫሪነት ተግባር በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የምላሽ መግለጫ ብቻ የሚበቃ ሊሆን አይገባም።መንግስት ያልሰራው ግዙፍ ስራ ኢትዮጵያን ለአደጋ እንዳያጋልጣት ያሰጋል።

የኢትዮጵያ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ዋና መስሪያቤት

  • መንግስት በፍጥነት ሊሰራቸው የሚገቡት አምስት ወሳኝ ዲፕሎማሲያዊ ተግባራት
=========
ጉዳያችን አለርት
=========

የአረብሊግ አንዱ የሚታወቅበት መለያው እንደባዶ ቆርቆሮ ብዙ መጮህ እና ትንሽ ማድረግ ነው።በፍልስጤም እስራኤል ግጭት፣በሊብያ፣የመን እና ሶርያ መንግስታት መፍረስ ላይ ሁሉ ብዙ በመጮህ የሚታወቀው የአረብሊግ ነገር ግን አንድ የጋራ ሰላም አስከባሪ ልኮ በጋራ የቀጠናውን ችግር ሲፈታ አልታየም። ሰሞኑን በሱዳን ጉዳይ ላይም ስብሰባ ተቀምጦ ብዙ ንግግር ሰምቷል። የአረብ ሊግ በውስጡ የተለያየ የመከፋፈል ስንጥቆች ስላሉት በስሜት የአካፋ ያህል የሚናገረውን አንዲት ማንኪያ ያህል የማድረግ ልማድ እንደሌለው ብዙዎች በድርጅቱ ላይ የሚሰጡት ምስክርነት ነው።

ሊጉ በኢትዮጵያ የአባይ ግድብ አንጻር በግብጽ አነሳሽነት አማካይነት ያሳየው ድፍረት ግን እንዲሁ በቀላል የሚታይ አይደለም። የግብጹ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር  ሳማህ ሃሰን ሸሪክ የአባይ ጉዳይ በአረብ ሊግ እያንዳንዱ መደበኛ ስብሰባ ላይ ቋሚ አጀንዳ እንዲሆን አስደርገዋል።የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የረጅም ጊዜ የዲፕሎማሲ ልምድ ያላቸው ግለሰብ ናቸው።የዛሬ ሦስት ዓመት ጉዳያችን ስለግለሰቡ ማንነት የጻፈችውን በእዚህ ሊንክ ላይ ያንብቡ።

የአረብ ሊግ መደበኛ ስብሰባውን ባደረገ ቁጥር የአባይ ግድብ ጉዳይን እያነሳ መፈትፈቱን የኢትዮጵያ መንግስት እንደዋዛ ሊመለከተው አይገባም። ባሕር ተሻግረው የኢትዮጵያ ወንዞች ጉዳይ ይመለከተናል የመካከለኛ ምስራቅ ጉዳይ ነው የሚለው የአረብ ሊግ የድፍረት ድፍረት ወሳኝ የሆነ አጸፋዊ የዲፕሎማሲያዊ ምት ይፈልጋል። ለእዚህ ደግሞ ኢትዮጵያ አቅሙም ሆነ ብቃቱ አላት። ነገር ግን ጉዳዩን እንዴት ማስተናገድ እንዳለባት መንግስት የተረዳ አይመስልም። የአረብ ሊግ በኢትዮጵያ የውስጥ ወንዝ ጉዳይ ላይ ውሳኔ ማሳለፉ የሰሞኑ ዜና ነው። የኢትዮጵያ መንግስትም ዛሬ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል መግለጫ አውጥቷል። ከመግለጫው በላይ ግን ከዲፕሎማሲያዊ መፋዘዝ ወጥቶ መንግስት በፍጥነት ሊሰራቸው የሚገቡ አምስት ተግባራት አሉ።


የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ለአረብ ሊግ ውሳኔ ዛሬ የሰጠው ምላሽ

መንግስት በፍጥነት ሊሰራቸው የሚገቡት አምስት ወሳኝ ዲፕሎማሲያዊ ተግባራት:

1/ የአፍሪካ ሀገሮችን የውሳኔው አደገኛነት እንዲገባቸው ማድረግ፣ ጉዳዩን ወደ አፍሪካ ሕብረት መርቶ ተጻራሪ መግለጫ ማሰጠት እና የዲፕሎማሲ ጉዞ ወደ አፍሪካ ሀገሮች መላክ።በእዚህ አንጻር የሚከተሉት ተግባራት መንግስት መከወን ይችላል።
  • የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ልዩ መልዕክት የያዘ ደብዳቤ ለአፍሪካ ሀገራት የሚያደርስ ከፍተኛ ልዑክ መላክ እና የአረብ ሊግ ጣልቃ ገብነትን ኢትዮጵያ ፈጽሞ የማትቀበለው ብቻ ሳይሆን በአፍሪካውያን ላይ የተቃጣ የቅኝ ግዛታዊ መንፈስ መያዙን ማሳየት፣
  • ለአፍሪካ ቀንድ ቀጣይ የጸጥታ ስጋት መሆኑን በሚገባ ማስረዳት፣
  • የአፍሪካውያን ጉዳይ በራሳቸው በአፍሪካውያን በግብጽ እና ኢትዮጵያ መካከል የሚታይ እንጂ የሌሎች ጣልቃ ገብነትን እንደማይቀበሉ የአፍሪካ ሀገሮችን ማግባባት እና ይህንኑ እንዲገልጹ ሰፊ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ማቀጣጠል፣
  • የአፍሪካ ሕብረት የአረብ ሊግን ውሳኔ እንዲቃወም ኢትዮጵያ ከፍተኛ ተጽዕኖዋን በድርጅቱ ላይ ማሳየት አለባት፣
  • ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መቀመጫ እንደመሆኗ መጠን የአፍሪካ ሕብረት ላይ በእዚህ ጉዳይ ከፍተኛ ተጽዕኖዋን ማሳየት አለባት። በሕብረቱ ስብሰባዎች ላይ የአረብ ሊግ የአፍሪካን ሉአላዊነት መዳፈሩን ደጋግማ መንገር አለባት።በመቀጠልም ኅብረቱ የአረብ ሊግን ውሳኔ በሌላ ውሳኔ እስኪሽር ድረስ ዲፕሎማሲዋን አጠናክራ መቀጠል አለባት።
2/ ኢትዮጵያ የአረብ ሊግን አካሄድ ለተመድ፣ የአውሮፓ፣የአሜሪካ፣ቻይና፣እስራኤልና ሩስያ መንግስታት እንዲቃወሙት የዲፕሎማሲ ዘመቻ ማጠናከር አለባት።
  • በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተላከ ልዩ መልዕክት ለሀገራቱ  እና ለተመድ ዋና ጸሐፊ በልዩ ልዑክ ተልኮ መስጠት እና ጉዳዩ የሉአላዊነት ጉዳይ መሆኑን ማስረዳት እና ሀገራት አቋም እንዲወስዱ መወትወት፣
  • አሁን በመካከለኛው ምሥራቅ አንጻር ያሉትን የሀገራቱን አሰላለፍ ተመልክቶ በበቂ ሁኔታ አስልቶ መንቀሳቀስ
3/ የአረብ ሊግ አባል ሀገር የሆኑ ጎረቤቶቻችን ጂቡቲ፣ሱማሊያና ሱዳን የድርጅቱን ውሳኔ በብርቱ እንዲቃወሙ የጠነከረ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ማድረግ፣ ያሉትን የተጽዕኖ መንገዶች ሁሉ መጠቀም እና

4/ የአረብ ሊግ ውሳኔ ምን ያህል የኢትዮጵያን ሉአላዊነት የተጻረረ እንደሆነ ለኢትዮጵያ ህዝብ በሚገባ መግለጽ።
  • አስገራሚው ጉዳይ የአረብ ሊግ ውሳኔ በሚገባም የምሬት አቀራረብ የመንግስት መገናኛዎች ለኢትዮጵያ ህዝብ አልነገሩትም። ይህ መታረም ያለበት ነው።
  • የመንግስትም ሆኑ የግል መገናኛ ብዙሃን በሚገባ ጉዳዩ ምን ያህል የሉዓላዊነት ጥሰት እንደሆነ መግለጽ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጣውን እንዲገልጽ ሊደረግ ይገባል። ይህ በራሱ የዲፕሎማሲው አንዱ አካል ነው።
5/ የአረብ ሊግን ውሳኔ በመቃወም ኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎች በውጭ ሃገር አጠቃላይ የተቃውሞ ሰልፍ በመላው ዓለም ሊያደርጉ እና ለሚመለከታቸው ዓለም አቀፍ ድርጅቶችም ሆነ መንግስታት ማሳወቅ አለባቸው። በተመሳሳይ በሀገር ውስጥም ኢትዮጵያውያን አደባባይ ወጥተው ሊቃወሙትና የሉዐላዊነቱን አደጋ በሀገር ውስጥ ያለው ህዝብ በሚገባ እንዲረዳው መደረግ አለበት።

ባጠቃላይ የአረብ ሊግ ውሳኔ ኢትዮጵያ በብርቱ ልትቃወመው እና በቀላሉ ልታየው የሚገባ ጉዳይ አይደለም። ከመካከለኛው ምስራቅ ጋር ኢትዮጵያ ባላት ስልታዊ አቀማመጥ ብቻ ሳይሆን ባላት የህዝብ ብዛት እና ታሪካዊ ሃይማኖታዊ ዳራ ሳይቀር ኢትዮጵያን ለማጥፋት የሚፈልጉ አንዳንድ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች ኢትዮጵያ በአባይ ግድብ አንጻር የምታደርገውን መንሰራራት እንደ የራሳቸው ስጋት አያዩትም ማለት ሞኝነት ነው። ኢትዮጵያን ለማጥቃት ደግሞ እንደ አንድ ምክንያት ሊጠቀሙበት የሚፈልጉት በማይመለከታቸው የአባይ ጉዳይ እጃቸውን ለመንከር እንዳሰፈሰፉ በሚገባ እያሳዩን ነው። በቀጣይ ዓመታት የሚኖረው የዓለማችን የኃይል አሰላልፍ ደግሞ የአካባቢ ጉልበተኞች በአካባቢያቸው ያሉ ደካማ ሀገሮች የመውረር ስልት እንደሚይዝና የዓለምም የጸጥታ ስጋት እንደሚሆን የሚናገሩ ቀላል አይደሉም። ከመካከለኛው ሀገሮች ጋር ግብጽ የገባችው የወታደራዊ ስምምነቶች ደግሞ በአረብ ሊግ ስም አንዳንድ የመካከለኛው ምስራቅ ሀገሮች ኢትዮጵያን በወታደራዊ ኃይልም ጭምር ለማጥቃት አይቃዡም ማለት አይቻልም። ስለሆነም የኢትዮጵያ መንግስት የአረብ ሊግን ውሳኔ ከመግለጫ ባለፈ በጠነከረ የዲፕሎማሲ ምት መመለስና አስተማሪ እንዲሆን የማድረግ ስራውን ከላይ በተጠቀሱት አምስት መንገዶች ቢከውን ጠቃሚ ነው። ጉዳዩ ለኢትዮጵያ ህዝብ በሚገባ ጎልቶ ያልተገለጸበት ምክንያትና ዲፕሎማሲውን በሚገባ አድምቶ እንዳይሰራ በራሱ በመንግስት መዋቅር ውስጥ ያዘናጉት ካሉም እራሱን ይፈትሽ። ጉዳዩ ግን በምንም መለኪያ አደገኛ የሉዐላዊነት ድፍረት ነው።

======================///////==================

Saturday, May 20, 2023

ጎሳንና የፖለቲካ ተጽዕኖን መሰረት ያደረገ የጵጵስና ሹመት በመስጠት ቤተክርስቲያን የሲሞን መሰሪን መንገድ አትከተልም።

  • ቤተክርስቲያን ጳጳሳትን የምትሾመው የፖለቲካው አውድ እንዲፈነጥዝ ወይንም ይህኛው ጎሳ ደስ እንዲለው ሌላው እንዲከፋው አይደለም።
=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

ሲሞን በሰማርያ ይኖር የነበረ አስማተኛ ሰው ነበር፡፡ ሕዝቡም የሚያደረገውን ምትሐት እያዩ ይከተሉት ነበር በኋላ ግን በፊልጶስ ትምህርት አምነው ሲጠመቁ እሱም ተጠመቀ፡፡ በኢየሩሳሌም የነበሩ ሐዋርያት በሰማርያ ያሉ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል መቀበላቸውን ሲያውቁ ቅዱስ ጴጥሮስንና ቅዱስ ዮሐንስን ላኩበቸው፡፡ እነርሱ እጃቸውን በመጫን በሕዝቡ ላይ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ አሳዳሩባቸው፡፡ ይህንን ያየ ሲሞን መሰሪንም ብዙ ገንዘብ አምጥቶ እኔም እጅን የሚጭንበት ሰው መንፈስ ቅዱስ እንዲያድርበት ይህንን ሥልጣን ስጡኝ አለቸው ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹የእግዚአብሔርን ሥጦታ በገንዘብ ልትገዛ አስበሃልና ገንዘብህ ከአንተ ጋር ይጥፋ›› አለው፡፡ ሙሉ ታሪኩ በመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያት ሥራ ምዕ 8፣18-23 ላይ ይገኛል።

ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ የሚያስተምረን ሁለት ቁምነገር አለ። አንዱ መንፈስ ቅዱስን ለማታለል የመሞከር ተግባር ሰይጣናዊ እንጂ መንፈስቅዱሳዊ እንዳልሆነ ሲሆን ሌላው ይህንኑ በገንዘብ እና በሌላ ጥቅማዊ መንገድ የእግዚአብሔርን ሹመት ለማግኘት መሞከር በሐዋርያት ዘመንም ታይቶ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ የሚመሩት ሐዋርያት እንዴት እንደተዋጉት ያሳየናል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የሚመራው በመንፈስ ቅዱስ ነው።ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዋለበት እየዋሉ እና ካደረበት እያደሩ የተማሩት ሐዋርያት የመጀመርያ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤያቸውን በ50 ዓም ካደረጉ ጀምሮ ከእዚያ ቀድሞም ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጴጥሮስ የሰጠው ስልጣነ ክህነት  መሰረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንም ሆነች ምስራቃውያን የኦርቶዶክስ አብያተክርስቲያናት በጳጳሳት ሹመት ሂደት ላይ የመንፈስ ቅዱስ ሥራ ብቻ እንዲሆን እና ምንም ዓይነት የፖለቲካ፣የዘር፣የገንዘብ እና ሌላም  ተጽዕኖ እንዲኖረው አይፈቀድም። ይህ መንፈስ ቅዱስን በውጪያዊ ተጽዕኖ ለማግኘት የሚሞክር ሁሉ የሲሞን መሰሪያዊ መንገድ የተከተለ ተደርጎ ይወሰዳል።

ሰሞኑን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እያካሄደች ያለው የርክበካሕናት ጉባኤ ላይ ከቀረቡት አጀንዳዎች ውስጥ በጎሳዊ እና ፖለቲካዊ አድመኝነት የቤተክርስቲያኒቱን ቅዱስ ሲኖዶስ ለመክፈል የሞከሩ እና በኋላም በመግባባት ወደ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተመለሱት ሶስቱ ጳጳሳት በሕገወጥ መንገድ የሾሟቸውን አሁን በቅዱስ ሲኖዶስ በሚገባ ሳይመረመሩ እና የሚገባቸውና የማይገባቸውን ቤተክርስቲያን ከሐዋርያት ጉባኤ ጀምሮ የምትመረምርባቸውን የመንፈስ ቅዱሳዊ መንገዶች በመግፋት እንዲሾሙ የሚገፉ ደፋሮች እያየን ያለበት ጊዜ ነው። ይህ ሲሞን መሰሪያዊነት ነው።ፈጽሞ ተቀባይነት የለውም።

ቤተክርስቲያን ጳጳሳትን የምትሾመው የፖለቲካው አውድ እንዲፈነጥዝ ወይንም ይህኛው ጎሳ ደስ እንዲለው ሌላው እንዲከፋው አይደለም።ማንም ማን ቢሆን መንፈስ ቅዱስ የሚሾመውን ከሁሉም የሀገሪቱ ክፍል በእኩል ዓይን አይታ፣መርምራ እና ጸሎት አድርጋ ትሾማለች እንጂ በሆያሆዬ እና የፖለቲካ ትኩሳት ለማብረድ የምትሾምበት የጳጳሳት አሿሿም መንገድ የለም።ይህንን ቤተክርስቲያኒቱን በቅርበት የማያውቁ ፖለቲከኞች ጠንቅቀው ሊያውቁት የሚገባ እና በእንቢተኝነት ቤተክርስቲያኒቱን ለማዋከብ ከሞከሩ የሲሞን መሰሪ የተሰጠ ቅጣት ለእነርሱም እንደሚተርፍ ሊረዱት ይገባል።


Thursday, May 4, 2023

በአማራ ክልል ያለው ወቅታዊ ሁኔታ በመመካከር፣በመግባባትና በሽምግልና ብቻ ነው የሚፈታው።በአማራ ክልል ጸብ ከምታባብሱ የመረጃ አዛቢዎች በላይ የአማራም ሆነ የመላዋ ኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት የለም።


 

በአማራ ክልል ያለው ወቅታዊ ሁኔታ ፈጽሞ ወደ የደም ማፋሰስ ሊያመራ የሚገባው ጉዳይ ሊሆን አይችልም። ህዝብም ሆነ መከላከያ ፈጽሞ ምንም ዓይነት ግጭት እንዲፈጠር ፍላጎት ብቻ ሳይሆን የሚያጋድል በቂ ምክንያት አለመኖሩንም ጭምር ያምኑበታል። ይህም ሆኖ ግን ከውጪ ሆነው በአማራ ህዝብ ላይ ጦርነት እንዲነሳ ግፋ በለው የሚሉ እና በሰራዊቱም ውስጥ መንግስት አላስፈላጊ እርምጃ እንዲወስድ እና ህዝብ በመከላከያ ላይ ቅሬታ እንዲኖረው የሚፈልጉ ይጠፋሉ ማለት አይቻልም። ከእዚህ በተጨማሪ የኢትዮጵያን የጸጥታ መደፍረስ ከሱዳን ጋር ተያይዞ ምስራቅ አፍሪካን ለማበጣበጥ የሚፈልጉ ደግሞ የራሳቸውን የቤት ሥራ አይሰሩም ማለት አይቻልም።

የመረጃ አዛቢዎች መከላከያን ሊያጠቅ የመጣ ታጣቂ እንዳለ ይነግሩታል። በሌላ በኩል ደግሞ መከላከያ የሆነ ብሔር ወክሎ የመጣ አድርገው የመከላከያን ቁመና ለማውረድ የሚሞክሩ ደግሞ ሕዝቡን በሌላ አቅጣጫ ለማስደንበር ይሞክራሉ።ከእዚህ ሁሉ ጋር ደግሞ እራሱ መንግስት ከመጀመርያው የልዩ ኃይልን ወደ መደበኛ ሰራዊት የማስኬድ ሂደት አስመልክቶ መንግስት ከአማራ ክልል ጋር ያደረገው የኮሚኒኬሽን መንገድ መልክ ባለው አካሄድ አለመሆኑ ሌላው አሁን ላሉት አለመግባባቶች ያደረሱ ናቸው።

ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን መከላከያ አይገድሉም።መከላከያም ለሀገር ሕልውና የቆመን የመግደል ፍላጎት የለውም። ይህ በእንዲህ እያለ ግን የመረጃ አዛቢዎች በተለያዩ የማኅበራዊ ሚድያ ገጾች እየተጠቀሙ በተከታታይ የሚለቋቸው መረጃዎች የሰራዊቱን አመራሮችንም ሆነ ከህዝቡ የወጡ ታጣቂዎችን የማስደንበር ሥራ በመስራት ነገሮች ከሚገባ በላይ እንዲጋጋሉ የማድረግ እኩይ ተግባር ላይ ተጠምደዋል።

 አሁን የተጀመሩ የሽምግልና እና ወደ ሕጋዊ የመግባባት መስመር የመምጣት ሂደቶች በጎንደር በጥሩ ደረጃ ተጀምሯል። ነገ ጧትም ከመከላከያ ጄነራሎች እና የሕዝብ ታጣቂዎች መሃል ቀጠሮ ተይዟል። ዛሬ ከቀትር በኋላም የመከላከያ ጄነራሎችም ሆኑ ታጣቂዎች በተማመነ መንገድ መነጋገራቸው ነው የተሰማው። ከእዚህ በፊትም በሰሜን ወሎ ተመሳሳይ መነጋገር ተደርጎ ጉዳዩ በመግባባት ካለቀ በኋላ አሁንም የመረጃ አዛቢዎች የተወሰኑትን ለማስደንበር መሞከራቸው ይታወቃል።

የአማራ ክልል የጦርነት አውድማ እንዲሆን የሚፈልጉ የተለያዩ ፍላጎት ያላቸው የውስጥም ሆነ የውጭ ኃይሎች መኖራቸው የታወቀ ነው። ሆኖም ግን አማራን እንወክላለን የሚሉም ሆኑ የአማራ ህዝብ እንደተቀረው የኢትዮጵያ ሕዝብ በ21ኛው ክ/ዘመን ወደ የተሻለ እድገት እንዲሻገር ይህ እርባና የለሽ እና የራስ የሆነ የቀኝ እጅ መከላከያን በመቁረጥ የአማራ ክልልም ሆነ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያተርፈው አንዳች ነገር የለም። ስለሆነም በሁሉም አካባቢዎች ያሉ የሀገር ሽማግሌዎች፣የኃይማኖት አባቶች እና የንግዱ ማኅበረሰብም ጭምር በታጣቂዎች እና በመከላከያ መሃል በመሸምገል እና ሁሉንም ጉዳይ በህጋዊነት መልኩ እንዲያልቅ በማድረግ ሰላም የግድ መምጣት አለበት። በመንግስት በኩልም የሕዝብ ባሕላዊ ዕሴቶችን የማወቅ እና የማክበር ጉዳይም በአሁኑ የአማራ ክልል በተነሳው አለመግባባት ውስጥ መኖሩን ማመን አለበት። የወታደራዊ መንግስት እስከወደቀበት ጊዜ ድረስ የወልቃይት ህዝብ፣የቦረና የቀድሞ ሲዳማ፣አፋር እና የሱማሌ ቆላማ ቦታዎችን ላይ መሳርያ የመግፈፍ ሥራ ሙሉ በሙሉ ያልፈጸመው ይህንኑ የአንዳንዳ አካባቢዎች የባሕላዊ ዕሴቶች ዋጋ ስለሚያውቅ መሆኑም መረዳት ያስፈልጋል። በአማራ ክልልም ያለው ሁኔታም በደንብ መታየት ያለበት እና በሀገሪቱ ሕግ የመሳርያ ማስመዝገብ ሕግ ላይ አጥብቆ መስራት እና ሌሎች የጸጥታ ህጎች ላይ መስራት ይገባል። የነፍስ ወከፍ መሳርያዎች በተመለከተ ግን በኢትዮጵያ ሕግ መሰረት መመዝገባቸው በቂ መሆኑን ቢያንስ በእዚህ ጊዜ በደንብ መረዳት ያስፈልጋል። አሁንም ግን በአማራ ክልል ጸብ ከምታባብሱ የመረጃ አዛቢዎች በላይ የአማራም ሆነ የኢትዮጵያ ሕዝብ ጠላት የለም። ሰላም፣መረጋጋት እና መከላከያን በጋራ ማጠናከር የአማራ ክልልም ሆነ የሁሉም ኢትዮጵያውያን የውዴታ ግዴታ ነው። በመከላከያም ሆነ በህዝቡ መሃል ሆነው የመረጃ መዛባት የሚፈጥሩ ቢያንስ የህዝብ ስቃይ እንዲታያችሁ ወደ ህሊናችሁ ተመለሱ።

==============/////===========
 

Wednesday, May 3, 2023

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን አንዳንዶች ለማጣጣል በምትሞክሩት ደረጃ ዕውን ሀገር አጥፍቷል? እናንተ ጠቅላይ ሚንስትር ብትሆኑ ኢትዮጵያ የገጠሟትን ችግሮች እንዴት ነበር የምትፈቷቸው?



==========
ጉዳያችን ምጥን
==========

ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ ለኢትዮጵያ በመስራት፣በማሰብ እና አዳዲስ ሀሳቦችን በማፍለቅ ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ የሔደችባቸው መንገዶች የፈተና እና የችግር ብቻ እንዳይሆኑ ትልቅ ድርሻ ተወጥተዋል። ይህንን ዕውነታ መጋረድ ምን ያህል አሳዛኝ እና ኢፍትሃዊነት እንደሆነ አይገባኝም። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ገና ለፓርላማ ንግግር ሳያደርጉ ጀምሮ ከኋላ ታሪካቸው በመነሳት በከፍተኛ ተስፋ ከደገፉት ውስጥ ነኝ። ጠቅላይ ሚኒስትሩን በዓይን ፊት ለፊት ያየኋቸው በኦስሎ የኖቤል ሽልማት ለመቀበል በተገኙበት የኦስሎ ማዘጋጃቤት አዳራሽ ተገኝቼ ሽልማታቸውን ሲቀበሉም ሆነ ታሪካዊ ንግግራቸውን ሲያደርጉ በዝግጅቱ ለመታደም በገጠመኝ ዕድል ጊዜ ነው። ከእዚህ ውጪ የማያቸውም የምሰማቸውም በመገናኛ ብዙኃን ነው። 

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደማንም ሰው ከስህተት ነጻ እንደማይሆኑ አምናለሁ። በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ የሆነውን ሁሉ ለእኔ አዎን! ለእኔ መለኪያዬ እርሳቸው  በዘር እና በጎሳ ፖለቲካ እንዲሁም ለ27 ዓመታት በነቀዘ አስተዳደር የተጎሳቆለች ኢትዮጵያን መረከባቸው እና እርሳቸው ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላ ይህች በተቋማቷ ብቻ ሳይሆን በአካቢያችን እና በአፍሪካ ደረጃ የተጎሳቆለ ጥግ ላይ የቆመች ሃገር እንዴት ከግራ እና ከቀኝ የነበረውን መጓተት  አንዴ ወደ አንዱ ሌላ ጊዜ ወደሌላው እየተጎተተ ሃገር ሲንገላታ እርሳቸው ያንንም ያንንም ለመያያዝ እየደከሙ የሄዱበት አስቸጋሪ መንገድ ሁሉ ሲታሰብ በእርሳቸው ቦታ ብንሆን ምን ነበር የምናደርገው? የሚለው ከማሰብ በመነሳት ነው።

አዎን! ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕግ ማስከበር ላይ ችግሮች እስኪያድጉ የመጠበቅ እና አንዳንድ ጉዳዮች ለምሳሌ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሲኖዶስ የመክፈል ሙከራ ላይ መጀመርያ የያዙበት አያያዝ እና ሌሎች ላይ የፈጠሩት ክፍተት በደንብ ይገባኛል። ለእኔ አልገባህ ያለኝ አንዳንዶች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሆን ብለው ሀገር የማፍረስ ዓላማ ያላቸው አድርገው የሚያቀርቡት ብቻ ሳይሆን መንገዳቸው የጎሳ ፖለቲካ አዋጪ ነው ብለው የሚያምኑ አድርገው የሚያቀርቡት ኢተአማኔ የሆነው ጉዳይ ነው። የጻፏቸው የመደመር መጽሐፍ ላይ የጎሳ ፖለቲካ እንደማያዋጣ ብቻ ሳይሆን መደመር ብቻ አማራጭ እንደሆነ በሚገባ ተንትነው ገልጸው ጽፈውታል። አንድ ሰው ያላመነበትን በእዚህን ያህል የተብራራ እና ከውስጥ ፈንቅሎ በወጣ ስሜት ስለ መደመር እንዴት ይጽፋል?

ለኢትዮጵያ አንድነት ቤተመንግስቱ ትቶ ዘመቻ ለሔደ፣ የኢትዮጵያን ቤተመንግስት ለማደስ ለሰራ ብቻ ሳይሆን የቀደሙትን ነገስታት ሙዜም ላስቀመጠ፣ በጦርነት ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን ካቆመ ብሎ ለሰላም ደም ከተቃባቸው ጋር በሰላም አብሮ ገበታ ለተቀመጠ፣ የዓባይ ግድብ ብቻ ሳይሆን መከላከያ፣አየር ኃይል፣የትምሕርት ፖሊሲን፣የወደቀውን የልማት ባንክ፣ የተዳከመው የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እና ሌሎችን የኢትዮጵያ ተቋማት መልሶ ለማቆም ሥራዎችን በመስራት ዓይነተኛ ለውጥ ላመጣ መሪ የምንሰጠው የማጥላላት ደረጃ ዕውን ሰውየውን የሚመጥን ነው? ዐቢይ ዕውን ማኅበራዊ ሚድያው ብቻ ሳይሆን አንዳንድ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ ሃሳባቸውን የሚሰጡ ፖለቲከኞች እንደሚሉት ነው? ነው ወይንስ ለእኔ የማይታየኝ ለሌላው የሚታየው ሌላ ዓለም አለ? 

እዚህ ላይ አሁንም እደግመዋለሁ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሸኔ አንጻር እና የሸኔ ጽንፈኛ በኦሮምያ የስልጣን መዋቅር ውስጥ ገብተው እንደፈለጉ ሲሆን ወሳኝ እርምጃ አለመውሰዳቸው በተመለከተ አሁንም የእኔም ቅሬታ ነው። ይህም ሆኖ ግን ይህንን በዓላማ እና በተንኮል ኢትዮጵያን ለመጉዳት ብለው ነው ብዬ ሳይሆን እሳቸው ችግር ይፈታል የሚሉበት የራሳቸው ዓለም ውስጥ የገቡ ሆኖ ይሰማኛል።በእዚህ ሁሉ ሂደት ላይ ከወለጋ በተፈናቀሉት አንጻር እና አሁንም የኦሮምያ ክልል በአዲስ አበባ ዙርያ እና በአዲስ አበባ ነዋሪዎች ላይ እያደረሰ ያለው ግፍ ዙርያ የወሰዱት እርምጃ አለመኖሩ ሌላው ተጠቃሽ የመንግስታቸው ተአማኒነት ብቻ ሳይሆን ብዙ ሕዝብ ተስፋ እንዲቆርጥ ያደረገው ነው። 

ይህ በእንዲህ እያለ፣
  • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደስልጣን ባይመጡ ኖሮ ወደኋላ አምስት ዓመት እንሂድ እና በኦሮምያ እና በአማራ መካከል የነበረው የዚያን ጊዜ ውጥረት ወዴት ይደርስ ነበር? እዚህ ላይ የዛሬ አምስት ዓመት የነበረውን የለውጡ ሂደት ሲጀመር የነበረውን አውዳሚ አካሄዶች ሁሉ እናስታውስ።
  •  እርሳቸው በሔዱበት ደረጃ በደረጃ ስልጣን የመረከብ አካሄድ ባይኬድበት ኖሮ ህወሓት ስልጣኑን ይለቅ ነበር?
  • የዓባይ ግድብ በተዝረከረከበት ሁኔታ አሁን ያለበት ደረጃ ይደርስ ነበር?
  • ተዳክመው የነበሩት የኢትዮጵያ ቁልፍ ተቋማት መከላከያ፣አየር ኃይል፣የልማት ባንክ፣የትምሕርት ፖሊሲ፣ የክክሎች የፌድራል መንግስት አካል መሆን፣ የሱማሌ የአብዲኤሊ የመገንጠል ሙከራ አደጋ፣ ከኤርትራ ጋር የተሻሻለው ግንኙነት፣የህወሃት የዙር ጦርነት እና የሃገር ህልውና አደጋው፣ቆይቶም ወደ እርቁ ለመምጣት የተሄደበት ሂደት ሁሉ የመሪው የነገሮችን አጠቃላይ ሁኔታ የመረዳት አቅም ውጤት አይደለም?
በመጨረሻ ባለፉት አምስት ዓመታት ኢትዮጵያ የገጠሟትን ፈተናዎች ሁሉ እኛ ጠቅላይ ሚኒስትር ብንሆን የቱን አስቀድመን የቱን እናስከትል ነበር? እስኪ እራሳችንን እንጠይቅ። ፈተናዎች ነበሩ። አዎን! እጅግ የሚያሳዝኑ ፈተናዎች አልፈናል። እነኝህ ፈተናዎች ግን እኔ እስከሚገባኝ ድረስ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ ስልጣን ባይመጡም የሚቀሩ ፈተናዎች አይደሉም።ይልቁንም ክልሎች አሁን ከምናየው በላይ የተመሳቀለ አደጋዎች ውስጥ እንገባ እንደ ነበር ነው የሚገባኝ። በትንሹ የሱማሌን የአብዲ ዔሊ የመገንጠል ሙከራ በራሱ ለኢትዮጵያ ትልቅ አደጋ ይዞ ይመጣል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በአቅም፣በርዕይ እና በአፈጻጸም ፍጥነት እና ጥራት እንዲሁም ክትትል የሚታማ መሪ አይደለም። ሰውየው አንድ ነው። አስር አይደለም። በብዙ ችግር በታጠረች እና ሀገሪቱን ለማጥፋት የ24 ሰዓት ጊዜ ወስደው በሚሰሩ የውጭ እና የአካባቢ ሀገሮች ውስብስብ መንገድ ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከውስጥ ሆነን የሚሰራውን ብቻ ሳይሆን ሲያነጥስ ሁሉ ተንኮል አለበት እያልን ነገር በመጎንጎን የማናሰራው ሁሉ ተደምረን እና እነኝህን ሁሉ ተቋቁሞ መስራት በራሱ አንድ እራሱን የቻለ ፕሮጀክት ነው። እስኪ ከመተቸት እና ከማብጠልጠል በላይ ይህ የኢትዮጵያ የጋራ ጉዳያችን ነው ብለን ያገዝነው ሥራ ምንድን ነው? በህልውናው ዘመቻ የነበረውን ተሳትፎ ሳንጨምር ማለት ነው። በህልውና ዘመቻ የብዙዎች ርብርብ ስለነበር።

አሁንም በአዕምሮዬ ያለው ጥያቄ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን አንዳንዶች በእዚህ ደረጃ ለማጣጣል የምትሞክሩትን ያህል ሀገር አጥፍቷል? እናንተ ጠቅላይ ሚንስትር ብትሆኑ እነኝህን ችግሮች እንዴት ነበር የምትፈቱት? የሚለው ነው።
አንዳንዴ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆኖ ወጥ ሲጨልፍ ስናየው፣መንገድ ሲጠርግ ስንመለከት ሌላው ቀርቶ በመሪ ደረጃ ዝናብ ሲመጣ ዣንጥላ ሳያስይዝ እራሱ ይዞ እና ዝቅ ብሎ ስናየው እንደፈለግን ለመተቸት ተመቸን መሰለኝ። ስንወቅስ እና ስንተችም ኢትዮጵያዊ ጨዋነት የሚባል ነገር አንርሳ እንጂ! የሰፈራችንን የዕድር ሊቀመንበር የምናከብርበትን ክብር ሰጥተን ከእዝያ የሚሰማንን መውቀስ የወግ ነው። ሰውየው ግን በማኅበራዊ ሚድያ በሚሉት ደረጃ የሀገር አጥፊ ነው ብሎ ማመን ከቀላል አመክንዮ የመራቅ ችግር ብቻ ነው።ለሁሉም ጊዜ እና ታሪክ ያሳየናል። ይህም ሁላችንም ዕድሜ ካደለን ነው።ባጭሩ የአንዳንዶቻችን አወቃቀስ መሰረተ ቢስነቱ ቢብስብኝ ነው ይህንን ለማለት የተገደድኩት።
=========================////===========

Friday, April 28, 2023

የኦነግ/ኦህዴድ እና የህወሓት ጽንፈኝነት የአማራ ጽንፈኝነትን ወለደ። ኢትዮጵያን መልሰን ወደ አንደኛ ክ/ዘመን እንዳንከታት መንግስት የኃይል መንገድን ብቻ ከማሰብ ይልቅ ቀድሞ መከወን ያለበት ተግባር ላይ ያተኩር።

ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም እና ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ

በእዚህ ጽሑፍ ሥር 
  • '' ዐማራን እናንተ ትፈጥሩታላችሁ የሚል ስጋት ነው ያለኝ '' ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ለአቶ መለስ የነገሯቸው።
  • የኦነግ/ኦህዴድ እና የህወሓት ጽንፈኝነት የአማራ ጽንፈኝነትን ወለደ።
  • ህወሃት እና ኦነግ/ኦህዴድ የአማራ ብሔርተኝነትን እንዴት ፈጠሩት?
  • የአማራ ብሔርተኝነትን ያባባሱት የቅርብ ክስተቶች 
  • መንግስት ሊያስተካክላቸው የሚገቡ ሦስት ጉዳዮች

=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

በኢትዮጵያ የፖለቲካ እና ምጣኔ ሃብት ችግሮች ውስጥ ሁሉም በጋራ የሚያዜማት ዜማ አለች።የዜማው አቀራርብ ይለያይ እንጂ የፖለቲካ ፓርቲዎችም፣ ሕዝብም፣ ጋዜጠኛውም ሆነ ጸሓፊው የሚለው የሚያጠነጥነው የሃሳብ መቋጠሪያ  ''የሁላችንም የሆነች ኢትዮጵያ ''የጋራ ተጠቃሚነት"  እና ''እኩልነት '' የሚሉት ናቸው። እነኝህ ዜማዎች አሁን እንደቅንጦት እየተቆጠሩ መጥተው ሌላው አንገብጋቢው ጥያቄ ''የሕግ የበላይነት '' እና ''የጸጥታ ደህንነት '' የሚሉት እየገዘፉ መጥተዋል።

ኢትዮጵያውያን ቤተመንግስት ውስጥ ማንም ከየት ብሔር መጣ እምነት ዋና ጉዳያቸው አይደለም። ይህ ማለት ግን ቤተመንግስት የገባው ሁሉ የራሱን የጎሳ አስተሳሰብ ያለውን ወይንም የግል የእምነት መንገዱን ሕዝብ ላይ እንዲጭን ወይንም የህዝብን መልካም ዕሴት እንደፈለገ እንዲያጎሳቁል ይፈቅዳሉ ማለት አይደለም። እነኝህ ጉዳዮች በተለይ ህወሃት/ኢህአዴግ አራት ኪሎ ከገባ ወዲህ ይዞት የመጣው የጎሳ ፖለቲካ ብዙ ነገራችንን ጎድቶብናል። 

'' ዐማራን እናንተ ትፈጥሩታላችሁ የሚል ስጋት ነው ያለኝ '' ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ለአቶ መለስ የነገሯቸው።

አቶ መለስ ወደ አራት ኪሎ እንደገቡ ፊት ለፊት አግኝተው ካነጋገሯቸው ውስጥ ፕሮፌሰር  መስፍን ወልደማርያም አንዱ ነበሩ። ፕሮፈሰር መስፍን በወቅቱ የዐማራ ብሔርተኝነት የአሁኑን ያህል ገንግኖ ሳይወጣ የብሔርተኝነት አካሄድ ያለውን ችግር ብቻ ሳይሆን አማራ የምትሉት እራሱ አማራ እንደሆነ አያምንም እኔ በተወለድኩበት አካባቢ እናቴም አማራ የሚለውን የምትጠቀመው ለብሄር አይደለም በሚል ለማስረዳት ሞከሩ። አቶ መለስ ግን ስለ ጭቁን አማራ እና ገዢ አማራ እያሉ በጫካ ስላነበቡት እና ካድሬዎቻቸውን ሲያሰለጥኑ የነበረበትን ትርክት መንገር ጀመሩ። በመጨረሻ ፕሮፌሰር መስፍን ተናገሩ '' አሁን በሚሉት ደረጃ የአማራ ብሔር ብሎ እራሱን አገንግኖ የወጣ የለም። ሆኖም ግን የእኔ ስጋት ይህንን አማራ የሚባል የብሔርተኝነት ስሜት እናንተ እንዳትፈጥሩት ነው።'' በማለት ተናገሩ። 

ይህንን የፕሮፌሰር መስፍን አማራን ትፈጥሩታላችሁ ንግግር አንዳንዶች ፕሮፌሰር የአማራን ህልውና ከድተውታል በሚል ሲወቅሷቸው ነበር።የፕሮፌሰሩ ሃሳብ ግን መሬት ላይ የአማራ ማኅበረሰብም የሚያስበውን (በወቅቱ የነበረውን) እና ወደፊት የሚሆነውን ነበር ለማንጸባረቅ የሞከሩት። ዛሬ ላይ ስንመለከት የኦነግ እና የህወሃት ጽንፈኛ የብሔርተኝነት አካሄድ የአማራ ብሔርተኝነት አገንግኖ እንዲወጣ እያደረገው እንደሆነ እንመለከታለን።

የኦነግ/ኦህዴድ እና የህወሓት ጽንፈኝነት የአማራ ጽንፈኝነትን ወለደ።

በኢትዮጵያ ያለፉት ሃምሳ ዓመታት የፖለቲካ ትግል ውስጥ ከጎሰኝነት ፖለቲካ ከማገንገኑ በፊት የኢትዮጵያ ወጣቶች የትግል ማጠንጠኛ የነበረው የርዕዮተ ዓለም ፍትጊያ ነበር። ይህ ሁኔታ ግን ህወሃት ወደ ስልጣን ከመጣ በኋላ ግን የፖለቲካ አውዱ ተቀየረ። የጎሳ ፖለቲካ አስተሳሰብ ተማርን እና ነቃን በሚሉ ጥቅም ፈላጊዎች እየተቀነቀነ በህወሃት ዙርያ የተኮለኮሉ አዳዲስ የጎሳ ፖለቲከኞች መፈልፈል ጀመሩ። እነኝህ የጎሳ ፖለቲካ አቀንቃኝ ፖለቲከኞች በኢህአዴግ ጥላ ውስት ቆይተው የብልጽግና ፓርቲ ሲመሰረትም ኢትዮጵያ የሚለውን አጀንዳ ይዘው ቀጠሉ። በብልጽግና ዘመን የጎሳ ፖለቲካ በእየክልላቸው ሲያራምዱ የነበሩ አመራሮች ላይ የበለጠ ጽንፈኛ የሆነው የኦነግ ፖለቲከኞች ከክልል ምክርቤት እስከ የጸጥታ መዋቅር ተቀላቀሉ። በአዲስ አበባ ከተማ ሳይቀር የኢትዮጵያ አረንጓዴ፣ቢጫ እና ቀይ ሰንደቅ ዓላማ ምልክት ያለበት መኪናቸው ላይ እና እጃቸው ላይ አድርገው ሃይማኖታዊም ሆነ ሌላ ክብረበዓላት ላይ የሚገኙትን እነኝህ ከኦነግ የተቀላቀሉ እና ቀድሞም በኦህዴድ ስር የነበሩ ጽንፈኞች ሲያስወልቋቸው የህዝብ ቁጣ ቀሰቀሰ።

የለውጡ ሂደትን በከፍተኛ ደረጃ በተለይ የዶ/ር ዐቢይ ኢትዮጵያዊነትን በቦታው እንመልሳለን፣ኢትዮጵያ የሁሉም ትሆናለች የሚሉት ንግግሮች ተከትሎ የአማራ ክልል ህዝብ ደግፎ ቆሟል። አንድወቅትም በመላው የአማራ ክልል የዶ/ር አብይን የለውጥ ሂደት የደገፈ ሰልፍ ሲደረግ በኦሮምያ ክልል ምንም ዓይነት ሰልፍ ሳይደረግ የዋለባቸው ጊዜዎች ነበሩ። ይህ ሁኔታ ደግሞ በቅርቡ ተገልብጦ በኦሮምያ ክልል ከተሞች የድጋፍ ሰልፍ ሲደረግ በአማራ ክልል ደግሞ ምንም ዓይነት የድጋፍ ሰልፍ ሳይደረግ አልፏል። 

ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው የአማራ ክልል ህዝብ በብሔር ፖለቲካ ውስጥ የገባበት ሂደት በራሱ ዘገምተኛ ቢሆንም በሂደት ግን የህወሃት እና የኦነግ የጽንፍ እና የጥላቻ ትርክቶች ፕሮፌሰር መስፍን እንዳሉት የአማራ ብሔርተኝነትን የጽንፈኞቹ መግፋት ፈጥሮታል። ይህንን ሁሉም ወገን ሊያምነው የሚገባው እውነታ ነው። የአማራ ክልል ህዝብም ሆነ ፖለቲከኞች በአሁኑ የለውጥ ሂደት ላይ እጅግ አዎንታዊ ምላሽ ሲሰጡ ቤተመንግስት የገባው ከኦሮሞ ሆነ ከበሻሻ፣ከባሌ ሆነ ከአፋር የሚል ትንተና ውስጥ አልገቡም። ይህንን የጎሳ አስተሳሰብ ከመጸየፋቸው የተነሳም ነው የህውሃትን ያንን ሁሉ የጎሳ ጥላቻ ውርጅብኝ እየታየ እንዳላዩ በማለፍ የኢትዮጵያን ህልውና ላይ ሌላ እራስ ምታት ሳይሆኑ ያለፉት ብሎ መውሰድ ይቻላል። ይህንን በተለያዩ ጥናቶች ቢዳሰስ ከእዚህ የተለየ ውጤት የሚያሳይ አይመስለኝም።

ህወሃት እና ኦነግ/ኦህዴድ የአማራ ብሔርተኝነትን እንዴት ፈጠሩት?

አንዳዶች ከኦነግም ሆነ ከህወሃት መንደር የአማራ ብሔርተኝነትን አስመልክተው የሚሉት ቀድሞ በነበሩ መንግስታት ውስጥ እንደነበረ አድርገው ለመተረት ይሞክራሉ። በመጀመርያ ደረጃ በኢትዮጵያ የጥንትም ሆነ የመካከለኛው ዘመን ታሪክ ውስጥ የጎሳ ፖለቲካ ብሎ ጉዳይ የለም።ከእዚህ ይልቅ የሃይማኖት ጉዳይ ቀዳሚ ጉዳይ ሆኖ እንደኖረ ማንም የኢትዮጵያን ታሪክ የሚዳስስ የሚረዳው ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ ነገስታት ለስልጣን በሚያደርጉት ሹክቻ የሚነሱት ከመንደራቸው ሰው በማሰባሰብ ስለሆነ በዙርያቸው የቅርብ ዘመዶቻቸው እና የተወለዱበት መንደር ሊገኙ ይችላሉ። እንደ መዋቅር እና የመንግስት ስሪት ግን የገበረላቸው ሁሉ ልጃቸውን ሳይቀር እየዳሩ ግዛት ያስፋፋሉ እንጂ በጎሳ ስሜት መሄድ በራሱ የታየ ክስተት አይደለም።ለእዚህም የእርስ በርስ ጦርነት ሲያደርጉ በቦታው ይጠራሉ እንጂ የእገሌ ጎሳን እንዲህ አድርጌ ወይንም የእኔ ይህ ጎሳዬ ብለው የጻፉት ጽሁፍ የለም። በወቅቱ ከወሎው ገዢ ከትግራዩ ባላባት ወይንም ከሐረሩ ባላባት እያሉ ከመጻፍ ውጪ ያ ባላባት በትውልዱ ሌላ ቢሆንም የትውልድ ሃረጉን እንደ የግጭት ወይንም የስልጣን መፋተጊያ ምክንያት አልነበረም። ከእዚህ ይልቅ የስልጣን ጉዳይ ቀዳሚ አጀንዳ ነበር።

የአማራ ክልልም የሚያውቃት ኢትዮጵያ ይህች ነች።ጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ ወደ ስልጣን ሲመጡም ኢትዮጵያዊ ናቸው የሚለው ገዢ ሃሳብ ብቻ በውስጡ የነበረ እና አንዳንድ በውጪ የነበሩ የአማራ ብሔርተኝነት ገንግኖ እንዲወጣ የሚወተውቱትን ሁሉ የማይሰማ ህዝብ ነበር። ይህ ሁኔታ ግን በኦነግ የለየለት አማራን የለየ የዘር ጭፍጨፋ ከወለጋ እስከ ሌሎች የኦሮምያ ክልሎች እና የህወሃት የቅርብ ወረራ ወደ የአማራ ክልል የፈጸማቸው ጸያፍ ዘርን ምክንያት ያደርጉ ግፎች የአማራ ክልል ህዝብ የብሔርተኝነት ወይንም የጎሳ ፖለቲካ አቀንቃኞች የአማራ አክቲቪስቶችን ወደ መስማት አዘነበለ። የአማራ የጎሳ የጽንፍ አስተሳሰብ አወላለድ እንዲህ በግፊት እና ኢትዮጵያዊነትን እና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚገፋ አሰራር በኦነግ እና በህወሃት የጽንፍ አካሄድ የተወለደ የቅርብ ክስተት ነው።

የአማራ ብሔርተኝነትን ያባባሱት የቅርብ ክስተቶች 

ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው የአማራ የብሔርተኝነት ስሜት የቅርብ ክስተት ነው። ያባባሱት ደግሞ የብልጽግና መንግስት ጥንቃቄ የጎደለው አሰራር ብቻ ሳይሆን ከጽንፈኛ የህወሃት እና የኦነግ አካላት ጋር እየተሞዳሞደ የኢትዮጵያዊነት እሴቶችን እየገፈተረ መምጣቱ ነው። ለእዚህ ብዙ አብነቶችን መጥቀስ ይቻላል።ከወለጋ በመቶሺዎች ተፈናቅለው ከአዲስ አበባ እስከ ደብረብርሃን፣ደሴ እና ባሕርዳር ሲበተኑ። የተፈናቀሉትን በመጠለያ ቦታቸው ሄዶ ያጽናና ከፍተኛ ባለስልጣን አልታየም።የምግብ አቅርቦቱ ተጓድሎ፣ፍትህ ተረግጣ እና ኦነግ ሸኔ በመቶዎች የሚቆጠሩ ንጹሃን ገበሬዎችን እየሰበሰበ ሲገድል የህመሙን መጠን የሚያስተናግድ ስሜት ከብልጽግና ከፍተኛ ባለስልጣናት አለመታየቱ ለአማራ ክልል ብቻ ሳይሆን ለተቀረው ኢትዮጵያዊም ያስደነገጠ ነበር። 

ከእዚህ በተጨማሪ የኢትዮጵያዊነት እሴቶች እና መገለጫዎች ውስጥ የሆኑ ህዝባዊ በዓላት ሳይቀሩ በብልጽግና ፖሊሶች ሲበተኑ የመንግስት መግለጫ የሆኑ ኃይሎች ያደረጉት ነው እያለ መግለጫ ሲያወጣ የሚያርም የለም። ለእዚህ የዘንድሮውን የዓድዋ በዓል በምንሊክ አደባባይ እንዴት በፖሊሶች እንደተበተነ እና በአራዳ መናገሻ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ቅጽር ግቢ ውስጥ ታቦተ ሕጉ በወጣበት አስለቃሽ ጋዝ በመርጨት በኢትዮጵያውያን ላይ ፋሺሽታዊ ግፍ ተፈጸመ። ይህ ሁሉ ሲሆን የኦነግ እና የህወሃት ጽንፈኛ አክቲቪስቶች በማኅበራዊ ሚድያ ተሳለቁ። መንግስት እራሱ ሕግ ከማክበር ይልቅ ጥፋቱን ለመሸፈን ያወጣቸው መግለጫዎች የግፍ ግፍ የሚያሳዩ ሆኑ። 

በእነኝህ ሁሉ ግፎች ውስጥ መንግስት ማስተካከል ያለበትን ሳያስተካክል የኦነግ የጽንፍ ቡድን ሲነካ የሚያለቅሰው የኦፌኮው ጀዋር መሐመድ የጽንፍ ቡድኑ ስልጣን መያዙን ዳጎስ ባለ መግለጫ ጽፎ ሲበትን መንግስት ሊጠይቀው አልደፈረም።ከእዚህ ይልቅ አስተያየት ሰጡ፣ዜና አሰራጩ እየተባሉ የማኅበራዊ ሚድያ አሰራጮች እና ጋዜጠኞች ካለ ፍርድቤት ትዕዛዝ እየታፈኑ ተወስደው ሲለቀቁ ህዝብ ተመለከተ። መንግስት ገልብጠናል የእኛ የጽንፍ መንግስት ነው አሁን ያለው። ቀሪው ሥራችን ይህንን እንዴት እናጽናው ነው ብሎ የጻፈን የማይጠይቅ የመንግስት አሰራር እንዴት ታቦት ሊያነግስ በተሰበሰበ ህዝብ ላይ የተወረወረውን የአስለቃሽ ቦንብ የማውገዝ ድፍረት አጣ? የብዙዎች ጥያቄ ሆኖ ከረመ።

ይህ ሁሉ በእንዲህ እያለ በኦሮምያ የጽንፍ ቡድን የተደራጁ እና የኦሮሞ ሚድያ ኔትዎርክ ብቻ ሳይሆን በአቶ ሽመልስ የሚመራው የኦሮምያ ክልል የጸጥታ አካል ሙሉ ጥበቃ የተደረገለት እንዲሁም በመጀመርያ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጭምር የተሞገሰ (በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስህተታቸውን አርመው የማስታረቅ ደረጃ ቢሄዱበትም) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ለመክፈል የተደረገው የድፍረት የእርቀት ሂደት የኢትዮጵያን ህዝብ በተለይ የአማራ ክልልን ህዝብ በመንግስት ላይ ያለውን ተስፋ መቁረጥ ብቻ ሳይሆን የኦነግ የጽንፍ ቡድን የቱን ያህል ለመሄድ የድፍረት ድፍረት እንዳለው አሳየው። ''ይህንን ያህል ይባልጋሉም ሃይማኖትን ይደፍራሉ ብዬ አልጠበኩም" ያሉት አንድ ኢትዮጵያዊ የድርጊቱ እርቀት የኢትዮጵያን ህዝብ በመንግስት ላይ ያለውን ተስፋ መቁረጥ ግልጽ አደረገው። ሃገር ለሦስት ቀናት ጥቁር የለበሰበት እናቶች መሬት ተኝተው ያለቀሱበት እና ገዳማውያን እና የሙስሊም አባቶች ሳይቀሩ ወደ ፈጣሪያቸው በኦርቶዶክስ ላይ የተሰራውን ግፍ ያመለከቱበት ይህ ድርጊት በኦሮምያ ክልል ህገወጦቹ አብያተክርስቲያናትን ለመቆጣጠር ያደረጉት ሙከራ በተቃወመ ህዝብ ላይ በተወሰደ የግፍ እርምጃ ወጣቶች ህይወታቸው አጡ።

እነኝህ የቅርብ ጊዜ ድርጊቶች የአማራ ብሄርተኝነትን የሚጠላው እና ኢትዮጵያዊነት ብሎ የሚያስበውን የአማራ፣የደቡብ እና የሱማሌ ክልል እና ሌሎች ሳይቀሩ ከጎኑ በሃሳብ ደረጃ ማሰለፍ ቻለ። ይህ በራሱ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት ስብራት ነው። ሂደቱ የጽንፈኝነት መንገድ ከመሆን አልፎ አንዱ ከአንዱ የበለጠ ጽንፈኛ ለመሆን የሚጋጋጥበት መሆኑ በራሱ ሌላው አሳዛኝና ለኢትዮጵያ ምንም የማይፈይድ ክስተት መሆኑ ግልጽ ነው። ይህ ችግር ግን መንግስትም ሆነ የጽንፍ ኃይሎች ከስህተቶቻቸው ታርመው የማያስተካክሉት ጉዳይ ሊሆን አይችልም። 

መንግስት ሊያስተካክላቸው የሚገቡ ሦስት ጉዳዮች

መንግስት በመጀመርያ የጽንፈኝነት ሃሳብን ሌሎች ላይ እያላከከ በቃላት ከመጫወት በፊት ከጉያው ያሉትን የጽንፍ አስተሳሰብ ያላቸውን በሁሉም የቢሮክራሲ እና የጸጥታ አካላት ውስጥ ያሉትን ያስወጣ። ይህ የመጀመርያው መጀመርያ ይመስለኛል። ይህ ሳይደረግ ምንም ዓይነት ጽንፈኝነት የመዋጋት ስራ መስራት አይቻልም። ከእዚህ በፊት በጉዳያችን ላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ጽንፈኞች ይመጋገባሉ። ምንም ያህል በተቃራኔ ጎራ ቢሆኑ የአንዱ ፍም ለሌላው ደጋፊ ስለሚያስገኝ ተናበው ነው እሳቱን የሚያፋፍሙት።ስለሆነም ከውስጥ ያሉ ጽንፈኞች መንግስትን ወደየተሳሳተ የመረጃ ማመሳቀል እየወሰዱ እንዲደነብር በማድረግ ለግድያ እና ለእስር እንዲፈጥን በማድረግ ጠላት ያሉትን ብሔር ለማጥቃት ሲሰሩ መንግስት እራሱ በሕዝብ የተጠላ ያደርጉታል። ስለሆነም መንግስት ከውስጡ ያሉትን የጽንፍ አራማጆች እንደ የፖለቲካ ስልጣኑ መጠበቂያ ሚዛን የማየት የእብደት አስተሳሰቡን መተው አለበት።

ሁለተኛው ጉዳይ ስህተቶችን ማረም ነው። ከወለጋ እና ከሌሎች ቦታዎች የተፈናቀሉ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ሜዳ ላይ ወድቀው የአዲስ አበባ አስተዳደር መንገድ ላይ አንድ ጭልፋ ወጥ እያሳየ ድሆችን እረዳን ቢል ድርጊቱ ምን ያህል መልካም እና መሆን ያለበት ቢሆንም ከሌላ በኩል ያለውን ህመም የሚያይ ባለመኖሩ መፍትሄ አይሆንም። በዘንድሮው የትንሣዔ በዓል ዋዜማ ላይ የአሚኮ የክልል ቴሌቭዥን ከወለጋ የተፈናቀሉ በደሴ ዙርያ ገራዶ መጠለያ ጣቢያ ወደ አራት መቶ ሺህ የሚሆኑ የአማራ ክልል ተወላጆች ምግብ ካገኘን ወራት ተቆጠሩ የሚረዳን የለም ረሃብ ላይ ነን ብለው ሲናገሩ እና የደቡብ ወሎ የምግብ ዋስትና ሃላፊም ይህንኑ ምስክርነት ሲሰጡ ለህዝብ ተላልፏል። ይህንን ተከትሎ የተወሰደ እርምጃ ግን በየትኛውም ሚድያ ላይ አልታየም። ይህ ምን ማለት እንደሆነ የሚያውቀው የሚመለከተው ብቻ ሳይሆን የንግድ ማኅበረሰቡም ሆነ የዲይስፖራውም ማኅበረሰብን የሚመለከት ነው። አሁንም መንግስት እነኝህን ተፈናቃዮች ወደ ቦታቸው ለመመለስ ምን እያደረገ ነው? ከኦነግ ጋርም የሚደረገው ድርድር እንደወጡ ይቅሩ የማያስብል እና ኦነግ ሸኔም ይህንን መቀበል ካልፈለገ መንግስት በሕግ እንዴት ወደቀያቸው ሊመልስ ይፍለጋል? በእዚህ ዙርያ ላይ እነኝህ በኢትዮጵያዊነታቸው የተገፉ ግፏን ላይ አንዳች ሥራ እየተሰራ ለመሆኑ የሚጠቅስ አንድ ሪፖርት እንዴት ይጠፋል? ይህንን ከልብ እንደመንግስት መንግስት የደህንነታቸው ከለላ ባለመሆኑ የተሰደዱ ኢትዮጵያውያን ሃላፊነት በራሱ ላይ ነው የሚወድቀው።

ሦስተኛው ጉዳይ ብልጽግና እንደገና ከጎሳ ፖለቲካ በራቀ መልኩ መበወዝ እና አዳዲስ አዕምሮዎችን ወደ አመራራ ማምጣት አለበት። የብልጽግና የሰው ኃይል ምንጭ በጎሳ ፖለቲካ የታሸው ያው የኢህአዴግ የሰው ኃይል ነው። ይህ የሰው ኃይል አሁንም ከጎሳ እና ከክክልል አስተሳሰብ መራቅ አልቻለም። አንዳንዴ አብሮ ተሰፍቶ ያደገበት ስለሆነ ይህንን የጎሳ አስተሳሰብ ለመንቀል ይቸገራል።ስለሆነም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እንደሚናገሩት መደመርንና ኢትዮጵያዊነትን የሚይራምዱ ከሆነ በጎሳ ፖለቲካ የታሹ አስተሳሰቦች ብቻ ሳይሆን የክልል አወቃቀሮች፣የሕገመንግስቶ አንቀጾች እና ከላይ እስከታች ያሉ አመራሮች ከጎሰኝነት የጸዱ እና ሁሉን አቀፍ አመለካከት ተቀብለው ሌሎች ላይ ማስረጽ የሚችሉ መሆን አለባቸው። 

ባጠቃላይ የጎሰኝነት የጽንፍ አስተሳሰብ እያገነገነ እንዲመጣ ያደረገው የራሱ የመንግስት ደካማ አሰራር ብቻ ሳይሆን በጽንፈኞች መዋቅሩ ሲንገዳገድ አብሮ በመሞዳሞዱም ጭምር ነው። በአማራ አንጻር ያለውን የጽንፍ የጎሳ አስተሳሰብ የወለዱትም ይሄው የኦነግ እና የህወሃት የጽንፍ መንገድ ነው። ይህ ማለት ግን ምክንያቱም ምንም ይሁን ምን የጽንፍ የጎሳ አስተሳሰብ አማራ ጋር ሲሆን ትክክል ሌላው ጋር ሲሆን ኝ ኃጢአት ነው ማለት አይደለም። በየትኛውም መንገድ ቢከሰት የጽንፍ የጎሳ ፖለቲካ ኢትዮጵያን ከመበተን ያነሰ ነገር ይዞ አይመጣም። ችግሩን ለመፍታት ግን ቁልፉ አሁንም መንግስት ጋር ነው።መንግስት ሥራውን በትክክል ሲሰራ ሕዝብ በራሱ የጽንፈኝነትን ሰንኮፍ ከውስጡ እንዴት እንደሚነቅል ያውቅበታል።

==============/////=========




Thursday, April 20, 2023

በህወሓት አፍቃሪዎችና መዋቅር የሚዘወረው የአማራ እና የኦሮሞ ብሔርተኝነትና በ''ሪሞት'' እየዘወራቸው እንደሆነ የሚያውቁም፣ የማያውቁም በአንድ ጎዳና የመንጎድ ተውኔት።



=========
ጉዳያችን ምጥን
=========

የብሔርተኝነት አንዱ ገጽታ ከራሱ ብሔር ውስጥ የሚቃወሙትን ለመቀንጠስ ይሉኝታ የማይዘው ብቻ ሳይሆን ለማግለልም ሲውተረተር የሚገኝ ነው።''በሮማዊነት ከሆነ ከእኔ በላይ ሮማዊ'' አይደላችሁም እንዲል፣ዛሬ ደርሰው ፖለቲካ ሁሉ የአማራ ብሔርተኝነት፣ወይንም የኦሮሞ ትግል የሚል ትርክት በማውራት አድርገው የሚመለከቱ፣ ነገር ግን ማን ለምን ዓላማ እየነዳኝ ነው ብለው ማሰብ የማይችሉ ከዩቱብ ሚድያ እስከ መስጊድ እና አብያተ ክርስቲያናት ጭምር እነርሱ በጠፋባቸው የፖለቲካ ምህዋር ሌላውም እንዲገባ ሲደክሙ ይታያሉ።

ህወሓት በወታደራዊ መስክ ቢሸነፍም ሰንኮፍ የመከፋፈል እና በጥቅም የመግዛት ልምዱም ሆነ አቅሙ አሁንም ባለው መዋቅር እየሰራበት ነው። በህወሓት በኩል ያለው አዲሱ ክስተት ከወታደራዊ ሽንፈቱ በላይ የትግራይ ተወላጆች በብዙ መዋቅሩ እርግፍ አድርገው የተዉት እና በሰላም ለመኖር የሚፈልጉት ከቀደመው በበለጠ መበራከታቸው መዋቅሩ ከመንገዳገድ አልፎ የሚያርፍበት ማረፍያ ቅርንጫፍ እያጣ በማኅበራዊ መዋቅሮች ውስጥ ብቻ ለመሰግሰግ እየጣረ መሆኑ ነው።

በእዚህ ዘመን ማንም ማንንም አያታልለውም። በአማራ ብሔርተኝነት መዋቅር በማደራጀት ህወሓትን የማይነቅፉ ነገር ግን ዐቢይን እና መንግስትን (በሰሞኑ ክስተቶች ተጠቅሞ አሁን ወደ መከላከያም ተመንድጓል) የማጥላላት የፖለቲካ አጀንዳ የተሰጣቸው የህወሃት የቀድሞ አፍቃሪዎች ብቻ ሳይሆኑ በህወሃት የውጭ መዋቅር ውስጥ በስደተኛው መካከል ተሰግስገው ማኅበራዊ ሰላም ሲነሱ የነበሩ፣ዛሬ ተነስተው የአማራ ብሔርተኝነት አደራጅ እና ያዙኝ ልቀቁኝ ባዮች ሆኖ ማየት ያስደምማል። የሚገርመው የዋሁ እና ከእዚህ በፊት ፖለቲካ አይሽተተኝ የሚለው፣ውሎ እና አዳሩ መስጊድና አብያተክርስቲያናት የሆነ ሁሉ የህወሃት መዋቅሮች ቀድመው በቀረቡት በእዚሁ የማኅበራዊ መረብ ተለሳልሰው እየቀረቡ በብሔሩ ካልተደራጀ እና ሌላውን ካልራቀ በቀር አደጋ ላይ ነህ፣መጥፋትህ ነው፣ወዘተ በሚል የማስደንበርያ መንገድ በስራቸው እየኮለኮሉት ነው።

በመጀመርያ ደረጃ ይህ በመስጊድ እና አብያተክርስቲያናት የነበረ አካል ስለ ፖለቲካ በህወሃት/ኢህአዴግ ዘመን አልሰማም፣አላይም እኔ ስለሰማያዊ ህይወት ብቻ ነው የማውቀው ሲል ስለነበር፣ የሴራ ፖለቲከኞች አደረጃጀት እና እራሱ ህወሃት እንዴት ከርቀት ሆኖ በ''ሪሞት'' እንደሚነዳ አያውቅም። ስለሆነም በቅርቡ የሚያውቀው ጥሩ ያለው ሰው በዘረጋለት የጎሳ የአደረጃጀት መረብ ውስጥ ሆኖ ፖለቲከኝ እንደሆነ እየተነገረው እራሱን በራሱ እንዲያዝናና ይደረጋል። እዚህ ላይ የጥቅምም ጉዳይ ስለሚጨመርበት አንዳንዴ ይህ የጎሳ መዋቅር የህወሃት መሆኑ ቢሸተውም እንዳላወቀ እራሱን በመደለል የመውቅሩ ተጠቃሚ ከመሆን ባለፈ፣ህወሃትበኢትዮጵያ ላይ የዘራውን የጎሳ ፖለቲካ እንደ የተሻለ አድርጎ ለመስበክ ደፋር ምላስ ሊኖረው ሁሉ ይችላል።

ቀልዱ በእዚህ አያበቃም።በአማራ ብሔርተኝነት በኩል የተደራጀው ቡድን ያህል ደግሞ በኦሮሞ ብሔርተኝነት የተደራጀው አቀጣጣይ እና ከዋናው የብልጽግና አክራሪ የኦሮሞ ብሔርተኛ ቢሮክራሲ እና የጸጥታ አካል ጋር የሚናበበው ቡድን ደግሞ ከህወሓት ጋር እጅና ጓንት ሆኖ እየሰራ ያለ ነው።ይህ ቡድን በህወሃት ስር ሙሉ በሙሉ በገንዘብም በመዋቅር ድጋፍም የሚንቀሳቀስ የመኖሩን ያህል ከህወሃት ውጭ የሆነ በጋራ ግንኙነት ብቻ ህወሓትን የሚያገኝ አክራሪ እና ፍጹም የጥፋት ኃይልም በውስጡ ይዟል። በህወሓት ስር የሚንቀሳቀሰው ኦሮምኛ ተናጋሪ አንዳንድ የትግራይ ተወላጆችን ይዞ እና በኦሮምያ ያደጉ የአማራም ሆነ የኦሮሞ ተወላጆችን ያቀፈ ነው። የእዚህ ቡድን ተልዕኮ በአማራ ብሔርተኝነት ላይ የማጥላላት ሥራ ከመስራት ባለፈ የኦሮሞ ተወላጆችን የሚያስደነብሩ ሃሳቦች እያፈለቀ የህዝቦች ግንኙነት እንዲሻክር ከማኅበራዊ ሚድያ እስከ ታች ጠላ ቤት የሚሰራ መዋቅር ነው።እነኝህ ሁለት ቡድኖች እራሳቸውን አንዳንዴ ኦነግ ሸኔ በማድረግ ሌላ ጊዜ የብልጽግና የኦሮሞ ወኪል በመሆን የሚያተራምሱ ናቸው። አስገራሚው ጉዳይ ደግሞ ከኦነግሸኔ እና የብልጽግና ውስጥ ከተሰገሰገው ጽንፈኛ የኦሮሞ ብሔርተኛ ከሚያገኙት ሙገሳ ባለፈ፣አልፎ አልፎ በህወሃት ከሚዘወረው የአማራ ብሔርተኛ እንቅስቃሴ ቀንደኛ መሪዎች ጋር የሁሉም ቡድን አባላት ባላወቁት መስመር እየተገናኙ አንዱ ለአንዱ ቤንዚን የሚያርከፈክፉበትን መንገድ በገደምዳሜ እየተናበቡ ይሰራሉ።

ይህንን አጭር ምጥን ለማጠቃለል፣ የአማራም ሆነ የኦሮሞ ብሔርተኝነት እንዲያቀጣጥሉ የሚዘወሩ ቡድኖች ከባሕር ማዶ እስከ ሃገር ቤት እንዳሉ እና የወቅቱ አንዱ የችግራችን ምክንያቶች እንደሆኑ በማሳሰብ ነው።በውጭ ሃገር በተለይ የህወሓት ስውር መዋቅር ውስጥ የነበሩ ዛሬ ''እሳት ለብሰው እሳት ጎርሰው '' አማራ ሁሉ በኢትዮጵያዊነት ሳይሆን በብሔርተኝነት ተደራጅቶ መጀመርያ ዐብይና መንግስትን እና መከላከያን እንዲያጥላላ፣ህወሓትን እና ኦነግ ሸኔን ግን አልፎ አልፎ ለኮፍ አድርጎ እያለፈ እንዲሄድ የቤት ሥራ ተሰጥቷቸው እየከወኑት ነው። እስኪ ኦነግ ሸኔን የሚቃወሙበትን ድምጸት ልክ ዛሬ ዛሬ መከላከያን የሚነቅፉበትን ድምጽ ለኩበት።

ነገሩ ''ለማያውቅሽ ታጠኚ '' ነው። ዛሬ ማንንም ማታለል አይቻልም።የዋሆች ገራገር በመሰሏቸው እና በማኅበራዊ ሚድያም ሆነ በእምነት ዙርያ የሚያውቋቸው የህወሓት መዋቅር አስተባባሪ መሆናቸውን ያላወቁ በማያውቁት የብሔር መዋቅር እየተነዱ ነው።  በሴል መደራጀት፣ፖለቲካ በዙም ማውራት፣ተልዕኮ መቀበል ወዘተ ብርቃቸው ስለሆነ የሆነ ትልቅ ሥራ ለሃገር እየሰሩ እንደሆነ እንዲያስቡ ሲጣደፉ ያሳዝናሉ። የጉዳያችን ምክር አንድ እና አንድ ነው።ፖለቲካው የረቀቀበትን ደረጃ ካልገባን በደንብ ማን፣ምን እያለ ነው? ለምን? ብሎ ከመጠየቅ አንስቶ ዋና ማገናዘቢያችን (reference) መሆን የሚገባው ኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያዊነት ብቻ መሆኑን መረዳት ብልሕነት ነው። ሕሊናም፣ታሪክም፣ፈጣሪም የማያዝኑበት እና ካለው ሰውነት የማያወርደን ሁሉንም ጉዳይ ከኢትዮጵያዊነት አንጻር አይተን ስንሰራ ብቻ እና ብቻ ነው።ከእዚህ ውጪ አዎን! ስሜት የሚያቆስሉ የጽንፈኞች ድርጊት ከመንግስት መዋቅር ጀምሮ እስከ የተለያዩ ቡድኖች በተለይ አማራን ለይቶ የማጥቃት ሂደቶች የሉም ማለት አይደለም። ይህ ጥቃት ግን ዋና የጀርባ ግቡ ኢትዮጵያን የማጥቃት ግብ መሆኑን ላወቀ ሰው፣ነገ ለደቡቡ፣ለሱማሌው፣ለአፋሩና ለሌላውም የማይቀር መሆኑን ተረድቶ ለሙሉዋ ኢትዮጵያ በመቆም መፍትሄ ላይ መድረስ ይቻላል። ልጆቹና ሚስቱ እንዳይጠቁበት የፈለገ አስተዋይ አባወራ የግቢውን በር ብቻ በመጠበቅ እንደማያድን ያውቃል።ከእዚህ ይልቅ የመንደሩን ሰዎች በህብረት አስተባብሮ እንደሃገር የመጣውን ፈተና በመቋቋም መንደሩንም፣ግቢውንም፣ቤቱንም ሆነ ቤተሰቡን አብሮ ይጠብቃል። ተነጣጥለህ በጎሳ ፖለቲካ እንድትነከር የሚፈልጉ ሁሉ ነጣጥለው ሊበሉህ እና ሊያስበሉህ የሚፈልጉ መሆናቸውን ማወቅ እና እውቀትንም፣ጊዜንም ሆነ ሃብትን ከመባከን በጊዜ ማዳን ተገቢ ነው።
===============//////==========


Tuesday, April 11, 2023

ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከሰላም ውጪ ሌላ የምትሸከምበት ትከሻ የላትም። አሁን በአማራ ክልል ከመከላከያ ጋር የተፈጠረው ግጭት ተከትሎ ለተፈጠረው ችግር ሦስቱ አካላት መንግስት፣መከላከያ፣ልዩ ኃይልና ፋኖ መውሰድ ያለባቸው ፈጣን የመፍትሔ ተግባራት።


  • በዓለማችን ላይ የመፍረስ አደጋ የደረሰባቸው ሀገሮች የችግሩን አነሳስ ብንመለከት የመጀመርያው መጀመርያ በሀገር መከላከያ ላይ የሚተኮስ ተኩስ ነው።
  • መከላከያ አባትም ነው። ምን ቢከፋ፣ምን ቢያስከፋ፣ምን ቢማታ፣ምን ቢያጠፋ እና እየሰከረ ቢያስቸግር አባት ቁጣው በርዶ እስኪያዳምጥ ይጠበቃል እንጂ አባት አይደበደብም።ልጅ አባቱን ከደበደበ ቤቱን አፈረሰ ማለት ነው።

======
ጉዳያችን
======

ጦርነት እና ግጭት እንደውሃ ጠብታ ነው። ግጭቶች ሲጀመሩ በትንሽ እልህ መለዋወጥ በኋላ ይቆማሉ በሚል ዕሳቤ ትናንሽ ግጭቶች አቅልሎ የማየት እና ሃገር የሚያፈርሱ የማይመስሉት ሰው ቁጥሩ ቀላል አይደለም። ነገር ግን በዓለማችን ላይ የመፍረስ አደጋ የደረሰባቸው ሀገሮች የችግሩን አነሳስ ብንመለከት የመጀመርያው መጀመርያ በሀገር መከላከያ ላይ የሚተኮስ ተኩስ ነው።በሶርያም፣ሊብያም ሆነ የመን የሆነው ይሄው ነው። ስለሆነም ምንም ዓይነት ምክንያቶች ቢሰጡ መከላከያ መከላከያ ነው።መከላከያ ሀገር ነው።መከላከያ አባትም ነው። ምን ቢከፋ፣ምን ቢያስከፋ፣ምን ቢማታ፣ምን ቢያጠፋ አባት ቁጣው በርዶ እስኪያዳምጥ ይጠበቃል እንጂ አባት አይደበደብም። አባት እየሰከረ ቢያስቸግር ልጅ ተነስቶ አባቱን አይደበድብም። ልጅ አባቱን ከደበደበ ቤቱን አፈረሰ ማለት ነው።

አሁን በአማራ ክልል ከልዩ ኃይል ጋር ተያይዞ የተነሳው አለመግባባት  ፈጣን ምክንያቱ (immediate cause) የልዩ ኃይል ጉዳይ ይሁን እንጂ ዋና ምክንያቶቹ የብልጽግና ኦሮምያ በኢትዮጵያዊነት ላይ የጋረጠው ስጋት እና አደጋ እና የህዝብ ብሶት ነው። ይህንን ጠቅላይ ሚኒስትሩም ብልጽግናም ሆነ የመከላከያ ከፍተኛ አመራሮች የአማር ክልል ጉዳይ የልዩ ኃይል ጉዳይ ሳይሆን ከእዚህ ይልቅ ስጋት እና ብሶት የሚሉት ቃላት በሚገባ እንደሚገልጹት መረዳት አለባቸው። ስጋት እና ብሶት ተደምረው በመከላከያ ላይ ያሉ መተማመኖችን የብልጽግና የፖለቲካ አመራር እንዲሸረሸር አድርጎታል።በእዚህ ላይ መተማመን ከተደረሰ ሦስቱ ፈጣን መፍትሔዎች ላይ መንግስት፣መከላከያ እና የአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና ፋኖ በጋራ መስራት አለባቸው። መፍትሔዎች በመንግስት፣በመከላከያ እና በአማራ ክልል ልዩ ኃይልና ፋኖ መከናወን ያለባቸው ናቸው።

1) መንግስት 

በብልጽግና የሚመራው የአሁኑ መንግስት ያለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ስለኢትዮጵያ ብዙ ቢናገርም መሬት ላይ ያሳየው በተለይ ኢትዮጵያዊነትን በተመለከተ ደረጃ በትምሕርት ካሪኩለም፣መገናኛ ብዙኃን ስለ ኢትዮጵያ እንዲናገሩ በማድረግ፣ተቋማትን በኢትዮጵያዊነት ለመቃኘት እና የኢትዮጵያ የሆኑ ቅርሶችን መልሶ ለመስራት (ለምሣሌ የቤተመንግስት ሙዚየም) ጥረቶች ቢያሳይም በሌላ በኩል ደግሞ ከኢሃዴግ አስተዳደር በባሰ ደረጃ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ዕሴቶች ሲጎሳቆሉ የተመለከተ ብቻ ሳይሆን እጅግ አደገኛ ጸረ ኢትዮጵያ ሥራዎች በራሱ በብልጽግና መዋቅር ሲሰራ ሰንብቷል። ከእነዚህ ውስጥ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ በኢሃዴግ ዘመን ለምሣሌ በኦሮምያ ክልል ይውለበለብ የነበረበትን ያህል አሁን አይውለበለብም ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ያዛችሁ ተብለው የኢትዮጵያን እንጀራ በልቶ በሚያድር ፖሊስ ተደብድበዋል፣ታስረዋል ተንገላተዋል። ይህ ኢትዮጵያውያንን ሲያንገበግብ የሚኖር ብቻ ሳይሆን አሁን በአማር ክልል ለተነሳው ዓይነት ህዝባዊ አመጽ እንደሚያስነሳ ግልጽ ነበር። እዚህ ላይ የሰንደቅ ዓላማው ጉዳይ ቀላል የሚመስላቸው አንዳንድ ወገኖች ቢኖሩም የሚያመላክተው መልዕክት እና የኦሮምያ ብልጽግና ሊፈጥራት የሚፈልጋት ኢትዮጵያ ለብዙዎቻችን ግልጽ ያደረገ ቁልፍ ጉዳይ ነው።

ከእዚህ በተጨማሪ ሰዎች በአማራነታቸው እየተለዩ ከወለጋ እና ሌሎች ቦታዎች አዲስ አበባ ዙርያ እና አዲስ አበባ ጨምሮ ሲፈናቀሉ፣ሲገደሉ እና የተለያዩ ግፍ ሲፈጸምባቸው በተለያዩ የኦሮምያ ክልል የብልጽግና ባለስልጣናት ግልጽ ዘርና ታሪክን የሚያንቋሽሽ ንግግሮች ህዝብ አቁስለዋል ብቻ ሳይሆን ብልጽግና እየሄደበት ያለው ግልጽ እና የከረረ የጎሳ ፖለቲካ እንደሆነ የብዙ ህዝብ ድምዳሜ ነው። በመሆኑም መፍትሔው ይህንን ታሳቢ ያደረገ መሆን አለበት።

 መንግስት የሚከተሉትን ፈጣን የመፍትሔ እርምጃዎች መውሰድ አለበት።

1) መንግስት በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ከደብረብርሃን እስከ ባሕርዳር እና አዲስ አበባ የተበተኑት ከወለጋ እና ከተለያዩ ቦታዎች የተፈናቀሉ ወደ ቦታቸው እንዲመለሱ መንግስት በቅድምያ በልመና እና በችግር የተበተነው ቤተሰብ በቶሎ ድጋፍ እንዲደረግለት ጥሪ አድርጎ ሰብስቦ ይዞ የሚመለሱበትን መንገድ በቶሎ መጀመር፣ይህንንም የሚከታተለው የአደጋ እና ዝግጁነት ኮሚሽን በየጊዜው ሁኔታውን እያሳወቀ እንዲሰራ ማድረግ።

2) መንግግስት አሁን በአማራ ክልል ልዩ ኃይል እና ፋኖ ጋር በተያያዘ ከአማራ ክልል የሃገር ሽማግሌዎች፣ አማራ ብሔራዊ ንቅናቄና ሌሎች ህዝቡን ይወክላሉ ካላቸው ጋር በጠቅላይ ሚኒስትሩ ደረጃ ቁጭ ብለው መነጋገር እና አንድ ልዩ ኮሚቴ በጋር መስርቶ የመፍትሄ መንገዶች ማፈላለግ። በአማራ ክልል ያለው ህዝብ እንደየቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ ሁሉ ህግ የሚያክበር እና መንግስት የሚለው ተቋም ከሕግ ውጭ እስካልሆነበት ድረስ አክብሮ ለመኖር እንግዳ ህዝብ አይደለም። 

ይህንን መሰረታዊ የህዝብ ባህሪ መረዳት ብልህነት ነው።የኢትዮጵያ ህዝብ ከናቁት ይንቃል፣ካከበሩት ያከብራል።ሕግ ጥሶ ሕግ አክብር ከሚለው ይልቅ ሕግ ያከበረ ሲያገኝ መሬት ላይ ይነጠፋል። በእዚህ ጉዳይ የሚታማ ሕዝብ አይደለም። መንግስት ዘሎ በኃይል አስፈጽማለሁ ከማለት በፊት የህዝብን ባህሪ ማወቅ ጠቃሚ ይመስላል። ሁሉም ህዝብ ደግሞ የራሱ ባሕል እና አቀራረብ ዘይቤ አለው። ቤኒሻንጉል የራሱ ባህል አለው። አማራ ጋር ስትሄድ የራሱ ዕሴት የሚለው አለው። ኦሮሞው፣ ትግራይ ሁሉም የራሱ የባህል ዕሴቱ አቀራረቡን ሊቀርጸው ይችላል። ስለሆነም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከመተኮስ ይልቅ ወረድ ብለው የህዝቡን ተወካዮች  ማነጋገር አለባቸው።አሁን በሚታየው ሁኔታ ህዝብ ነው በከተሞች እየወጣ ያለው። ይህ ማለት ተወካዮችን ማናገር ህዝብን ማናገር ሲያንስ እንጂ የሚበዛ ጉዳይ አይደለም።

3) መንግስት ከኢህአዴግ የጎሳ የዘውግ ፖለቲካ የተለየ ለመሆኑ ጎሰኛ ፖለቲከኞቹን በሙሉ ከቢሮክራሲው ውስጥ እና ከክልል አስተዳደሮች ውስጥ በቶሎ መንጥሮ ማውጣት እና በትክክል የኢትዮጵያዊነትን ፖለቲካ ያስፍን። ኢትዮጵያ ለገጠማት ችግር ቢያንስ ዛሬ ላይ የመደመር መጽሐፍ በመድረክ ላይ መነገሩ እና መነበቡ ብቻ መፍትሔ አልሆነም። መጪው ትውልድ ሲደርስ አሁን ያለው የጎሳ ፖለቲካ ይቀየራል ብለው ለሚያስቡ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ እየዘነጉት የመጣው ዛሬ ከወለጋ የተሰደደው ታዳጊ ህጻን፣ዛሬ ዘሩ እየተለይ ከአዲስ አበባ ዙርይ የተፈናቀለው ወጣት ነገ የመደመር ትውልድ እንዴን ሊሆን ይችላል? ይህ ትውልድ እናቱ በዘር ተገፍታ መንገድ ዳር ስታለቅስ እያየ አድጎ መደመር ይቀበላል ብሎ ማሰብ ዘበት ነው። ስለሆነም አሁን ያለው ትውልድ መከላከያ ላይ ድንጋይ ሳይሆን ክላሽ መተኮስ የጀመረው በብልጽግና አካሄድ ተስፋ ስለቆረጠ ነው። አሁንም መንግስት የጎሳ ፖለቲካ ያዋጣኛል ካላለ በቀር በቢሮክራሲው የሰገሰጋቸውን የጎሳ ፖለቲካ አራማጆች በፍጥነት በተለይ ከኦሮምያ ክልል እና ከፌድራል ክልል ማስወጣት አለበት። የጎሰኝነት ችግሩ በእርግጥ በኦሮምያ ብቻ የሚታይ በሽታ እንዳልሆነ ሳይረሳ ማለት ነው።

መከላከያ ሊወስድ የሚገባው እርምጃ 

መከላከያ ሦስት ተግባራትን በፍጥነት ሊሰራ ይገባል።

1) መከላከያ የኢትዮጵያ የመንግስትም ሆነ የግል ሚድያዎችን በመጠቀም የሕዝብ ግንኙነት እንዲሰራ በተለይ ከሰሞኑ በልዩ ሁኔታ ሊፈቀድለት ይገባል።የግል ቴሌቭዥኖችም የመከላከያን የሕዝብ ግንኙነት ሥራዎች የማስተላለፍ ግዴታ ሊጣልባቸው ይገባል። የሕዝብ ግንኙነት ሥራውን እንዴት እንደሚሰራ ለመከላከያ ተዉለት። እንዴት እንደሚያቀርቡት ብቃት ያለው የሰው ኃይል መከላከያ አለው።

2) መከላከያ አሁን በአማራ ክልል ያለው ግጭት በቀናት ውስጥ እንደረገበ ሀገር አቀፍ መከላከያን የሚደግፍ እና ከመከላከያ ጎን ነኝ የሚል የድጋፍ ሰልፍ በሁሉም ክልሎች ከተሞች እና የገጠር ቦታዎች በምሽት መከላከያ ከገበሬው ጋር በጋራ ችቦ የሚያበራበት ልዩ ሰልፎች ማዘጋጀት እና አሁን ያለውን መንፈስ በፍጥነት መቀየር ይቻላል። ይህ ከጊዜ ጋር መሰራት ያለበት የሚያደርገው ደግሞ በማንኛውም ሰዓት እነኝህ ሥራዎች በፍትነት ሳይሰሩ የውጭ ወረራ አያጋጥምም የሚል የሞኝ ሃሳብ ሊኖር አይገባም። አሁን ያለንበት ዓለም ተለዋዋጭ ብቻ ሳይሆን በዓለም ላይ የሚነሱ ግጭቶች ከየት እንደሚነሱ ስለማይታወቅ እያንዳንዱ ኮሽታ ተጠቅመው ጠላቶቻችን አይጠቀሙበትም ማለት አይቻልም።

3) መከላከያ የኢትዮጵያን አጠቃላይ ጸጥታ በተመለከት የራሱን ''ሮድ ማፕ '' አዘጋጅቶ ያቅርብ በእዚህ መሰረት አፈጻጸሙን ህዝብ አሳትፎ እንዴት እንደሚፈጽም ከላይ በተሰጠው የመንግስት እና የግል ሚድያዎች ተጠቅሞ ይከውን። እዚህ ላይ መከላከያ በሳምን ሁለት ሳምንት የራሱ የጸጥታ ጉዳይን በተመለከተ የሚያቀርብበት የግማሽ ሰዓት የቴሌቭዥን እና ራድዮ መርሐግብር ሊኖረው ይችላል። አሁን ያለው የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን ማቅረብ ያለበትን በቀጥታ ከመከላከያ ወስዶ ሊያቅርብ ይችላል። እዚህ ላይ መከላከያ ለብቻው ተነጥሎ የእዚህ ያህል በጸጥታ ጉዳይ የሚያቀርብ ከሆነ የመንግስት ሚና ምንድነው? የሚል ጥያቄ ሊኖር ይችላል። ነገር ግን አሁን በኢትዮጵያ ካለው ሁኔታ አንጻር የጸጥታው ጉዳይ እስኪረጋገጥ ድረስ ለአንድ ዓመት ወይንም ለስድስት ወራት ይህ አካሄድ አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን ወቅታዊ ህመም የሚያክም ነው።

በልዩ ኃይሎች እና በአማራ ፋኖ አንጻር መወሰድ ያለበት የመፍትሔ እርምጃ 

1) በሁሉም ክልሎች ያሉ ልዩ ኃይሎች አመራሮች እና የታች መኮንኖች ጭምር ቢያንስ ለሳምንታት ያህል አብረው በአንድ የመዝናኛ ወይንም ቀንና ሌሊት አብረው የሚቆዩበት እና መደበኛ ያልሆነ የግንኙነት እና የመወያያ ጊዜ ያስፈልጋቸዋል። በማኅበራዊ ሚድያ እርስ በርስ እንዲፈራሩ የተደረገው ሥራ መፍረስ አለበት። ይህንን የጋራ ጊዜ ለምሳሌ መከላከያ ሚኒስቴር በሚኒስቴር መስርያ ቤቱ ወይንም ሌላ ምቹ ቦታ ወስዶ ማወያያት እና አብረው የጋራ ጊዜ እንዲያሳልፉ ማድረግ ይገባል።

2) ልዩ ኃይሎችም ሆኑ የአማራ ፋኖ መከላከያ የማይገሰስ ሀገራዊ የጋራ ኃይል መሆኑን በውድም በግድም የመቀበል ስነልቦና ማዳበር አለበት። ልዩ ኃይልም ሆነ ፋኖ የኢትዮጵያ መከላከያ ሳይሆኑ ድጋፍ ሰጪ ናቸው።

3) ልዩ ኃይል ወደ መከላከያ፣ፌድራል ፖሊስ፣ክልል ፖሊስ ወይንም ሰላማዊ ሕይወት መግባት ዛሬ ባይሆን ነገ፣ነገ ባይሆን ከነገ ወዲያ የማይቀር ነው።ይህንን ዝርዝር አሰራር ከላይ መንግስት መስራት ከሚገባው ሥራዎች ስር በተጠቀሰው መሰረት ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ሲነጋገሩ ዝርዝር ጉዳይ ላይ መነጋገር የሚከወን እንዲሆን መስራት።
በፋኖ አንጻር ግን በአማራ ክልል ፋኖ ማኅበራዊ እውቅና በክልል ደረጃ እንዲያገኙ መጠየቅ እና የአማራ ክልልም ማኅበራዊ ዕውቅና የሚሰጥበት አንድ ዓይነት መንገድ መፈለግ እና ቢያንስ የያዙት ትጥቅ ከማኅበራዊ ዕውቅና ጋር ሃላፊነት በተሰማ መልኩ ከግዴታ እና ውል ጋር እንዲፈቀድላቸው ቢደረግ ምንም ዓይነት ጉዳይ ለኢትዮጵያ ጸጥታ የሚያመጣው ችግር አይኖርም። ፋኖ ቢያንስ ኢትዮጵያ ቀውጢ በሆነችበት ጊዜ ህይወቱን ለመስጠት የቆመ ብቻ ሳይሆን ወደፊት እራሱ ባሕሉን ጠብቆ መኖር ኢትዮጵያን ከውጭ ጠላት ጭምር ለሚመጣ ጠላት መከላከያን የሚያግዝ ባሕላዊ ዕሴት በመሆኑ መጠበቅ ያለበት መሆኑን መንግስትንም፣መከላከያና የኢትዮጵያን ሕዝብ በፍቅር የማሳመን ሥራ በሁሉም ክልሎች ለመከወን መነሳት አለበት። አሁን ፋኖ ለሌላው ክልል የሚያስፈራ ተደርጎ እንዲቀርብ የተሳለው ስዕል ለአማራ ክልል ብቻ ጀግና መሆኑ ታውቆ እንዲቀር ባልሆነ ነበር። ችግሩ ያለው የምንመርጠው መንገድ አጠቃቀማችን ነው እንጂ ሁሉም የሚግባባት የጋራ መንገድ ከተፈለገ በርካታ መንገድ አለ።

ለማጠቃላል ኢትዮጵያ ከሰላም ሌላ መሸከም የምትችለው ሌላ ምንም ዓይነት ነገር የለም።አሁን ያለው ውጥረት በቶሎ መስተካክለ ይችላል። ጉዳዩ በማባባስ ሌላ ዙር ንትርክ ውስጥ ኢትዮጵያ በመግባቷ የተሻለ መንገድ ላይ ትገባለች ብለው የሚያስቡ ምን ያህል እንደተሳሳቱ የሚገባቸው ኢትዮጵያ በውስጧ እና በውጭ ያሉ ጠላቶቿ አሰላለፍ ማየት ያልቻሉ ናቸው። ከሰላም የአሁኑ ትውልድ ብቻ ሳይሆን መጪው ትውልድም ይጠቀማል። መንግስት ተሳስቷል፣አዎን ተሳስቷል። እንዲስተካከል መንግስትን በሰላማዊ መንገድ የማስገደድ ሥራ የሁሉም ዜጋ ሃላፊነት ነው። መከላከያን ተገዳድሮ የሚመጣ ለውጥ መጀመርያ በር ከፍቶ ብር የመቁጠር ያህል ነው። በሩን ከፍቶ ብር የሚቆጥር ሰው ሌባ ያልሆነ አላፊ አግዳሚም ይዘርፈዋል። የኢትዮጵያን ሰላም በማደፍረስ ኢትዮጵያ ወደየባሰ አዘቅት የማትገባ ብቻ ሳይሆን እንደእነ ሶርያ የማንሆን እንዳመስለንና እንዳንሳሳት። የሰላም አስፈላጊነት ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የስልጣን ዕድሜ አይደለም። ለኢትዮጵያ እና ለሁላችንም የጋራ ደህንነት ሰላምን በማደፍረስ ኢትዮጵያን ማንም እንደማይጠቅማት ማወቅ አለብን። ከላይ የተጠቀሱት በመንግስት፣በመከላከያ እና በልዩ ኃይሎች እና ፋኖ መሰራት ያለባቸው ሥራዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ መስራት እጅግ እጅግ አስፈላጊ ነው። ዓለማችን ካለችበት ተለዋዋጭ ጊዜ አንጻር ከሁለት ሳምንት በኋላ የሚሆነው አካባቢያዊና ዓለማቀፋዊ ሁኔታ ስለማይታወቅ ሁሉ ሥራ ከጊዜ ጋር ተሻምቶ መስተካከል ነው ያለበት።
==================////===========

The Ethiopian Orthodox Tewahedo Church is in turmoil in Athens, Greece.

His Holiness Abune Mathias I, Patriarch of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church, met with Greece's Ambassador to Ethiopia, Antonios Sg...