ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, April 30, 2016

ሰበር ዜና - በዴር ሱልጣን የሚገኘው የኢትዮጵያ ይዞታ ላይ ትናንት በስቅለት በዓል ወቅት ግብፆች ሁከት ለማንሳት ሞክረው ነበር ( Gudayachn exclusive)



ለጉዳያችን በደረሰ መረጃ መሰረት በኢየሩሳሌም ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት ጎልጎታ፣ ዴር ሱልጣን የሚገኘው የኢትዮጵያ ይዞታ ላይ ትናንት ሚያዝያ 29/2008 ዓም በስቅለት ዕለት ግብፆች በቦታው ይገባናል ሁከት ለማስነሳት ሞክረው ነበር።በስፍራው ለትንሣኤ በዓል የመጡ እና በእስራኤል የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ''አባቶቻችን ባቆዩት ቅርስ ላይ መቃብራችን እዚሁ ይሆናል'' ብለው የመጣውን ለመቀበል በዝግጅት ላይ እንዳሉ በመካከል የእስራኤል ፖሊስ ገብቶ ጉዳዩን ለማብረድ ችሏል።ግብፆች የእዚህ አይነቱን ግርግር በዴር ሱልጣን የኢትዮጵያ ይዞታ ላይ ሲፈፅሙ ይህ የመጀመርያ አይደለም።የዴር ሱልጣን ጉዳይ በሁሉም ወገኖች ትኩረት የሚሻ እና በተለይ በእስራኤል የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ገዳማቱን የማስከበር ኃላፊነታቸውን በተደራጀ መልክ መወጣት እንዳለባቸው የሁሉም እምነት ነው። 

ከእዚህ በታች የኢትዮጵያ ይዞታ የሆኑ ገዳማት በኢየሩሳሌም የሚገኙባቸውን ቦታዎች ለማወቅ ይረዳን ዘንድ ከቀሲስ ፋሲል ታደሰ ገፅ ላይ የተገኘውን ፅሁፍ  የገዳማቱን ቦታ የሚገልፀው ክፍል ብቻ እንደሚከተለው ቀርቧል።

የኢትዮጵያ ገዳማት በኢየሩሳሌም

የኢትዮጵያና የእስራኤል ግንኙነት በዘመነ ብሉይ በንግሥተ ሳባ ወደ ሰሎሞን በመሄዷ የተጀመረ መሆኑ የተረጋገጠ ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ሕዝበ ኢትዮጵያ ለበዓል /ሊሠግዱ/ ወደ ኢየሩሳሌም እየተጓዙ ኖረዋል፡፡ በመሆኑም ከዴር ሱልጣን ጀምሮ የኢትዮጵያ ቦታዎች አሏት፡፡ 

1.    ዴር ሱልጣን፡- ንግሥት ሳባ ከክ.ል በፊት በ1013 ዓመተ ዓለም ገደማ ኢየሩሳሌም ስትሄድ ሠራዊቷን እና ጓዟን ያሳረፈችበት ቦታ ነው፡፡ 1ኛ ነገ. 10፣ 2ኛ ዜና. 9÷1-9 ቀራንዮ (ጎልጎታ) አጠገብ ይገኛል፡፡ በተለያዩ የተንኮል ተግባራት ዋናውን ግብጻውያን የወሰዱት ሲሆን አሁን የአርባዕቱ እንስሳ እና የቅዱስ ሚካኤል ታቦታት የሚገኝበት ጠበብ ያሉ ቤተመቅደሶች እና በጥም ጠባብ የሆኑ የመነኮሳት ማደሪያዎች ይገኙበታል፡፡ 

2.   ቅዱስ ፊልጶስ፡- የኢትዮጵያ መንበረ ጵጵስና የሚገኝበት ሲሆን የገዳሙ ጽ/ቤት እና ኢትዮጵያዊውን ጀንደረባ ባጠመቀው በቅዱስ ፊልጶስ ስም ቤተክርስቲያን ይገኛል፡፡ በአፄ ዮሐንስ ትእዛዝ መ/ር ወልደሰማዕት በ1883 ዓ.ም የገዙት ቦታ ነው፡፡ 

3.   ደብረገነት ኪዳነምህረት፡- አሮጌ ከተማ ከሚባለው ውጪ በነቢያት መንገድ አጠገበት ትገኛለች፡፡ የመነኮሳት መኖሪያ የእንግዶች መቀበያ እና አዳራሽ በመግቢያዋ የሚገኝ ሰፋ ያለ ይዞታችን ሲሆን ወደ ገዳሙ የሚወስደው መግቢያ መንገድም “ርሆብ ኢትዮጵያ” ተብሎ ይጠራል፡፡  ቦታው በ1882 ዓ.ም አፄ ዮሐንስ በላኩት ወርቅ የተገዛ ሲሆን ሕንጻውን ያስፈጸሙት በ1885 ዓ.ም. አፄ ምኒልክ ናቸው፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ይዞታቸው በኢሩሳሌም ከተማ የሚገኙ ናቸው፡፡ 

4.   አቡነ ተክለሃይማኖት/አልአዛር/- በኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ 12ሺህ ሜትር ካሬ ስፋት ለው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ይዞታ ሲገኝ በጽድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት ስም ቤ/ክ ታንጿል፡፡  የኢትዮጵያን መካነ መቃብር በዚህ ይገኛል፡፡ አፄ ኃ/ሥላሴ ያስገዙት ቦታ ሲሆን በአቡነ ፊልጶስ ጊዜ በ1953 ዓ.ም. ተመሠረተ፡፡ 


5.   ቅድስት ሥላሴ፡- በዮርዳኖስ ወንዝ አጠገብ ከሩብ ጋሻ የማያንስ ቦታ ሲኖር የቅድስት ሥላሴ ቤተክርስቲያን ተሰርቷል፡፡ ነገር ግን በአረቦችና በእሥራኤል ጦርነት ምክንያት በአካባቢ ሰው ሊኖር ባለመቻሉ ታቦቱም መነኮሳቱም ተዘዋውረው በኢያሪኮ ይኖራሉ፡፡ ቤተክርስቲያኑ በ1925 ዓ.ም. በእቴጌ መነን የጠተሠራ እንደነበረ ይነገራል፡፡ 

6.   ቅዱስ ገብርኤል፡- በኢያሪኮ ከተማ ለብዙ ጊዜያት የአትክልት ቦታ ሆኖ የቆየው የኢትዮጵያ ይዞታ የቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ይገኝበታል፡፡ ቦታውን የሠጡት ወ/ሮ አማረች ዋለሉ በኋላ እማሆይ አማረች የተባሉ እናት በ1928 ዓ.ም ገዝተውት ለገዳሙ ሰጥተዋል፡፡ 

7.   ቤተልሔም፡- በምድረ ፍልስጥኤም ጌታችን ከተወለደበት ቦታ አጠገብ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ይገኛል፡፡ ቦታው ልዑል ራስ ካሣና ልዑል መኮንን ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጡ ያስገዙት ነው፡፡ 

                                                 
ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።