ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, February 21, 2015

ሰበር - እምነትን ከእምነት ጋር ማጋጨቱ ቀጥሏል፣በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ውስጥ 'የእሬቻ' በዓል እንደሚከበር ኢቢሲ መግለጡ ቁጣ ቀስቅሷል።



የአቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ አመታዊ ንግሥገዳሙ የሚገኝበት ተራራ ላይ ያለው ሀይቅ ዙርያ ታቦተ ሕጉ ሲዞር 

ባለፈው መስከረም 15/2007 ዓም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (በቀድሞ ስሙ ኢቲቪ) በአማርኛ እና በኦሮምኛ እንደተለቀቀው ዜና ከሆነ ''በመጪው መጋቢት ወር መጨረሻ ላይ የእሬቻ በዓል በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ውስጥ ይከበራል ''ይላል።ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ከተከበሩት እና ከታፈሩት ገዳማት ውስጥ አንዱ ነው።ገዳሙ ፃድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ከግብፅ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ለኢትዮጵያ እና ለመላው የሰው ዘር የፀለዩበት ቅዱስ ስፍራ ነው።

ይህንን ከ800 ዓመታት በላይ ፀንቶ የኖረ ገዳም ''እሬቻ'' እንዲከበርበት የተደረገበት ዋና ምክንያት እምነትን ከእምነት ለማጋጨት በስርዓቱ የተሸረበ ተንኮል ነው የሚሉ ብዙዎች ናቸው።ከእዚህ ቀደም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን መሰረተ እምነትን የጣሱ ተግባራት ሲፈፀሙ እና ሙስና የሚፈፅሙ የስርዓቱ አጎብዳጆች (በቤተ ክህነቱ ዙርያ 'የጨለማው ቡድን አባላት' በመባል የሚታወቁቱ)  የቤተ ክርስቲያኒቱን ንብረት  እና ገንዘብ መተዳደርያቸው ሲያደርጉት አንዳች እርምጃ ሳይወሰድባቸው አመታት መቆጠራቸው ይታወሳል።

በቅርቡም በርዕሰ አድባራት እንጦጦ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሙዚየም የወርቅ መስቀልን ጨምሮ ሌሎች በቅርስነት የተመዘገቡ ንብረቶች መጥፋታቸው ይታወሳል።ከእዚሁ ጋር ተያይዞ የደብሩ አስተዳዳሪ ቀደም ብለው ሰራተኞችን ሰብስበው ''በሙዚየሙ የሚገኙ ቅርሶች ተሸጠው ለአባይ ቦንድ መግዣ ይዋሉ'' የሚል ሃሳብ አቅርበው በደብሩ አገልጋዮች እና ሰራተኞች ''ታሪክ አጥፍተን ታሪክ አንሰራም'' የሚል ምላሽ እንደሰጧቸው የገለፀው የሪፖርተር ጋዜጣ ባለፈው ሮብ የካቲት11/2007 ዓም በዘገባው  ''የቤተ ክርስቲያኗ ካህናት፣ ሠራተኞችና የአካባቢው ነዋሪዎች የደብሩን አስተዳዳሪና ሌሎች ኃላፊዎች ተባብረው ወርቆቹን ማጥፋታቸውን፣ በቤተ ክርስቲያኗ ሠራተኞች ላይ በደልና ብልሹ አሠራር እንዲደርስ ማድረጋቸውን በመግለጽ ተቃውሟቸውን በፊርማ በተደገፈ አቤቱታ ለሚመለከታቸው ሁሉ መላካቸውን'' ይገልጣል። 

ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ላይ የእሬቻ በዓል እንዲከበርበት መገለፁን የዘገበው የማኅበረ ቅዱሳንድረ-ገፅ  በበኩሉ ጉዳዩን አስመልክተው አቡነ ማትያስ ለኦሮምያ ፕሬዝዳንት አቶ ሙክታር ከድር ደብዳቤ መፃፋቸውን ይገልጣል።

ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ታሪክ እና አመሰራረት 

የዝቋላ አቡ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም በ1168 ዓ.ም.ታላቁ ጻድቅ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ በነበሩበት ጊዜ ከግብጽ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ቅዱሳት በሆኑ እግሮቻቸው በመርገጥና በመባረክ በተራራው አናት ላይ በሚገኘው ውብና ማራኪ በሆነው ባሕር ውስጥ ለ1ዐዐ ዓመታት በመጸለይ ከዘለዓለማዊው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የማይታበል ሕያው ቃል ኪዳን የተቀበሉበት በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ በኋላ ጽላታቸው የተቀረጸበት ቤተክርስቲያናቸው የታነጸበት በክቡር ስማቸው ገዳም የተመሠረተበት አምላከ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ብርሃነ ረድኤቱን በየጊዜው የሚገልጥበት በሀገራችን ኢትዮጵያ አሉ ከሚባሉት ጥንታዊና ታሪካዊ ገዳማት አንዱ ነው፡፡

የደብረ ዝቋላ ገዳም ከተመሠረተ ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርነው የ835 ዓመት እድሜን ያስቆጠረ ታላቅ ገዳም ነው፡፡ የመጀመሪያው መሥራች በውስጡ ልዩ ልዩ ጸዋትወ መከራዎችን በመቀበል ገድላቸውን የፈጸሙበት ታላቁ ጻድቅ አቡ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሲሆኑ እርሣቸው በ14ዐዐ ዓመት ውስጥ በነበረውና በኢትዮጵያው ንጉሥ በአጼ ዳዊት ልጅ በሕዝበናኝ (እንድርያስ) ዘመነ መንግሥት ካረፉ በኋላ ንጉሡ ሕዝበናኝ (ሁለተኛ ስሙ እንድርያስ) በዚህ አምሳለ ደብረ ታቦር በተሰኘ፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የማይታበል ሕያው ቃል ኪዳን ከልዑል እግዚአብሔር በተቀበሉበት ተራራ ላይ በስማቸው ጽላት በማስቀረፅ ቤተክርስቲያን በማነጽ ገዳም እንዲመሠረት ካደረጉ በኋላ በሺህ የሚቆጠሩ መናንያን መነኮሳት በውስጡ ለዓለም ሰላም ለሕዝበ ክርስቲያን ይቅርታና ምሕረትን ከእግዚአብሔር እየለመኑ ትሩፋን እየሠሩ መንፈሳዊ አገልግሎትን እያገለገሉ እስከ ግራኝ ወረራ ድረስ ገዳሙን በማስፋፋት ቆይተዋል፡፡

ኋላም ግራኝ መሐመድ የኢትዮጵያን ገዳማትና አድባራት ባቃጠለና ባጠፋ ጊዜ ይህም ገዳም በግራኝ ወረራ መነኮሳቱ ተጨፍጭፈው አልቀዋል፣ ቤተክርስቲያኑም ተቃጥሏል፣ ገዳሙም ፈርሷል፡፡ ይሁን እንጂ ገዳሙ ዘወትር መንፈስ ቅዱስ የማይለየው እውነተኛ የቅዱሳን ቦታ በመሆኑ ሥራውን ባህታውያን ሳይለዩት እስከ ንጉሥ ማህለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ድረስ ለብዙ ዓመታት ያህል ጠፍ (ባዶ መሬት) ሆኖ ቆይቷል፡፡
የደብረ ዝቋላ ገዳምን መልክአ ምድር አቀማመጥ ከአየር ላይ ሲታይ  
በኋላም የንጉሥ ወሰን ሰገድ ልጅ የሆኑት ንጉሥ ሣህለ ሥላሴ የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ መካነ ገድል የሆነውን የዝቋላን ገዳም እንደገና አሳድሰው እንደ ቀድሞው የመንፈሳውያንና የመናንያን መነኮሳት መሰብሰቢያ አድርገው አቋቁመውታል፡፡ ከዚያም በኋላ አጼ ምኒልክ ለገዳሙ መናንያን መነኮሳት መተዳደሪያ ሰፊ ርስት ጉልት ከመስጠታቸውም በላይ የመንፈሳዊ መተዳደሪያ ሕግና ሥርዓቱንም በወቅቱ ከነበሩት መንፈሳውያን አባቶች ጋር ሆነው በመወሰን ያወጡት ሕግ የሚሻሻለው በቅዱስ ሲኖዶስ ተሻሽሎ እነሆ እስከ አሁን ያለው የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተክርስቲያንም አጼ ምኒልክ ያሠሩት ነው፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን አጼ ምኒልክ ለደብረ ዝቋላ ገዳም ብዙ መጻሕፍትና ንዋየ ቅድሳትን የሰጡ ሲሆን አስከ አሁንም በቅርስነት ተጠብቀው ይገኛሉ፡፡

የዝቋላ አቡ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም በታላቅ ተራራ ላይ የተመሠረተ ውብና ማራኪ የሆነ ምን ጊዜም ጸጋ እግዚአብሔር የማይለየውና ንጹህ ጤናማ አየር ያለው በአጠቃላይ ተፈጥሮ ያደለው እውነተኛ መካነ ቅዱሳን ነው፡፡ ወደዚህ ታላቅ ገዳም ለመድረስ ከአዲስ አበባ እስከ ዝቋላ ተራራ 82 ኪ.ሜ. ርዝመት ያለው ሲሆን የተራራው ርዝመት በመኪና መንገድ 9 ኪ.ሜ. ነው፡፡ በእግር ተራራው ብቻ ከ2 ሰዓት ተኩል እስከ 3 ሰዓት ያስኬዳል፡፡ ይሁን እንጂ የዝቋላ ተራራ ዙሪያውን በደን የተሸፈነ በመሆኑ ተራራውን ለመውጣት ጉዞ ሲጀምሩ ውብና ማራኪ የሆነው የደን መዓዛ፣ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ፣ የቅዱሳን ረድኤት ልብን እየመሰጠ ያለምንም ድካም ከተራራው አናት ላይ ያደርሳል፡፡

ከዚያም ታላቁ ጻድቅ አቡነ ገብረ መንፈስ ቀዱስ ለዓለም ሰላም ለኢተዮጵያ ምሕረትን በመለመን )/1ዐዐ ዓመት ሙሉ በውስጡ የጸለዩበትን ባህር ዙሪያውን ጥቅጥቅ ባለ የተፈጥሮ ደንና የባሕር ዛፍ አጣና በሚያካክል ቀጤማ ተከቦ ሲታይ ሰማያዊ ገነትን የሚያስታውስ ምድራዊ ገነት እውነተኛ የጽድቅ ቦታ ለመንፈሳውያን መኖሪያ የተፈጠረ መሆኑንና ታላቅነቱን ያስመሰክራል፡፡ በዚህም የሐይቅ ጸበል ብዙ ሕሙማን ከልዩ ልዩ ደዌያቸው ይፈወሱበታል፡፡
የዚህ ሐይቅ አቀማመጥ ከተራራው አናት ላይ እንደ ገበታ ወይም ሣህን በጎድጓዳ ቦታ ላይ ያለ ሆኖ ዙሪያው በደንና በቀጤማ የተከበበ ነው፡፡ እጅግ በጣም የሚያስደንቀው ይህ ባህር ባልታሰበ ጊዜ እንደ አምፖል ያለ ብርሃን በግምት ርዝመቱ ከ2 እስከ 3 ሜትር የሚደርስ በባህሩ መካከል ሲበራ ማየት በዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚኖሩ መነኮሳት የተለመደ ነው፡፡ 

የብርሃኑም ዓይነት ነጭ ሲሆን ይህ ከላይ የጠቀስነው ዓይነት ብርሃን በመካከሉ የሚቆም ሲሆን በቀጤማው ዙሪያ ደግሞ እንደ አምፖል ዓይነት ብርሃን ባህሩን ከቦት ለብዙ ሰዓት ይቆያል አንዳንድ ቀንም ሙሉ ሌሊቱን ሲያበራ የሚያድርበት ጊዜ አለ፤ ይህን ስንል ለአንባብያን ማመን ያስቸግር ይሆናል፡፡ ነገር ግን የሚጠራጠር ሁሉ በዝቋላ ገዳም ለጥቂት ቀን ከተቀመጠና እግዚአብሔር ከፈቀደለት አይቶ ማመን ይችላል፡፡


ከዚህ በላይ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን አስደናቂ ተአምርና የገዳሙን ይዘት በመጠኑ አቅርበናል፡፡ በዝቋላ አቡ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገደም በየዋሻውና በየጫካው ወድቀው ለዓለም ሰላምን ለሕዝበ ክርስቲያን ይቅርታና ምሕረትን ከልዑል እግዚአብሔር እየለመኑ የሚኖሩ ባህታውያን ያሉበት በብዙ የሚቆጠሩ አረጋውያን አባቶችና እናቶች እንዲሁም አቅመ ደካሞች የሚጦሩበት አምላከ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ብርሃነ ረድኤቱን ሁል ጊዜ የሚገልጥበት ታላቅ ገዳም ስለሆነ ምዕመናን በዚህ ቅዱስ ቦታ በመገኘት የቅዱሳንን በረከት በመቀበል የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የቃል ኪዳናቸው ተካፋይ ትሆኑ ዘንድ እያመላከትን ጽሁፋችንን በዚሁ እናጠቃልላለን፡፡


ጉዳያችን GUDAYACHN

የካቲት 14/2007 ዓም (ፈብሯሪ 21/2015)

የገዳሙ ታሪክ ምንጭ - የአዲስ አበባ ቅድስት ስላሴ ካቴድራል ድረ-ገፅ 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።