ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Saturday, February 28, 2015

«እኔ ሴት ነኝ ጦርነት አልወድም። ሆኖም 
ይህን ኢትዮጵያን የኢጣሊያ ጥገኛ የሚያድርግ ውል ከመቀበል 
ጦርነትን እመርጣለሁ» እቴጌ ጣይቱ





 ቅድመ የዓድዋ ድል(1885 እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር)

እንደ  አውሮፓውያኑ አቆጣጠር የካቲት 16/1885 ጀርመን በርሊን ከተማ በሚገኘው ውብ በሆነው የ ሀገሪቱ ቻንስለር ቬን ቢስማርክ ባለስልጣን መኖርያ ህንፃ ሳሎን ፌሽታ በ ፌሽታ ሆኗል።ሶስት ወር ሙሉ አሰልቺ ውይይት የተደረገበት ዋና ዋናዎቹ የ አውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ተሰብስበው '' አንተ ይሄን ያዝ አንተ በእዚህ ውረድ''ተባብለው የ አፍሪካ ካርታ  በመካከላቸው ተዘርግቶ ከወታደራዊ ዘመቻ በፊት አፍሪካን የተከፋፈሉባት ቀን ነበረች። በእዚህ ስብሰባ ከ80 በ መቶ በላይ የ አፍሪካ መሬት በ ሃሳብ መስመር እያሰመሩ ተከፋፈሉት። የበርልኑ''General act of Berlin conference''በ ታሪክ ባብዛኛው የሚታወቀው’'The division of Africa ''ወይንም ''scramble of Africa''(አፍሪካንየመቀራመትጉባኤ)ተብሎነው።በእዚህጉባኤላይጀርመን፣ኦስትሮሀንጋሪ፣ቤልጅየም፣ደንማርክ፣ፈረንሳይ፣ታላቅዋብሪታንያ፣ጣልያን ፣ኔዘርላንድ፣ፖርቱጋልን ጨምሮ የተገኙ ሲሆን ቅኝ ግዛትን ሕጋዊ ሽፋን ለመስጠት የተሞከረ ና በዚሁ መሰረት በ 1914 በ ፈረንጆቹ አቆጣጠር አብዛኛው የ አፍሪካ ግዛት በ ቅኝ ገዢዎች የወደቀበት ሁኔታ ነበር።

 ''ቀን እባብ ያየ   ምሽት ልጥ ይፈራል''

ጣልያን ከዚህ ስብሰባ ብዙ የተጠቀመች መሰላት።ቢያንስ ሀገራችንን ስትወር በ አፋርና ኢሳ (የአሁኑ ጅቡቲ) ከሰፈረው የ ፈረንሳይ ሰራዊትና ከ ግብፅ አስከ ሱዳን ከተዘረጋው ከ ብሪታንያ ቅኝ ግዛቶች ጋር አያተናኩልም ብላ አሰበች። የመስፋፋት ሕልሟንም ቀጠለች ።ዋናው  የጣሊያን የመስፋፋት ዘመቻ የመሰረት ድንጋይ የተጣለው አሰብ ላይ ነበር። ሩባቲኖ የተባለ የጣሊያን የመርከብ ድርጅት በወቅቱ የአሰብ ግዛት አስተዳደሪ ከነበሩት ሱልጣን ስፋት ያለው መሬት  በ9 ሺ ዶላር ገዛ። በሁዋላ ግን የጣሊያን መንግስት ወደ ተቀረው የኢትዮጵያ ክፍል ለመረማመጃነት እንደሚጠቀምበት በማመኑ፣ ከዚሁ ኩባንያ  መሬቱን በ43 ሺ ዶላር ገዛው(ይህ ግዢ ኢጣልያ በአድዋም ሆነ በ 1928 ዓም ኢትዮጵያን ለመውረር በርከፋች ከመሆኑም በላይ ለአካባቢው ችግር መዘዝ ደውል ተደርጎ ይጠቀሳል)።                                                                                                                        

ጣሊያንም አሰብን መያዝዋ እንደታወቀላት በቀጥታ አፍሪካን ለመቀራመት አላማ ካደረገው የበርሊን ጉባኤ እንድትሳተፍ ተደረገ።ይህ ብቻ አደለም ቅደም ብላ ጣልያን ምፅዋን ይዛ ስለነበር ከ ራስ አሉላ ጦር ጋር ተደጋጋሚ ውግያ ገጠማት።ለምሳሌ አንደፈረንጆቹ አቆጣጠር ጥር 26 /1887 ራስ አሉላ ''የ ኢትዮጵያ ድንበር ቀይ ባህር ነው ያለው'' በሚለው የፀና አምነታቸው ዶጋል ላይ ጣልያንን ሙሉ በሙሉ ድል አርገው መልሰውታል። የበርሊን ጉባኤ ተሳታፊ አገሮችም ጣሊያን ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት እንድትይዝ ፈቃድ የሰጡት ከዚህ ሁሉ ትንኮሳ በሁዋላ ነበር ።ዛሬ ብዙ ወገኖች በ ኢንቨስትመንት ስም ለ ባአዳን በሀገራችን ደቡባዊ ና ምራባዊ ክፍል የሚደረገውን ቅጥ ያጣ የ መሬት ሊዝ'' ኪራይ'' ይባል ''ውል'' በ ስጋት ቢያዩት አይፈረድባቸውም።በ ትክክልም ''በ ቀን እባብ ያየ በ ምሽት ልጥ ይፈራል'' እንዲሉ የ አሰብን ታሪክ ና ቀጥሎ የተከተለውን ያየ ተመሳሳይ ችግር ነገ አይመጣም ለማለት ዋስትና የለውም።                                         

''እግዚአብሄር ድንበር ይሁናችሁ ብሎ የሰጠንን ባህር እየተሻገረ እንደፍልፈል መሬት እየቆፈረ በመስፈር ላይ ነው''

የ ኢትዮጵያ ና ጣልያን ጦርነት ዋነኛ መነሻ የ ጣልያን የ ቅኝ ግዛት ጥማት ሲሆን እንደ ፈጣን ምክንያት  የሚጠቀሰው ግን የ ውጫሌ ውል አንቀፅ 17 ትርጉም ነው።የትርጉም ልዩነቱ ጉዳይ ሊታወቅ የቻለው እቴጌ ጣይቱ የውጫሌው ውል አንቀፅ 17 ላይ ዓለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ የተባሉት የጣልያንኛ ቋንቋ አዋቂ ዓፄ ምኒልክ በሰጧቸው ትዕዛዝ መሠረት የውሉን ሰነድ በመመርመር የውሉ አስራ ሰባተኛው አንቀፅ የያዘውን የትርጉም መዛባት በመግለፅ ጉዳዮ ኢትዮጵያ የምትጐዳበት ስለመለሆኑ ጭምር በማስረዳት በሰጡት ቃል ሲሆን እቴጌ በዚህ ወቅት ነገሮችን በጥንቃቄ የሚከታተሉ ስለነበር ዓፄ ምኒልክ በመጀመሪያ ሳይረዱ ዓለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ እንዲታሰሩ ቢያደርጉም እቴጌ ጣይቱ ግን እኒህ ሰው  ትክክለኛ የኢትዮጵያ ወዳጅ መሆናቸውን ለዓፄ ምኒልክ በማስረዳት ከሦስት ዓመታት እስራት በኋላ ማስፈታቸው ይታወቃል።

በዚህ በኩል ሲታይ እቴጌ ጣይቱ የምኒልክ የቅርብ አማካሪ በመሆን በፖለቲካ ተግባሮች ምን ያህል አስተዋፅኦ እንዳበረከቱ መገንዘብ ይቻላል። እቴጌ እንደተናገሩትም «ዓፅመ ጊዮርጊስ ቢታሰር ቢፈታም ለሀገሩ የሚገባውን ሠርቶ ነው። ኧረ ለመሆኑ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለውዮሴፍ፣ ጣሊያኖች በተንኮል ገብተው በማታለል ይህን የመሰለ ሥራ ሲሠሩ አነጋጋሪ ሆኖ ሳለ እንዴት ሳይስጠነቅቅዎ ቀረ?»በማለት የእቴጌ ጣይቱ የቁጣ መዓት ወደ ዮሴፍ ዞረ።ከዚያም ጨምረው «ከእንግዲህ ወዲህ የኢትዮጵያን ጥቅም የሚነካ፣ ሥር የሚነቅል፣ መሠረት የሚያፈርስ ጉዳዮን ሁሉ እኔ ሳላየው እንዳያልፍ ይፍቀዱልኝ» ብለው ለንጉሡ ባመለከቱት መሠረት ይኸው አንቺ ሳታይው ሳትመረምሪው አያልፍም በማለት ፈቀዱላቸው፣ይህ እንደሚያመለክተው እቴጌ ጣይቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የነበራቸውን ተገቢ ቦታ የሚያመለክት ነው። ውሉንም ለማስተካከል ዓፄ ምኒልክ ያደረጉት የዲፕሎማቲክ ጥረትው ጤታማ ሊሆን ባለመቻሉ ሚኒስትሮች የጦር አለቆችና መኳንንት የሚገኙበት ጉባዔ እንዲጠራ አደረጉ።

በአንቀጽ 17 ላይ የሰፈረው ስምምነት ኢትዮጵያን ሙሉ በሙሉ በጣሊያን ቅኝ ግዛት ውስጥ የሚያስገባ ነበር። ይህ አንቀጽ በአማርኛው ቅጅ ላይ የሚከተለውን አሰፍሯል “ኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት በምታደርግበት ጊዜ የጣሊያንን መንግስት እገዛ ከፈለገች ጣሊያን የኢትዮጵያን ፈቃድ ለመፈጸም ፈቃደኛ ነች።” ይሁን እንጅ በጣሊያንኛ ቁዋንቁዋ በተፈረመው ቅጅ ላይ ያለው ስሜት ከዚህ በተለየ ቀርቦአል “ኢትዮጵያ ማንኛውንም አይነት የውጭ ግንኙነት በጣሊያን መንግስት በኩል ታደርጋለች'' የሚል ትርጉም ይዞ ነበር።ይህም ቆይቶ ዓፄምኒልክ ከ አንግሊዝ መንግስት ጋር ሊያደርጉ ላሰቡት ግንኙነት በ ጣልያን በኩል ይምጡ መባላቸው ሲሰማ የ ውሉ ትርጉም ምንነት ለየለት።ይህ ብቻ አደለም የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር የነበረው ክርስፒ ግን ጉራና ንቀት በተሞላበት ሁኔታ ኢትዮጵያ ከዛሬ ጀምሮ በጣሊያን ስር ነች እያለ ከማወጅ በስተቀር ውሉን ለማስተካካል የሚያስችል እርምጃ አልወሰደም ነበር። ይባስ ብሎም ኤርትራን በመውረር የመጀመሪያዋ የጣሊያን ቅኝ ግዛት አገር ተመሰረተች ብሎ 1890ዓም አዋጅ አስነገረ። እንግሊዝም ሳትውል ሳታድር ጣሊያን ላቀረበችው ሀሳብ ድገፉዋን ሰጠች

የጣሊያንና የሌሎች መንግስታት ተንኮል ያበሳጫቸው አጼ ሚኒሊክ፣ ወዲያውኑ ከጀርመን፣ ከሩስያና ከቱርክ መንግስታት ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማጠንከር፣ ጣሊያንን ለመፋለም ወስነው ዝግጅት ጀመሩ። እንዲህም ሲሉ ለህዝባቸው ተናገሩ “ እግዚአብሄር በቸርነቱ ጠላቶቼን ድባቅ መትቶልኝ፣ ግዛቴንም አስፍቶልኝ፤ እስከዛሬ ድረስ አቆየኝ። በእግዚአብሄር ጸጋም ነግሻለሁ። ጠላት አገራችንን ለመውረር ሀይማኖታችንንም ለማስለወጥ ደጃፋችን ድረስ መጥቷል። እግዚአብሄር ድንበር ይሁናችሁ ብሎ የሰጠንን ባህር እየተሻገረ እንደፍልፈል መሬት እየቆፈረ በመስፈር ላይ ነው። ጉልበት ያለህ በ ጉልበትህ ጉልበት የለለህ በ ፀሎትህ አግዘኝ። ከዚህ ሌላ ወስልተህ የማገኝህ ግን ማርያምን አልምርህም''

  «እኔ ሴት ነኝ ጦርነት አልወድም። ሆኖም ይህን ኢትዮጵያን የኢጣሊያ ጥገኛ የሚያድርግ ውል ከመቀበል ጦርነትን እመርጣለሁ» እቴጌ ጣይቱ

ዳግማዊ ምኒሊክ እና ንግስት ጣይቱ እውነተኛ ፎቶ (ፎቶ አዲስ ጆርናል) 

ጣሊያን ከባዱን የአድዋ ጦርነት ከማካሄዷ በፊት በርካታ መለስተኛ የሆኑ ጦርነቶችን ከኢትዮጵያውያን ጋር ስታደርግ ቆይታለች። እነዚህ ጦርነቶች ግን ሁሌም በጀግኖቹ የኢትዮጵያ መሪዎች አሸናፊነት ይጠናቀቁ ነበር። በተለይ የራስ አሉላ ብልህ የጦር አመራር ና ብቃት ያለው ሰራዊታቸው ለ ጣልያኖች የ ውስጥ አግር  ፍም ሆኖባቸው ቆየ።

የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም በአፍሪካ ምድር ያልታየ አዲስ ታሪክ በኢትዮጵያ ምድር ተሰራ። እለቱ በኦሮቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ የቅዱስ ጊዮርጊስ ወርሀዊ በአል የሚከበርበት ቀን ነበር ። ሰማይ ከ መሬት ሳይለቅ ከ ለሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ገደማ ንጉሡ ና የ ጦር ሹማምቶቻቸው ከ አዲስ አበባ ድረስ አብሮ በመጣው የ አራዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦተ-ሕግ ዙርያ ከበው ቆመው የ ኪዳን ፀሎት በማረግ ላይ   ነብሩ።  በ መካከል የሚኒሊክ የመረጃ ክፍል የሆነ አንድ ወጣት እየተንደረደረ መጥቶ ለንጉስ ሚኒልክ ''ጌታየ “ባራቴሪ” ተኩስ ከፍታብናለችና ቶሎ ብለው አንድ ነገር ያድርጉ'' በማለት ሹክ ያላቸው ፣ በመቀጠል ከ መቅደሱ ውስጥ ለ አፄ ሚኒሊክ ና ሹማምንቱ '' የቀረውን ፀሎት እኛ እንፈፅመዋለን ሂዱ አይዟችሁ የ ኢትዮጵያ አምላክ ይከተላችሁ'' የሚል ቃል ተቀብለው ፣ መስቀል ተሳልመው ዘመናዊ መሳሪያ እስካፍንጫው የታጠቀውን የጠቅላይ ሚኒስትር ክርስፒን ጦር ለመግጠም ቤተክርስቲያኑዋን ለቀው ወጡ።

ማታ ነው ድሌ


ጣሊያን ጂኔራል ባራቴሪ ለተባለው የጦር መሪዋ የቀይ ንስር የተባለውን ከፍተኛ ወታደራዊ ማእረግ ሸልማ ላከች። ጄኔራሉ ከ20 ሺ በላይ የሚሆነውን ጦሩን ይዞ፣ የኢትዮጵያን ጦር ለመግጠም ጦሩን በሶስት ማእዘን አንቀሳቀሰ። በጄኔራል ዳቦር ሜዳ የሚመራው ጦር የበለሀ ተራሮችን በቀኝ በኩል አጥሮ እንዲይዝ፣ የጄኔራል አርሞንዲ ጦር ደግሞ በመሀል ሰንጥቆ እንዲገባ ታዘዘ። ጄኔራል አልቤርቶኒ በበኩሉ የኪዳነምህረት ታራራን እንዲቆጣጠር ትእዛዝ ቢሰጠውም፣ እንዳ ኪዳነምህርትና ኪዳነምህረት የሚባሉት ሁለቱ ቦታዎች ስለተምታቱበት፣ ከኪዳንምህረት ተራራ ሳይደርስ በሌላ ቦታ ላይ ሰፈረ በጄኔራል ኢሊና የሚመራው ጦር ደግሞ ከጀኔራል ባራቴሪ ጦር ጋር በመሆን በተጠባባቂነት እንደቀመጥ ተደለደለ:: 

ከ አንድመቶ ሺ የሚበልጡት የ ኢትዮጵያ ሰራዊት   በየጦር አበጋዞቻቸው ና ''ፋኖ ተሰማራ '' ብሎ ልጁን ቤተሰቡን ተሰናብቶ ተነቃነቀ።ጦርነቱን የተቀላቀለው ከ ሁሉም የሀገሪቱ ክፍል የተውጣጣው ጦር ውግያውን በየመጣበት ጠመደው።ድሉ ግን የማታ ማታ የ ኢትዮጵያ ሆነ። ጣልያኖች መሸሽ ጀመሩ። የንግሥት ጣይቱ በተመረጡ ወታደሮች ሥልታዊውን የ ጣልያኖች የ ውሃ ቦታ አስያዙ።ጣልያን ጀነራሏን በቁሙ አስማርካ በወቅቱ በ ምስራቅ አፍሪካ ከነበራት ከ ግማሽ በላይ የሚሆን ሰራዊቷን አጥታ ጦርነቱ ተጠናቀቀ።                                                                                                
ዶክተር ታደሰ ስለ ድሉ ሲገልፁ-
''በኢትዮጵያዊያን የጦር ሃይል ጥቅም ላይ የዋሉት ስትራቴጂዎች እና ታክቲኮች በንጉሰነገስቱ ዲፕሎማሲያዊ እና ወታደራዊ ክህሎት ላይ ብቻ የተመሰረቱ ሳይሆኑ በበርካታ ሺዎች በሚቆጠሩ አመታት በኢትዮጵያ የጎለበቱ ልዩ አስተሳሰቦች ላይም ጭምር የተመሰረቱ ነበሩ፡፡ እነዚህ አስተሳሰቦች በሌሎች የአለም ክፍሎች ትምህርት ከተወሰደባቸው ወታደራዊ ትምህርቶች ለየት ባሉ ሁኔታዎች የተፈጠሩ ነበሩ፡፡ ከዚህም ባሻገር እነዚህ የጦር ታክቲኮች እና ስትራቴጂዎች በሃገሪቱ ታሪክ እና መልክአ ምድራዊ አቀማመጥ ተንፀባርቀው ነበር፡፡ በዚህ አካሄድ የኢትዮጵያ ሃይሎች ጣሊያኖች ይጠብቁት ከነበረው አኳኃን በተለየ ደረጃ ላይ ይገኙ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት የአድዋ ጦርነት በቀጣይ ምእተ አመት በተለያዩ ወታደራዊ /ቤቶች የጥናት ርእስ ሆኗል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን የአድዋ ጦርነት ከተካሄደበት ጊዜ ጀምሮ ለረጅም ጊዜ የትኩረት ምንጭ ሆኖ ቆይቷል፡፡'' ብለዋል።
የ ድሉ ዜና በመላ ዓለም ተናኘ ። ጥቁር አፍርካውያን አውሮፓውያንን አሸነፉ የሚለው ዜና ጣልያንን ብቻ ሳይሆን በተዋበው ህንፃ ውስጥ አፍሪካን ለመቀራመት ተሰብስበው የነበሩ   
መንግስታትን ሁሉ 'ክው !' ያደረገ መራር ዜና ነበር።በወቅቱ የ ኒውዮርክ ታይምስ  ጋዜጣ በ  ሽፋኑ ላይ በ ያወጣው ዜና ርአስ''ITALY's TERRIBLE DEFEAT'' የጣልያን አስፈሪው ሽንፈት''ማለቱ አስፈሪነቱ ለ በርሊኑ ጉባኤተኞች ሁሉ ማለቱ ሳይሆን ይቀራል?

አድዋ ጦርነት ድል ተከትለው የመጡ ክስተቶች


የ አድዋ ድል በ ኢትዮጵያ ድል አድራጊነት መጠናቀቅ የሚከተሉትን ሁኔታዎች በ ሀገርውስጥም ሆነ በ ዓለም አቀፍ የ ዲፕሎማሲ መድረክ ላይ ተከስቷል;-

    በ ጥቅምት ወር ላይ ጣልያን ከ ኢትዮጵያ ጋር ''አዲስ አበባ ውል '' የተባለ አዲስ ውል ለመፈረም ተገዳለች፣

    በ አሜሪካ፣አፍሪካ ና በመላው ዓለም ያሉ ጥቁሮች ለመብታቸው ተነሳስተዋል፣

    እ.ኤ.አ. በ1903 ዊሊያም ሄንሪ የተባሉት አፍሪካ አሜሪካዊ የንግድ ስራ ዋነኛ አንቀሳቃሽ የሄይቲ ዜግነት ካላቸው ገጣሚ እና ተጓዥ ከሆኑት ቤኒቶ ሲልቪያን ጋር በመሆን ወደ ኢትዮጵያ መጡ፡፡አላማቸውም ንጉሰ ነገስት ሚኒሊክን ለመጎብኘት እና ከእርሳቸውም ጋር ለመተዋወቅ ነበር፣

    የኢትዮጵያን ነፃነት በአሜሪካ ለሚኖሩ ጥቁሮች እንደ ነፃነት ነፀብራቅ እና መሰረት በማየት ጋርቬይ በቂ ገንዘብ ለማሰባሰብ የሚያስችል የባህር ላይ የንግድ ስራ ለመመስረት አሰቡ፡፡ ከዚህም ሌላ ወደ አፍሪካ የሚመለሱ በርካታ አባላትን ለመመዝገብ አቀዱ፡፡ በጥቂት አመታት ውስጥ የጋርቬይ ማህበር ከሞላ ጎደል 10 ሚሊዮን ዶላር በማሰባሰብ እስከ ግማሽ ሚሊዮን የሚደርሱ አባላትን ለማቀፍ ችሏል፣

    ታዋቂ የሆነው የሲቪል መብቶች መሪ ማልኮም ኤክስ አባቱን ቄስ ኢያርል ሊትልን በመጥቀስ የሕይወት ታሪኩን መፃፍ ጀመረ፡፡ ለዚህም ምክንያት የሆነው አባቱ ከላይ የተጠቀሰው 'የዩናይትድ ኒግሮ ኢምፕሩቭመንት አሶሲየሽን' ከፍተኛ ደጋፊ ነበሩ፡፡ ማልኮም በዚህ ረገድ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥቷል፡- ‘አባቴ ወደ ጋርቬይ ማህበር ስብሰባዎች የሚወስደው እኔን ብቻ ነበር፡፡ እነዚህ ስብሰባዎች በተለያዩ ሰዎች ቤቶችበሚስጥር ይካሄዱ ነበር፡፡ አባቴም እኔን አንዳንድ ጊዜ ወደ እነዚህ ስብሰባዎች ይወስደኝ ነበር፡፡ “አፍሪካ ለአፍሪካውያን የሚለውን አባባል አስታውሳለሁ፣ ኢትዮጵያዊያን ተነሱ’ ማልኮን ከጋርቤይ የፓን አፍሪካ መልእክት ጋር የነበረው ቁርኝት እና ይህም መልእክት በንባብ፣ በፅሑፍ እና በታሪክ ራሱን ሲያስተምር እንደ መነሻ ምክንያት የሚጠቀምበት ነበር፡፡ ‘በከፍተኛ ደረጃ ያስደሰቱኝን የመጀመሪያዎቹን መፅሐፍት በሚገባ ማስታወስ እችላለሁ፡፡ ጄኤ ፕሮዘርስ በፃፋቸው ሶስት መፅሐፍት ጥቁር የነበረው ኤዞፕ ስለ ታላቋ የ ክርስቲያን ግዛት ማለትም ስለ ኢትዮጵያ ገልጸል፡፡ ይህችም ሃገር የጥቁርን ቀጣይ እድገት ያስመሰከረች የምድርን ረጅም እድሜ ያስቆጠረች ሃገር ናት'' ብሎላታል።

    የናይጄሪያው ናሜንዲ አዚኪዊ፣ የጋናው ኩዋሜ ንክሩማ እና የኬንያው ጆሞ ኬኒያታ በመጀመሪዎቹ የአፍሪካ ነፃነት እንቅስቃሴዎች እንዲሁም በምእራብ ኢንዲንስ ያሉ መሪዎች ማለትም ጆርጅ ፓድሞሬ እና ማርከስ ጋርቬ (ጀማይካ) በድሉ ከፍተኛ የተነሳሽነት ስሜት እንዲያድርባቸው ሆኗል፡፡


ዳግማዊ ምኒልክ በ ኢትዮጵያ ታሪክ ላይ የፈጠሩት በጎ ሁኔታዎች

ዳግማዊ ምኒልክ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ የፈጠሩት በጎ ሁኔታዎች ሁሉ ሲወሱ የሚኖሩ ናቸው።ሀገራችን ለመጀመርያ ጊዜ የ ሚንስትሮች ካቢኔ፣ስልክ፣ባቡር፣ሆቴል፣መኪና፣ ያየችው በ ዳግማዊ ምኒልክ ዘመን ነበር። ከሁሉ የሚገርሙኝ ግን ሁለት ነገሮች ናቸው።የመጀመርያው ዛሬ ተማሩ በሚባሉ ሰዎች ዘንድ ስለ አካባቢ ጥበቃ ለማስረዳት ብዙ ጊዜ የመፍጀቱን ያህል የ ዛሬ መቶ ዓመት በፊት የነበሩት ዳግማዊ ምኒልክ ለ ወደፊቱ ትውልድ የ አካባቢ ጥበቅ ልማት አስበው በሃርዛፍ ከ አውስትራልያ ድረስ ማስመጣታቸው ና አጀንዳ ብለው መነጋገራቸው ሲሆን ሁለተኛው በ 1988 አዲስ ዓለም ማርያም ሙዜም ስጎበኝ የ ሙዝየሙ አስጎብኚ የነገሩን ነገር ነው። ጉዳዩ አንዲህ ነው-

ዳግማዊ ምኒልክ አንድ ቀን ጠባቂዎቼ በደንብ ይጠብቁኝ አንደሆነ ና አንዳልሆነ ላረጋግጥ ብለው ሌሊት ጋቢ  ለብሰው ይወጣሉ። ግቢውን ሲዞሩ  ጠባቅያቸው ከሩቅ ያየውን ሰው ስላላወቀ ''ቁም!ቁም!'' ብሎ መሣርያውን ያቀባብላል። ምኒልክ ቀልድ ያሉት ነገር ስህተት መሆኑን አውቀው ባለማወቅ አንዳይተኮስባቸው '' አይዞህ ምኒልክ ነኝ....ጌታህ ነኝ አይዞህ....''ይሉታል። ጠባቂውም ከሩቅ ሆኖ ''በምን አውቃለሁ ምኒልክ ተኝቷል'' ይላቸዋል። ወደአርሱ ቀርበው ''ምኒልክ ነኝ አይዞህ ስራህን በደንብ መስራትህን ላይ ነው'' ይሉታል። ተባቅያቸው ይደነግጣል። ''አሁን ተኩሼ ቢሆን ጌታዬን ገድዬ ነበር'' ብሎ ላብ አጠመቀው። ቀጥሎ ግን ተናደደ አሳስተውኝ ቢሆንስ ብሎ ዱላውን አውጥቶ ሁለት ጊዜ መታቸው። ምኒልክ አየፎከሩ አንዴት አንተ ሲሉ ግቢውን ለቆ ወጣ። ጧት ግብር ተበልቶ። ዳግማዊ ምኒልክ ያን ጠባቂ አስጠሩት። በሰራው ሥራ ግዞት አንደማይቀርለት ገምቶ ከፊታቸው ቆመ። ሌሊት የሆነውን ሁሉ አስረድተው ለ ሹማምንቱ ፍረዱ አሉ። ሁሉም ተነስቶ '' ግማሹ አርባ ይገረፍ....ሌላው ይገደል....'' ብሎ ፈረደ። ዳግማዊ ምኒልክ ግን '' ምን አረገ ካለበት የሄድኩበት ሳለሁ ስራውን በሚገባ በሰራ ሰው ላይ ለምን ትፈርዳላችሁ?'' ብለው መሬት ሸልመው ሾሙት።'' አሉን የ ሙዝየሙ አስተዋዋቂ። ቀጥለውም ''የናንተ ዲሞክራሲ  ዱላ አደለም ተናገራችሁኝ ብሎ ፍዳ የሚያሳይ ነው። ያኔ ይህም ተደርግዋል።ይህ ሲፈፀም የነበሩ የ 96 ዓመት የአድሜ  ባለፀጋመኖራቸውን ነገሩን ።የዚህ አይነት ዲሞክራሲ ነበረ!

ጉዳያችን

2 comments:

Richo said...

minew bezemenu beneberku noro.
RICHO

Anonymous said...

Ejig analytical girum ye atsatsaf kihlot. Bertalin

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።