ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, February 4, 2021

መተማ ላይ ለኢትዮጵያ እና ለሰንደቅ ዓላማዋ የፈሰሰውን የአፄ ዮሐንስ 4ኛን ደም ለረገጡ ፍርዱ አይዘገይም!

ጉዳያችን/Gudayachn

ኢትዮጵያ ዛሬ ላይ የደረሰችው ብዙዎች መስዋዕት ከፍለውላት ነው።መስዋዕትነቱ ከተራ ገበሬ እስከ ነገስታቶቿ እራሳቸውን ሰጥተው፣ደማቸውን አፍስሰው እስካሁን አስጠብቀው አስረክበውናል።ለኢትዮጵያ ሰማዕት ከሆኑት ውስጥ አፄ ዮሐንስ አራተኛ አንዱ ናቸው።የሸገር ኤፍ ኤም ጋዜጠኛ እሸቴ አሰፋ ከሶስት ዓመታት በፊት የአፄ ዮሐንስን እረፍት አስመልክቶ በሰራው የራድዮ ፕሮግራም ላይ እንዲህ አለ -

''በ1881 ዓም የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት አፄ ዮሐንስ በወረራ መተማንና አልፎም እስከ ሳር ውሃ ተቆጣጥሮ የነበረውን የሱዳን ሰራዊት ለመዋጋት ወደ መተማ ዘመቱ፡፡አፄ ዮሐንስ ወደ መተማ ሰራዊታቸውን አስከትለው የሄዱት፣ ሰሃጢ ላይ ከጣሊያኖች ጋር የነበራቸውን ፍጥጫ ትተው ነው፡፡መጋቢት 1 ቀን ጠዋት ጦርነቱ ተጀመረ፡፡ አፄ ዮሐስን ራሳቸው እንደ አንደ አንድያ ወታደር ሆነው በጦር ግንባር ገብተው ተዋጉ፡፡በጦርነቱም የኢትዮጵያ ሠራዊት ድል ለማድረግ በተቃረበበትና የሱዳን ሠራዊት ከምሽጉ ወጥቶ ለመሸሽ በተዘጋጀበት ወቅት አፄ ዮሐንስ እጃቸው ላይ ቆሰሉ፡፡ ቢሆንም ከጦርነቱ መካከል አልወጡም፡፡እንደገና በግራ እጃቸው አልፋ ወደ ደረታቸው የዘለቀች ጥይት መታቻቸው፡፡ አጃቢዎቻቸው ወደ ድንኳናቸው ወሰዷቸው፡፡

አፄ ዮሐንስ በመቁሰላቸው ምክንያት በማግስቱ መጋቢት 2፣ 1881 ዓ.ም አረፉ፡፡የኢትዮጵያኖቹን መሸሽ ያየው የሱዳን ሰራዊት እግር በግር እየተከታተለ ማጥቃቱን ቀጠለ፡፡የአፄ ዮሐንስን አስከሬን ድንኳንም ከበበው፡፡ታላላቅ የጦር መኮንኖቻቸውና በርካታ ታማኝ ሰራዊታቸውም የጌታችንን አስክሬን አናስማርክም እያሉ ፅኑ ውጊያ አደረጉ፡፡ብዙዎችም በአስክሬናቸው ዙሪያ ረገፉ፡፡በመጨረሻ የደርቡሽ ጦር ድል አድርጐ፣ የአፄ ዮሐንስን አስክሬን ማረከ፡፡ አንገታቸውንም ቆርጦ ካርቱም ገበያ ላይ አዞሩት፡፡የአፄ ዮሐንስ ሰራዊት የሞተው ሞቶ የተማረከው ተማርኮ የቀረው ወደ ደጋው አፈገፈገ፡፡ምንም እንኳ አፄ ዮሐንስ ሞተው ሰራዊቶቻቸው ተበታትኖ ደርቡሾች ጊዚያዊ ድል ቢያገኙም የኢትዮጵያን መሬት ይዘው ለመቆየት አልቻሉም፡፡

አፄ ዮሐንስ አንገታቸውን የሰጡላት ኢትዮጵያም በነፃነት እስከ አሁን ኖራለች፡፡'' አሰፋ እሸቴ ሸገር ራድዮ መጋቢት 2፣2009 ዓም 


ይህ ዓመት አፄ ዮሐንስ ለኢትዮጵያ ክብር እና ለሰንደቅ ዓላማዋ ከተሰዉ 132 ዓመታቸው ነው።አሁን ባለንበት ዘመን የኢትዮጵያ ፍቅር ሳይሆን የድርጅት ፍቅር ያሰከራቸው የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አደባባይ ክደው የህወሓትን ዓርማ እንደ የሀገር ዓርማ ይዘው በእየአደባባዩ የሚሰለፉት ለኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ደማቸው የፈሰሰውን የአፄ ዮሐንስን ደም የረገጡ ናቸው።ይህ ብቻ አይደለም ኢትዮጵያን ከመካድ በላይ የአፄ ዮሐንስን አንገት ቆርጠው ካርቱም ላይ ካዞሩት ጋር ወግነው ኢትዮጵያን ለመውጋት ሲያደቡ ማየት ምን ዓይነት ክህደት በኢትዮጵያ ላይ እየተፈፀመ እንደሆነ ያመላክታል።

የአፄ ዮሐንስ ደም ላይ የሚረማመዱቱ የዛሬዎቹ ቅምጥሎች በኢትዮጵያ የጦር ሰራዊት ላይ የእልቂት ድግስ ደግሶ ጥቅምት 24/2013 ዓም በተኛበት ሊፈጀው የሞከረውን እና ኢትዮጵያን ለባዕዳን አሳልፎ ለመስጠት የተደራደረውን ህወሓት በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀይረው ኢትዮጵያን በዓለም አደባባይ ይሰድቧት ይዘዋል።ለነገሩ ፊታቸው ያብለጨለጨው፣ባዕዳንም ያከበሯቸው ለዘመናት አባቶቻቸው በተሰዉላት ሰንደቅ ዓላማ ነበር።ዛሬ በአደባባይ ክደዋት ''ኢትዮጵያዊ አይደለንም'' እያሉ ተዘባበቱባት እንጂ። ''ከተራበ ለጠገበ አዝናለሁ'' እንዲሉ አሁን በእየውጭ ሀገሩ የአፄ ዮሐንስን ደም የነጠበባትን ሰንደቅ ዓላማ እየጣሉ የድርጅት ጨርቅ ይዘው የሚንገላወዱት እና ህዝብን ለማታለል የሚሞክሩት በትግራይ ሕዝብ ስም በመነገድ ነው።በየትኛውም የዓለም ክፍል ጦርነት ካለ ረሃብ እና የህዝብ መፈናቀል ይከተላል።ይህ የሚያሳዝን ታሪክ ነው።በትግራይ የደረሰውም ረሃብም ሆነ የህዝብ መፈናቀል ያሳዝናል።የኢትዮጵያ ሕዝብም ሆነ መንግስት ቀን ከሌት ተረባርቦ አስፈላጊው ዕርዳታ እንዲደርስ እያደረገ ነው።በኢትዮጵያ ሕዝብ ገንዘብ ወደ ውጪ የሄዱት ኢትዮጵያን መካዳቸውን በአደባባይ የተናገሩቱ ግን አንዲት ሳንቲም ለትግራይ ሕዝብ ስልኩ አልታዩም።ይልቁንም አፄ ዮሐንስ የሞቱላትን ሰንደቅ ዓላማ  ክደው የፈሰሰውን ደማቸውን ሲረግጡ እየታዩ ነው። መተማ ላይ ለኢትዮጵያ እና ለሰንደቅ ዓላማዋ የፈሰሰውን የአፄ ዮሐንስ 4ኛን ደም ለረገጡ ፍርዱ አይዘገይም! 
=====================///=============
ድምፃዊ ፀሐዬ ዮሐንስ ኢትዮጵያ!


============
ማስታወቂያ 
============
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 

አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

 

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።