የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ ክልሎችን እና የምርጫ ጣቢያዎችን በመላው ሀገሪቱ እንዲያቋቁም በአዋጅ ቁጥር 1133/2011 አንቀፅ 7 ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ በዚህ መሠረት የተቋቋሙ የምርጫ ክልሎች በአዋጅ ቁጥር 1162/2011 አንቀጽ 14 መሠረት አንድ የምርጫ ክልል ቦርዱ በሚያወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፦የምርጫ ቁሳቁሶችን ለምርጫ ጣቢያዎች ያሰራጫል፣ ዕጩዎችን ይመዘግባል፣ መስፈርቱን ለሚያሟሉ ዕጩዎች የመታወቂያ ካርድ ይሰጣል።
በያዝነው ዓመት እንደሚደረግ የሚጠበቀው የኢትዮጵያ ምርጫ አሁን እየተጠበቀ ያለው የጊዜ ሰሌዳው ነው።ምናልባት ከምርጫው በፊት መንግስት የህዝብ ቆጠራ ማድረግ ይችላል ወይ? የሚሉ ጥያቄዎች እዚህም እዚያም ይነሳሉ።በተለይ የህዝብ ቆጠራ ለማድረግም ሆነ ምርጫውን ለማድረግ አብዛኛው ዝግጅቶች በመጠናቀቃቸው ሁለቱንም በአንድ ዓመት ሊያከናውን ቢያስብ ይችላል።የሚሉ የመኖራቸውን ያህል አሁን ምርጫው ላይ ነው በቀዳሚነት ማተኮር ያለበት የሚሉ ሃሳቦች የሚሰጡም አሉ።
ምርጫው በእዚህ ዓመት መደረግ እንዳለበት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይም ምርጫውን ማድረግ አስፈላጊ መሆኑ ላይ በቅርቡም ደግመው ተናግረዋል።አሁን ጥያቄው አዲሱ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳ እና ዋናው የምርጫ ጊዜ መቼ ቢሆን ይሻላል? የሚለው ጥያቄ ነው። አንዳንድ ጊዜ የሚወሰኑት የጊዜ ሰሌዳዎች የህዝቡን ማኅበራዊ ጉዳዮች ያላገናዘቡ መሆናቸው በራሱ ችግር ስለሚፈጥር ከአሁኑ ጥንቃቄ የሚፈልግ መሆኑን ካለፈው ምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መቀየር መረዳት ይገባል።ለምሳሌ ባለፈው የጊዜ ሰሌዳ በኮቪድ ምክንያት ከመቀየሩ በፊት መጀመርያ ነሐሴ የመጀመርያ ሳምንት ውስጥ ሆኖ በኃላ ወቅቱ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተከታዮች የፆም እና ሱባኤ ወቅት መሆኑ ተገልጦ በማኅበራዊ ሚድያ ተቃውሞ ከተሰማ በኃላ ወደ ነሐሴ ሶስተኛ ሳምንት መዞሩ ይታወሳል።በመጪው ምርጫ ላይም ታሳቢ የሚሆኑ ጉዳዮች ከአሁኑ ቀድሞ መጠቆሙ አስፈላጊ ያደርገዋል።
የዘንድሮው ምርጫ መቼ ይሁን? ለቀኑ መመረጥ ሶስቱ ምክንያቶች
የዘንድሮው ምርጫ ወደ ክረምቱ ባይገባ፣ከግንቦት የመጀመርያ ሳምንት ባይቀድም ነገር ግን በግንቦት ወር አጋማሽ የተሻለ ጊዜ ይመስላል።ምክንያቶቹ ሶስት ናቸው። እነርሱም -
1) በመጪው ክረምት ኢትዮጵያ የዓባይን ግድብ የምትሞላበት ጊዜ ነው።ይህ ጊዜ ደግሞ ካለፈው ዓመት ተሞክሮ እንደምንማረው የግብፅ ብቻ ሳይሆን የእርሷ ደጋፊዎች የሆኑ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ጫና የሚበዛበት ነው።ስለሆነም ኢትዮጵያ ምርጫዋን በጊዜ አጠናቃ ወደ ውሃ ሙሌቱ መሄዱ ከውስጥ ጥንካሬ አንፃር አስፈላጊ ነው።
2) ሚያዝያ 24/2013 ዓም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የትንሣኤ በዓል ነው።ይህ ማለት ከበዓሉ በፊት ያለው ሳምንት የሰሞነ ሕማማት ሳምንት ነው።ይህ ማለት በኢትዮጵያ በርካታ ከተሞች እና ገጠሮች ብዙ ሕዝብ በነቃ ሁኔታ የማይሳተፍበት ሁኔታ አለ ማለ ትነው ።
3) ግንቦት 5/2013 ዓም የኢትዮጵያ እስልምና ዕምነት ተከታዮች የረመዳን ፆም የሚፈታበት ጊዜ ነው።በመሆኑም ከግንቦት 5 በፊት ያለው አንድ ወር የፆም ወቅት በመሆኑ አሁንም በርካታ ኢትዮጵያውያን በእዚህ ወቅት በተገቢ መልክ በምርጫው ሂደት ሊሳተፉ አይችሉም ማለት ነው።
No comments:
Post a Comment