ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, February 29, 2012

በ ታሪክ ''ጢቢ ጢቢ'' መጫወት እና መዘዙ -የአድዋ ድል/ victory of Adwa.


አሜሪካኖቹ ስለ ሃገራቸው ቀደም ስላሉት አመታት ሲናገሩ(ስለ ሁለት መቶ አመት ታሪክ ቢሆንም) የሚጠቀሙበት አንዲት ብሂል አለቻቸው።'' መስራች አባቶቻችን'' የምትል።ስለ ህገ መንግስታቸውም ሆነ ስለ የነፃነት ቀን ሲያወሱ ''መስራች አባቶቻችን'' የምትለው ቃል አትለያቸውም።አውሮፓውያንም ተመሳሳይ ሁኔታ ይጋራሉ።ህገ መንግስታቸው ከረቀቀ  ከመቶ ዓመታት  በላይ የሆናቸው በየዘመኑ አንዳንድ ማሻሻያ ከማድረግ በላይ መሰረቱን ሳያናጉት ይሄው ዛሬም አሉ።ለዚህም ሳይሆን አይቀርም ብዙዎች የአውሮፓ ሃገራት ምክር ቤቶች የመጀመርያውን ምክር ቤት ወይንም ፓርላማ መስራችዋን ሀገር እንግሊዝን ጨምሮ ስፍራቸውን ሳይቀይሩ የመስራች አባቶቻቸውን በማሰብ ቀደምቶቻቸው በሰሩት ህንፃዎች አሁን ድረስ የሚገለገሉት ።የካቲት 23/2004 ዓም (ማርች 2 /2012) የዓድዋ ድል አንድ መቶ አስራ ስድስተኛ ዓመቱ ታስቦ ይውላል። ዘንድሮ ደግሞ ብዙ ወጣቶች ታሪኩ በሚገባ ለትውልድ መተላለፍ አለበት ብለው ከሃገር ውጭ ባሉ ከተሞች እንደሚከበር እይተወሳ ነው።ጥሩ ጅማሮ ነው።በርቱ ማለት ደግሞ ጤናማ ና ኃላፊነት የሚሰማው ሰው ሁሉ  አስተሳሰብ ነው።
ቅድመ  የ ዓድዋ ድል  (1885 እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር)
እንደ  አውሮፓውያኑ አቆጣጠር የካቲት 16 /1885 ጀርመን በርሊን ከተማ በሚገኘው ውብ በሆነው የ ሀገሪቱ ቻንስለር ቬን ቢስማርክ ባለስልጣን መኖርያ ህንፃ ሳሎን ፌሽታ በ ፌሽታ ሆኗል።ሶስት ወር ሙሉ አሰልቺ ውይይት የተደረገበት ዋና ዋናዎቹ የ አውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ተሰብስበው '' አንተ ይሄን ያዝ አንተ በእዚህ ውረድ''ተባብለው የ አፍሪካ ካርታ እንደምግብ በመካከላቸው ተዘርግቶ ከወታደራዊ ዘመቻ በፊት አፍሪካን የተከፋፈሉባት ቀን ነበረች። በ እዚህ ስብሰባ ከ 80 በ መቶ በላይ የ አፍሪካ መሬት በ ሃሳብ መስመር እያሰመሩ ተከፋፈሉት። የ በርልኑ ''General act of Berlin conference '' በ ታሪክ ባብዛኛው የሚታወቀው '' The division of Africa '' ወይንም ''scramble of Africa'' (አፍሪካን የ መቀራመት ጉባኤ) ተብሎ ነው ።በ እዚህ ጉባኤ ላይ ጀርመን፣ኦስትሮ-ሀንጋሪ፣ቤልጅየም፣ደንማርክ፣ፈረንሳይ፣ታላቅዋ ብሪታንያ፣ጣልያን ፣ኔዘርላንድ፣ፖርቱጋልን ጨምሮ የተገኙ ሲሆን ቅኝ ግዛትን ሕጋዊ ሽፋን ለመስጠት የተሞከረ ና በዚሁ መሰረት በ 1914 በ ፈረንጆቹ አቆጣጠር አብዛኛው የ አፍሪካ ግዛት በ ቅኝ ገዢዎች የወደቀበት ሁኔታ ነበር።
''ቀን እባብ ያየ  በ ምሽት ልጥ ይፈራል''
                                                                                  
''የኛዋ'' ጣልያን ከዚህ ስብሰባ ብዙ የተጠቀመች መሰላት።ቢያንስ ሀገራችንን ስትወር በ አፋርና ኢሳ (የ አሁኑ ጅቡቲ) ከሰፈረው የ ፈረንሳይ ሰራዊትና ከ ግብፅ አስከ ሱዳን ከተዘረጋው ከ ብሪታንያ ቅኝ ግዛቶች ጋር አያተናኮለም ብላ አሰበች። የመስፋፋት ሕልሟንም ቀጠለች ።ዋናው  የጣሊያን የመስፋፋት ዘመቻ የመሰረት ድንጋይ የተጣለው አሰብ ላይ ነበር ሩባቲኖ የተባለ የጣሊያን የመርከብ ድርጅት በወቅቱ የአሰብ ግዛት አስተዳደሪ ከነበሩት ሱልጣን ስፋት ያለው መሬት  9 ዶላር ገዛ። በሁዋላ ግን የጣሊያን መንግስት ወደ ተቀረው የኢትዮጵያ ክፍል ለመረማመጃነት እንደሚጠቀምበት በማመኑ፣ ከዚሁ ኩባንያ  መሬቱን 43 ዶላር ገዛው                                                                                                                        
                                                                                                           
                                                                     ዳግማዊ ምኒልክ
ጣሊያንም አሰብን መያዙዋ እንደታወቀላት በቀጥታ አፍሪካን ለመቀራመት አላማ ካደረገው የበርሊን ጉባኤ እንድትሳተፍ ተደረገ።ይህ ብቻ አደለም ቅደም ብላ ጣልያን ምፅዋን ይዛ ስለነበር ከ ራስ አሉላ ጦር ጋር ተደጋጋሚ ውግያ ገጠማት።ለምሳሌ አንደፈረንጆቹ አቆጣጠር ጥር 26 /1887 ራስ አሉላ ''የ ኢትዮጵያ ድንበር ቀይ ባህር ነው ያለው'' በሚለው የፀና አምነታቸው ዶጋል ላይ ጣልያንን ሙሉ በሙሉ ድል አርገው መልሰውታል። የ በርሊን ጉባኤ ተሳታፊ አገሮችም ጣሊያን ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት እንድትይዝ ፈቃድ የሰጡት ከዚህ ሁሉ ትንኮሳ በሁዋላ ነበር ዛሬ ብዙ ወገኖች በ ኢንቨስትመንት ስም ለ ባአዳን በሀገራችን ደቡባዊ ና ምራባዊ ክፍል የሚደረገውን ቅጥ ያጣ የ መሬት ሊዝ'' ኪራይ'' ይባል ''ውል'' በ ስጋት ቢያዩት አይፈረድባቸውም።በ ትክክልም ''በ ቀን እባብ ያየ በ ምሽት ልጥ ይፈራል'' እንዲሉ የ አሰብን ታሪክ ና ቀጥሎ የተከተለውን ያየ ተመሳሳይ ችግር ነገ አይመጣም ለማለት ዋስትና የለውም።    
                                                      
''እግዚአብሄር ድንበር ይሁናችሁ ብሎ    የሰጠንን
ባህር እየተሻገረ እንደፍልፈል መሬት  እየቆፈረ በመስፈር ላይ ነው''
የ ኢትዮጵያ ና ጣልያን ጦርነት ዋነኛ መነሻ የ ጣልያን የ ቅኝ ግዛት ጥማት ሲሆን እንደ ፈጣን ምክንያት የሚጠቀሰው ግን የ ውጫሌ ውል አንቀፅ 17 ትርጉም ነው።የትርጉም ልዩነቱ ጉዳይ ሊታወቅ የቻለው እቴጌ ጣይቱ የውጫሌው ውል አንቀፅ 17 ላይ ዓለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ የተባሉት የጣልያንኛ ቋንቋ አዋቂ ዓፄ ምኒልክ በሰጧቸው ትዕዛዝ መሠረት የውሉን ሰነድ በመመርመር የውሉ አስራ ሰባተኛው አንቀፅ የያዘውን የትርጉም መዛባት በመግለፅ ጉዳዮ ኢትዮጵያ የምትጐዳበት ስለመለሆኑ ጭምር በማስረዳት በሰጡት ቃል ሲሆን እቴጌ በዚህ ወቅት ነገሮችን በጥንቃቄ የሚከታተሉ ስለነበር ዓፄ ምኒልክ በመጀመሪያ ሳይረዱ ዓለቃ ዓፅመ ጊዮርጊስ እንዲታሰሩ ቢያደርጉም እቴጌ ጣይቱ ግን እኒህ ሰው  ትክክለኛ የኢትዮጵያ ወዳጅ መሆናቸውን ለዓፄ ምኒልክ በማስረዳት ከሦስት ዓመታት እስራት በኋላ ማስፈታቸው ይታወቃል።

በዚህ በኩል ሲታይ እቴጌ ጣይቱ የምኒልክ የቅርብ አማካሪ በመሆን በፖለቲካ ተግባሮች ምን ያህል አስተዋፅኦ እንዳበረከቱ መገንዘብ ይቻላል። እቴጌ እንደተናገሩትም «ዓፅመ ጊዮርጊስ ቢታሰር ቢፈታም ለሀገሩ የሚገባውን ሠርቶ ነው። ኧረ ለመሆኑ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚለውዮሴፍ፣ ጣሊያኖች በተንኮል ገብተው በማታለል ይህን የመሰለ ሥራ ሲሠሩ አነጋጋሪ ሆኖ ሳለ እንዴት ሳይስጠነቅቅዎ ቀረ?»በማለት የእቴጌ ጣይቱ የቁጣ መዓት ወደ ዮሴፍ ዞረ።ከዚያም ጨምረው «ከእንግዲህ ወዲህ የኢትዮጵያን ጥቅም የሚነካ፣ ሥር የሚነቅል፣ መሠረት የሚያፈርስ ጉዳዮን ሁሉ እኔ ሳላየው እንዳያልፍ ይፍቀዱልኝ» ብለው ለንጉሡ ባመለከቱት መሠረት ይኸው አንቺ ሳታይው ሳትመረምሪው አያልፍም በማለት ፈቀዱላቸው፣ይህ እንደሚያመለክተው እቴጌ ጣይቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የነበራቸውን ተገቢ ቦታ የሚያመለክት ነው። ውሉንም ለማስተካከል ዓፄ ምኒልክ ያደረጉት የዲፕሎማቲክ ጥረትው ጤታማ ሊሆን ባለመቻሉ ሚኒስትሮች የጦር አለቆችና መኳንንት የሚገኙበት ጉባዔ እንዲጠራ አደረጉ።
በአንቀጽ 17 ላይ የሰፈረው ስምምነት ኢትዮጵያን ሙሉ በሙሉ በጣሊያን ቅኝ ግዛት ውስጥ የሚያስገባ ነበር። ይህ አንቀጽ በአማርኛው ቅጅ ላይ የሚከተለውን አሰፍሯልኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት በምታደርግበት ጊዜ የጣሊያንን መንግስት እገዛ ከፈለገች ጣሊያን የኢትዮጵያን ፈቃድ ለመፈጸም ፈቃደኛ ነች።ይሁን እንጅ በጣሊያንኛ ቁዋንቁዋ በተፈረመው ቅጅ ላይ ያለው ስሜት ከዚህ በተለየ ቀርቦአልኢትዮጵያ ማንኛውንም አይነት የውጭ ግንኙነት በጣሊያን መንግስት በኩል ታደርጋለች'' የሚል ትርጉም ይዞ ነበር።ይህም ቆይቶ ዓፄምኒልክ ከ አንግሊዝ መንግስት ጋር ሊያደርጉ ላሰቡት ግንኙነት በ ጣልያን በኩል ይምጡ መባላቸው ሲሰማ የ ውሉ ትርጉም ምንነት ለየለት።ይህ ብቻ አደለም የጣሊያን ጠቅላይ ሚኒስትር የነበረው ክርስፒ ግን ጉራና ንቀት በተሞላበት ሁኔታ ኢትዮጵያ ከዛሬ ጀምሮ በጣሊያን ስር ነች እያለ ከማወጅ በስተቀር ውሉን ለማስተካካል የሚያስችል እርምጃ አልወሰደም ነበር። ይባስ ብሎም ኤርትራን በመውረር የመጀመሪያዋ የጣሊያን ቅኝ ግዛት አገር ተመሰረተች ብሎ 1890ዓም አዋጅ አስነገረ። እንግሊዝም ሳትውል ሳታድር ጣሊያን ላቀረበችው ሀሳብ ድገፉዋን ሰጠች

የጣሊያንና የሌሎች መንግስታት ተንኮል ያበሳጫቸው አጼ ሚኒሊክ፣ ወዲያውኑ ከጀርመን፣ ከሩስያና ከቱርክ መንግስታት ጋር ያላቸውን ግንኙነት በማጠንከር፣ ጣሊያንን ለመፋለም ወስነው ዝግጅት ጀመሩ። እንዲህም ሲሉ ለህዝባቸው ተናገሩእግዚአብሄር በቸርነቱ ጠላቶቼን ድባቅ መትቶልኝ፣ ግዛቴንም አስፍቶልኝ፤ እስከዛሬ ድረስ አቆየኝ። በእግዚአብሄር ጸጋም ነግሻለሁ። ጠላት አገራችንን ለመውረር ሀይማኖታችንንም ለማስለወጥ ደጃፋችን ድረስ መጥቷል። እግዚአብሄር ድንበር ይሁናችሁ ብሎ የሰጠንን ባህር እየተሻገረ እንደፍልፈል መሬት እየቆፈረ በመስፈር ላይ ነው። ጉልበት ያለህ በ ጉልበትህ ጉልበት የለለህ በ ፀሎትህ አግዘኝ። ከዚህ ሌላ ወስልተህ የማገኝህ ግን ማርያምን አልምርህም''

የ አድዋ ጦርነት የተካሄደባቸው ተራሮች

«እኔ ሴት ነኝ ጦርነት አልወድም። ሆኖም
ይህን ኢትዮጵያን የኢጣሊያ ጥገኛ የሚያድርግ ውል ከመቀበል
ጦርነትን እመርጣለሁ» እቴጌ ጣይቱ

ጣሊያን ከባዱን የአድዋ ጦርነት ከማካሄዷ በፊት በርካታ መለስተኛ የሆኑ ጦርነቶችን ከኢትዮጵያውያን ጋር ስታደርግ ቆይታለች። እነዚህ ጦርነቶች ግን ሁሌም በጀግኖቹ የኢትዮጵያ መሪዎች አሸናፊነት ይጠናቀቁ ነበር። በተለይ የራስ አሉላ ብልህ የጦር አመራር ና ብቃት ያለው ሰራዊታቸው ለ ጣልያኖች የ ውስጥ አግር  ፍም ሆኖባቸው ቆየ።
የካቲት 23 ቀን 1888 . የዛሬ 116 አመት መሆኑ ነው፣ በአፍሪካ ምድር ያልታየ አዲስ ታሪክ በኢትዮጵያ ምድር ተሰራ። እለቱ በኦሮቶዶክስ እምነት ተከታዮች ዘንድ የፈረሰኛው ቅዱስ ጊዮርጊስ ወርሀዊ በአል የሚከበርበት ቀን ነበር ። ሰማይ ከ መሬት ሳይለቅ ከ ለሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ገደማ ንጉሡ ና የ ጦር ሹማምቶቻቸው ከ አዲስ አበባ ድረስ አብሮ በመጣው የ አራዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦተ-ሕግ ዙርያ ከበው ቆመው የ ኪዳን ፀሎት በማረግ ላይ   ነብሩ።  በ መካከል የሚኒሊክ የመረጃ ክፍል የሆነ አንድ ወጣት እየተንደረደረ መጥቶ ለንጉስ ሚኒልክ ''ጌታየባራቴሪተኩስ ከፍታብናለችና ቶሎ ብለው አንድ ነገር ያድርጉ'' በማለት ሹክ ያላቸው በመቀጠል ከ መቅደሱ ውስጥ ለ አፄ ሚኒሊክ ና ሹማምንቱ '' የቀረውን ፀሎት እኛ እንፈፅመዋለን ሂዱ አይዟችሁ የ ኢትዮጵያ አምላክ ይከተላችሁ'' የሚል ቃል ተቀብለው ፣ መስቀል ተሳልመው ዘመናዊ መሳሪያ እስካፍንጫው የታጠቀውን የጠቅላይ ሚኒስትር ክርስፒን ጦር ለመግጠም ቤተክርስቲያኑዋን ለቀው ወጡ።
ማታ ነው ድሌ
ጣሊያን ጂኔራል ባራቴሪ ለተባለው የጦር መሪዋ የቀይ ንስር የተባለውን ከፍተኛ ወታደራዊ ማእረግ ሸልማ ላከች ጄኔራሉ 20 በላይ የሚሆነውን ጦሩን ይዞ፣ የኢትዮጵያን ጦር ለመግጠም ጦሩን በሶስት ማእዘን አንቀሳቀሰ። በጄኔራል ዳቦር ሜዳ የሚመራው ጦር የበለሀ ተራሮችን በቀኝ በኩል አጥሮ እንዲይዝ፣ የጄኔራል አርሞንዲ ጦር ደግሞ በመሀል ሰንጥቆ እንዲገባ ታዘዘ። ጄኔራል አልቤርቶኒ በበኩሉ የኪዳነምህረት ታራራን እንዲቆጣጠር ትእዛዝ ቢሰጠውም፣ እንዳ ኪዳነምህርትና ኪዳነምህረት የሚባሉት ሁለቱ ቦታዎች ስለተምታቱበት፣ ከኪዳንምህረት ተራራ ሳይደርስ በሌላ ቦታ ላይ ሰፈረ በጄኔራል ኢሊና የሚመራው ጦር ደግሞ ከጀኔራል ባራቴሪ ጦር ጋር በመሆን በተጠባባቂነት እንደቀመጥ ተደለደለ::

ከ አንድመቶ ሺ የምበልጡት የ ኢትዮጵያ ሰራዊት   በየጦር አበጋዞቻቸው ና ''ፋኖ ተሰማራ '' ብሎ ልጁን ቤተሰቡን ተሰናብቶ ተነቃነቀ።ጦርነቱን የተቀላቀለው ከ ሁሉም የሀገሪቱ ክፍል የተውጣጣው ጦር ውግያውን በየመጣበት ጠመደው።ድሉ ግን የማታ ማታ የ ኢትዮጵያ ሆነ። ጣልያኖች መሸሽ ጀመሩ። የ ንግሥት ጣይቱ በተመረጡ ወታደሮች ሥልታዊውን የ ጣልያኖች የ ውሃ ቦታ አስያዙ።ጣልያን ጀነራሏን በቁሙ አስማርካ በወቅቱ በ ምስራቅ አፍሪካ ከነበራት ከ ግማሽ በላይ የሚሆን ሰራዊቷን አጥታ ጦርነቱ ተጠናቀቀ።                                                                                                
                                                                                                                            
    ዶክተር ታደሰ ስለ ድሉ ሲገልፁ ''በኢትዮጵያዊያን የጦር ሃይል ጥቅም ላይ የዋሉት ስትራቴጂዎች እና ታክቲኮች በንጉሰነገስቱ ዲፕሎማሲያዊ እና ወታደራዊ ክህሎት ላይ ብቻ የተመሰረቱ ሳይሆኑ በበርካታ ሺዎች በሚቆጠሩ አመታት በኢትዮጵያ የጎለበቱ ልዩ አስተሳሰቦች ላይም ጭምር የተመሰረቱ ነበሩ፡፡ እነዚህ አስተሳሰቦች በሌሎች የአለም ክፍሎች ትምህርት ከተወሰደባቸው ወታደራዊ ትምህርቶች ለየት ባሉ ሁኔታዎች የተፈጠሩ ነበሩ፡፡ ከዚህም ባሻገር እነዚህ የጦር ታክቲኮች እና ስትራቴጂዎች በሃገሪቱ ታሪክ እና መልክአ ምድራዊ አቀማመጥ ተንፀባርቀው ነበር፡፡ በዚህ አካሄድ የኢትዮጵያ ሃይሎች ጣሊያኖች ይጠብቁት ከነበረው አኳኃን በተለየ ደረጃ ላይ ይገኙ ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት የአድዋ ጦርነት በቀጣይ ምእተ አመት በተለያዩ ወታደራዊ ት/ቤቶች የጥናት ርእስ ሆኗል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን የአድዋ ጦርነት ከተካሄደበት ጊዜ ጀምሮ ለረጅም ጊዜ የትኩረት ምንጭ ሆኖ ቆይቷል፡፡'' ብለዋል።
                                                                          ራስ አሉላ
የ ድሉ ዜና በመላ ዓለም ተናኘ ። ጥቁር አፍርካውያን አውሮፓውያንን አሸነፉ የሚለው ዜና ጣልያንን ብቻ ሳይሆን በተዋበው ህንፃ ውስጥ አፍሪካን ለመቀራመት ተሰብስበው የነበሩ   
መንግስታትን ሁሉ 'ክው !' ያደረገ መራር ዜና ነበር።በወቅቱ የ ኒውዮርክ ታይምስ  ጋዜጣ በ  ሽፋኑ ላይ በ ያወጣው ዜና ርአስ''ITALY's TERRIBLE DEFEAT'' '' የ ጣልያን አስፈሪው ሽንፈት''ማለቱ አስፈሪነቱ ለ በርሊኑ ጉባኤተኞች ሁሉ ማለቱ ሳይሆን ይቀራል?
የ አድዋ ጦርነት ድል ተከትለው የመጡ ክስተቶች

የ አድዋ ድል በ ኢትዮጵያ ድል አድራጊነት መጠናቀቅ የሚከተሉትን ሁኔታዎች በ ሀገርውስጥም ሆነ በ ዓለም አቀፍ የ ዲፕሎማሲ መድረክ ላይ ተከስቷል;-
  • በ ጥቅምት ወር ላይ ጣልያን ከ ኢትዮጵያ ጋር ''አዲስ አበባ ውል '' የተባለ አዲስ ውል ለመፈረም ተገዳለች፣
  • በ አሜሪካ፣አፍሪካ ና በመላው ዓለም ያሉ ጥቁሮች ለመብታቸው ተነሳስተዋል፣
  • እ.ኤ.አ. በ1903 ዊሊያም ሄንሪ የተባሉት አፍሪካ አሜሪካዊ የንግድ ስራ ዋነኛ አንቀሳቃሽ የሄይቲ ዜግነት ካላቸው ገጣሚ እና ተጓዥ ከሆኑት ቤኒቶ ሲልቪያን ጋር በመሆን ወደ ኢትዮጵያ መጡ፡፡አላማቸውም ንጉሰ ነገስት ሚኒሊክን ለመጎብኘት እና ከእርሳቸውም ጋር ለመተዋወቅ ነበር፣
  • የኢትዮጵያን ነፃነት በአሜሪካ ለሚኖሩ ጥቁሮች እንደ ነፃነት ነፀብራቅ እና መሰረት በማየት ጋርቬይ በቂ ገንዘብ ለማሰባሰብ የሚያስችል የባህር ላይ የንግድ ስራ ለመመስረት አሰቡ፡፡ ከዚህም ሌላ ወደ አፍሪካ የሚመለሱ በርካታ አባላትን ለመመዝገብ አቀዱ፡፡ በጥቂት አመታት ውስጥ የጋርቬይ ማህበር ከሞላ ጎደል 10 ሚሊዮን ዶላር በማሰባሰብ እስከ ግማሽ ሚሊዮን የሚደርሱ አባላትን ለማቀፍ ችሏል፣
  • ታዋቂ የሆነው የሲቪል መብቶች መሪ ማልኮም ኤክስ አባቱን ቄስ ኢያርል ሊትልን በመጥቀስ የሕይወት ታሪኩን መፃፍ ጀመረ፡፡ ለዚህም ምክንያት የሆነው አባቱ ከላይ የተጠቀሰው 'የዩናይትድ ኒግሮ ኢምፕሩቭመንት አሶሲየሽን' ከፍተኛ ደጋፊ ነበሩ፡፡ ማልኮም በዚህ ረገድ የሚከተለውን አስተያየት ሰጥቷል፡- ‘አባቴ ወደ ጋርቬይ ማህበር ስብሰባዎች የሚወስደው እኔን ብቻ ነበር፡፡ እነዚህ ስብሰባዎች በተለያዩ ሰዎች ቤቶችበሚስጥር ይካሄዱ ነበር፡፡ አባቴም እኔን አንዳንድ ጊዜ ወደ እነዚህ ስብሰባዎች ይወስደኝ ነበር፡፡ አፍሪካ ለአፍሪካውያን የሚለውን አባባል አስታውሳለሁ፣ ኢትዮጵያዊያን ተነሱ’ ማልኮን ከጋርቤይ የፓን አፍሪካ መልእክት ጋር የነበረው ቁርኝት እና ይህም መልእክት በንባብ፣ በፅሑፍ እና በታሪክ ራሱን ሲያስተምር እንደ መነሻ ምክንያት የሚጠቀምበት ነበር፡፡ ‘በከፍተኛ ደረጃ ያስደሰቱኝን የመጀመሪያዎቹን መፅሐፍት በሚገባ ማስታወስ እችላለሁ፡፡ ጄኤ ፕሮዘርስ በፃፋቸው ሶስት መፅሐፍት ጥቁር የነበረው ኤዞፕ ስለ ታላቋ የ ክርስቲያን ግዛት ማለትም ስለ ኢትዮጵያ ገልል፡፡ ይህችም ሃገር የጥቁርን ቀጣይ እድገት ያስመሰከረች የምድርን ረጅም እድሜ ያስቆጠረች ሃገር ናት'' ብሎላታል።
  • የናይጄሪያው ናሜንዲ አዚኪዊ፣ የጋናው ኩዋሜ ንክሩማ እና የኬንያው ጆሞ ኬኒያታ በመጀመሪዎቹ የአፍሪካ ነፃነት እንቅስቃሴዎች እንዲሁም በምእራብ ኢንዲንስ ያሉ መሪዎች ማለትም ጆርጅ ፓድሞሬ እና ማርከስ ጋርቬ (ጀማይካ) በድሉ ከፍተኛ የተነሳሽነት ስሜት እንዲያድርባቸው ሆኗል፡፡
አድዋና ከ መረብ ወንዝ ማዶ ያሉት ወገኖቻችን
ዛሬ የ አድዋ ድል ከተመዘገበ ገና አንድ መቶ አስራ ስድስት ዓመቱ ነው። የ አድዋ ተፅኖ ፈጣሪነቱ ግን ዛሬም አለ።ከ አድዋ ጋር ተያይዞ የሚነሳው'' አፄ ምኒልክ ከመረብ ተሻግረው ቢዘምቱ ና ጣልያን ምፅዋን አልፈው ቢያሻግሩት ኖሮ በ ምድረ ኤርትራ ከሚኖሩት ወንድሞቻቻን ጋር አይለየንም ነበር'' ብለው የሚያነሱ መኖራቸው ሳይካድ። በወቅቱ ገበሬው በ ጦርነት ተጠምዶ የ ሰብል ምርት ጊዜ ከማለፉ ና የ ቤት አንስሳት በሽታ ያስከተለው ተፅኖ ጣልያን ቢያንስ የ ኤርትራን ደጋማ ግዛት ይዞ ለመቆየት ካለው ሕልም አንፃር አፄ ምኒልክ ወደ አዲስ አበባው ውል ለመግባት ቢያስገድዳቸውም ከመረብ ማዶ ያሉት ወገኖቻችንን ግን ኢትዮጵያውያን ስለመሆናቸው በ ጥያቄ መልክ አልመውትም አያውቁም። ይልቁን ይህን  የተጠራጠረ ና ለዚህም አበክሮ የሰራ የ ሀገራችን መንግስት ቢኖር የ ዛሬው የ ኢትዮጵያ መንግስት ብቻ ነው ።


ከ አፄ ካለብ ጀምሮ እስከ ራስ አሉላ ከራስ አሉላ እስከ አፄ ኃይለሰላሴ ቀጥሎም በ ደርግ ስርዓትም ቢሆን (ምንም የደርግ ግፍ በ ሀገሪቱ ሁሉ ላይ ፈተና ያበዛ ቢሆንም) ከ መረብ ማዶ ባሉት ወንድሞቻችን ኢትዮጵያውነት ላይ  ምንም አይነት የ ኢትዮጵያውነት  ጥያቄ ብሎም ግራ መጋባት አልነበረበም። የ አፄ ምኒልክ የ መጀመርያ የ አድዋ ጦርነት አስከ ምፅዋ ጣልያንን ማባረር የነበረ መሆኑን ና የ አቅም ማጣት ብቻ ሃሳባቸውን ማገዱን የምናውቀው ካወጡት የ ክተት አዋጅ ሐረግ ነው።ይሄውም አፄ ምኒልክ በ አድዋ ክተት ዘመቻቸው ላይ ''እግዚአብሄር ድንበር ይሁናችሁ ብሎ የሰጠንን ባህር እየተሻገረ'' የሚለው ሐረግ ልባቸው ባህሩ ድረስ የነበረውን ወገን ሁሉ መሆኑን ያመለክታል። ለማንኛውም ዛሬ ለምንሰራው ሥራ ነገ አውነታውን የተረዳ   በ ጥያቄ የሚያርበደብድ ትውልድ መነሳቱ አይቀርም ና ግራ ቀኙን መጠየቁ፣አውነታውን ማሳየቱ ዛሬም ለትውልዱ ማስተማር የሁሉም ድርሻ ሊሆን ይገባል።

የ ዳግማዊ ምኒልክ 'ዲሞክራሲ' ና  ጠባቂያቸው

የዳግማዊ ምኒልክን የ አትዮጵያ ታሪክ ላይ የፈጠሩት በጎ ሁኔታዎች ሁሉ ሲወሱ የሚኖሩ ናቸው።ሀገራችን ለመጀመርያ ጊዜ የ ሚንስትሮች ካቢኔ፣ስልክ፣ባቡር፣ሆቴል፣መኪና፣ ያየችው በ ዳግማዊ ምኒልክ ዘመን ነበር። ከሁሉ የሚገርሙኝ ግን ሁለት ነገሮች ናቸው።የመጀመርያው ዛሬ ተማሩ በሚባሉ ሰዎች ዘንድ ስለ አካባቢ ጥበቃ ለማስረዳት ብዙ ጊዜ የመፍጀቱን ያህል የ ዛሬ መቶ ዓመት በፊት የነበሩት ዳግማዊ ምኒልክ ለ ወደፊቱ ትውልድ የ አካባቢ ጥበቅ ልማት አስበው በሃርዛፍ ከ አውስትራልያ ድረስ ማስመጣታቸው ና አጀንዳ ብለው መነጋገራቸው ሲሆን ሁለተኛው በ 1988 አዲስ ዓለም ማርያም ሙዜም ስጎበኝ የ ሙዝየሙ አስጎብኚ የነገሩን ነገር ነው። ጉዳዩ አንዲህ ነው-


        ዳግማዊ ምኒልክ አንድ ቀን ጠባቂዎቼ በደንብ ይጠብቁኝ አንደሆነ ና አንዳልሆነ ላረጋግጥ ብለው ሌሊት ጋቢ  ለብሰው ይወጣሉ። ግቢውን ሲዞሩ  ጠባቅያቸው ከሩቅ ያየውን ሰው ስላላወቀ ''ቁም!ቁም!'' ብሎ መሣርያውን ያቀባብላል። ምኒልክ ቀልድ ያሉት ነገር ስህተት መሆኑን አውቀው ባለማወቅ አንዳይተኮስባቸው '' አይዞህ ምኒልክ ነኝ ---ጌታህ ነኝ አይዞህ---''ይሉታል። ጠባቂውም ከሩቅ ሆኖ ''በምን አውቃለሁ ምኒልክ ተኝቷል'' ይላቸዋል። ወደአርሱ ቀርበው ''ምኒልክ ነኝ አይዞህ ስራህን በደንብ መስራትህን ላይ ነው'' ይሉታል። ተባቅያቸው ይደነግጣል። ''አሁን ተኩሼ ቢሆን ጌታዬን ገድዬ ነበር'' ብሎ ላብ አጠመቀው። ቀጥሎ ግን ተናደደ አሳስተውኝ ቢሆንስ ብሎ ዱላውን አውጥቶ ሁለት ጊዜ መታቸው። ምኒልክ አየፎከሩ አንዴት አንተ ሲሉ ግቢውን ለቆ ወጣ። ጧት ግብር ተበልቶ። ዳግማዊ ምኒልክ ያን ጠባቂ አስጠሩት። በሰራው ሥራ ግዞት አንደማይቀርለት ገምቶ ከፊታቸው ቆመ። ሌሊት የሆነውን ሁሉ አስረድተው ለ ሹማምንቱ ፍረዱ አሉ። ሁሉም ተነስቶ '' ግማሹ አርባ ይገረፍ---ሌላው ይገደል----'' ብሎ ፈረደ። ዳግማዊ ምኒልክ ግን '' ምን አረገ ካለበት የሄድኩበት ሳለሁ ስራውን በሚገባ በሰራ ሰው ላይ ለምን ትፈርዳላችሁ?'' ብለው መሬት ሸልመው ሾሙት። አሉን የ ሙዝየሙ አስተዋዋቂ። ቀጥለውም የናንተ ዲሞክራሲ  ዱላ አደለም ተናገራችሁኝ ብሎ ፍዳ የሚያሳይ ነው። ያኔ ይህም ተደርጉአል።ይህ ሲፈፀም የነበሩ የ 96 ዓመት የአድሜ ባለፀጋንም ያሉበትን ቦታ ሁሉ ነግረውን ሄደን ታሪኩን ከሳቸው ሰማን። በሉ ደሞ  ጋዜጠኞቻችንን አናንተ ስለፃፋችሁ ለ ፍርድ ቀረባችሁ የ ዛሬ መቶ ዓመት  መፃፍ አደለም መሪውን በዱላ የተማታም የዚህ አይነት ዲሞክራሲ ነበረው  ብላችሁ አንዳትነግሩብኝ  አደራ።

በ  ታሪክ ''ጢቢ ጢቢ'' መጫወት እና መዘዙ
ከዚህ ሁሉ በላይ  ግን ይህን ፅሁፍ ለማጠናቀር ያነሳሳኝ የ ዘመኑ በ ታሪክ ላይ የሚደረግ የ ''ጢቢ ጢቢ'' ጫወታ ነው።በ አክሱም ታሪክ ዙርያ በሚቀርቡ ስምቦዜም ላይ ሆነ በ መፅሐፍ መልክ በ ወጣ ፅሁፍ ያውም የ ሀገራችን ቁልፍ ባለስልጣናት በታደሙበት ፀሐፍያን ''ጆሮ የሚጠልዙ'' የሚሏቸው ታሪኮች መውጣታቸውና ለ ምረቃ መብቃታቸው በታሪክ ዙርያ ባለሙያ ለሆኑ በሙሉ የ ሞት ሞት መስሎ ስለተሰማኝ ና ስላሳዘነኝ ነው። አሁንም የታሪክ ምሁራን ያለውን አውነታ ለትውልድ ፅፈው ማስቀመጥ፣ተከታታይ የ ግንዛቤ ማስያዣ መርሃግብሮች ማዘጋጀት ማንን ገደለባቸው? ነው ወይንስ አነሱም የውሸት ታሪክ ሰለባ ሆኑብን።ታድያ ለምን ታሪክ ተማሩ? ዛሬ  የ አድዋ ድል ለ ሽረው ምኑ ነው? ለ ከፋው ምኑ ነው? ለ ሃማሰኑ ምኑ ነው? ለ ወሎው ምኑ ነው? አየተባለ በ ታሪክ ላይ ሌላ  ''ጢቢ ጢቢ''  የተጀመረበት ጊዜ ላይ መሆናችን ተረሳ?

አበቃሁ ።

ጌታቸው
ኦስሎ

11 comments:

Anonymous said...

A Great peace Gecho! Keep it up.

Habtamu said...

I am rally impressed with the history u svare us. Pls. Keep it up!!!

Anonymous said...

it is realy interesting gech,good job ,God bellus u

Anonymous said...

Getcho,
Well done!! keep it up.
drj

Teklu said...

Great, Geta!

But I would prefer an exclusive focus on current understandings and practices related to that all-time victory to its mere historical description. The latter is already in chronicles, books, articles, .... A much more critical evaluation of how and to what extent we view and 'live' Adwa victory is crucial. That approach would significantly benefit the young generation and could be considered an effective response to people who ascribe to be hitory writers who limit the scope of Ethiopian history only to some periods and persons.
Teklu

Teklu said...

Great, Geta!

But I would prefer an exclusive focus on current understandings and practices related to that all-time victory to its mere historical description. The latter is already in chronicles, books, articles, .... A much more critical evaluation of how and to what extent we view and 'live' Adwa victory is crucial. That approach would significantly benefit the young generation and could be considered an effective response to people who ascribe to be hitory writers who limit the scope of Ethiopian history only to some periods and persons.
Teklu

Anonymous said...

Good job Gecho, interesting narration.

Tesfaberhan said...

Very true bro. Keep it up. Let all of us unit to keep the history alive.

May God bless your initiative. Amen.

Tesfaberhan

Mekonnen Aderaw said...

Hey Getch, its really nice article that reminds us once again about the prices paid by our fathers for the Sovereign Ethiopia! It is also a lively lesson for my generation to point his three fingers towards him/herself! BZW, I am happy that you started blogging! Wow1 An amazing responsibility and please keep up the good work!

Anonymous said...

Short but to the point, precise but very informative and educating. Ethiopia had already started modern civil service during the reign of Emperor Minilik II. I really am very astonished with Empress Tayitu's tenacity and love for her people and her country. Democracy was exercised in that period.
Good job getcho, keep on telling the truth.
Yantew k.w

Anonymous said...

Wow impressive,
Liked the flow of the history..but it would have been good if you included some references ...you know.

Also I wish if you could produce the english version of this article.

Otherwise keep it up

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።