ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Wednesday, December 7, 2016

ኢትዮጵያ ከውስጥ እና በዙርያዋ እየሆነ ያለው እና መፍትሄው።ለኢትዮጵያ ሕዝብ፣ተቃዋሚዎች እና አክቲቪስቶች (የጉዳያችን አጭር ማስታወሻ)

 ጉዳያችን
ህዳር 28፣2009 ዓም (December 7, 2016)
===========================

ኢትዮጵያ ከውስጥ አሁን 
================= 
  • የተፈጥሮ ሃብቷ  እየተዝረከረከ፣ ባለቤት የሌለው፣ከየትም የመጣ አረብ ለባለስልጣን ጉቦ እየሰጠ መሬት እና ውሃ የሚወስድባት፣
  • አርሶ ያበላ ገበሬ እየተገደለ፣ ጎጆው ሆን ተብሎ እየነደደ፣
  • ከተሞቿ የከተማ ዕቅድ የሚል ትምህርት ያልነካቸው በጎጥ የተጠራሩ አለቆች የሚያተረማምሱት፣
  • የሃይማኖት ቦታዎቿ ለቦታው በማይመጥኑ መንፈሳዊ ሕይወት ባልጎበኛቸው የተሞሉ፣የገንዘብ መዝረፍያ ቦታዎች፣
  • ምሁራኑ ተስፋ ቆርጠው የጎጠኛ ስርዓት ባርያ ሆነው ሃሳባቸውን ለሀገር ማበርከት ያልቻሉበት።ከተናገሩ በሚቀጥለው ቀን እስር ቤት የሚገቡባት።
  • ከያንያኑ ገንዘብን እንጂ ጥበብን የማያደንቁ፣ኪነጥበብን እንዴት ወደ ገንዘብ መቀየር እንደሚቻል ብቻ ሲያሰላስሉ የሚያድሩ፣
  •  ፀሐፍያኑ አናታቸው ላይ ክላሽ የተደገነባቸው፣ መፃፍ አይደለም፣መናገር አይደለም ምን ማሰብ እንዳለባቸው ሁሉ የሚነገራቸው፣
  • ሕዝቡም የቱን ቴሌቭዥን ማየት እንዳለበት፣የቱን ማየት እንደሌለበት በመሳርያ ኃይል ተገዶ የሚሰቃይ፣


ኢትዮጵያ ዙርያዋን 
  • በየመን የኢራን እና የሳውዲ ቡድን ሌላውን የመካከለኛ ምስራቅ ያሳተፈ ጦርነት የሚደረግበት፣
  • ሳውዲ ከጅቡቲ እና ኤርትራ ጋር ተዋውላ የጦር ሰፈር የመሰረተችበት እና ለመመስረት ሽር ጉድ የምትለብት፣
  • ሳውዲ እና ኩአታር ልዩ ስምምነት አድርገው መሪዎቿ የጥንት የአረብ ጎራዴ እያወዛወዙ የሚፎክሩበት፣
  • ሱዳን ከሳውዲ ከፍተኛ ገንዘብ ተመድቦላት የጦር መሳርያ ግዢ ላይ የተጠመደችበት፣
  • ሳውዲ አረብያ በዓለም ላይ የጦር ኃይላቸውን በከፍተኛ ገንዘብ ከሚገነቡት 3 አገሮች መካከል የሆነችበት፣


መፍትሄው

ኢትዮጵያ አሁን ያለችበትን እና መጪውን ፈተና ከሕወሓት ጋር ልትፈታው አትችልም።ሕዝብ የማያምነው ብቻ ሳይሆን የህዝብ ጎጆ እያፈረሰ እየገደለ እና ከ200 ሺህ በላይ ሕዝብ እስር ቤት ያሰረ መንግስት ከውጭ አስጊ ኃይሎች በበለጠ አደጋ ነው።በምንም አይነት ፍጥነት የሕወሓት መንግስት አጥፍቶ ለምጥፋት ያለመ እንጂ ኢትዮጵያ ከገባችበት ማጥ ውስጥ ለማውጣት ፍቃደኛ አይደለም።በመጀመርያ ኢትዮጵያን ማጥ ውስጥ የከተታት ማን ሆነ እና ነው።ስለሆነም ሁሉም በትብብር በፍጥነት የህወሓት መንግስት መወገድ እና ኢትዮጵያ የሚሆናትን መንግስት መመስረት አለባት።የህዝብ ተሳትፎ ካለ ከየትኛውም በኩል የሚያጋጥም የደህንነት ስጋትን መቋቋም ይቻላል።ከእዚህ ውጭ ግን ሕወሓት ስልጣን ላይ እያለ ማንም ከእርሱ ጋር ሊተባበር ስለማይችል ኢትዮጵያ የበለጠ ፈተና ውስጥ ትገባለች።

የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ተቃዋሚዎች፣አክትቪስቶች ስለ ኢትዮጵያ ስታስቡ ውስጡንም ዙርያውንም ተመልከቱ።የሕወሓት ከስልጣን መውረድ እጅግ አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን ከበፊቱ በበለጠ ተረዱት።እዚህ ላይ የስርዓቱ ደጋፊዎች ምናልባት ሕወሓት በስልጣን ላይ መቆየቱ ለትግራይ ይጠቅማል ብላችሁ ካሰባችሁ መሳሳታችሁን ልነግራችሁ እፈልጋለሁ።ቀልድ እያወራሁ መስሏችሁ ሊሆን ይችላል። እውነታው ግን ሌላ ነው።ኢትዮጵያ እንደ ሀገር የሚመጡባትን አደጋዎች እኩል ደቡብም፣ሰሜንም ሆነ ምዕራብ እና ምስራቅ በኅብረት ካልመከተ የትኛውም ጥቃት መጀመርያ የሚያርፈው ኃይሉ አለ የሚባለው ትግራይ ላይ ነው።ይህ ደግሞ አሁን ባለው ሁኔታ ክፍፍል ይፈጥራል።ሕወሓት በሁሉም ዘርፍ ክልሉን ከቀሪው ኢትዮጵያ ጋር ስላጣላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ምላሽ በወቅቱ የተለያየ ነው የሚሆነው።ለእዚህ መፍትሄው የአባይ ወልዱን ፉከራ መስማት ሳይሆን ኢትዮጵያ  እውነተኛ ለውጥ እንዲመጣ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር የሚስማማ መንግስት እንዲመጣ ከእንቅፋቶቹ ጋር  ተጋፍጦ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር በቶሎ መቆም ነው።

ተወደደም ተጠላ ለውጡ አይቀርም።ነገር ግን ኢትዮጵያን ለባእዳን ያጋለጠ እንዳይሆን ሁሉም ድርሻ አለው። መታወቅ ያለበት ግን ሕወሓት በምንም አይነት ኢትዮጵያን እንዲያድናት ከእራሴ ጀምሮ አልለምነውም። ለእራሱ የሞተ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን በእራሱ አደጋ ስለሆነ።ሕዝብ የጠላው መንግስት ይዞ አንዲት ቀን ለምታድር ሀገር ወዮላት።በእዚህ መሃል የሚመጣ አደጋ እንደ ጎርፍ ይዞን ነው የሚሄደው።በ1928 ዓም ጣልያን ኢትዮጵያን ሲወር ኢትዮጵያ የአድዋ ጦርነት ወቅት የነበረ መሪ ብቻ ቢኖራት ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲውን እንዴት ብላ ተጋፍጣ ለነፃነት ጥበቃ ነበር? ነገር ግን ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ስላሴ ጉዳዩን ከሜዳ ላይ ውግያ ባለፈ በዓለም አቀፍ ዲፕሎማስም ከእንግሊዝ ጋር በሰሩት ሥራ የኢትዮጵያ ነፃነት ተፋጠነ።እዚህ ላይ አርበኞቻችን ምንም አልሰሩም ለማለት አይደለም።ነገር ግን የተጣጣመ ሥራ የሚሰራ መንግስት ኢትዮጵያ ዛሬ ትፈልጋለች። የሕወሓት መንግስት በፍጥነት በሕዝባዊ መንግስት መቀየር እና ኢትዮጵያ ውስጣዊ አንድነቷን በቶሎ መገንባት ያለባት ቁልፍ ጊዜ ላይ ያለች ሆኖ ይሰማኛል።

በምንም መለኪያ ሕውሐት ለኢትዮጵያ አደጋ የሆነበት ጊዜ አሁን ነው።እርሱ በኢትዮጵያ ጥቅም ላይ ስልጣኑን ሊደራደር ይፈልጋል።በምንም አይነት ሕወሓት ኢትዮጵያን የማዳን አቅም የለውም።አደጋው በስልጣን ላይ መቆየቱ እና የህዝብ ህብረት የበለጠ መበተኑ ነው።ከሕወሓት የስልጣን መቆየት ከሚመጣው አደጋ ይባስ  የመጥፎ መጥፎው ላይ የሚታይ የብርሃን ጭላንጭል የተሻለ ተስፋ ይሰጣል።የመጥፎ መጥፎ ስል ምን ማለት እንደሆነ አሁን ለማብራራት አልፈልግም።የኢትዮጵያን ጉዳይ ሕወሓት ወደገደል እየወሰደው ነው።ሕወሓት ሞተ ማለት ኢትዮጵያ ትንሳኤ ነው።ለትግራይ ህዝብም እፎይታ ነው።ምክንያቱም ሰው በምግብ እና በኤፈርት ሀብት  ብቻ መኖር አይችልም እና ነፃነት ይፈልጋል።ነፃነት ተፈጥሯዊ ነው። የኢትዮጵያ ሰራዊትም አስብበት።

ኤርትራን በተመለከተ አዲስ የተጨመረ 
============================
በፌስ ቡክ የውስጥ መስመር አንዱ (ስሙ ይቆየን)  የኤርትራን አደጋነት በፅሁፍህ አላሳየህም አለኝ።ነገሩ ተገቢነት ያለው ነው።ስለሆነም በኤርትራ ላይ ያለኝን  የግል እይታዬን ላስቀምጥ።ትክክል ነው አይደለም ጊዜ የሚያሳየን ነው። 

አቶ ኢሳያስ በኢራን እና ሳውዲ ፍትግያ መሃል የገቡ ናቸው።የቅርብ አዋጭ የሆነችው የሳውዲ እና የተባበሩት አረብ ኢምረቶች ጦር አሰብ ላይ ቢሰፍርም ይህንን ያደረጉት ከጭንቀት ጋር ለመሆኑ መገመት ይቻላል።ምክንያቱም ይህንን አለማድረግ አይችሉም። ይህንን ባያደርጉ ኩአታር እና ሳውዲ ኤርትራ ቆላው ያለውን ፅንፈኛ በቀላሉ ረድተው ሊያስገለብጧቸው ይችላሉ።አቶ ኢሳያስ የሚታዩት ከሀማሴን ደገኛው ክርስቲያን ወገን ነው።በእዛ ላይ የተባበሩት መንግሥታት የጦር መሳርያ እቀባ አለ።በእረጅም ጊዜ ከሳውዲ አረብያም ሆነ ከመካከለኛ ምስራቅ የሚመጣ ስጋት ኤርትራን ሊያድን የሚችለው ከባለ መቶ ሚልዮን የህዝብ ብዛት ባለቤቷ ኢትዮጵያ ጋር መወዳጀት እና አንድ አይነት ግንኙነት አድርጎ ከብቸኝነት በመዳን ብቻ መሆኑን አቶ ኢሳያስ ከ40 ዓመት በኃላም የገባቸው ጊዜ አሁን ነው።ይህ ካልሆነ አደጋው ትልቅ ነው።ግብፅ በእራሷ ከሳውዲ ጋር ሙሉ በሙሉ ቆማለች ማለት አይቻልም።ኩአታር እና ሳውዲ ያላቸውን ግንኙነት ያህል ግብፅ እና ኩአታር የላቸውም።ኩአታር ያለፈውን የእስልምና ወንድማማቾች መንግስት ደጋፊ ነበረች።የአሁኑን መንግስት ለብ ባለ ሁኔታ ነው የምትመለከተው።ለእዚህ ነው አቶ ኢሳያስ ከወያኔ ጋር ያላቸው ፀብ እንዳለ ሆኖ የእነ ሳውዲ እና የኩአታር ግንኙነት ሲያሰጋቸው ከግብፅ ጋር ወዳጅነታቸውን ማጥበቅ የጀመሩት።


ጉዳያችን GUDAYACHN

 www.gudayachn.com