Friday, June 18, 2021

በሳውዲ አረብያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስቃይ ላይ ናቸው።በጉዳዩ ላይ በሳውዲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ከሳውዲ ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር መነጋገራቸው ተሰምቷል።

አምባሳደር ሌንጮ ከሳውዲ ምክትል ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር እና በሳውዲ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳይ ዳይሬክተር  አምባሳደር  ጋር ሲወያዩ 

ጉዳያችን ዜና  / Gudayachn News

በሳውዲ አረብያ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በሳውዲ ፖሊሶች ቤታቸው እየተሰበረ ጭምር እየታሰሩ ነው።ኢትዮጵያውያኑን የሳውዲ ፖሊሶች እና ተባባሪ ታጣቂዎች የሚያሳድዷቸው የመኖርያ ፈቃድ የላችሁም እያሉ ሲሆን።ከተያዙት ውስጥ ግን ፍቃድ ያላቸውም እንደሚገኙበት የሚናገሩ አሉ።ኢትዮጵያውያኑን ፖሊሶቹ ከያዙ በኃላ እጅግ አስከፊ ወደ ሆነ እስር ቤት የሚወረውሯቸው ሲሆን በእስር ቤት ውስጥ የገቡ ኢትዮጵያውያን እንደሚናገሩት እስር ቤቱ ከፍተኛ ሙቀት ያለው፣የሚተኙበት ቦታም  በተባይ የተሞላ መሆኑን በሳውዲ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ይናገራሉ።

በአሁኑ ጊዜ በርካታ ኢትዮጵያውያን በከተማ የሚደረገው የቤት ለቤት ፍተሻ እና በመንገድ ላይ መያዝን በመፍራት ወደበረሃማው የሳውዲ ገጠራማ ቦታ ለመደበቅ እየሞከሩ ሲሆን በእነኝህ የገጠር ቦታዎች ደግሞ ከ40 ዲግሪ በላይ የሚወጣው  ሙቀት ያሰቃያቸዋል። ወደገጠር የሚወጡት ሳይታሰብ ስለሆነ የሚበሉትም ሆነ የሚጠጡትን ሳይዙ ስለሚሄዱ አንዳንድ ጊዜ በአጋጣሚ ከሚያገኙት መንደር ተጠግተው ለመለመን ይገደዳሉ።በአሁኑ ጊዜ በሳውዲ እስር ቤት ከሚገኙት ኢትዮያውያን ውስጥ ሕፃን ልጆቻቸውን እንደያዙ ቤታቸው እየተሰበረ እንዲወጡ ተደርገው እስር ቤት የገቡ ሁሉ የሚገኙ ሲሆን በእስር ቤት ውስጥ በህመም ላይ ያሉ ቁጥራቸው ቀላል እንዳልሆነ ከሳውዲ የሚሰማው ዜና ያመለክታል።

ይህ በእንዲህ እያለ በሳውዲ አረብያ የኢትዮጵያ አምባሳደር፣ አምባሳደር ሌንጮ ከሳውዲ ምክትል ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር እና በሳውዲ ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳይ አምባሳደር  ጋር ትናንት መነጋገራቸው ለማወቅ ተችሏል።አምባሳደር ሌንጮ ከምክትል ውጪ ጉዳይ ሚኒስቴሩ ጋር ባደረጉት ውይይት ኢትዮጵያውያኑ የመኖርያ ፍቃዳቸው (''ኢቃማ'') እንደተቃጠለባቸው እና በእጃቸው ላይም ገንዘብ አለመኖሩ ለችግር እንደዳረጋቸው አምባሳደሩ ለሳውዲው ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አስረድተዋል።ከእዚህ በተጨማሪ በእስር ቤት ያሉት ኢትዮያውያን ጉዳይ እና ፖሊሶቹ በኢትዮጵያውያን ላይ እያደረሱ ስለሚገኘው በደል እና ኢትዮጵያም የዜጎቿ መብት እንዲከበር በዝርዝር መነጋገራቸው ለማወቅ ተችሏል።

በሌላ በኩል በሳውዲ የኢትዮጵያ ኤምባሲም ይህንኑ ንግግር አረጋግጦ ንግግሩ እንደቀጠለ እና አንድ ዓይነት መፍትሄ ላይ እስኪደርሱ ድረስ እንደሚቀጥል ከጠቀሰ በኃላ ኢትዮጵያውያን እስከዛው ድረስ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የሚጠይቅ መልዕክት በማኅበራዊ ሚድያ አሰራጭቷል።አሁን ዘግይቶ በወጣ ዘገባ ደግሞ የፖሊሶች የቤት መስበር ተግባር ትንሽ ጋብ ያለ ሲሆን ይህ ግን እስከመቼ እንደሚዘልቅ አልታወቀም።በትናንትናው ዕለት በሳውዲ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ኢትዮጵያንን ወደ ሀገር ቤት የመመለስ ሥራ በቅርቡ እንደሚጀምር የሚገልጥ ከእዚህ በታች የምታዩትን ማስታወቂያ አውጥቷል።
ሆኖም ግን ብዙዎች በእዚህ ማስታወቂያ ብዙም ተስፋቸው አልለመለመም።ምክንያቱም ያለው ቁጥር እና ወደ ኢትዮጵያ ተመለሱ የሚባሉት ቁጥር አይመጣጠንም።አልፎ አልፎ እንደሚታየውም ወደ ሀገር ቤት ከተመለሱ በኃላ ተመልሰው ወደ ሳውዲ የሚገቡ መኖራቸው ሌላው አስቸጋሪ ጉዳይ ነው። በሳውዲ አረብያ የሚኖሩ በርካታ ኢትዮጵያውያን በባህር እየተሻገሩ የገቡ እና የመንን እንደመሸጋገርያ አድርገው ወደ ሳውዲ አረብያ የገቡ እንደሆነ ይነገራል።በሳውዲ የሚኖሩ ኢትዮያውያን ትኩረት ይሻሉ።ኢትዮጵያ በብዙ ጉዳዮች ተወጥራ ብትገኝም የዜጎች ጉዳይን ግን በሳውዲ ለረጅም ጊዜ ከኖሩ እና ስለ ሀገሩም የጠለቀ ዕውቀቱም ሆነ አቅም ያላቸው ኢትዮጵያንን ያጣመረ ሥራ መስራት እና የኢትዮጵያንን ስቃይ ጋብ የሚልበትን መላ መፈየድ ያስፈልጋል።

==========================
ማስታወቂያ /Advertisement 
===============================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

Tuesday, June 15, 2021

ሰበር ዜና - ኢትዮጵያ የትግራይ ክልልን መልሶ ለመገንባት 1ነጥብ 2 ቢልዮን ብር በጀት ያዘች።ከዓለም ባንክም በተጨማሪ ለግንባታው 8 ቢልዮን ብር በላይ ለማግኘት ተነጋግራለች። Ethiopian Government set a 1.2 Billion Birr Budget to rebuild Tigray region. In addition, the Gov't has also negotiated with the World Bank to get $200 million (USD),that is about 8 billion birr, for the same project purpose

የገንዘብ ሚንስትር አቶ አህመድ ሸዲ / Ethiopian Finance Ministr Ahmed Shedi
(Photo - MOFED website)

ጉዳያችን ዜና /Gudayachn News
(Please Read in English under Amharic version)
ኢትዮጵያ የትግራይ ክልልን መልሶ ለመገንባት 1ነጥብ 2 ቢልዮን ብር በጀት ያዘች።ከዓለም ባንክም በተጨማሪ ለግንባታው 8 ቢልዮን ብር በላይ ለማግኘት መነጋገር መቻሏን የኢትዮጵያ ገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመዲን ሸዴ ዛሬ ገልጠዋል።ሚኒስትሩ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ለመጪው ዓመት ማለትም ለ2014 ዓም በጀት ለፓርላማ በቀረበው የውሳኔ ሰነድ ዙርያ ዛሬ ማብራርያ ለፓርላማው አባላት በሰጡበት ጊዜ ነው ለትግራይ መንግስት የመደበውን በጀት የገለጡት።በእዚህም መሰረት መንግስት ከራሱ ለክልሉ ግንባታ የሚውል 1 ነጥብ 2 ቢልዮን ብር መያዙን እና ከእዚህ በተጨማሪ ወደ 8 ቢልዮን የሚሆን ብር ከዓለም ባንክ ለማግኘት መነጋገሩን አብራርተዋል።

ሚኒስትሩ ከእዚህ ጋርም አያይዘው በመጪው ዓመት የመንግስት ሰራተኞች ደሞዝ በተመለከተ መንግስት አሁን የያዘው የደረጃ ማውጣት ሥራ ካጠናቀቀ በኃላ የሚሰራ ሲሆን በመጪው ዓመት በእዚሁ የደረጃ ማውጣት ሥራ ሂደት የእርከን ጭማሪ የሚኖር መሆኑን ነገር ንግ ተጠንቶ የሚቀርብ ሙሉ ጭማሪ ከመጪው ዓመት በኃላ የሚታሰብ መሆኑን ገልጠዋል።

በመጨረሻም ባለፈው ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በብዙ ሰው ሰራሽ እና የተፈጥሮ ችግር ላይ ቢሆንም 6 ነጥብ 1 ፐርሰንት ማደጉን ጠቅሰው በመጪው ዓመት ግን በመንግሥታቸውም ስሌት ሆነ በዓለም አቀፍ ድርጅቶች ስሌት መሰረት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በተሻለ መንገድ እንደሚያድግ አብራርተዋል። የዋጋ ግሽበትን በተመለከተ ሚኒስትሩ እስካሁን ፈታኝ ሆኖ መቆየቱን አብራርተው በመጪው ዓመት ግን የዋጋ ግሽበቱን ወደ አንድ ዲጅት ለማውረድ መንግስት እየሰራ እንደሆነ እና የተቀመጠውም ግብ ይሄው መሆኑን ገልጠዋል።

Ethiopian Government set a 1.2 Billion Birr Budget to rebuild Tigray region. In addition, the Gov't has also negotiated with the World Bank to get $200 million (USD),that is about 8 billion birr, for the same project purpose, that is to rebuild Tigray.

 

The Finance minister, Ahmed Shide, speaks today for the Ethiopian parliament meeting on the new Ethiopian National Budget.On his speech he disclosed that the Government has determined to rebuild Tigray in all sectors. Ahmed Shide has also explained about the last year’s Economy of the country and on what the future looks like.

 

According to the minister's report,Ethiopian economy in the last Covid-19 year, even though there were serious national and natural problems, the country could achieve 6.2% economic development. Regarding the coming budget year, the minister says it is a bright future and this is not only confirmed with their office's analysis but according to International Financial Institutions predictions, Ethiopia will score better growth rate. 

 

At last, the parliament members asked him about the current challenge of Inflation and the possible solutions that the Government is proposing. Concerning inflation challenges,the minister confirmed to the parliament that his Government is working strongly to get inflation down to a single digit by the coming budget year. Ethiopian New Budget will be functional from September. End of June is the current year's budget closing month.

 

It was last week that Ethiopia awarded its first private telecom licence to Global telecom companies.The Prime Minister Abiy Ahmed has disclosed, two years back, as it is his plan to open up Ethiopia's state controlled economy to the private sector. Many investors have a great interest to invest in Ethiopia’s 109 million peoples economy with favourable landscape and weather. 


Currently, the ‘talk of the city’ in Ethiopia is election.Ethiopians will vote to elect their parliament representatives on June 21,2021. About 40 million Ethiopians are registered to vote. The National Election Board  is an independent institution in Ethiopia which earns a lot of confidence by both the people and the opposition parties. Therefore, many are witnessing the coming election of Ethiopia as a unique and fair election in modern history of the country.

Gudayachn News
==========================
ማስታወቂያ /Advertisement 
===============================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

Monday, June 14, 2021

ከምርጫው በፊትና በኃላ ባሉት ሁለት ሣምንታት ዓለም አቀፍ ጫናውን በስልታዊ መንገድ ለመመከት የማኅበራዊ ሚድያው ማትኮር ያለበት ዓበይት ተግባር


>> የኢትዮጵያን መጪ ምርጫ የዓለም ዓቀፍ ማኅበረሰብ እንዳያውቀው አንዳንድ የውጭ ሚድያዎች እያፈኑት እንደሆነ እንንቃ!

ጉዳያችን / Gudayachn

ኢትዮጵያ ስድስተኛውን ብሔራዊ ምርጫ ሰኔ 14/2013 ዓም (ጁን 21/2021 ዓም) ልታካሂድ የቀራት ስድስት ቀናት ብቻ ናቸው።ይህ ምርጫ ኢትዮጵያ ከእዚህ በፊት ካደረገቻቸው ምርጫዎች የተሻለ የሚባልባቸው ብዙ ነጥቦች አሉት።በአንፃሩ ደግሞ ለመጪው የምርጫ ጊዜ መሻሻል የሚችሉ ልምዶችም የሚቀሰሙበት ነው።የምርጫ ቦርድ በተሻለ መልኩ ከመንግስት ጣልቃ ገብነት ሲሰራ መታየቱ፣የተወዳዳሪ ፓርቲዎችን ለመወዳደር የሚያበቁ መስፈርቶች ግልፅነት እና ደረጃ መጠበቅ፣የምርጫ ካርዶች አሰረጫጨት እና ችግር ያለባቸው ጣብያዎችን ለመሰረዝ ያሳየው ቁርጠኝነት እና የመረጃ ፍሰቱ ጥሩ የሚያስብሉት ናቸው።በአንፃሩ በአንዳንዳንድ የምርጫ ጣብያዎች በተለይ በኦሮምያ እጩዎችም ሆኑ ፓርቲዎች እንደፈለጉ ለማስተዋወቅ አለመቻላቸው እንደ ጉድለት የሚታይ ነው።

ይህ ምርጫ መታየት ያለበት ኢትዮጵያ ካለችበት ከጊዜው ነባራዊ ሁኔታ አንፃር ነው።ኢትዮጵያውያን የተለያየ አስተሳሰብ እንዲይዙ ከሶስት አስር ዓመታት በላይ ተሰርቶብናል፣በጎሳ ፖለቲካ ተሰቃይተው ብዙ ጉዳት ደርሶብናል፣ፅንፍ የያዙ ሃሳቦች ሀገሪቱን ወጥረው ይዘው ትውልዱን ለማደናበር ሞክረዋል፣በሌላ በኩል የውጪ ኃይሎች በኢትዮጵያ ላይ ለመረባረብ ያሰፈሰፉበት ጊዜ ነው።ስለሆነም ምርጫው ሃገረ መንግስት ከማቆም ባለፈ የኢትዮጵያን ህልውና የማስጠበቅ አደራም ይዟል።

ይህንን ምርጫ በተመለከተ የዓለም ዓቀፍ ማኅበረሰብ እንዳያውቀው አንዳንድ የውጭ ሚድያዎች እያፈኑት እንደሆነ ማስተዋል ይገባል።ይህ ደግሞ የኢትዮጵያን መልካም ስም ለማጠልሸት ከያዙት ፕሮጀክት አንፃር መሆኑ ግልጥ ነው።ስለሆነም በአዲስ አበባ ወኪሎች ያሏቸው ዓለም አቀፍ ሚድያዎች በአዲስ አበባ ስላለው የምርጫ ዜና እና ስለሂደቱ ይህ ነው የተባለ ዘገባ አልሰሩም።አሁንም ምናልባት የምርጫው ቀን ኢትዮጵያን ለማጠለሸት ይጠቅማል ያሉትን ክፍል ብቻ መርጠው እንደሚያቀርቡ ግልጥ ነው።ስለሆነም ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የማስተዋወቁ ሥራ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ላይ መውደቁን መረዳት ይገባል።

ስለሆነም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ባለው የማኅበራዊ ሚድያ በተለይ በትውተር ከምርጫው በፊት ኢትዮጵያ ምርጫ ልታደርግ መሆኑን የሚገልጡ ፅሁፎች በውጭ  ቋንቋዎች ማስተዋወቅ እና ከምርጫው በኃላ ባሉት ጥቂት ቀናትም ምርጫው መካሄዱን እና ውጤቶቹን ማስተዋወቅ ለሀገር ገፅታ የሚሰጠው ጥቅም ትልቅ ነው።እነኝህን ስራዎች ማድረጉ የሚከተሉት ጥቅሞች አሉት። እነርሱም -
  • ኢትዮጵያን በጦርነት፣በረሃብ ለመሳል የሚታትሩትን የውጭ ኃይሎች ኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ላይ መሆኗን እንዲነገር ስለማይፈልጉ ይህንኑ ለዓለም ሕዝብ ለመንገር ይጠቅማል፣
  • ኢትዮጵያን በአምባገነን መንግስት ለመፈረጅ እና በአፍሪካውያን ወንድሞቻችን መሃል ለማስጠላት የሚደረገውን ጥረት ያከሽፋል፣
  • በውጭ የተወለዱ ኢትዮጵያውያንም መረጃ የሚያገኙት ከተሳሳተ የውጭ ሚድያ ስለሆነ በእዚህ የምርጫ ማስተዋወቅ ሥራ በሀገራቸው ምን እየተደረገ እንዳለ እንዲረዱ ያደርጋል፣
  • ከምርጫው በኃላ የኢትዮጵያን መንግስት ሕጋዊ እንዳልሆነ ለማስመሰል ጥረት የሚያደርጉት ዛሬ ምርጫው እንዲነገር ስለማይፈልጉ ከወዲሁ የምርጫውን ሂደት ለዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ በመንገር የስነ ልቦና ዝግጅት እንዲያደርግ ለማዘጋጀት ይጠቅማል። 
በመሆኑም የኢትዮጵያን ስድስተኛ ምርጫ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ባለን መንገድ ሁሉ ማስተዋወቅ የሁለት ሣምንታት ስራችን መሆን አለበት።
 ==========================
ማስታወቂያ /Advertisement 
===============================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

Saturday, June 12, 2021

ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ በኢትዮጵያ ክብራቸውን የሚመጥን አቀባባል እንዲደረግላቸው ጠ/ሚ/ር ዓቢይና መንግስት ዝግጅት ላይ ነበሩ። ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ማን ናቸው?

ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ በኢትዮጵያ ክብራቸውን የሚመጥን አቀባባል እንዲደረግላቸው ጠ/ሚ/ር ዓቢይና መንግስት ዝግጅት ላይ ነበሩ።

ፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ ማን ናቸው?
በዩቱብ ለመከታተል ሊንኩን ይጫኑ 

==========================
ማስታወቂያ /Advertisement 
===============================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

Sunday, June 6, 2021

በኢትዮጵያ ዓባይ ግድብ ላይ የግብፅ እና የኃያላኑ የማይሳካላቸው ዋናው ምስጢራዊ ዕቅድ


   

ጉዳያችን /  Gudayachn

ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ ግድቧን መስራት ከጀመረች አስር ዓመታት የሆነው ቢሆንም ግብፅም ሆነች ኃያላኑን ከፍተኛ መወራጨት ያሳዩት ባለፉት ሦስት ዓመታት ውስጥ ነው።ለእዚህ ደግሞ ዋናው ምክንያት ግድቡ በነበረበት አያያዝ በፕሮጀክት አፈፃፀሙ ለዓመታትም የማያልቅ መሆኑን ባላቸው መረጃ ባዕዳኑ ያውቁት ስለነበረ ነው።የግንባታው ኮንትራት የወሰደው እና በከፍተኛ የሙስና እንዲሁም የአቅም ማነስ ሲንገዳገድ የነበረው የብረታ ብረት እና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) በምን ያህል ደረጃ ግድቡን የመፈፀም አቅም የሌለው ነገር ግን የሕዝብ ገንዘብ አለአግባብ እየዘረፈ እንደነበር በዝርዝር ባእዳኑ ያውቁ ነበር።ሜቴክ እስከ 37 ቢልዮን ዶላር የሚያወጣ የውጭ ግዢ ሲፈፅም ካለጨረታ በዘመድ አዝማድ የድለላ ሥራ እንደነበር ከሁለት ዓመት በፊት የአቃቢ ሕግ ሪፖርት ያስረዳል።ከእዚህ ባለፈ በዓባይ ግድብ ግንባታ ላይ ያልሰራውን የፕሮጀክት ሥራ ክፍያ ቀድሞ በመውሰድ የሚወነጀለው ይሄው ድርጅት ኢትዮጵያን ቀብሮ እንደሚሄድ ባዕዳኑ ጠንቅቀው ያውቁ ስለነበር በግድቡ ላይ የጠነከረ ስሞታ ማሰማት አላስፈለጋቸውም። 

ባለፉት ሦስት ዓመታት ግን በፕሮጀክቱ ላይ የተወሰደው መሰረታዊ የለውጥ ማስተካከያ ፕሮጀክቱ በሁለት እግሩ መቆም መቻሉ እና እውን እየሆነ መምጣቱን ሲታወቅ ነው ግብፅም ሆነች ኃያላኑ መንግሥታት ድምፃቸው መሰማት የጀመረው እና በኢትዮጵያ ላይ በቀጥታ ተፅኖ ለመፍጠር እየሞከሩ ያሉት።ላለፉት አንድ ዓመታት ከግድቡ ጋር በተያያዘ ብዙ ሰበቦች ሲደረድሩ የነበሩት የውጭ ኃይሎች አሁን በቀጥታ ስለ ግድቡ ከማውራት ይልቅ በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ላይ የሚገቡበት ሰበብ ፍለጋ ለማግኘት ሲባዝኑ ይታያሉ።ስለሆነም የኢትዮጵያን የውስጥ ጉዳይ እስከ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ድረስ ለማድረስ ላይ ታች ሲሉ የከረሙበትም ሆነ አሁን ደግሞ ወደ ቡድን 7 እና በሰሜን የጦር ቃልኪዳን ሀገሮች ስብሰባ ምክክር ላይ ሳይቀር የኢትዮጵያን የውስጥ ጉዳይ መነጋገርያ ያደረጉበት ዋናውን ሚስጥር ማወቁ ጠቃሚ ነው።ይህንን ምስጢር ለማወቅ ግን ግብፅ እና ኃያላኑ ምን እንዲሆን ነው የሚፈልጉት? በጋራ ጥቅም በተለይ የዓባይን ግድብ በተመለከተ የምያስማማቸው ነጥብ ምን ሊሆን ይችላል? ወደ እዚህ ነጥብ ለመምጣት ስልታዊ መንገድ አድርገው ያሰቡት መንገድ ምንድነው ብሎ መጠየቅ ያስፈላግል።

በአባይ ግድብ አንፃር ግብፅም ሆነች ሱዳን የመጀመርያ ዕቅዳቸው የነበረው ኢትዮጵያን በውስጥ የማተራመስ አጀንዳ ከሞላ ጎደል እንዳልሰራ እና ኢትዮጵያን ለመበተን አጀንዳ የተሰጣቸው ኃይሎች አንድ በአንድ እንደተመቱ የቀረው አስተሳሰባቸውም ከምርጫው በኃላ በርዕዮተ ዓለም ደረጃም እንደሚመታ ግልጥ ሆኖላቸዋል።ስለሆነም አሁን ሃያላኑንም ሆነ ግብፅ እና ሱዳንን በጋራ በአባይ ግድብ ላይ እንዲሆን የሚፈልጉት ምንድነው? ግብፅም ሆነች ሱዳን በቀጥታ ኢትዮጵያን መውረር እንደማይችሉ ያውቁታል።ግብፅም ግድቡ ላይ አንዳች አደጋ ልፍጠር ብትል እስከ 6ሺህ ኪሎሜትር የሚወነጨፍ ሚሳኤል የታጠቀቸው ኢትዮጵያ የአስዋንን ግድብ በደቂቃ እንደምታደባየው ግብፆች ያውቃሉ።አንድ ሺህ ኪሎሜትር ማለት ከአዲስ አበባ አስመራ ነው ከአዲስ አበባ ካይሮ 3ሺህ አምስት መቶ ኪሎሜትር ነው።ኢትዮጵያ በእዚህ በኩል አልፋ ሄዳለች።በሌላ በኩል የአባይ ግድብ ማለት ግብፅን መቆጣጠር ማለት ብቻ ሳይሆን መካከለኛው ምሥራቅን መቆጣጠር እንደሆነ ኃያላኑ መንግሥታት ገብቷቸዋል።መካከለኛው ምስራቅ የታሸገ ውሃም ሆነ የሩዝ፣የፍራፍሬ እና የስጋ ምርት ሳይቀር ከግብፅ የሚቀርብለት የአባይ ወንዝ ትሩፋት  ነው።

ስለሆነም ኃያላኑም ሆኑ ግብፅ የአባይ ግድብን በወታደራዊ ጣልቃ ገብነት በቀጥታ መቆጣጠርን እንደአንድ መፍትሄ ሊያስቡት አይችሉም ማለት አይቻልም።አሁን እየሄዱበት ያለው ሂደት የሚያሳየው ይህንኑ ነው።በመጀመርያ ግብፅ ጉዳዩን የዓለም አቀፍ ፀጥታ ችግር አድርጋ እንድታቀርብ ተነገራት ከአውሮፓ እስከ መካከለኛው ምስራቅ፣ከሩቅ ምስራቅ እስከ ደቡብ አፍሪካ የግብፁ ውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ሮጡ።ሆኖም አልተሳካም።ግብፅ የአባይ ግድብ በኢትዮጵያ ቁጥጥር ስር ከሚሆን የፀጥታ ችግር ነው ተብሎ በሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ሀገሮች (ናቶ) ወይንም በተባበሩት መንግሥታት ስር ቢሆን የተሻለ የፀጥታ ዋስትና እንደሚሆናት ታስባለች።ኃያላኑ ደግሞ ይህ ለእነርሱ ግብፅን መቆጣጠር ብቻ ሳይሆን መካከለኛው ምሥራቅን መቆጣጠር እና ኢትዮጵያ እንዲሁም አፍሪካ እንዳይነሱ መድፈቂያ አንዱ መንገድ እንደሚሆን ያስባሉ።ጥያቄው ይህንን ግብ ለማሳካት ኃያላኑ ምን ሲያደርጉ ሰነበቱ? የሚለው ነው። 

ይህንን ግብ ለማሳካት ኃያላኑ በመጀመርያ ያደረጉት ሱዳንን ማማለል ነው።የባዕዳን ጦር ካለ ሱዳን መሸጋገርያነት ሊሆን እንደማይችል ያውቃሉ።ስለሆነም ሱዳንን ከአሸባሪነት መዝገብ ከመሰረዝ ጀምሮ እስከ ድጎማ ድረስ ባለፈው አንድ ዓመት ብቻ የተሰራ ሥራ ነው።ከአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣናት እስከ የእስራኤል የደህንነት ኃላፊዎች በተደጋጋሚ ወደ ካርቱም በረራ ያደረጉትም ላለፈው አንድ ዓመት ብቻ ነው።የግብፅ እና ሱዳን ጦር የጦር ልምምድ ሁለት ጊዜ ያደረጉት ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ ብቻ ነው።የኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ እና የአባይ ግድብ ጉዳይ ከሦስት ጊዜ በላይ በተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ውስጥ ውይይት እንዲደረግበት የተሞከረው ባለፉት ጥቂት ወራት ውስጥ ነው።በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ላይ በመግባት አሜሪካ ግልፅ የሆነ የተፅኖ እጇን ለማሳረፍ በምክርቤት ደረጃ ውሳኔ ያሳለፈችው ባለፉት ጥቂት ቀናት ነው። የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ የሕግ ማስከበር ተግባር መውሰዱን እና እርሱን ተከትሎ በከፍተኛ የፕሮፓጋንዳ ሥራ የሚራገበው የሰብዓዊ መብት ጉዳይን እንደ አንድ መግቢያ ጉዳይ ወስዶ 'ወደፊት ርሃብ ትራባላችሁ' ዘመቻ በኃያላኑ ሚድያም ሆነ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች ከአሁኑ እየተራገበ ያለው ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ነው።ይህ ሁሉ ውክብያ እንደ መንገድ ጠራጊ እያመቻቸ ያለው ኢትዮጵያን ማተራመስ እና የፀጥታ ችግር አለ፣ሕግ ለማስከበር ዓለም አቀፍ ኃላፊነት አለብን በሚል ሰበብ ወደ ኢትዮጵያ ጦራቸውን ለማትመም ነው።ባጭሩ እነኝህ ሁሉ ግባቸው አንድ ነው።ዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡን አዋክቦ ኢትዮጵያን በተባበሩት መንግሥታት ጭምር ለማስወገዝ እና በሰብዓዊ መብት ሰበብ የኢትዮጵያን ሕዝብ ሉዓላዊነት መግፈፍ እና የዓባይ ግድብን ለአካባቢው ፀጥታ ሲባል በሚል ግድቡን በ'ናቶ' ቁጥጥር ስር ማዋል ነው።የ'ናቶ' ያለፉት የቅርብ ታሪኮች ደግሞ ለእዚህ ምስክር ናቸው።በቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ መፍረስ ሂደት ኃላፊነት አለብኝ ብሎ ድርጅቱ በቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ ላይ ያዘነበው የቦንብ ውርጅብኝ ማስታወስ ነው።በሊብያ የውስጥ ጉዳይ ገብቶ በትርፖሊ ላይ የወረደው የአየር ኃይል ድብደባ ማሰብ ነው። 

ስለሆነም ኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያ ላይ እየታሰበ ነገር ግን የማይሳካው የባዕዳን የሃሳብ ጥግ የት ድረስ እንደሚሄድ ከአሁኑ ማወቅ እና በአስፈላጊ ንቃት እና ትጋት ላይ መገኘት አስፈላጊ ነው።''ኢትዮጵያ የዓለሙ መፋረጃ'' ነች የሚባለው አባባል ቀላል አባባል አይደለም።ግፈኛ ኃያላን ብዙ ግፍ ሊውሉባት ሞክረዋል።ዛሬ ግን የሉም።ከማለፋቸው በፊት ግን ጥፋት አላደረሱባትም ማለት ግን አይደለም።ለጥፋቷ ሌላው እና ዋና ጠላቶቿ ደግሞ ከውስጧ ሆነው ለባእዳን አሳልፈው የሚሰጧት ናቸው።ጠላቶቿም የሚነሱት በእዚሁ የውስጥ ከሃዲዎች በተነሱባት ጊዜ ነው።ዛሬ ለኢትዮጵያ ከምንጊዜውም በላይ ጥብቅና የምንቆምበት፣ከሀዲዎችን ካለምንም ይሉኝታ የምንዋጋበት እና ኢትዮጵያ ወደፊት ቀጥላ እንድትነሳ የራሳችንን ድርሻ ጥለን ለወደፊቱ ትውልድ የምናሸጋግርበት ጊዜ ነው።ኢትዮጵያ ታሸንፋለች።በእዚህ ማንም ጥርጥር ሊገባው አይገባም።ከስነልቦና ጥቃት እራስንም ሆነ ህዝብን መጠበቅ እና የባዕዳን የድፍረት ሃሳብን ጥግ አውቆ መዘጋጀት ግን  ይጠበቃል።በኢትዮጵያ ላይ ከኃያላኑ እስከ የተባበሩት መንግሥታት፣ከ'ኔቶ' እስከ ቡድን 7 የሚያደርጉትን ጣልቃ ገብነት በየጊዜው ከሚሰጡን ከፋፋይ አጀንዳዎች እራሳችንን ጠብቀን ለኢትዮጵያ ዘብ መቆም ግዴታ ነው።

==========================
ማስታወቂያ /Advertisement 
===============================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

Wednesday, June 2, 2021

ኢትዮጵያ በማኅበራዊ ሚድያው በኩል ያለውን ችግር የምትፈታበት ቀላል ግን ትልቅ ውጤት የሚያመጣው የመፍትሄ መንገድ

Picture Source: - Harvard Business Review Staff/Roc Canals/ azatvaleev/Getty Images

ጉዳያችን /Gudayachn

የማኅበራዊ ሚድያዎች በመላው ዓለም ሕዝብ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የፈጠሩት መልካም ከባቢያዊ ሁኔታ ቢኖርም፣በሌላ በኩል ያበላሹት ደግሞ እጅግ ብዙ ጉዳዮች አሉ።የህዝብ ለሕዝብ ግንኙነቶችን ለማበላሸት ተንኮለኞች ተጠቅመውበታል።በሀገሮች መሃል ግጭት እንዲባባስ ከማድረግ አልፎ በቀላሉ ሊፈቱ የሚችሉ ጉዳዮች እንዲወሳሰቡ ምክንያት ሆኗል።በሌላ በኩል ሀገሮች የውስጥ የፖለቲካ ጉዳያቸው ባልተፈለገ መንገድ እንዲሄድ ከማድረግ አልፎ የምርጫ ሂደቶች ወደ አልተፈለገ መንገድ እንዲሄዱ ማድረጉ ተነግሯል።ለምሳሌ በዩክሬን እና ሩስያ መሃል ያለው የማኅበራዊ ሚድያ ንትርክ፣በአዘርባጃን እና አርመንያ መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየው አለመግባባት እንዲቀጣጠል የማኅበራዊ ሚድያው ንትርክ መንግሥታቱ ተረጋግተው እና በሰከነ መንገድ  ለመፈለግ ፋታ የሚሰጣቸው አልሆነም። በሌላ በኩል በአፍሪካም ሆነ በአሜሪካ ማኅበራዊ ሚድያው በቀጥታ ተፅዕኖ ሲፈጥር ታይቷል።

በኢትዮጵያ የማኅበራዊ ሚድያው መረጃ  ከመስጠት ባለፈ ህዝብን በዕውቀት ለማነፅ ያደረገው አስተዋፅኦ ምንድነው? ብለን ብንጠይቅ ራሱን የቻለ ምርምር ቢጠይቅም በደምሳሳው የሚታየው ግን እዚህ ግባ የሚባል ጥቅም እየሰጠ አይደለም።ከእዚህ ይልቅ ለፖለቲካ ሹክቻ እና አንዱን ጎሳ ከሌላው ለማጋጨት የማኅበራዊ ሚድያው ሚና ቀላል አይደለም።በእርግጥ መረሳት የሌለበት ጉዳይ የማኅበራዊ ሚድያ ላለፉት ሠላሳ ዓመታት ያህል በኢትዮጵያ ሰፍኖ የነበረውን ጎሳን መሰረት ያደርገው የህወሓት መር ኢህአዴግ ስርዓትን ለማጋለጥ የተጫወተው ሚና ቀላል እንዳልነበር መካድ አይቻልም።

በሌላ በኩል አሁን ያለው ዓለም አቀፍ መሰረት ያደርገው የማኅበራዊ ሚድያ ለምሳሌ እንደ ፌስቡክ እና ትውተር ያሉት ሚድያዎች  እንደ ኢትዮጵያ የራሷ ታሪክ፣ባሕል እና የሕዝብ ግንኙነት ላለው ሀገር የተደበላለቀ ውቅያኖስ ውስጥ የመዘፈቅ ዕጣ  ያተረፈ ከመሆኑም በላይ ወጣቶቻችን በማይኖሩበት አኗኗር ዘይቤ የተቀረፀው እና በማያውቁት የውጭው ዓለም ባሕል እና አስተሳሰብ የታሸው እሳቤ በራሱ ሌላ ውጥንቅጥ የሆነ ሁኔታ እየፈጠረ ለመሆኑ በቀላሉ ማስተዋል ይቻላል።ይህ ደግሞ ውሎ አድሮ ውጤቱ ትውልዱ የሚኖርበት ማኅበረሰብ ሌላ ነገር ግን የገባበት የማኅበራዊ ሚድያ በአዕምሮው ውስጥ እየፈጠረበት ያለው ደግሞ ሌላ መሆኑ በራሱ በአካል ሀገር ውስጥ በአስተሳሰብ ግን የባዕዳን ተገዢ የሆነ የሀገሩን ችግር የማይፈታ ትውልድ እያፈራን እንዳንሄድ ያሰጋል።ስለሆነም ኢትዮጵያ በማኅበራዊ ሚድያ አንፃር የገጠማት እና ወደፊት ሊገጥማት የሚችለውን ችግር  ያገናዘበ አፋጣኝ እርምጃ መውሰድ አለባት።

ከላይ የተጠቀሰው የማኅበራዊ ሚድያ የራሳቸው ባሕል እና ታሪክ ያላቸው ሀገሮች ገብተው እንደፈለጉ እንዋኝበት ቢሉ ፈፅሞ ሊሆን የሚችል አይደለም።ለእዚህ ደግሞ አስተማሪዋ ቻይና ነች። ቢቢሲ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በመስከረም 1፣2012 ዓም የቻይናን ማኅበራዊ ሚድያ አጠቃቀም አስመልክቶ ''Social media in China: What you need to know" በሚል ርዕስ ባወጣው ዘገባ ላይ ቻይና በዓለም ላይ ካሉ ሁሉ የማኅበራዊ ሚድያን ለገበያ ከሚጠቀሙት ውስጥ ቀዳሚ ሀገር መሆኗን ጠቅሶ ሆኖም ግን ፌስቡክ፣ትውተር እና ዩቱብ ዝግ መሆናቸውን ጠቅሶ ቻይናውያን እነኝህን ማኅበራዊ ሚድያዎች በዜና ምንጭነት እንደማይጠቀሙባቸው ያብራራል።በአንፃሩ ግን ቻይና የራሷ የሆነ ብሔራዊ  ማኅበራዊ ሚድያዎች አሏት።
እነኝህም ወይቦ፣ተንረን እና ዮኩ (Weibo, Renren & YouKu) የተሰኙ ማኅበራዊ ሚድያዎች ሥራ ላይ እንደሆኑ ያብራራል።

ወደ ኢትዮጵያም ስንመጣ መፍትሄው ይሄው ነው።ኢትዮጵያ የሕዝቧን ባሕል፣ስነልቦና፣ታሪክ እና የእርስ በርስ ግንኙነት የሚያጠነክር  የሀገሪቱን የኤሌክትሮኒክስ ገበያ ልውውጥ በሚያፋጥን መልኩ የራሷ የማኅበራዊ ሚድያ በኢትዮጵያ ቴሌ ተቆጣጣሪነት እና አጋዥነት መክፈት አለባት።በእዚህ ማኅበራዊ ሚድያ ታዋቂ አርቲስቶች፣ምሑራን እና ታዋቂ ሰዎች ሁሉ ወጣቱን የሚያስተምሩበት፣ክልል ከክልል የሚተዋወቁበት እና የሚቀራረቡበት፣ወጣቶች በተሻለ መልክ ተቀራርበው ጠቃሚ መረጃዎች የሚያገኙበት ይሆናል።ኢትዮጵያ የራሷ ማኅበራዊ ሚድያ በብሔራዊ ደረጃ ትውልዷን በሚያንፅ እና አሁን ሀገሪቱን እየጎዳ ያለው የጎሳ ፖለቲካን ለማርገብ የራሷን ማኅበራዊ ሚድያ መፍጠር እና ይህ ሀገርኛ ቃና ያለው ማድረጉ በእጅጉ ጠቀሜታ አለው።በእዚህ ትውልድ ይታነፃል፣ማኅበራዊ ሚድያውም ከማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ አገናኝነት በዘለለ ለምጣኔ ሃብቱም የሚያደርገው አስተዋፅኦ ቀላል አይሆንም።ስለሆነም መንግስት ይህንን ጉዳይ በጥብቅ ሊያስብበት ይገባል።ኢትዮጵያ የራሷ ማኅበራዊ ሚድያ በሀገር አቀፍ ደረጃ ስታዘጋጅ ከውጭ የሚመጡትን እንደ ቻይና መዝጋት አይኖርባትም።በሀገር ውስጥ የተፈጠረው በራሱ ተመራጭ ሆኖ ህዝቡ እንዲወደው በማድረግ ብቻ ለውጥ ማምጣት ይቻላል።በሀገር ውስጥ የሚፈጠረው ማኅበራዊ ሚድያ ትስስር መረብ የውጭውን ቀድሞ ወይንም እኩል እንደሚሄድ ለማወቅ ሕዝብ በቀላሉ ባህላዊ መሰረቱን የተበቀለትን ማኅበራዊ ሚድያ እንደሚመርጥ መረዳት በራሱ በቂ ነው።

 ********************************
ማስታወቂያ /Advertisement 
====================
Click the link below to Top-up your friends or family's mobile air time.
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

The Ethiopian Orthodox Tewahedo Church is in turmoil in Athens, Greece.

His Holiness Abune Mathias I, Patriarch of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church, met with Greece's Ambassador to Ethiopia, Antonios Sg...