Thursday, May 13, 2021

''ኢትዮጵያን ለረጅም ጊዜ እናውቃታለን እንደ ደራጎን ለረጅም ጊዜ ተኝታ ድንገት የምትነሳ ሃገር ነች ብለው የግብፁ ፕሬዝዳንት ሳዳት ሲናገሩ ሰምቻለሁ'' ኮለኔል መንግስቱ ኃይለማርያም የሰጡት መግለጫ (ኦድዮ) ሁሉም ሰው ሊያዳምጠው የሚገባ

 የኢትዮጵያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ኮ/ል መንግስቱ ኃይለማርያም ከኢትዮጵያ ከወጡ ግንቦት 13/2013 ዓም ሠላሳ ዓመት ይሞላቸዋል።ከእዚህ በታች ካለው ሊንክ ላይ የኮ/ል መንግስቱ ቃለ መጠይቅ ያድምጡ።በርካታ አሁንም ያለው የኢትዮጵያ አመራርም ሆነ ሕዝብ ሊማርበት የሚገባ ነጥቦች ይዟል።
  
በቃለ መጠይቁ  
>> ደህንነት ሚንስትሩ ተስፋዬ ወ/ስላሴ መጨረሻ ላይ የሰሩትን ክህደት አንስተዋል፣ 
>> አሜሪካ እንዴት ባለሥልጣናቱን እንዳታለለች፣
>> ወደ ኬንያ የሄዱበት ምክንያት ያወሳሉ፣
>> የስነ ልቦና ጦርነት ምን ያህል አሁንም አደገኛ እንደሆነ ያስረዳሉ።
>> ቅድመ አያቶቻችንን አባቶቻችንንም እኛንም ዛሬ የሚፈትነው አንድ ጉዳይ ምን እንደሆነ ያስረዳሉ።
>> ኢትዮጵያ እንደ ሀገር እንድትቀጥል የሚያስፈልገው አንድ እና አንድ ጉዳይ ያስረዳሉ። 
>> የኢትዮጵያ ሕዝብ የተማረ፣በተፈጥሮ በቀላሉ ሊማር የሚችል ጥሩ መሪ ካገኘ ባጭር ጊዜ ያሰበበት የሚደርስ ነው።
>> የኢትዮፖያ ሀብት ከ400 ሚልዮን ሕዝብ በላይ የሚያስተዳድር ሀብት ያላት ሀገር ነች።
ሌሎች እጅግ ድንቅ የሆኑ መልዕክቶች ይዘዋል።ዛሬ ላለንበት ሁኔታ ምላሽ የሚሰጡ ብዙ ሃሳቦች ይዘዋል።እስከመጨረሻ ይከታተሉ።


Wednesday, May 12, 2021

ሱዳን ለሩስያ የባህር ኃይል ወደብ ለመስጠት የተስማማችውን ውል መሰረዝ ለአፍሪካ ቀንድ ፖለቲካ ምን ዓይነት በረከት እና እርግማን ያመጣል?

የሩስያ መርከብ (ፎቶ ታስ ዜና አገልግሎት)

>> የአሜሪካ ኢትዮጵያን በትግራይ ጉዳይ የመጎንተል ሥራ በቅርቡ ወደ መቃብር ይወርዳል።

ጉዳያችን/Gudayachn 


ሱዳን እና ሩስያ የሩስያ ባህር ኃይል ጣብያ በሱዳን ወደብ ላይ የጦር ሰፈር እንዲያገኝ ለመጪዎቹ 25 ዓመታት የሚቆይ ውል መዋዋላቸው የተሰማው ባለፈው ታህሳስ ወር መጀመርያ ሳምንት ላይ ነበር።ስምምነቱ ሩስያ የጦር መርከቦቿን በወደቡ ላይ ከማስፈር ባለፈ የመርከብ ጥገና ስራም የምትሰራበት እንደሚሆን ተጠቅሶ፣የኒኩለር ተሸካሚ መርከቦችን ማሳረፍ የጨመረ ዕድል ለሩስያ ሲሰጣት፣ሱዳን በምላሹ ነፃ የጦር መሳርያዎችን ከሩስያ የማግኘት ዕድል እንደሚከፍት ነው የተነገረው።የሩስያ በሱዳን የባህር ዳር ላይ ቦታ ማግኘት የአፍሪካ መግቢያ በር እንደሚሆናት ታስቦ ነበር።በሌላ በኩል የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃል ኪዳን ሀገሮች (ናቶ) ወደ ደቡብ የሚያደርገውን መስፋፋት ለመግታት የታሰበ የሩስያ አካሄድ ነው በማለት የተነተኑም ነበሩ።

የሩስያ በሱዳን ወደብ ላይ ቦታ ማግኘቷ በዋናነት የቆጠቆጣት አሜሪካ ነበረች።አሜሪካ ከሱዳን ጋር ያላትን ግንኙነት በቶሎ ከማሻሻል አንስቶ ሱዳንን ከአሸባሪ መዝገብ እንድትሰረዝ እና የዓለም ባንክ ገንዘብም ለወቅታዊ ችግሮቿ እንዲሸፍኑ ተሰጥቷታል። አሜሪካ ሩስያ በሶርያ ያላትን መሰረት ማጠናከሯ እንደትልቅ ስጋት የምታየው ሲሆን ወደ ሱዳን ያደረገችውን ግስጋሴ በሱዳን የውስጥ ጉዳይ በመግባት እና በማባበል ውሉ እንዲሰረዝ ያደረገችው አሜሪካ ነች እየተባለች ትታማለች።

የሩስያ ዜና አገልግሎት ''ታስ'' ከሳምንት በፊት እንደዘገበው ስምምነቱ አንድ ዓመት ሳይሆነው ለማቆም መሞከር ሁለቱም ወገኖች አንዳንዳቸው ለአንዳቸው በማሳወቅ ሳይስማሙበት ሊሆን እንደማይችል ከፍተኛ የሩስያ ባለስልጣን እንደገለጡለት ነው ያስታወቀው።ባለሥልጣኑ ይህንን ይበሉ እንጂ ውሉ መሰረዙን ግን የመካከለኛ ምስራቅ መገናኛ አውታሮች እና የሩስያ ዜና አገልግሎትም ገልጧል።

ጉድዩ ለአፍሪካ ቀንድ ይዞት የሚመጣው በረከት እና እርግማን ምንድነው? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ነው። ሩስያ ፊቷን ወደ አፍሪካ እንደ ቻይና እና ምዕራባውያን ማዙሯ የአደባባይ ምስጢር ነው።ለእዚህም የሩስያ አፍሪካ ግንኙነት ላይ ያተኮረ ጉባኤ ከአንድ ዓመት በፊት በሩስያ ከተደረገ በኃላ ቀጣይ ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠው ጉባኤ በአፍሪካ እንደሚደረግ መነገሩ ያታወቃል።ጉባኤውን ለማዘጋጀት ኢትዮጵያ ፈቃደኛ መሆኗን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር  እና የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር አቶ ደመቀ መኮንን አማካይነት መግለጧ ይታወሳል።አማርኛ አቀላጥፈው የሚናገሩት በኢትዮጵያ የሩስያ አምባሳደር ኤቭገኒ ተረኪን ሩስያ የኢትዮጵያ አጋር ሀገር መሆኗን ባገኙት አጋጣሚ ሲገልጡ ተሰምተዋል።ሩስያ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት የኢትዮጵያን ወቅታዊ ጉዳይ አስታኮ የጠራቸውን ስብሰባዎች በሙሉ በመቃወም ማክሸፍ ከቻሉት ሀገሮች ውስጥ ግንባር ቀደሟ ነች።ከእዚህ በኃላ ነው የተባበሩት መንግሥታት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት የሚያከብር እና በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ ላይ መግባት ተገቢ አለመሆኑን አፅንኦት የሚሰጥ መግለጫ ያወጣው። 

የአፍሪካ ቀንድ በሁሉም የዓለም ኃያላን ዘንድ መጪው ቁልፍ የበለጠ ስልታዊ ብቻ ሳይሆን ግዙፍ ምጣኔ ሀብት ይዞ ይወጣል ተብሎ የሚታሰበው እና ለአንዳንዶች ''የሚፈራው'' ጠቅላይ ዓቢይ ወደ ስልጣን እንደመጡ ያቀነቀኑት የኤርትራ፣ኢትዮጵያ እና ሱማሌ የምጣኔ ሀብት ጥምረት ሃሳብ ነው።ይህ ሃሳብ ግዙፍ የገበያ ማዕከል ብቻ ሳይሆን ይዞ የሚመጣው የቀይ ባህርን በተሻለ ጉልበት የመቆጣጠር ኃይል ለሶስቱ ሀገሮች ይሰጣል።ስለሆነም የሩስያ ቀጣይ መንገድ በኤርትራ የባህር ኃይል መሰረት የማግኘት ዕድል ከገጠማት እና ኢትዮጵያ የባህር ኃይሏን እንደጀመረችው ማደራጀት ከቻለች በአካባቢው ላይ ተፅኖ መፍጠር የሚፈልጉ ኃያላን ጥቅማቸው የሚነካ አድርገው ያዩታል።ስለሆነም ሩስያ እና ቻይና ከሚጠቀሙ የአፍሪካ ቀንድ ቢበታተን የሚመርጡ የሉም ማለት አይቻልም።የሶስቱ ሀገሮች የምጣኔ ሐብት ጥምረት ግን ለሦስቱም ሀገሮች ከፍተኛ ጥቅም ይዞ መምጣቱ አያጠራጥርም።በተለይ  በአንፃሩ የተሻለ የሰው ኃይልም ሆነ የምጣኔ አደረጃጀት ያላት ኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥላ የምታጠላበት ጥምረት እንደሚሆን ነው የሚታመነው። ስለሆነም ሶስቱ ሀገሮች በሩስያ እና በአሜሪካ አንፃር የሚጫወቱት ጫወታ ከሀገሮቹ ዘላቂ ጥቅም አንፃር በደንብ አጥንተው የሚገቡበት መሆን አለበት ማለት ነው።

የሩስያ ከሱዳን የባህር ኃይል ማረፍያ አለማግኘት ማለት አማራጭ ቦታ የላትም ማለት አይደለም።በኢትዮጵያ አግባቢነት በኤርትራ የማግኘት ዕድል አሁንም አላት።ይህ እንዳይሆን አሜሪካ ኢትዮጵያን የማትለምንበት መንገድ አይኖርም።በእርግጥ ከመለመን በፊት አሜሪካ በትግራይ ጉዳይ አሳባ ብዙ የማወክ ሙከራ በኢትዮጵያ ላይ ላለፉት ስድስት ወራት ስታስኬድ ሰንብታለች።በውጤቱ ግን የተሳካ ሆኖ አላገኘችውም።የግብፅ የደህንነት ባለስልጣናት ለአሜሪካ 'የኢትዮጵያን ነገር ተይው ከውስጥ የጀመርነው ፕሮጀክት አለ' እያለች ስታማልል ብትከርምም በቅርቡ ግን ከቤንሻንጉል እስከ መቀሌ ያለው የተንኮል ድር በሙሉ በመበጣጠሱ አሜሪካ ከሰሞኑ የመለሳለስ መልክ ብታሳይም አይገርምም።

አሁን የአሜሪካ ስጋት ሩስያ ከኢትዮጵያ ጋር ከገጠመች በተለይ በኤርትራ ወደብ የባህር ኃይል ከመሰረተች ከሶርያ ቀጥሎ ሩስያ ቁልፍ ማረፍያ እንዳገኘች ትቆትረዋለች ብቻ ሳይሆን ከመካከለኛው ምስራቅ ወደ አፍሪካ የምታደርገው እመርታ ወሳኝ ምዕራፍ እንደሆነ ተረድታዋለች። ይህም ከቀዝቃዛው ጦርነት በኃላ ሩስያ እንደገና ወደ አፍሪካ አንፃር አንሰራራች ማለት ነው።ስለሆነም የሱዳን ውል ማፍረስ ለኢትዮጵያ ይዞ የሚመጣው አንዱ በረከት አሜሪካ ኢትዮጵያን በትግራይ ጉዳይ መጎንተሏን ታቆማለች ወይንም ታቀዘቅዛለች።በመቀጠልም ሰሞኑን እያሳየች እንዳለው የዓባይ ግድብ አንፃር ኢትዮጵያ የራሷን የተፈጥሮ ሀብት የማልማት መብት አላት የሚለውን አረፍተነገር በመደጋገም ታፈገፍጋለች።ኢትዮጵያ ይህንን የሩስያን ጉዳይ ከኤርትራ ጋር ተመካክራ እንደ ታላቅ ወንድም እያስፈራራች ምርጫውን እና የውሃ ሙሌቷን ከጨረሰች ቀሪውን ውሳኔዋን ከመስከረም አደይ አበባ መፈንዳት ጋር ቀስ ብላ ቡና ፉት እያለች መወሰን ትችላለች።

ለማጠቃለል የአሜሪካ በትግራይ ጉዳይ ኢትዮጵያን የመጎንተል ሂደት በቅርቡ ወደ መቃብር በእዚሁ በሩስያ ጉዳይ እንደሚያበቃ ግን ከወዲሁ መገመት ይቻላል።ይህ ማለት አንዳንድ በሎቢ የቀወሱ ሴናተሮች እና ጋዜጠኞች ዝም ይላሉ ማለት አይደለም። ዋናዎቹ የውጭ ፖሊሲ አውጪዎች ግን አንዳች እርምጃ ሊወስዱ አይችሉም ቢያንስ ለመጪዎቹ አራት ወራት።ሌላው ቀርቶ የአውሮፓ ህብረት አዲስ የሳተላይት መሳርያ ካላስገባሁ፣የምርጫ ውጤቱን እኔ ቀድሜ የመናገር መብት ካላገኘሁ እያለ ትንሽ  ጠገብ ብሎ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ሃሳቡ ተቀይሮ ባላችሁት መሰረት ለምርጫው ታዛቢ እልካለሁ ማለቱ ሁሉ የኢትዮጵያ ቦታ መልሶ መሬት እየቆነጠጠ መሆኑን ብቻ ሳይሆን የሚያሳየው አፍሪካ ቀንድ ላይ ያለው መራኮት ኢትዮጵያን ከሁሉ በላይ አስፈላጊ መሆኗንም ጭምር ነው።ይህ እንግዲህ በመላው አፍሪካ ላይ ያላትን ተፅኖ የመፍጠር አቅም ሳናነሳ ነው።ኢትዮጵያውያን ግን አሁን ማተኮር የሚገባው ግዙፍ እርዳታ በተለይ በቤተ እምነቶች አንፃር ለትግራይ እና በልዩ ልዩ ስፍራ አደጋ እና ጥቃት ለደረሰባቸው ኢትዮጵያውያን የእርዳታ ሀብት ማሰባሰብ እና መርዳት ነው።የኢትዮጵያ ቁስል ይሽራል።ከትግራት እስከ መተከል፣ከአጣዬ እስከ ወለጋ የተጎዱትን የመርዳቱ ተግባር ግን መቀጠል አለበት።
=======================////=============

Tuesday, May 11, 2021

የክርስትና እና የሙስሊም የእምነት አደረጃጀቶች የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች እንዳይጎትቷቸው መጠንቀቅ አለባቸው።


ጉዳያችን/Gudayachn


ኢትዮጵያ የእምነት ሀገር ነች።ህዝቧ ከሊቅ እስከ ደቂቅ በፈጠረው አምላክ ያምናል።በችግሩ እና በደስታው ጊዜ ብቻ ሳይሆን በሰላምታው ጊዜም ሳይቀር አምላኩን የሚጠራ ሕዝብ ነው።ይህ ሕዝብ ካለምንም ማጋነን ከየትኛውም የዓለማችን ክፍል በተለየ እና በፀና ደረጃ በብዙ ፈተና ውስጥም ቢሆን ከፈጣሪው ጋር ግንኙነት አለው።በሌላው ሀገር የማናገኘው የሞራል ልዕልና በኢትዮጵያውያን ላይ የሚታየው ሌላ ሳይሆን የሕዝቡ በፈጣሪው ላይ ያለው ዕምነት ነው።በቅርቡ በአዲስ አበባ አስተዳደር ከፍተኛ ባለስልጣን እንደተገለጠው በአዲስ አበባ ብቻ በቀን አንዴ በልተው ለማደር የሚቸገሩ ከአንድ መቶ ሺህ በላይ ሕዝብ አለ።በእዚህ ደረጃ ችግር ላይ ያለ ሕዝብ ግን የእምነት ሕዝብ ስለሆነ አንዱ አንዱን እየረዳ የሚኖር የተቸገረውም በትሕትና እንጂ በነጠቃ የማይኖርባት ሀገር መሆኗን ይህ በራሱ ምስክር ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ይህ ወቅት የኢትዮጵያ የክርስትናም ሆነ የሙስሊም አደረጃጀቶች ከመቼውም ጊዜ በላይ ነቅተው እና ተግተው የሚቆሙበት ጊዜ ነው።በሁለቱም ዕምነቶች ውስጥ አደረጃጀቶቻቸውን ለመክፈል እና የፀብ መድረክ ለማድረግ በተለያዩ የፖለቲካ አካላት ጉተታ ይታያል።ጉተታዎቹ ሦስት ዓላማዎችን ይዟል። እነርሱም -  የእምነት ድርጅቶቹን እርስ በርስ በውስጣቸው ሰላም እንዳያገኙ ማበጣበጥ፣ከመንግስት ጋር ማጋጨት እና አንዱን እምነት ሌላውን እንዲጠራጠር ወሬ መንዛት ናቸው። 

በእስልምናም ሆነ በክርስትና ውስጥ ያሉ የውስጥ ቁርሾዎችን ማባባስ እና አደረጃጀቶቹ ሰላም እንዳይሆኑ በማድረግ ተከታዩ ምዕመንን ሰላም መንሳት እና በውጤቱ ሀገር እንዳይረጋጋ እና ሰላም እንዲጠፋ በማድረግ ርካሽ የፖለቲካ ግብ መምታት ነው።
በእዚህ መሰረት በሙስሊም ኢትዮጵያውያን ውስጥ የበላይ አመራር መጅሊሱን ሕዝብ እንዳይቀበል የሚቀሰቅስ ቅስቀሳ በማካሄድ የፅንፍ ኃይሉ የበላይ እንዲሆን የማድረግ ሙከራ ነው።

በተመሳሳይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንም ውስጥ ተመሳሳይ ድርጊቶች ይታያሉ።በተለይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሰሞኑን ቅዱስ ፓትርያሪኩ ከአንድ ወር በፊት የተቀዳው እና ወቅታዊ የኢትዮጵያን ሁኔታ የተመለከተ ቪድዮ ሰሞኑን መለቀቁን  የቤተክርስቲያኒቱን መዋቅር እና ድምፅ በትክክል የማይወክሉ የቤተክርስቲያኒቱ አገልጋዮች እዚህም እዝያም በሚድያ እየቀረቡ በቤተክርስቲያኒቱ ስም ሲናገሩ እየታየ ነው።በተለይ የኢትዮጵያ ሚድያዎች የቤተክርስቲያኒቱን ተዋረድ ሳይጠብቁ ያገኙትን ካህን በቤተክርስቲያኒቱ ስም ማናዘዝ እጅግ አደገኛ አካሄድ ነው።ቤተክርስቲያኒቱም የህዝብ ግንኙነት በተመለከተ በማዕከላዊነት የምትመራበት አንድ ድምፅ እንዲኖራት እና ማንም ከእዚህ ማዕከላዊ የህዝብ ግንኙነት ውጪ በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የሚናገር አገልጋይ እንዳይኖር ጥብቅ መመርያ ያስፈልጋታል። 

ሌላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንም ሆነ የእልምና ተከታዮች በተለያየ ጥግ ሆነው ከመንግስት ጋር እንዲጋጩ የሚሰሩ አሉ። እነኝህ የተለያየ ዓላማ የያዙ ናቸው።በእስልምና ውስጥ እጅግ ፅንፍ የያዘ እና የራሱን መጅሊስ ቆርጥሞ በልቶ እና እውነተኛ አማኙን ከመስጊድ አስወጥቶ በሌሎች ሀገሮች የሚታየው የፅንፍ አስተዳደር በእምነት ስም መለጠፍ የምፈልገው ቡድን በቅድምያ ሙስሊሙ ከመንግስት ጋር እንዲጋጭ ማድረግን እንደዋና ግቡ ወስዶታል።ለእዚህም ያገኘውን  እያሰፋ ነገር ስጎነጉን የሚያድር ነው።ይህንን አብዛኛው ሙስሊም ስላወቀበት አንዳንዴ ተመሳስሎ ሲቆም ይታያል።

በተመሳሳይ መንገድ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንም ውስጥ በተለይ ላለፉት 27 ዓመታት በሌሎቹ የእምነት አደረጃጀቶች ውስጥ የታየው  ፀሐይ የሞቀው የአንድ ብሔር የበላይነት ባለፉት ሦስት ዓመታት በኢትዮጵያ በመጣው ለውጥም ሆነ በቀድሞው ሥርዓት ላይ በቅርቡ የተወሰደው የሕግ ማስከበር እርምጃ ሳይቀር ስላስከፋው ቤተክርስቲያኒቱን ለመከፋፈል በተለይ በውጭ ሀገር አንዳንድ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርግ እየታየ ነበር።ይሄውም የትግራይ ካሕናትን ከቅዱስ ሲኖዶስ ስር ለመለየት አንዳንድ እንቅስቃሴዎች ሲያደርጉ ታይተው በትግራይ ካህናት ሳይቀር ከፍተኛ ተቃውሞ ስለገጠመው አድፍጦ መቀመጡ እየታየ ነው። በተለይ የእዚህ ዓይነቱ ቡድን በትግራይ በሚኖሩ አባቶች ቢሰማ የሚደርስበትን ውግዘት የተረዳው ቡድን ቤተክርስቲያኒቱን ለመረበሽ አንዳንድ ያልተሳኩ እና የማይሳኩ ሙከራዎች እያደረገ ነው።

የመጨረሻው በኢትዮጵያ የክርስትና እና የእስልምና አደረጃጀቶች ውስጥ እየታዩ ያሉ ተግዳሮቶች አንዱ ሌላውን በጥርጣሬ እንዲመለከት ማድረግ ነው።ይህ ደግሞ የሐሰት ወሬዎች በመንዛት ሲሆን በፅንፍ አካሄድ የሚታወቁ የፖለቲካ ድርጅቶች ዋና አቀጣጣዮች ናቸው።ይህ አለመተማመን የመፍጠር ሂደት በተለይ የእምነቶቹን ሊቃውንት ያገለለ በመሆኑ ''መደዴ'' የሆኑ የእምነቱ ተከታዮች ቀድመው በመናገራቸው ወይንም በመሳደባቸው ''እንደመሪ'' እየሆኑ የሚወጡበት ስለሆነ አደገኛ አካሄድ ይታይበታል።

ባጠቃላይ  የክርስትና እና የሙስሊም የእምነት አደረጃጀቶች የተለያዩ የፖለቲካ እና የፅንፍ ኃይሎች ጉተታ ውስጥ እንዳይገቡ  ከመቼውም ጊዜ በላይ የእስልምናም ሆነ የክርስትና አደረጃጀቶች የውስጣዊ ጥንካሪያቸውን፣በልቃውንቶቻቸው እና በሕጎቻቸው ላይ ብቻ በተመሰረተ መንገድ መመራታቸውን በደንብ መፈተሽ አለባቸው። 99% የሚሆን ሕዝብ በፈጣሪው የሚያምን ሕዝብ  ሀገር የእምነት አደረጃጀቷ ጤነኛ ብቻ ሳይሆን ለሀገር እድገትም አዎንታዊ አስተዋፅኦ ያለው እንዲሆን ያለምንም ወገንተኝነት የማገዝ ግዴታ ደግሞ መንግስት አለበት።መንግስት የኢትዮጵያ የእምነት አደረጃጀቶች መጠናከር እና ምእመናኖቻቸውን በሚገባ ማገልገል ማለት ሃገራዊ ሰላም ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን በሰላም የማሸጋገር አንዱ እና ወቅታዊው ወሳኝ ተግባር ነው።ከሁሉም በላይ ወሳኞቹ ግን የክርስትናም ሆነ የእስልምና የውስጥ ጤነኛ፣በፖለቲካ ኃይሎች ያልተዘወረ ግን የእምነት ነፃነቱን የጠበቀ የእምነት አደረጃጀት እንዲኖራቸው ጠንክረው ሲሰሩ ነው። ''እውነት አርነት ያወጣችኋል'' ዮሐንስ 8፣32 እንዲል ታላቅ ሀገር ኢትዮጵያን ነፃ የሚያወጣት፣ እምነቷን ጠብቆ የሚያቆይም እውነት እንጂ የተለያዩ አመለካከቶች ጉተታ እና የእነርሱ ሰለባ መሆን አይደለም።

========================///=============

እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው።"
(ዮሐንስ 8:32)
እውነትም አርነት ያወጣችኋል አላቸው።"
(ዮሐንስ 8:32)

Thursday, May 6, 2021

ጠ/ሚ/ር ዓቢይ ኢትዮጵያን ተረድቷታል PM Abiy Ahmed speech



“ህወሓት” እና “ሸኔ” በሽብርተኝነት እንዲፈረጁ በሚኒስትሮች ምክርቤት የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ የተወካዮች ምክርቤት ዛሬ አፀደቀ

Ethiopian Parliament approved the Council of Ministers decision to designate ''TPLF" & "Shene" as terrorist organization
.“ህወሓት” እና “ሸኔ” በሽብርተኝነት እንዲፈረጁ በሚኒስትሮች ምክርቤት የቀረበውን የውሳኔ ሀሳብ ዛሬ የተወካዮች ምክርቤት አፅድቆታል። የኢትዮጵያ ብሮድካስት ኮርፖሬሽን ጉዳዩን አስመልክቶ ዛሬ የዘገበው እንደሚከተለው ይቀርባል።
የሚኒስትሮች ምክር ቤት “ህወሓት” እና “ሸኔ” በሽብርተኝነት እንዲፈረጁ ባቀረበው የውሳኔ ሀሳብ ላይ ምክር ቤቱ በዛሬው መደበኛ ስብሰባው ከተወያየ በኋላ ውሳኔውን አሳልፏል።
ሁለቱ ቡድኖች በአገር እና በህዝብ ላይ የሽብር ተግባራትን በመፈፀም ላይ በመሆናቸው በሽብርተኝነት መፈረጃቸው አግባብ መሆኑን በመጠቅስ ነበር የሚኒስትሮች ምክር ቤት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሳኔ ሀሳቡን እንዲያፀድቀው አቅርቦ የነበረው።
የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በወጣው ዐዋጅ ቁጥር 1176/2012 አንቀጽ 18 እና 19 መሠረት “ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሓት)” እና “ሸኔ” የሽብር ወንጀልን ዓላማቸው አድርገው የሚንቀሳቀሱ በመሆኑና የድርጅቶቹ የሥራ አመራር ወይም ወሳኔ ሰጭ አካላት ወንጀሉን አምነው የተቀበሉት ወይም አፈጻጸሙን እየመሩት በመሆኑ፤ የሽብር ተግባር መፈጸምም የድርጅቶቹ ጠቅላላ መገለጫ በመሆኑ፤ ድርጅቶቹ በሽብርተኛ ድርጅትነት እንዲሰየሙም ሲል የሚኒስትሮች ምክር ቤት የውሳኔ ሐሳቡን ማቅረቡ ይታወሳል።
በመሆኑም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በዛሬው ውሎው “ህወሓት” እና “ሸኔ” በሽብርተኝነት እንዲፈረጁ በቀረበለት የውሳኔ ሀሳብ ከተወያየ በኋላ በሙሉ ድምፅ ውሳኔውን አሳልፏል።

Saturday, May 1, 2021

በአዲስ አበባ በቅርቡ ሰልፍ ያስፈልጋል! ለምን? ከፅሁፉ መልሱን ያገኙታል።ሕዝብ ይወያይበት መንግስትም ያስብበት።


ጉዳያችን/Gudayachn 

ኢትዮጵያ በነፃነቷ ከክፍለ ዘመን ወደ ክፍለዘመን የተሻገረች ሀገር ነች።እነኝህ የነፃነት ጉዞዎች እጅግ ውጣ ውረድ በተሞላባቸው የታሪክ ሂደቶች አባቶቻችን እያለፉ ሀገሪቱን ዛሬ ላለንበት ዘመን አሸጋግረውልናል።አሁን ያለንበት የዓለማችን ወቅታዊ ሁኔታ ደግሞ አንድ ዓይነት የሥርዓት ለውጥ ለማድረግ ፍትጊያ ላይ ነው።ከሀያኛው ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ ዓለምን ለመቆጣጠር የቻሉ ከነበሩበት ላለመውረድ የሚጥሩበት፣ተበድለው የነበሩ ከበደላቸው ሰብረው ለመውጣት የሚጥሩበት እና አዳዲስ ኃይሎች ደግሞ ወደፊት የሚመጡበት ጊዜ ነው።በዓለም ታሪክ በሁለተኛውም ሆነ በአንደኛው የዓለም ጦርነት የዓለም ስርዓት እንዲሁ ተቀይሯል።በዘመናችን ከተነሳው የኮቪድ ወረርሽኝ በኃላ የዓለም ስርዓት ፍትጊያ ያጣዋል ማለት አይቻልም።

የእነኝህ ፍትግያዎች አንዷ ሜዳ ደግሞ አፍሪካ ነች።አፍሪካ ከቅኝ ግዛት ብትላቀቀም ከእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ ግን ገና አልወጣችም።በመሆኑም አፍሪካውያን ዛሬ የፖለቲካ ነፃነታቸውን ካገኙ ከግማሽ ክፍለዘመን በኃላም በሀብት ላይ ተቀምጠው በድህነት እየማቀቁ ነው። የበለፀጉ ሀገሮች አፍሪቃውያንን ከሚያዋክቡባቸው መንገዶች ውስጥ አንዱ የምርጫ ሂደትን መተቸት ነው።ምርጫ ያላደረጉት ባለማድረጋቸው ሲወቀሱ ያደረጉት ደግሞ ሂደታቸው ይተቻል።ይህ በራሱ ችግር የለውም።ምርጫ አድርጉ ማለት እና ሂደቱ ላይ ሃሳብ መሰጠት ለበጎ ብለን እንውሰደው።ሆኖም ግን እኛ ያላቦካነው ዳቦ አይሆንም ዓይነት መቀባጠር የእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ አባዜ ጉዳይ ነው።

ኢትዮጵያ በግንቦት ወር መጨረሻ የምታደርገው ምርጫ በሀገሪቱ ታሪክ በምርጫ ኮሚሽን አደረጃጀትም ሆነ አፈፃፀም እጅግ የተሻለ እና የውስጥ ነቃፊዎች ሳይቀሩ የኮሚሽኑን አደረጃጀት እና አፈፃፀም ለመተቸት ቃላት ያጠራቸው ጊዜ ነው።ምክንያቱም እንከን ለማውጣትም እንከን ማግኘትን ይጠይቃል። አንዳንዶች በህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን የምርጫ አጃቢ የነበሩ ዛሬ ሁኔታው ግልጥ እና አስተማማኝ ሲሆን ምርጫው ላይ አንሳተፍም ቢሉም ምክንያታቸው በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት አጥተው ከመሸማቀቅ ባለመሳተፋችን ነው እንጂ እናሸንፍ ነበር እያሉ ከቤት ተቀምጠው መሸለሉ የተሻለ ስለመሰላቸው ነው።ለምሳሌ ፕሮፌሰር መራራ እና ድርጅታቸውን መጥቀስ ይቻላል።ለእነርሱ የተከተሉት መንገድ አዋጪ መስሏቸው ይሆናል።ሆኖም ግን ወክለነዋል የሚሉት ሕዝብ አንቅሮ የሚተፋቸው ጊዜ መሆኑን የፖለቲካ ምሑር የሆኑት አለመረዳታቸው ነው አስገራሚው ነገር።

ኢትዮጵያ መጪውን ምርጫ ልታደርግ በሄደችበት ሂደት ላይ እንቅፋት ይገጥማታል ብለው አድፍጠው የነበሩ አንዳንድ የምዕራብ ሀገር ባለስልጣናት አሁን የምርጫው ሂደት እየሰመረ መሆኑን ሲያውቁ የሚይዙት የሚጨብጡት ተፍቷቸዋል።በመሆኑም ከአሁኑ ምርጫው ዓለም አቀፍ መስፈርት አያሟላም እያሉ መለፈፍ ይዘዋል።ዓለም አቀፍ መስፈርት ማለት እነርሱ ይሁን ሲሉት የሚሆን እነርሱ ሲከለክሉ የሚቀር አድርገው ያስባሉ።ዓለም አቀፍ የምርጫ መስፈርት በሚለው መሰረት ኢትዮጵያ በቅርቡ የምታደርገው ምርጫ  ደረጃውን የጠበቀ ነው።ለዓለም አቀፍ የምርጫ መስፈርት አንዱ መነሻ ሕግ የተባበሩት መንግሥታት እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1948 ዓም  ያወጣው ሁሉን አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌ ነው።በእዚህ ድንጋጌ ላይ አንዱ እና ዋነኛ መስፈርቱ ምርጫ ሀገሮች በየተወሰነ ጊዜ የማድረጋቸውን አስፈላጊነት ጠቅሶ ምርጫው ሕዝብ በሚስጥር የመስጠቱን ፋይዳ በዋናነት ያነሳል።ይህ ደግሞ በዋናነት የሚያከናውነው የምርጫ ቦርድ አደረጃጀት፣አፈፃፀም እና የእስካሁኑን ሂደት ተረድቶ በምን ያህል የተሻለ ደረጃ ኢትዮጵያ እየሄደች እንዳለ ግልጥ ነው።የሚገርመው አንዳንድ የአሜሪካ ሴናተሮች በሺህ ማይሎች ርቀት ላይ ተቀምጠው የኢትዮጵያን ምርጫ ሊተቹ መሞከራቸው ነው። እንደነርሱ አባባል ከእዚህ በፊት ፕሬዝዳንት ኦባማ አዲስ አበባ ላይ ሱዛን ራይስ አሜሪካ ላይ ሆነው የህወሓት/ኢህአዴግን  የምርጫ ፌዝ ''ዲሞክራሲያዊ'' እያሉ ሲሳለቁ ያልታዘብናቸው ይመስላቸዋል።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሉአላዊነቱ የማይበገር መሆኑን ድምፁን የሚያሰማበት ጊዜ አሁን ነው። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ድምፃቸውን አሰምተዋል።አሁን የአዲስ አበባ ሕዝብ ድምፁን የሚያሰማበት ጊዜ የደረሰ ይመስለኛል።በመሆኑም አደባባይ ወጥቶ የማንንም የፖለቲካ ድርጅት ሳይነቅፍ እና ሳያጥላላ ነገር ግን በኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳይ አትግቡ የሚል ድምፁን ማሰማት አለበት። ይህ ብቻ አይደለም ግብፅንም ሆነ ሱዳንን በእዚሁ ሰልፍ ማስጠንቀቅ አለበት።ዛሬ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ያስተላለፈውን በህወሓት እና ኦነግ ሸኔ ላይ የሽብርተኝነት የውሳኔ ሃሳብ ስልፉ መደገፍ አለበት።ይህ ሰልፍ ለኢትዮጵያ የሚሰጠው ጥቅም አለ።ጥቅሞቹም - የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነት ለባዕዳን ያሳይበታል፣የራሱን ሕብረት ዳግም ያረጋግጥበታል፣ለኢትዮጵያ ጠላቶች ማስጠንቀቅያ ይሰጥበታል፣ሌላው የባዕዳንን ተንኮል ላልሰማ ኢትዮጵያዊም በሰልፉ ምክንያት እንዲነቃ ያደርገዋል። ስለሆነም አዲስ አበባ በመስቀል አደባባይ ወይንም በጃንሜዳ ወይንም ሌላ አመቺ ስፍራ ድምፁን ከፍ አድርጎ ማሰማቱ መልካም ለሚሰሩ የመንግስት ኃላፊዎችም ሕዝብ  ከበጎ ስራቸው ጎን ሁል ጊዜ የሚቆም እንደሆነ የሚያረጋግጡበት አንዱ የሞራል ስንቅም ነው። ሰልፉ ሲደረግ ሁለት አስጊ ጉዳዮች አሉ።እነርሱም ኮቪድ -19 ወረርሽኝ እና ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች የፀጥታ ችግር እንዳይሆኑ የሚሉት ናቸው።ሆኖም ግን የሰልፉ መልዕክት በተለይ በእዚህ ካለው ጥቅም አንፃር እያንዳንዱ ሰው የአፍ  እንዲያደርግ እና እርቀት እንዲጠቅብ በማድረግ እና የፀጥታ ጥበቃውንም በማጠናከር (ወደ ሰልፉ የሚሄዱትን መፈተሽ ጨምሮ) ጥንቃቄ ከተደረገ የሰልፉ የኢትዮጵያውያንን ሕብረት ከማንፀባረቁ አንፃር ጥቅሙ ከፍተኛ ነው።

ለማጠቃለል የአሜሪካን እና አጋሮቿን በኢትዮጵያ ጉዳይ ጣልቃ መግባት የሚቃወም ግዙፍ ሰላማዊ ሰልፍ በአዲስ አበባ ያስፈልጋል።ይህ ሰልፍ አስፈላጊ ነው ያልኩባቸው አምስት ምክንያቶች  -

1) ለአሜሪካ ግልፅ መልዕክት ከኢትዮጵያ ሕዝብ ያስተላልፋል።መንግስት ሕዝባዊ ድጋፍ የለውም የሚል ግምት ላላት አሜሪካ መልዕክት አለው።

2) በሰልፉ ላይ የዲሞክራቶችን የአፍሪካ ፖሊሲ በግልጥ መቃወም። በእዚህም ጉዳዩ የውጪ ፖሊሲ ክስረት እንደሆነ ለአሜሪካ ሕዝብ እና ምሁራን መልዕክት ያስተላልፋል።

3) አሜሪካኖች አፍሪካን የማጣት ዕድል እንደሚገጥማቸው ግልጥ መልዕክት ስለሚያስተላልፍ በሪፓብሊካን እና ዲሞክራቶች  ፖሊሲ አውጪዎቹ መካከል ቆይቶም ቢሆን አከራካሪ ጉዳይ መፍጠሩ አይቀርም።

4) የአሜሪካን ጣልቃ ገብነት የሚቃወሙ ሀገሮችም ከኢትዮጵያ ጎን እንዲቆሙ ጥሪ ያደርጋል።በአሜሪካ አንፃር ያሉ ሀገሮች የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያሳየውን ተቃውሞ አይተው ከኢትዮጵያ ጎን መቆም ዘለቄታዊ ጥቅም መሆኑን እንዲያስቡ ያደርጋል።

5) ለኢትዮጵያ ሕዝብ ለራሱም የአሜሪካ ጣልቃ ገብነት በምን ያህል ደረጃ አደጋ መሆኑን ያሳስባል።የአሜሪካ የጣልቃ ገብነት አደጋ በምን ያህል አደጋ እንዳለው በኢትዮጵያ ከገጠር እስከ ከተማ እኩል ተረድቶታል ማለት አይቻልም።ይህ ሰልፍ ግን የጉዳዩን አደገኛነት ለራሱ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማሳሰብያ ይሰጣል።

ኢትዮጵያን ፈጣሪ በጥባቆቱ ልጆቿ በተጋድሏቸው ተጠብቃ ለዘላለም ትኑር!

The Ethiopian Orthodox Tewahedo Church is in turmoil in Athens, Greece.

His Holiness Abune Mathias I, Patriarch of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church, met with Greece's Ambassador to Ethiopia, Antonios Sg...