ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, January 14, 2021

ኦነግ ሸኔ በመተከል ቢሮ ከፍቶ እየሰራ መሆኑ ተነገረ።የመተከል እልቂት አሁንም መፍትሄ አላገኘም።




የቤንሻንጉል ክልል ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቶማስ በሕዝቡ ላይ እየደረሰ ስላለው መከራ ምን እያደረጉ ነው?

ባለፈው ዓመት የካቲት/2012 ዓም  አዲስ አበባ የሚገኘው ኢትዮ ኤፍ ኤም በቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል መከላከል ዘርፍ ም/ል ኮሚሽነር ነጋ ጃራን ጠቅሶ የኦነግ ሸኔ የታጠቁ አካላት ወደ ክልሉ ገብተው ንብረት አቃጥለው እና ዘርፈው ሸሽተዋል ብለዋል።ዜናው አክሎም  ድርጊቱ የተፈጠረው ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም በአሶሳ ዞን ውስጥ ባባሲ ወረዳ ውሽማ ጥርጊጊ የሚባል ቀበሌ ላይ ቁጥር 1 እና ቁጥር 2 የሚባሉ ቦታዎች ነው ይላል።ከዚህ በፊትም ይላል ዘገባው በዚህ ቀበሌ ይኖሩ የነበሩ 4 ሰዎች አካባቢውን ለቀው የሄዱና በኋላም የኦነግ ሸኔ ቡድን የተቀላቀሉ ነበሩ፡፡የኋላ ኋላ እነርሱን ጨምሮ ወደ 28 የሚደርሱ የታጠቁ ሀይሎች በ25/5/2012 ዓ.ም ወደ ቀበሌው መጥተው የቀድሞውን የቀበሌ ሊቀ መንበር አቶ አደም ጉምዛ የተባለውን ግለሰብ ያገኙታል፡፡እኚህን የቀድሞ ሊቀመንበር ባገኙ ሰዓት በወቅቱ የነበራቸው ፍላጎት የጦር መሳሪያና ከዚህ በፊት የተሰበሰበ ግብር አለ እርሱን ማምጣት አለብህ ብለው በጠየቋቸው ሰዓት ምንም እንደሌለ በመንገር ይመልሷቸዋል፡፡በኋላም የዚህን ሰውዬ 6 ቤቶች አቃጥለው 3 ኩንታል ቦሎቄ ፤ ሁለት ኩንታል ጤፍ 1 ኩንታል ጥቁር አዝሙድ ግማሽ ኩንታል ተልባና ሁለት ኩንታል ኑግ በሳት ማቃጠላቸው ተገልጿል።በዛው ቀበሌ ውስጥ ያገኙትን የኢትዮጵያና የክልሉን ሰንደቅ አላማ በማቃጠል ከሚኒሻዎችና ከግለሰቦች ላይ መሣርያዎች ነጥቀው አመለጡ ይላል አምና የተለቀቀው ዜና።

ይህ ዜና ከተዘገበ አንድ ዓመት ሊሆነው ቀናት ነው የቀሩት።ዜናው ግን በቤንሻንጉል ጉሙዝ እየተፈፀመ ያለ የፍጅት ተግባር እንጂ የኦነግ ሸኔ ተግባር ብዙም አይነገረም።ኦነግ ሸኔን በተመለከተ እስካሁን በኦሮምያ ክልል የሚነገረው ይህንን ያህል የኦነግ ሸኔ ጀሌ ተገደለ ወይንም የእዚህ አካባቢ ሕዝብ ኦነግ ሸኔን ተቃውሞ ሰልፍ ወጣ የሚል ነው።ብዙዎች ተገደሉ የሚባለው የኦነግ ሸኔ ቁጥር ላይ ጥርጣሬያቸውን ይገልጣሉ።ለእዚህ ጥርጣሬያቸው መነሻ የሚያደርጉት የኦነግ ሸኔ ሰዎች እራሱ ብልጥግና  ኦሮምያ ውስጥ አሉ የሚል ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ዛሬ ጥር 6/2013 ዓም መቀመጫውን በአሜሪካ ያደረገው የአደባባይ ሚድያ የኢትዮጵያን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ ባደረገው ውይይት ላይ የመተከልን የሰሞኑን በጉሙዝ አሸባሪዎች የተፈፀመውን እልቂት እና የህዝብ መፈናቀል አስመልክቶ ክልሉን በሚገባ ከሚያውቁ ከመምህር አበራ ጋር በቀጥታ የቪድዮ ውይይት ላይ በክልሉ ነዋሪ በሆኑ የአማራ፣ኦሮሞ፣ሽናሻ እና አገው ላይ የደረሰው ጥቃት ያስከተለው አሰቃቂ እልቂት እና ሰብዓዊ ቀውስ አስመልክተው ልብ በሚነካ መልኩ አብራርተዋል።መምህር አበራ የቤንሻንጉል ክልልን በሚገባ እንደሚያውቁት በሥራ ዓለምም ሆነ በቅርቡ ከሳምንት በፊት ወደ ክልሉ ሄደው እንደመጡ እና የተመለከቱት ሁኔታ ሁሉ እጅግ እንዳሳዘናቸው ሲገልጡ  ከስልሳ በላይ አስከሬን በመኪና እየተጫነ መራገፉ፣በሺህ የሚቆጠር ሕዝብ በብርድ ካለምንም መጠለያ እና አንድም የክልሉ መንግስት መጠየቅ ሜዳ ላይ እንደወደቁ እና አንዲት እናት ሜዳ ላይ መውለዷን ሁሉ በሚያሳዝን አገላለጥ አብራርተዋል።ከእዚህ በመቀጠል መምህር አበራ  የኦነግ ሸኔ ፅህፈት ቤት መተከል ውስጥ መኖሩን እና ይህንንም ለሚመለከተው የመንግስት አካል በተደጋጋሚ ማመልከታቸውን ገልጠዋል። 

በመጨረሻም በእዚሁ ውይይት ላይ መምህር አበራ የክልሉ ሕዝብ ላይ እየደረሰ ያለውን ጥፋት መንግስት ተገቢውን ሕግ የማስከበር ተግባሩን እንዲያከናውን መጮህ ብቻ ሳይሆን ወደተሰደዱት ወርደው ማፅናናት ይገባቸው እንደነበር የጠቀሷቸው የክልሉ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቶማስ ናቸው።መምህር አበራ ሊቀ ጳጳሱ በክልሉ ሕዝብ ላይ ለሚደርሰው እልቂት እና ስደት ድምፃቸውን አለማሰማታቸው አሳዛኝ መሆኑን አምርረው ተናግረዋል። 

በቤንሻንጉል፣መተከል  በቡለን ወረዳ በኩጅ ቀበሌ ከሶስት ሳምንት በፊት ማንነትን መሰረት ባደረገ በአራት አቅጣጫ በታጠቁ ኃይሎች በደረሰ ጥቃት  222 ኢትዮጵያውያን ከዓማራ፣ሽናሻ፣አገው እና ኦሮሞ ተወላጆች በአሰቃቂ ደረጃ ህይወታቸውን ማጣታቸው ይታወሳል።ግድያው በክልሉ ልዩ ኃይል ጭምር መከናወኑን የአይን ምስክሮች መግለጣቸው እና በግድያው ላይ አንድ አባት ዘጠኝ ልጆቻቸውን ካጡት ጀምሮ በአንድ ቤተሰብ እስከ 12 የሚደርሱ የቤተሰብ አባላት መገደላቸው እና የሞቱትን አስከሬን በግሬደር ተግዘው በጅምላ መቀበራቸው ይታወሳል።እዚህ ግድያ በኃላ  የቤንሻንጉል ክልል የፀጥታ ጉዳይ በጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ አህመድ የሚመራ በአንድ ግብረ ኃይል መመራት መጀመሩ ይታወቃል።ሆኖም ግን ይህ ግብረ ኃይል ሥራ ከጀመረ በኃላ ነው የእዚህ ሳምንቱ ጥቃት  በንፁሃን ላይ የተፈፀመው።አንዳንድ የኦነግ ሸኔ ደጋፊዎች በኦሮምያ ብልጥግና ውስጥ በሕቡ እየሰሩ መሆናቸውን የሚያወሱ  ወገኖች የቤንሻንጉል ክልልም ተመሳሳይ የሎጀስቲክም ሆነ የሽፋን ድጋፍ እያገኘ እንደሆነ እና በክልሉ የሚደርሱት እልቂቶች የእዚሁ በሕቡዕ በኦሮምያ በልጥግና ውስጥ በተሸሸገው የመንግስት መዋቅር አይዞህ ባይነት ነው በማለት ይከራከራሉ። 

በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ጉባኤ በጋራ በእዚህ ሳምንቱ የቤንሻንጉል ክልል የመተከል ዞን ጥቃት አንድ መቶ ሰዎች ሕይወት መቀጠፉን መግለጣቸውን እና የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) በመተከል የደረሰውን የንፁሃን ደም መፍሰስ ማውገዙን የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥን በዛሬው የምሽት ዜና እወጃው ላይ ገልጧል።
===============
============
ማስታወቂያ 
============
በአንድ ደቂቃ ውስጥ በሀገር ቤት የሚኖር የቤተሰብ ወይንም የወዳጅዎን ስልክ ሂሳብ ሊሞሉ እንደሚችሉ ያውቃሉ? 
አገልግሎቱን ለማግኘት ከስር ሊንኩን ይጫኑ - 

No comments: