ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, September 9, 2019

ሰበር ዜና - ጅማ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ላይ ዛሬ ጥቃት ለመፈፀም ተሞክሯል።የሽብር ጥቃት እየደረሰ የመንግስት ለዘብተኝነት ብዙዎችን አስቆጥቷል።


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አማኞች በደረሰባቸው በደል ሳብያ -
  • ለመንግስት አቤት ለማለት የሄዱ ጳጳሳት በቂ ምላሽ ሳያገኙ መመለሳቸው እና ይህንን ተከትሎ ቅዱስ ሲኖዶስ ያወጣው መግለጫ በመንግስት ሚድያዎች በሚገባ ሳይተላለፍ ሶስተኛ ቀኑን ማሳለፉ።
  • እራሱን የኦሮምያ ቤተ ክህነት አደራጅ ኮሚቴ  በማለት የሚጠራው ቡድን እንደ ቅዱስ ፓትርያሪኩ እራሱን ሰይሞ የአዲስ ዓመት መልካም ምኞት በኦኤምኤን ቴሌቭዥን ሲያስተላልፍ መታየቱ፣
  • በጅማ በአደባባይ ዛሬ ሰኞ ጳጉሜን 5 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ንዋየ ቅድሳት ለማቃጠል የተደረገው ሙከራ እና ምሽቱን የጅማ ሕዝብ ወጥቶ ቤተ ክርስቲያኑን እየጠበቀ መገኘቱ ሁሉ ከፍተኛ ቁጣ ቀስቅሷል።
ቅዱስ ሲኖዶስ ወቅታዊውን የቤተ ክርስቲያን ሁኔታ ላይ አስቸኳይ ጉባኤ ካካሄደ በኃላ ጳጕሜን 2 ቀን 2011 ዓ.ም. ጋዜጣዊ መግለጫ ማውጣቱ ይታወሳል፡፡ በመግለጫው ተራ ቁጥር 4 ላይም  የሚከተለው ጥሪ ለመላው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ተላልፏል፡፡
“እየደረሰ ያለውን ግፍ እና መከራ በሀገራዊ የኃላፊነት ስሜት ታግሶ እና ችሎ፤ ሞቱ፣ እሥራቱ፣ ዛቻው፣ ስደቱ እና እንግልቱ ሳይበግረው ሀገር በአንድነት እና በፍቅር እንዲሁም በመተሳሰብ እንድትቀጥል ታሪክ የማይረሳው መሥዋዕትነት እየከፈሉ ያሉትን አገልጋይ ካህናት እና መላውን ምእመናንን እንዲሁም ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በአጠቃላይ መላው የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ላሳያችሁት ትዕግስት የተመላበት ሀገራዊ ኃላፊነት ቅዱስ ሲኖዶስ በእጅጉ እያመሰገነ እንደ አሁን ቀደሙ ሁሉ ትዕግስት የተመላበት ሀገራዊ ኃላፊነታችሁ እንደተጠበቀ ኾኖ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየደረሰ ያለውን፣ ወደፊትም ሊደርስ የታቀደውን ግፍ እና ጥፋት በአንድነት እና በኅብረት ከእኛ ከመንፈስ ቅዱስ አባቶቻችሁ ጋር በመሰለፍ በጽናት ቤተ ክርስቲያናችሁን እንድትጠብቁ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡”

ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መግለጫ መሰረት ኦርቶዶክሳውያን የሀገሪቱን ሕግ አክብረው የደረሰባቸውን ግፍ ለማሳሰብ ለመስከረም 4 ቀን ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ተገቢውን ፈቃድ ጠይቀዋል።የሰልፉ አስተባባሪዎች የአዲስ አበባ አስተዳደርን ለማስፈቀድ በጠየቁት ጥያቄ ላይ እንደ ገለጡት ሰልፉ ሶስት ዓላማዎችን የያዘ ነው።እነርሱም -

1ኛ / በካህናት፣ ምእመናን እና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት ለመቃወም፣ ለሁሉም አካላት ለማሳወቅ እና እንዲቆም ለመጠየቅ፣
2ኛ/ አጥፊዎች በሕግ እንዲጠይቅ እና በቀጣይም ተመሳሳይ ጥቃት እንዳይደርስ መንግሥት ሕጋዊ ዋስትና እንዲሰጥ፣
3ኛ/ በዚህ ጥቃት መስዋዕትነት ለተቀበሉ አካላት ቋሚ መታሰቢያ እንዲቆም፣ በሃይማኖታቸው ምክንያት የተፈናቀሉ ሰዎች ወደ ነበሩበት እንዲመለሱና ለሚገባው አካል ተገቢው ካሳ እንዲከፈል ለመጠየቅ የሚሉት ናቸው።

የሰልፉ አስተባባሪዎች-  
★ የሰ/ት/ቤቶች አንድነት፤ 
★ የመንፈሳዊ ኰሌጅ ተማሪዎችና ምሩቃን፤ 
★ በሰ/ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን፤ 
★ የወጣቶችና ጎልማሶች ማኅበራት ኅብረት፤
★ የሠለስቱ ምዕት ማኅበራት ኅብረት፤
★ የአእላፋት ድምፅ የካህናትና ምእመናን ተናሥኦት ኅብረት፤
★ የጽዋ ማኅበራት 

ሲሆኑ ሰልፉ ፍፁም ሰላማዊ የማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ተቀጥላ ያልሆነ፣ ሆኖም ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ የተፈፀሙ የሽብር ድርጊቶች ሁሉ እንዲቆሙ መንግስት ኃላፊነቱን እንዲወጣ የሚያሳስብ ነው። 


በሌላ በኩል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚደርሰው በደል ለማስቆም መስከረም 4 ቀን የሚደረገው ሰልፍ ዓለም አቀፍ መልክ ይዟል።ቅዱስ ሲኖዶስ ያወጣውን መግለጫ በመደገፍ እና በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ የሚደርሰው በደል መቆም አለበት በሚል በጀርመን እና በስዊድን የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦሮቶዶክስ ተዋህዶ አብያተ ክርስቲያናት መግለጫ ያወጡ ሲሆን መስከረም 4 በተመሳሳይ ቀን በሰሜን አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ እና በጀርመንም ሰልፉ እንደሚደረግ ተሰምቷል።በተጨማሪም የኢትዮጵያ ቆንስላ ባለባቸው በሎሳንጀለስ እና ሚኒሶታ ተመሳሳይ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተሰምቷል።

ኦርቶዶክሳውያን ለታወጀባቸው ሽብር በዋናነት ተጠያቂ የሆኑት የፅንፍ የሃይማኖት እና የብሔር ቡድን ተጠያቂ ሲሆን በውስጥ ፅንፈኛ ብሔርተኞች እና የአካባቢው ሽብርተኛ ቡድኖች እንዳሉበት ይጠረጠራል። ዓላማው የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ማዳከም እና ከሕዝቡ መነጠል በመቀጠልም ሙሉ በሙሉ ለመምታት መሆኑ በብዙ ማስረጃዎች የተረጋገጠ ነው።

ይህ በእንዲህ እያለ ግን መንግስት አሁንም ተገቢውን ምላሽ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አለማድረጉ እና ግልጥ የሆነ የሽብር ሥራ የሚሰሩትን የጦር ሰራዊቱ አስፈላጊውን ፀጥታ የማስከበር ሥራ እንዳይሰራ ተገቢው መመርያ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ አለመሰጠቱ እንደ ትልቅ እንቅፋት ተቆጥሯል። በመሆኑም ቤተክርስቲያኒቱን እና ከሃምሳ ሚልዮን በላይ የሚሆነውን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ሀገሪቱን አደጋ ላይ የሚጥል አሰራር ከመንግስት እየታየ ነው።

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን ጉዳዩን በቀላሉ ተመልክተው እጃቸውን አጣጥፈው የሚቀመጡበት ጉዳይ ሳይሆን ከሊቅ እስከ ደቂቅ በሰላማዊ መንገድ ለቤተ ክርስቲያኑ ዘብ መቆም ያለባቸው እጅግ ወሳኝ ወቅት አሁን ነው።



ተዋህዶ  ሃይማኖቴ መዝሙር (ቪድዮ)


ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

No comments: