ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Thursday, January 27, 2022

ኢትዮጵያውያን በ''ወገን ፈንድ'' በኩል በድርቅ ለተጎዱት ለሱማሊያ ክልል አርብቶ አደሮች እና በጦርነቱ ለተጎዳው የዋግ ኽምራ ህዝብ የገቢ ማሰባሰብያ መርሃግብር ጀመሩ።

ሱማልያ ክልል የድርቅ አደጋው አሳሳቢ ሆኗል (Photo-DW-Germany Broadcast English Service)

============================
ጉዳያችን ዜና / Gudayachn Exclusive News
=============================

የ''ጎ ፈንድሚ'' አገልግሎትን እየተካ ያለው በኢትዮጵያውያን የአይቲ ባለሙያዎች አገልግሎት ላይ የዋለው እና የአቢሲንያ ባንክ እየተገበረው ያለው የተለያዩ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች የገንዘብ ማሰባሰብያ ''ፕላት ፎርም'' በድርቅ ለተጎዱ የሱማልያ ክልል አርብቶ አደሮች እና በጦርነቱ ለተጎዳው የዋግ ኽምራ ህዝብ የገንዘብ ማሰባሰብያ መርሃ ግብር ጀምሯል።ስለ ወገን ፈንድ ጉዳያችን በቅርቡ ያወጣችውን ዘገባ ይህንን በመጫን ያንብቡ።

ከእዚህ በታች ለሁለቱም ቦታዎች የድጋፍ ጥሪ ከወገን ፈንድ ላይ የተገኘው ዓረፍተ ነገር እንደሚከተለው ነው።

ለሱማሊያ ክልል ወገኖቻችን 

በደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ፣ በሶማሌ ክልል፣ በተከታታይ ዝናብ በመጥፋቱ ለከፋ ድርቅ ተጋልጠው በአካባቢው የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች፣ እንዲሁም የቤት እንስሳት መግብ እና ውሃ በመጥፋቱ ከፍተኛ ችግር ገጥሟቸዋል።
በተለይ ከ5 አመት በታች ያሉ ህጻናት እና ሴቶች የድርቁ የመጀመሪያ ተጎጂዎች ናቸው።

እነዚህን አስከፊ ሁኔታዎች ለመቀልበስ ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች የውሃ መኪና፣ ምግብ፣ የእንስሳት መኖ፣ አስፈላጊ መድሃኒቶች፣ ውሃ፣ ጨርቅ እና መጠለያ ለተጎዱ ወገኖች ለማቅረብ ዓለም አቀፍ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።

አስተባባሪ:- የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጥምረት ለኢትዮጵያ ህዝብ

ለሱማሌ ክልል የድጋፍ መስጫው መግቢያ ሊንክ =

https://www.wegenfund.com/causes/somalia-drought/ 


ለዋግ ኽምራ ህዝብ


በሀገራችን ኢትዮጵያ በተከሰተው ጦርነት እና ጦርነቱ ባስከተላቸው ቀውሶች ምክንያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ ኦርቶዶክሳውያንና ሌሎች ዜጎች ለከፋ ችግር እየተጋለጡ ይገኛሉ። ጦርነቱ ከባድ ጉዳት ካደረሰባቸው አካባቢዎች መሃል የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት አንዱ ነው (ሰቆጣ እና አካባቢው)። በዚህ አካባቢ ከአምስት ወር በላይ በተካሄደው ጦርነት ብዙ ዜጎች ሕይወታቸው አልፏል፣ ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል፣ አብያተ ክርስቲያናት ወድመዋል፣ ጉባኤ ቤቶች ተፈትተዋል፣ ገዳማውያንና ዜጎች ፈልሰዋል።

በአሁኑ ወቅት አንጻራዊ ሰላም ቢኖርም የአካባቢው አባወራዎች ከነቤተሰቦቻቸው ከዕለት ጉርስ ጀምሮ ልዩ ልዩ ድጋፍ ያስፈልጋቸዋል፣ ከ600 በላይ የሚደርሱ አብያተ ክርስቲያናት መቀደሻ ዕጣን እና ጧፍ የላቸውም፣ አገልጋይ ካህናት እንዲሁም የአብነት መምህራን እና ተማሪዎችም ምግብ እና መሠረታዊ ፍላጎቶች የሚያስፈልግበት ወቅት ነው። ስለሆነም በመላው ዓለም የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ለወገናችሁ በምትችሉት ሁሉ በዚህ በወገን ፈንድ በኩል ርዳታችሁን እንድታደርሱልን ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

ለዋግ ኽምራ ህዝብ ድጋፍ ማሰባሰቢያ የመግቢያ ሊንክ =

https://www.wegenfund.com/causes/eotc-waghimra/ 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን
የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት

================////==========

No comments: