ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, November 11, 2019

የኢህአዴግ ውሕደት ላይ ያተኮረው የድርጅቱ ወሳኝ ስብሰባ የፊታችን ሮብ ይጀመራል።ውህደቱ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ወደ አንድ ምዕራፍ እንዲያሸጋግር ጉጉታችን ነው።ህወሓት በውህደቱ ከመሳተፍ ሌላ ምንም ምርጫ እንደሌለው ሶስት ምክንያቶች አሉ።

ጉዳያችን /Gudayachn
ሕዳር 1/2012 ዓም (ኖቬምበር 11/2019 ዓም)

ኢህአዴግ ቀድም ብሎ በሐዋሳ ላይ በወሰነው ውሳኔ መሰረት በውሕደቱ ላይ ያተኮረው ጉባኤውን ለማካሄድ በመጪው ሮብ ለስብሰባ ይቀመጣል።እስካሁን ባለው መረጃ መሰረት በውህደቱ ላይ የተስማሙ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) ፣የዓማራ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ዓዴፓ) እና የደቡብ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ደሕዴድ)  ሲሆኑ ሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ግልጥ ውሳኔውን አላሳወቀም።ሆኖም ቀደም ብሎ ድርጅቱ ባወጣቸው መግለጫዎች ውህደቱን እንደሚቃወም አስታውቆ ነበር። በሌላ በኩል ህወሓት በውህደቱ ባይሳተፍ ይህ የድርጅት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን የሕዝብ ጉዳይ ስለሆነ ሌሎች የትግራይ ክልልን ወክለው በውህደቱ ሂደት ላይ ለመሳተፍ  የሚፈልጉ እንዳሉ ከአዲስ አበባ የሚሰሙ ዜናዎች አሉ።

ኢህአዴግ ወደ ውህደት ስመጣ ከእዚህ በፊት በኢትዮጵያ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ የጎላ ድርሻ ያልነበራቸው ማለትም በአጋርነት ብቻ ሲጠሩ የነበሩ የሐረሪ፣የቤንሻንጉል፣የጋምቤላ፣የአፋር እና የሱማሌ ድርጅቶች በአሁኑ የኢህአዴግ ውህደት ላይ ለመሳተፍ  ስምምነታቸውን መግለጣቸው ለማወቅ ተችሏል።ሆኖም ግን በውህደቱ የውሳኔ ድምፅ መስጠት ላይ ወሳኞቹ አራቱ ድርጅቶች ማለትም ኦዴፓ፣አዴፓ፣ህወሓት እና ድህዴድ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል።ከውሳኔው በኃላ ግን አጋር ድርጅቶች የውሕደት ጥያቄያቸው ወዲያውኑ ተቀባይነት እንደሚኖረው እና ውሕደቱ እንደሚከናወን ይታመናል።

ህወሓት በውህደቱ ከመሳተፍ ሌላ ምንም አይነት ምርጫ የለውም 

ይህ በእንዲህ እያለ ህወሓት በእዚህ ውህደት ላይ ከመሳተፍ ሌላ ምንም አይነት አምራጭ እንደሌለው በሶስት ምክንያቶች ማወቅ ይቻላል።እነኝህ ምክንያቶችም -

1ኛ) የትግራይ ምሁራን እና የንግዱ ማኅበረሰብ ውሕደቱን ስለሚደግፍ


የትግራይ ምሁራን እና  በተለይ ላለፉት 27 ዓመታት ከፍተኛ ሀብት ያገኘው የትግራይ ባለሀብት አሁን የሚፈልገው በየትኛውም ቦታ አድልዎ ሳይደረግበት ካፒታሉን ማፍሰስ እና መስራት ነው።ሌላው ምክንያት አሁንም ከፍተኛው ሀብት ያለው በአዲስ አበባ እና በሌሎች የኢትዮጵያ ክፍል ከመሆኑ አንፃር (በተለይ የማይንቀሳቀሰው ሀብት) ውህደቱን በከፍተኛ ደረጃ ይደግፋል። ህወሓት ውህደቱን ተቃውማ ብትቆም የመጀመርያ ጠብ ያለባት ከእዝህኛው የህብረተሰብ ክፍል ጋር ነው።

2ኛ) ህወሓት በሌላ የፖለቲካ ድርጅት የመተካት ዕጣ ሊገጥማት ስለሚችል

ህወሓት የኢህአዴግን ውህደት አልቀበልም ብትል ለተወሰነ ጊዜ ከማኩረፍ እና የተወሰኑ ችግሮች ለመፍጠር ከመሞከር ባለፈ በዘለቄታው ግን ሕወሃትን የሚቃረን የፖለቲካ ድርጅት በቀጥታ ወደ ውህደቱ የትግራይን ሕዝብ ወክሎ ሊቀላቀል ይችላል። ይህ ማለት ከአረና ትግራይ ጀምሮ ሌሎች አዳዲስ ድርጅቶች መፈጠራቸው ስለማይቀር ህወሓት በውህደቱ ባለመሳተፍ ትግራይ የነበራትን የፖለቲካ እና ማኅበራዊ መሰረት የማጣት ዕጣ ሊገጥማት ስለሚችል ከመዋሃድ ሌላ አማራጭ የለም።

3ኛ) ውህደቱ በራሱ ለሕወሀት ጥቅም ስላለው 

ህወሓት ከኢህአዴግ ውህደት ተጠቃሚ እንጂ ተጎጂ አይደለችም።ህወሓት የበላይ በሆነችበት ኢህአዴግ ውስጥ ውህደት ላይጠቅማት ይችላል።አሁን ግን የበላይነት በሌለበት የፖለቲካዊ ነባራዊ ሁኔታ ውስጥ ህወሓት በውህደት ውስጥ በመሆን ቢያንስ ትግራይ ያላትን  የበላይነት በምርጫው ወቅት አስጠብቆ ሌላ አመቺ ጊዜ መጠበቅ ብቸኛው አማራጭ ነው።ስለሆነም  ውህደቱን ከመቀበል ውጪ አማራጭ የጥቅም ሜዳ ሊኖራት አይችልም።


ስለሆነም ውህደቱ ሙሉ በሙሉ የሚሳካ እንደሚሆን ከወዲሁ ማወቅ ይቻላል።

በመጨረሻም የኦሮሞ የፅንፍ ኃይሎች ይህንን ውህደት በመቃወም አንዳንድ መግለጫ ሲሰጡ እንደሰነበቱ ይታወሳል።ሆኖም ግን ይህ ውህደት አንዱ ይዞ የሚመጣው ጉዳይ  የፅንፍ የኦሮሞ ድርጅቶችን ለብቻቸው የመነጠል መልካም የአደጋ ዕድል ይዞላቸው ይመጣል። ለእዚህም ነው ውህደቱን የፈድራሊዝም ጠላት እንደሆነ ለመለፈፍ ሲሞከር የከረመው። በእርግጥ ውህደቱ በርካታ ጥያቄዎች የሉትም ማለት አይደለም። ለምሳሌ ከውህደቱ በኃላ ሌላ የተረኝነት ወይንም አንዱ የበላይ የሚሆንበት ሂደት እንዳይከሰት የሚወሰዱ ምን እርምጃዎች አሉ? ውህደቱ ፍፁም ውህደት ካልሆነ እና የጎሳ አደረጃጀችን ካላጠፋ መልሶ የጎሳ ስሜትን እንዳይፈጥር እንዴት መከላከል ይቻላል? እና የመሳሰሉ ጥያቄዎች መመለስ ያስፈልጋል። በሌላ በኩል እነኝህ ጥያቄዎች የሚወሰኑት በክልሎች አከላል ዙርያ ያለው ለውጥ ጋር ተያይዞ የሚነሳ ጥያቄ እንደሚሆን ይታመናል። ለሁሉም ግን የኢህአዴግ ውህደት የህዝብ ጥያቄ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን ፖለቲካ ወደ አንድ ምዕራፍ እንዲያሸጋግር ጉጉታችን ነው።

ድምፃዊ አብርሐም ገብረመድሕን ''አገሬ''



ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...