ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, August 21, 2018

የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራሮች ሀገር ቤት የሚገቡበት ቀን ታወቀ።

ጉዳያችን / Gudayachn 
ነሐሴ 16/2010 ዓም (ኦገስት 22/2018 ዓም)

የአርበኞች ግንቦት ሰባት ለአንድነት እና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራሮች ወደ ሀገር ቤት የሚገቡበት ቀን ጳጉሜን 3/2010 እንደሆነ እና በሶስት ቡድን ሆኖ ወደ ሀገር ቤት እንደሚገባ ለማወቅ ተችሏል። ላለፉት አስር ዓመታት ለዲሞክራሲ እና ለአንድነት የሚደረገውን ትግል ከወደቀበት አንስቶ ሕይወት የዘራበት፣የትጥቅ ትግል እና ሕዝባዊ እምቢተኝነትን የትግል ስልት አድርጎ የተነሳው የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራሮች ብቻ ሳይሆኑ በኤርትራ የሚገኙ የንቅናቄው አባላትም ወደ ሀገር ቤት እንደሚገቡ መረጃው ይጠቁማል። 
የአርበኞች ግንቦት ሰባት በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ ያለውን ኢትዮጵያዊ የትግል ስሜት ከማነሳሳት እስከ የተጠና የፕሮፓጋንዳ፣ እንዲሁም  የገዢው መንግስትን ድብቅ ተግባራት በማጋለጥ፣ እንዲሁም በሀገር ቤት በሕቡዕ ሕዝባዊ ንቅናቄዎችን በመፍጠር እና በዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እንደ የአውሮፓ ሕብረት የመሳሰሉ አህጉራዊ ድርጅቶች ላይ ቀጥተኛ ተፅኖ በመፍጠር የኢትዮያን ጉዳይ ዓለም አቀፍ መልክ እንዲይዝ በማድረግ የአርበኞች ግንቦት ሰባት አሁን ኢትዮጵያ ለደረሰችበት የነፃነት ወቅት የእራሱን አስተዋፅኦ ማድረጉ የአደባባይ ምስጢር ነው።

ድርጅቱ በቀጣይ በሀገር ቤት በአዲስ መልክ ከንቅናቄ ወደ ፖለቲካ ፓርቲነት እንደሚሸጋገር እና በእዚሁም መሰረት ለመጪው የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ሽግግር ኢትዮጵያን የሚመጥን የፖለቲካ ፓርቲ እንደሚሆን የብዙዎች ተስፋ ነው። የአርበኞች ግንቦት ሰባት ንቅናቄ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ በከፍተኛ ደረጃ የትምህርት ዝግጅትም ሆነ ዓለም አቀፍ የስራ ልምድ ያላቸው አመራር እና አባላት ያሉት መሆኑ ይታወቃል።

የንቅናቄው አመራር በሶስት ዙር መግባት የሚጀምረው ጳጉሜን 3/2010 ዓም ሲሆን በእዚሁ ቀን ከፍተኛ አመራሩ ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ጋር ከሚመለሱት አመራሮች መካከል አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ፣ ዶ/ር ታደሰ ብሩ፣ አቶ ኤፍሬም ማዴቦ፣ ዶ/ር አዚዝ መሐመድ፣ዶ/ር ሙሉዓለም አዳም  እና አቶ ነአምን ዘለቀን የሚጨምር መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።በቀጣይ ዙር በኤርትራ የሚገኙ የሰራዊቱ አባላት እና በሶስተኛ ደረጃ ሌሎች አመራሮች በተመሳሳይ መንገድ የሚመለሱበት ሁኔታ እንደተመቻቸ ተሰምቷል።

በመጨረሻም በአዲስ አበባ ከፍተኛ አቀባበል ለማድረግ ዝግጅቱን በማጠናቀቅ ላይ የሚገኘው ኮሚቴ አመራሮቹ ወደሀገር ቤት ሲገቡ ከሕዝቡ ጋር ሆኖ  ከቦሌ ዓለም አቀፍ አየር መንገድ ጀምሮ  እንደሚቀበል ተሰምቷል።በቀጣይ ቀናትም አመራሮቹ በአዲስ አበባ እና ከአዲስ አበባ ውጭ የተለያዩ ከተሞች ከህዝብ ጋር የሚወያዩበት መድረክ የተዘጋጀ መሆኑ እና ሕዝብ በከፍተኛ ጉጉት እየጠበቀው የሚገኘው መርሐግብር እንደሆነ ከሀገር ቤት የሚወጡ ዘገባዎች ያመለክታሉ።



ቪድዮ = ኦስሎ፣ ኖርዌይ የአርበኞች ግንቦት ሰባት ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ሰኔ/2008 ዓም የተደረገው መርሐግብር መዝጊያ 



ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

No comments:

ህወሓት ሰሜን ወሎ ራያን ወርሮ የገጠር ወረዳዎችን እየዘረፈ ነው። ህዝብ ሲዘረፍ እና በአስር ሺዎች ሲፈናቀሉ የመንግስት የፖለቲካም ሆነ የወታደራዊው አመራሮች ዝምታቸው ከተጠያቂነት አያድናቸውም።

በሰሞኑ የህወሓት ወረራ ቆቦ ተፈናቅለው የገቡ የሰሜን ወሎ ተፈናቃዮች  በከፊል ፎቶ፡ ቢቢሲ ሚያዝያ 20፣2024 እኤአ ''ቅጥ አምባሩ የጠፋው'' የፕሪቶርያው ውል   ''ስኩዌር ዋን&#...