ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Monday, August 6, 2018

የመከላከያ ሰራዊት ጅጅጋን ለማረጋጋት በክልሉ መንግስት ጥያቄ መሰረት ገብቷል።ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ የዓለም አቀፍ ፀጥታ ጉዳይ አማካሪ ስለ ክልሉ ቀደም ብለው ምን ፅፈው ነበር?

ጉዳያችን/ Gudayachn
ሐምሌ 30/2010 ዓም ( ኦገስት 6/2018 ዓም)
በእዚህ ሪፖርት ውስጥ : -
  • የመከላከያ ሰራዊቱ እስካሁን ወደ ኢትዮጵያ ሱማሌ ገብቶ እርምጃ ያልወሰደበት ምክንያት፣ 
  • የሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ ክልሉን አስመልክተው ከእዚህ በፊት ያቀረቡት ትንተና ሙሉ ፅሁፍ  ያገኛሉ።


የኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል ዋና ከተማ ጅጅጋ፣ ካለፈው አርብ ጀምሮ ውጥረት ላይ ነች።ውጥረቱ ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ ላይ ይባስባት እንጂ ክልሉ በተለይ በዘመነ ህወሓት ሰላሙን እንዳጣ የሚታወቅ ነው።
የመከላከያ ሰራዊት ወደ ጅጅጋ ገብቶ እንዲያረጋጋ መታዘዙን የመንግስት ኮምዩኒኬሽን ቢሮ ማስታወቁ ተሰምቷል።
የኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል


እስካሁን መከላከያ እርምጃ ያልወሰደበት ምክንያት 
=========================== 
ይህንን ጥያቄዎች የሚጠይቁ ሰዎች ላለፉት 27 ዓመታት ኢትዮጵያ ውስጥ ምን ሲያስጮህ እንደነበር ያልሰሙ ይመስላሉ።ህወሓት ኢትዮጵያን ለመከፋፈል ላለፉት ሀያ ሰባት አመታት ምን ያህል እንደደከመ እና ይህንን ለማሳካት ሲታትር ድንገት ለውጡ እንደመጣበት ያልተገነዘቡ ናቸው።ሆኖም ግን ለውጡ መምጣቱ በእራሱ በሕገ መንግስቱ መሰረት ወደ ክልሎች  የፌድራል መንግስት መግባት የሚችለው የክልሉ መንግስት ሲፈቅድ ነው የሚለው ሕግ በመጠቀም የኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል ፕሬዝዳንት ይህ እንዳይሆን የክልሉን ምክር ቤት ሲያስፈራሩ ቆይተዋል። 

ሆኖም ግን ዛሬ ሰኞ ከቀትር በኃላ የመከላከያ ሰራዊት የጅጅጋ ከተማን ሙሉ በሙሉ መቆጣጠሩን እና የፀጥታ ኃላፊነቱን መውሰዱን የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳይ ኃላፊ አቶ አህመድ ሺዴ አስታውቀዋል።የመከላከያ ሰራዊት ከመግባቱ በፊት ከክልሉ ፕሬዝዳንት አቶ አብዲ ኤሊ ጋር ጉዳዩን በውይይት ለመፍታት መሞከሩ እና ጥረቱ ለሁለት ቀናት ቢቀጥልም አለመሳካቱ ተሰምቷል።ይህ ብቻ አይደለም በእዚህ ንግግር መሃከል እስከአሁን ከ39 ያላነሰ ሕይወት በአብዲ አሊ ልዩ ፖሊስ በሚጠሩት ኃይሎች አማካይነት መገደላቸው እና በፖሊሶቹ አይዞህ ባይነት ከሰባት ያላነሱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አብያተ ክርስቲያናት መቃጠላቸው ተሰምቷል። ይህ ሁኔታ ህገ መንግስቱ በራሱ መስተካከል እንደሚገባው አመላካች ነው።አሁን ዘግይቶ በወጣ ዘገባ መሰረት የክልሉ ፕሬዝዳንት አብዲ አሊ በተነሳባቸው የህዝብ አመፅ መሰረት ስልጣናቸውን ለመልቀቅ መገድዳቸውን የክልሉ ሕዝብ ግንኙነት እድሪስ እስማኤል እንዳረጋገጡለት ቢቢሲ ዘግቧል።ቢቢሲ የዘገበው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ነው።

President of Ethiopia's Somali region resigns


The Minister for Information for the Somali region of Ethiopia Idris Ismail has confirmed to the BBC Somali Service that regional President Abdi Mohamud Omar has handed over power and has agreed to step down.
This follows days of tension in the Somali region as the Federal Military were deployed to the region.
It’s believed that he has been pressured by the federal government to step down following protests and fighting between Somali and Oromo communities.
Reports say that more federal troops have been deployed to the regional capital, Jigjiga .
ምንጭ (source)  = BBC  


ክአዚህ በታች በዓለም አቀፍ የፀጥታ ጉዳዮች አማካሪ፣በቀድሞው መንግስት በተለያዩ የሚንስትር ማዕረግ ያገለገሎት ሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ የኡጋዴንን ሁኔታ አስታከው ከአንድ ዓመት በፊት ያወጡት ልዩ ትንተና ከእዚህ በታች ያንብቡ።

ማሳሰቢያ : - የሻለቃ ዳዊት ፅሁፍ  ከወጣ አንድ ዓመት ስለሆነው አንዳንድ ቦታዎች ከአንድ ዓመት በፊት የነበረውን የሀገራችንን ሁኔታ ቢገልጥ አንባቢ ይህንኑ ታሳቢ አድርጎ ያንብበው።
======================

ኦጋዴንና የሀገር አንድነት ሥጋቶች  ክፍል አንድ 

(በሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ የዓለም አቀፍ የፀጥታ ጉዳዮች አማካሪ ሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ)

ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ የዓለም አቀፍ ፀጥታ ጉዳዮች አማካሪ 

የኢትዮጵያ ህዝብ ወደ አዲስ ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ለመሸጋገር ትግሉን ባጧጧፈበት በአሁኑ ወቅት አገር ውስጥ ያለውን ክፍተት፣ ሁከትና የመንግስትን መዳከም በዓይነ ቁራኛ የሚከታተሉ የውጭ ጠላቶች ይህን አጋጣሚ በመጠቀም አንድነታችንን ለማደፍረስ በውስጥ ጉዳዮች ጣልቃ በመግባት የራሳቸውን አጀንዳ ለማስፈፀም የሚሞክሩ ብዙዎች አሉ፡፡ እነዚህንም ሁኔታዎች መከታተልና ጥንቃቄ ማድረግ ለውጡን የሚያራምዱ ድርጅቶችና ግለሰቦች ኃላፊነት ነው፡፡ እኔና የመሳሰሉ በተሞክሮና በእድሜ የበለፀጉ ደግሞ ከምናየው፣ ከምናነበውና ከምናጠናው ተነስተን ይህቺን ኢትዮጵያን የሚረከበው አዲስ ትውልድ ካለፈው ስተት እንዲማር ይቺ የኢትዮጵያ ምድር ለራሳቸው ባልኖሩ፣ ኢትዮጵያን አስቀድመው ካለፉ ጀግኖች አባቶቻችን፣ እናቶቻችን፣ ወንድሞቻችን፣ እህቶቻችን ደምና አጥንት የከበረች መሆኑን ዘወትር አስታውሰው በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ሁሉ ጥበብና ጥንቃቄ እንዳይጐድላቸው ማሳሰብ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ላይ ከውጪ የሚሰነዘሩ ጥቃቶችን መረዳት የሚቻለው በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ባለው የጂኦ ፖለቲካ አሰላለፍና ክልል ውስጥ ነው፡፡ (የአገር ደህንነት ጥያቄዎች፣ “ያሉና የሚኖሩ የኢትዮጵያ ሥጋቶች” በሚል ርዕስ ክህደት በደም መሬት በሚለው መጽሀፌ ላይ ዘርዝሬ አለሁኝ)፡፡
በአሁኑ ወቅት አዲስ መነጋገሪያ ርዕስ እንዲሆን የማቀርበው የኦጋዴንን ሁኔታ ነው፡፡
ዛሬ በሱማሌና በኦሮሞ ክልል የተፈጠረው ግጭትና የተፈፀመው ጭፍጨፋ የወያኔ ሴራ መሆኑ በማያሻማ ሁኔታ ተገልጿል፡፡ የወያኔ መንግስት ኃላፊነቱን በሚገባ ባለመወጣቱ በሁለቱ ህዝቦች መካከል ግጭት እንዲፈጠር ሁኔታውን አመቻችቷል፡፡ ይህም የተደረገው በዕቅድ አንጂ በድንገት የተፈፀመ አይደለም፡፡ ይህ ሴራ የተሸረበው ህዝቦችን እርስ በርስ በማጋጨት የሥልጣን ዘመኑን ለማራዘም ሲሆን ይህ የሚያስከትለው የርስ በርስ ጥላቻንና ፍጥጫ የሶማሌ ክልል ቀስ በቀስ ከኢትዮጵያ ለመራቅና፣ ለመነጠል ምክንያት ሆኖት ለመገንጠል ሁኔታውን ያመቻቻል፡፡ ይህ አሁን ከሚታየው በስተጀርባ ያለው ሴራ ነው ብዬ አምናለሁኝ፡፡ የረዥም ጊዜ ዕቅድ ያላቸው የኦጋዴን ተገንጣይ ቡድኖች በህዝቦች መሐከል ያለውን ግጭት ለረዥም ጊዜ ዓላማቸው ይፈልጉታል፡፡ የወያኔ መንግስት ሥልጣን ላይ ለመቆየት ህዝቡን ሲያጋጭ በዚያው መጠን የሶማሌ ተገንጣይ ጦረኞች የራሳቸውን ሀይል ለማጠንከርና ኦጋዴን ሶማሌ ያልሆነውን ሁሉ ከክልሉ አስወጥተው ኦጋዴን የኦጋዴኖች ብቻ አድርገው የመገንጠሉን እንቅስቃሴ ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋግሩታል::: የኦጋዴንን ጥያቄም ዓለም አቀፋዊ(Internationalize) ለማድረግ ይጥራሉ:: ይኸም የሚሆነው በመንግሥት በኩል በሚወሰዱ አክራሪ(Excessive) እርምጃዎች ወይንም ደግሞ በሕዝቦች መሀከል ያለውን ግጭት ለብዙ ሕይወት ማለፍና እንዲሁም መሰደድ ምክንያቶች ሲሆኑ ነው፡፡ በዚህን ጊዜ አጀንዳ የሌላቸው አገሮች ጣልቃ ይገባሉ፣ በተባበሩት መንግሥታትና በአፍሪካ አንድነት እንዲሁም በሌሎች ኢንተርናሽናል ድርጅቶች ውይይት ያስከፍታል፣ መግለጫዎች ያወጣሉ፣ ውሳኔም ያሰጣሉ:: ይህንን ኦብነግ ይፈልገዋል:: ሁኔታዎችንም ወደዚያ ይገፉሉ፡፡ ጉዳዩ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የሌሎችም ጉዳይ ይሆናል፡፡ የተገንጣዮች ስትራቴጂ ይህን ይመስላል፡፡ የኦጋዴን ጉዳይ እንደ ሌሎች የኢትዮጵያውያን ጥያቄ የኢትዮጵያ ጉዳይ ሆኖ መቆየት አለበት፡፡ ይህም ሊሆን የሚችለው የወያኔ መንግሥት ሲወገድና የሕዝቡን አንድነት የሚያረጋግጡ፣ ዋስትናም የሚሆኑ ፖሊሲዎች ሲቀየሱና ህዝቡ የተባበረ አቋም ይዞ ለአንድነቱ ሲታገል ነው:: ሁልጊዜ ማዕከላዊ መንግስት ሲዳከም ነው ጠላቶቻችን ጥንካሬ የሚያገኙት፡፡
ከዚህ በላይ በዘረዘርኳቸው ምክንያቶች በኦጋዴን ስለሚደረገው እንቅስቃሴና ስለኦጋዴን ኢትዮጵያዊነት ሕዝቡ እንዲነጋገርበት በጉዳዩ የበለጠ ዕውቀት እንዲኖረውና ጥንቃቄ እንዲያደርግ በሁለት ምዕራፍ የተከፈለ ጽሁፍ አቅርቤ አለሁኝ፡፡
በኦጋዴን በኩል ብዙ መስዋዕትነት ተከፍሏል፡፡ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ ወታደራዊ አካዳሚ እጩ መኮንን ሆኜ ሶስት ዓመት በቆየሁበት ጊዜ ወታደራዊ ስትራቴጂና ፖለቲካ ስንማር ዋና መለማመጃችን የካራማራ (ጅጅጋ) በር ነበር፡፡ ካራማራ ዋና የጠላት መተላለፊያ በር ስለሆነች ይቺን በር መጠበቅና መከላከል በዚያ አቅጣጫ ለሚመጣ ጥቃት ወሳኝ ነበር፡፡ ሶስተኛ ክፍለጦር በጀግናው ሜጀር ጀነራል አማን አንዶም ወይንም(ኮዳው ትራሱ) ሥር በነበረበት ጊዜ ብዙ ይወራለት ስለነበርና በተደጋጋሚ ጦሩንና አሰላለፉን በትምህርት መልክ ጐብኝቻለሁ፡፡ ከዚም በኋላ በአብዮት ወቅት የእድገት በህብረት አዝማች በነበርኩበት ጊዜ የዘመቻ ቦታ ለመምረጥና በኋላም ዘማቾችን ለማየት በኦጋዴን ብዙ ተጉዣለሁ፡፡ የእርዳታ ማስተባበሪያና ማቋቋሚያ ኮሚሽን ኃላፊ በነበርኩበት ጊዜ የዕለት ዕርዳታና የመልሶ ማቋቋም ፕሮጀክቶችን ለመከታተል በተለይም ደግሞ አርብቶ አደሩን የኡጋዴን ህዝብ በዋቢ ሸበሌ ሸለቆ(ጎዴ) ለማስፈር በተደረገው ሙከራ ኃላፊ ሆኜ በኦጋዴን ብዙ ተንቀሳቅሻለሁ፡፡
የውጪ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር(ቋሚ ተጠሪ) በነበርኩበት ጊዜ የኡጋዴንና የሱማሌን ሁኔታ በጥልቀት ለማወቅ እድል ሰጥቶኛል፡፡ በተለይም 1969 ሶማሊያ ኢትዮጵያን በወረረችበት ጊዜ ሁኔታዎችን በኃላፊነት በቅርብ ተከታትያለሁ፡፡ የተከፈለውን ከባድ መስዋዕትነት መስክሬ አለሁኝ፡፡ ሶቭየት ህብረት ኢትዮጵያንና ሶማሊያንም ይዛ ለመቆየት ባደረገችው የፖለቲካ ሙከራ ወቅት ሞስኮና አዲስ አበባ በከፍተኛ ደረጃ በተደረጉት ውይይቶች ውስጥ ተሳትፌአለሁ፡፡ በተባበሩት መንግስታት በቀድሞ ሶቭየት ህብረት በገለልተኛ አገሮች መንግስታት በአፍሪካ አንድነት ድርጅት፣ በአውሮፓ፣ በኢስያና በደቡብ አሜሪካ አገሮች የኢትዮጵያን አቋም ለማስረዳትና ድጋፍ ለማግኘት ተዘዋውሬአለሁ፡፡ አሁንም ከአገሬ ከወጣሁኝ በኋላ በአፍሪካ ውስጥ የእርስ በርስ ጦርነት በተፈጠረባቸው አገሮች ሁሉ ተዘዋውሬ ሰርቻለሁኝ፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በዚሁ ርዕስ ላይ በአንድ የምርምር ኢንስቲትዩት በመስራት የአፍሪካን ሁኔታ በቅርብ ተከታትያለሁኝ፡፡
ለነበረኝ ኃላፊነቴ እንዲረዳኝ ስለኡጋዴን ብዙ ያስተማሩኝ በጣም የማከብራቸው ሁለት ሰዎች ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማሪያምና ፊት አውራሪ ደምሴ ተፊራ ነበሩ፡፡ በጊዜው ምክር ፍለጋ እየሄድኩ ያገኘሁት ዕውቀት ብዙ ነው፡፡ ለመንግስትም የአቋም መግለጫ እንዲረዳ ፕሮፌሰር መስፍን በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፃፉት መጽሐፍ(The Problem Child of Africa Somalia) እና የአገር አስተዳደር ምክትል ሚኒስትር የነበሩት ፊታውራሪ ደምሴ ተፈራ ከሰፊ ልምዳቸው ከጻፉት መጽሐፍ ተነስቼ ብዙ ንግግርና ውይይት ለማድረግ ችያለሁ፡፡ እነዚህ ሁለት አርበኞች ለሀገር አንድነት ባላቸው ተቆርቋሪነት ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን በማማከር መንግስት በዲፕሎማሲና በወታደራዊ ጉዳይ ትክክለኛ ፖሊሲ እንዲወስድ አድርገዋል፡፡ በሁለተኛው ምዕራፍ የማቀርበው ብዙ ሐሳብ እነሱ ካስተማሩኝና ይህንንም ተመርኩዤ ካደረኳቸው ንግግሮች የተወሰደ ነው፡፡(ክህደት በደም መሬት በሚለው መጽሐፌ ውስጥ በዝርዝር ቀርቧል)፡፡
አፍሪካ ቀንድ
ዛሬ አፍሪካ ቀንድ ብዙ ሀይሎች የንግድ፣ የስትራቴጂና የሴኩሪቱ ጥቅማቸውን ለማስከበር የሚተራመሱባት አካባቢ ሆናለች፡፡ ዛሬ የአፍሪካ ቀንድ በአለም ውስጥ ካሉት ማናቸው ሴኩሪቲ ዞን የበለጠ የሚሊቴሪ እንቅስቃሴዎች የሚታዩባት አካባቢ ሆናለች፡፡ (The most complex militarized security zone in the world) ጅቡቲ ውስጥ ቀድሞ የፈረንሳይ ጦር ሰፈር የነበረው ካምፕ ለሙኒየር(Camp Lemonnier) ታድሶ፣ ተስፋፍቶ የአሜሪካን ጦር ሰፈር ሆኗል፡፡ ጅቡቲ የአሜሪካን አፍሪካ ኮማንድ (Africom) አፍሪካ ውስጥ የቋሚና የተንቀሳቃሽ ኃይሎች መምሪያ ሆናለች፡፡(የአፍሪኮም ዋና መምሪያ የሚገኘው አውሮፓ ነው)፡፡ የፈረንሳይ ጦርም ቁጥሩ ጨምሮ ተጠናክሮ ጅቡቲ ይገኛል፡፡ ቻይና ከአገሩ ውጪ ለመጀመሪያ ጊዜ የጦር ሰፈር በጅቡቲ አቋቁማለች፡፡ ሳውዲአረቢያም በኤርትራና በጅቡቲ የጦር ሰፈር እየመሰረተች ነው ይባላል፡፡ የዩናይትድ አረብ ኤሜሬት(UAE) በሶማሌ ላንድና አሰብ ላይ ጦር ሰፈር ከአቋቋሙ ሰንበት አለ፡፡ ጃፓን በበኩሏ በሚሊተሪ ኢንዱስትሪና ወታደራዊ እንቅስቃሴ ከሁለተኛ አለም ጦርነት በኋላ ራሷን አግልላ መኖሯ ይታወሳል፡፡ ዛሬ ጃፓን ጅቡቲ ላይ የጦር ሰፈር እየመሰረተች ነው፡፡ ሩሲያ በበኩሏ በሱዳን የጦር ሰፈር ለመመስረት በስምምነት ላይ ደርሳለች፡፡ ደቡብ ሱዳን በምዕራቡ የዓለም የጦር መሳሪያ ማዕቀብ ስለተደረገባት ከግብጽ ጋር አዲስ ሚሊተሪ ግንኙነት (Alliance) መሥርታለች፡፡
የአፍሪካ ቀንድ የብዙ ኃይሎች የጥቅም መናህሪያ እየሆነች በመጣች ቁጥር የነዚሁ ሀይሎች ተጽዕኖ የእያንዳንዱን ሀገር የፖለቲካ ሁኔታ የመንግስታት ፖሊሲና ሴኩሪቲ ይቀርፃል፡፡ የነዚህ ኃያላን ሀገሮች ብሔራዊ ጥቅም እርስ በእርስም ሆነ ከአፍሪካ ቀንድ መንግስታት ፖሊሲ ጋር የሚጋጭባቸው ብዙ ሁኔታዎችም አሉ፡፡ ኢትዮጵያን ነጥለን ስንመለከት ኢትዮጵያ ከእያንዳንዱ የአፍሪካ ቀንድ አገሮች ያላት ግንኙነትና ያላት ፖሊሲ እነዚሁ ሀያላን አገሮች ከሚያራምዱት አጀንዳ ጋር የሚጋጩበት ሁኔታዎች ብዙ አሉ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ሊፈጠር የሚችለው የፖለቲካ ቀውስ ሰላማዊ ሽግግር ውስጥ በአስቸኳይ ካልተገባ እንደ ሲሪያ፣ የመን፣ ኢራቅ፣ ሊቢያ፣ ሶማሊያ የራሷ ያልሆነ(PROXY) ጦርነትና፣ ትርምስ ውስጥ ልትገባ እንደምትችል በጣም ግልፅ ነው፡፡
በወያኔ ማበረታታት ያንሠራራው ቀድሞ “የምዕራብ ሶማሌ ነፃነት ግንባር” ተብሎ የሚታወቀው ንቅናቄ ዛሬ ደግሞ “የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ንቅናቄ” በቀይ ባሕር፣ በሱዳንና በግብፅ (ዓባይ) ካለው ሥጋት ጋር ተጣምሮ መታየት ያለበት ነው፡፡ ችግሩ የነበረ፣ ያለና በወያኔ ፖሊሲ እየተባባሰ የመጣ፣ የሀገሪቱን ሕልውና የሚፈታተን አደጋ ነው፡፡ ስለዚህም የኦጋዴን ሁኔታ ከመፈንዳቱ በፊት ሁሉም አውቆ ነቅቶ መጠበቅ አለበት፡፡
ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ ኢትዮጵያ ከጣሊያን ወረራ ነፃ ወጥታ ሕልውናዋን የተሟላ ለማድረግ ሦስት ዐበይት ሥራዎች መሠራት ነበረባቸው እነዚህም የንጉሠ ነገሥቱን ማዕካላዊ አገዛዝ ማጠናከር ኤርትራን ወደ ኢትዮጵያ ማስመለስ፣ በደቡብና በደቡብ ምሥራቅ እየተንከባለለ የመጣውን “ታላቋን ሶማሊያ” የመገንባት ፖሊሲና እንቅስቃሴ መቋቋም ነበሩ፡፡ እነዚህ ሦስት ሥጋቶች የኢትዮጵያን የመከላከያ ኃይል መስፋፋት አስገደዱ፡፡ ሌላውን ለጊዜው ትተን የሶማሊያን ሥጋት በአጭሩ እንመረምራለን፡፡
በኢጣሊያ ሶማሌ ላንድና በኢትዮጵያ በኩል የድንበር ጥያቄ የለም፡፡ እ.ኤ.አ በ1897 እና በ1908 ውል መሠረት ድንበሩ ተከልሏል፡፡ ጣሊያን በዚህ ውል ባለመደሰቷ ግን ኢትዮጵያን ለመውረር ሁልጊዜ ምክንያት ትፈልግ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው እ.ኤ.አ በ1934 የወልወል ግጭት የተደረገው ከ2ኛ ዓለም ጦርነት በኋላ የጣሊያን ሶማሌላንድ እንደገና በጣሊያን እጅ ወደቀች፡፡ ድንበሩ በሕግ የተከለለ ቢሆንም ምልክቶች ስላልተደረጉበት በየጊዜው በጣሊያንና በኢትዮጵያ መንግሥታት መካከል በኋላም ሶማሊያ ነፃ ከወጣችበር ጊዜ ጀምሮ በሶማሌ መንግሥትና በኢትየጵያ መንግሥት መካከል ለነበረው የማያቋርጥ ግጭት ምክንያት ሆኗል፡፡
ከእንግሊዝ ሶማሌላንድ ጋር ያለው ድንበር በሕግ የተከለለ ምልክትም የተደረገበት ስለሆነ በዚያ አቅጣጫ የድንበር ጥያቄ አልነበረም፡፡ ይህም ሆኖ እንግሊዞች እ.ኤ.አ በ1946 የጠነሰሱት ታሏቋ ሶማሊያን የመገንባት ዓላማ በሶማሊያ መንግሥት ዋና የውጭ ፖሊሲና ሕዝቡም እንደ ሃይማኖት ይዞት የሚገባ እምነት ሆኖ ይሰበክ ጀመር፡፡ ስለዚህም ሶማሊያ ነፃ ስትወጣ የተመሰረተው መንግሥት ይህንኑ ዓላማ የሕገ-መንግሥቱ ዋና አንቀጽ አድርጎ አወጀ፡፡ በዚህም መሠረት አምስቱን የሶማሌ ሕዝብ የሰፈረባቸውን ቦታዎች (ጅቡቲ፣ ኦጋዴን፣ ሰሜን ኬንያ(NFD)፣ የእንግሊዝን ሶማሌላንድና የጣሊያንን ሶማሌንድ) አንድ ለማድረግ ትግሉ ተጀመረ፡፡ ለእዚህም ዓላማ እንዲያመች በደቡብ ኢትዮጵያ “የኦሮሞ ነፃ አውጪ” ግንባር፣ በደቡብ ምሥራቅ የምዕራብ ሶማሌ ንቅናቄ፣ በባሌ በኩል በዋቆ ጉቱ የሚመራ ንቅናቄ ተደራጅቶ ከኤርትራ ነፃ አውጪ ድርጅቶች ጋር ግንባር በመፍጠር በኢትዮጵያ ውስጥ ሽብር መፍጠር ተጀመረ፡፡ ሽብሩ እየተስፋፋ በሄደ ቁጥር የኢትዮጵያ ወታደራዊ ድርጅት እያደገ እየተጠናከረ፣ በቁጥርም፣ በሥልጠናና በመሣሪያ ዓይነት ዘመናዊ እየሆነ መጣ፡፡ በ1984 ነሐሴ ወር የምዕራብ ሶማሌ ንቅናቄ በኦጋዴን ነፃ አውጪ ግንባር(ONLF)ተተካ፡፡
የሶማሌ መንግሥትና የኦጋዴን ጥያቄ
ሶማሊያ ነፃ ከወጣችበት ጊዜ ጀምሮ በሕገ መንግሥቷ የተንፀባረቀው(አንቀጽ 6) ታላቋ ሶማሊያን የመመሥረት ዓላማ በእያንዳንዱ አብዛኛው የሶማሌ ኤሊት ስነ ልቦና ውስጥ የተተከለ ሕልም ነው፡፡ ምንም እንኳን እ.ኤ.አ. በ2012 ዓ.ም. የወጣው አዲሱ ሕገ መንግሥት ይህንን አንቀፅ ባይጨምርም የሶማሊያ ባንዲራ አሁንም ያው ነው፡፡ ባንዲራው አስምት ጫፍ ያሉት ኮከብ ሲሆን እነዚህም የሚያመለክቱት አምስቱ የሶማሌ ታናጋሪ ሕዝቦች የሚኖሩበትን ነው፡፡ የኦጋዴን ሶማሌዎች ግን ኢትዮጵያዊነታቸውን አጥብቀው የያዙ፣ ከሌሎች ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ኢትዮጵያውያን ጋር ሆነው ለኢትዮጵያ አንድነት ብዙ የተዋጉ፣ የታገሉ መስዋዕትነት የከፈሉ ከኢትዮጵያ ያልተለዩ ታሪክ ያላቸው ሕዝቦች ናቸው፡፡ የሶማሌ መንግሥት በአጐራባች አገሮች የሚኖሩ ሶማሌ ተናጋሪዎችን በሞላ በአንድ ሶማሊያ ውስጥ ማጠቃለል ያላት ፖሊሲ በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ውዝግብ ፈጥፎአል፡፡ እነዚሁ አምስት ቦታዎች የሰሜን ዲስትሪክት ፍሮንቲየር(Northern District Frontire) በሰሜን ምሥራቅ ኬንያ፣ ጅቡቲ፣ የእንግሊዝ ሶማሌ ላንድ፣(Somali land) ኦጋዴንና፣ አሁን ሶማሊያ የሚባለው አገር ቀድሞ የጣሊያን ሶማሌ ላንድ ተብሎ የሚታወቀው ነው፡፡ የሶማሌ መንግሥታት ይህን ሕልማቸውን በሕግ ዕውን ለማድረግ ስለማይችሉ የነፃነት ነቅናቂዎች በማቋቋም የኢትዮጵያንም፣ የኬንያንም ፀጥታ ሲያናጉ ኖረዋል፡፡ ጅቡቲ ነፃ በወጣችበት ጊዜ በ1979 እ.አ.አ. ኢትዮጵያና ሶማሊያ ከባድ የዲፕሎማቲክ ጦርነት ላይ ነበሩ፡፡ ኢትዮጵያም ሶማሊያም በጅቡቲ ላይ የይገባኛል መብቶቻቸውን አቅርበው በመጨረሻ ላይ አስታራቂ ሆኖ የተገኘው ነፃ የሆነች ጅቡቲን መመሥረት ሆኖ ተገኘ፡፡ ሆኖም ሶማሊያ የመጀመሪያውን የግልፅ ጦርነት የከፈተችው በኢትዮጵያ ላይ ነው፡፡ ይህም የሆነው በዚያድ ባሬ አገዛዝ ነበር፡፡ በ1968 ዓ.ም. በምዕራብ ሶማሊያ የነፃነት ንቅናቄ(WSLF) ስም ሶማሊያ ኢትዮጵያን ወረረች፡፡ የምዕራብ ሶማሊያ የነፃነት ግንባርና ተቀጥያው የኦጋዴን ብሔራዊ የነፃነት ግንባር(ONLF) ያቋቋመው የሶማሌ መንግሥት ነው፡፡ የሁለቱም ዓላማ አንድ ነው፡፡ የዚያድ ባሬ መንግሥት በምዕራብ ሶማሌ ነፃ አውጪ ግንባርና በኦጋዴን ነፃ አውጪ ግንባር ስም ኦጋዴንን ወሮ ሠራዊቱ ጅጅጋን ይዞ፣ ድሬዳዋና ሐረር በቀረበበት ጊዜ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ፈተና ላይ ወድቃ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ባወጀው የሶሻሊስት ፖሊሲ ምክንያቶች ጦር መሣሪያ ከአሜሪካ ማምጣት በማቆሙና፣ የሶቭየት ዩኒየን ከሶማሌ ጋር ቀደም ያለ ግንኙነት ስለነበረው መሣሪያ በሚፈለገው ሁኔታ መገኘት ባለመቻሉ የሶማሊያ ጦር ገፍቶ ኢትዮጵያ ውስጥ መግባት ቻለ፡፡ በወቅቱ እኔ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቋሚ ተጠሪ( ምክትል ሚኒስትር) ነበርኩኝ፡፡ ፈታኝና አሳፋሪ ጊዜ ነበር::
ስለሆነም ከኢትዮጵያ ደሀ ገበሬ የተውጣጣ 300,000 ሺህ ሚሊሺያ የእናት ኢትዮጵያን ጦር በአጭር ጊዜ ጦር ተቀብሎ፣ ሰልጥኖ፣ በጀግንነት ተዋግቶ በከፈለው መስዋትነት የኢትዮጵያን ዳር ድንበር ማስከበር ችሏል፡፡ የሶማሌ መንግሥት ምኞት የኢትዮጵያን መንግሥት አንበርክኮ ኦጋዴንን አሳልፎ ከመስጠት ሌላ አማራጭ እንዳይኖረው ማድረግ ነበር፡፡(ለዝርዝሩ Red Tear መጽሐፍን አንብቡ) በምዕራብ ሶማሌ የነጻነት ግንባርና በኦጋዴን ብሔራዊ ነፃነት ግንባር የተሰነዘረው ጥቃትና የተቃጣው ድፍረት የኢትዮጵያን ሠራዊት ብቻ ሳይሆን ጠቅላላ ሕዝቡ ታላቅ መስዋዕትነት ክፍሏል፡፡ ቦታው ላይ ስለነበርኩኝ የመስዋዕትነቱን መጠን በቅርብ ሆኜ መስክሬአለሁኝ፡፡ (የመስዋዕትነቱን መጠን ክህደት በደም መሬት የሚለው መጽሐፌን አንብቡ)፡፡
ለዚህም ድፍረትና ለዚሁም ከፍተኛ መስዋዕት አፍራሽ ሚና የተጫወተው አንዱ ኢሀፓ ነው፡፡ ኢሀፓ ኦጋዴንን አስመልክቶ የኦጋዴን ሕዝብ ከፈለገ ከሶማሊያ ጋር ይቀላቀል የሚል አቋም ይዞ ቆይቶአል፡፡ የኢሀፓ አላማ ከሶማሊያ መንግስት መሣሪያና ገንዘብ ለማግኘት ነበር፡፡ ለዚህ ሲል የኢትዮጵያን አንደነት አደጋ ላይ እንዲወድቅ አደረገ::ከሶማሊያ መንግስትም ያገኝው እርዳታ እምብዛም አልነበረም፡፡ ቀጥሎም በእያንዳንዱ ቀበሮ ጉድጓድ በመቶ፣ በሻምበል፣ በሻለቃ፣ በብርጌድ በተሰለፈው ሠራዊቱ ውስጥ ሠርጐ በመግባት ሠራዊቱ እንዲያፈገፍግ በኢሀፓ ስም ጥሪ በማስተላለፍ ወረቀት በመበተን የአምስተኛ ረድፍ ሚና በመጫወት ሠራዊቱ እንዲሸሽና በሺህ የሚቆጠሩ ደግሞ እንዲያልቁ ምክንያት ሆኖአል:: ምንም እንኳን ይህ አቋም የሁሉም የኢሀፓ አመራርም ሆነ ወይም ተራ አባላት እንዳልሆነ ቢገመትም ይህ ድርጊት ለመፈፅሙ ምንም ጥርጥር የለም:: የኢሀፓ መሪዎች ከመቋዲሾ መንግሥት ጋር በቅርብ እንደሚሠሩና ከዚያም አዲስ አበባ ካለው ኤምባሲ ጋር ቅርብ ግንኙነት እንደነበራቸውም የሶማሌ መንግሥት ኤምባሲ እንዲዘጋ ሲደረግ ከተገኙት ዶክመንቶች ለመረዳት ተችሏል፡፡ እኔ በዚያን ጊዜ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ምክትል ስለነበርኩኝ ማስረጃዎቹን አይቻለሁኝ፡፡
የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጪ ግንባር ከምዕራብ ሶማሌ ነፃ አውጪ ግንባር አብሮ ሲሠራ የነበረ፣ የአሁኑ መሪዎችም ከዚሁ ድርጅት የተመለመሉ መሆናቸውንና የምዕራብ ሶማሊያ ነፃ አውጪ ግንባር በዚያድ ባሬ ትዕዛዝ እንዲጠፋ ሲደረግ በእሱ እግር የተተኩ፣ የሞቃዲሾ ተወላጆች ለመሆናቸው ሰነዶች ያመለክታሉ፡፡ የኦጋዴን ነፃ አውጪ ግንባር ፕሮግራም ግልፅ ነው፡፡
• ኦጋዴን የኢትዮጵያ አካል አልነበረችም አትሆንም
• የኦጋዴን ሕዝብ ትግል የነፃነት ትግል ነው
የሚል ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ እነዚህ አባባሎች ሽፋን ተብለው የራስ ዕድል በራስ መወሰን እስከ መገንጠል ድረስ ይላሉ፡፡ የኤርትራም ንቅናቄ ሲጀመር እንደዚሁ ነበር የሚለው፡፡
የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጭ ግንባር ኢሀፓን ተጠቅሞ ኢትዮጵያን እንደወረረ እየታወቀ ወያኔ ከእዚሁ ተገንጣይ ቡድን ጋር ግንባር ለመፍጠር መሞከሩ ወያኔ ቅድሚያ የሚሰጠው ለኢትዮጵያ አንድነት ሳይሆን ሥልጣኑን ለማጠናከርና ሕዝቡን በዘር ከፋፍሎ ለመግዛት መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ የኦሮሞ ነፃ አውጪ ድርጅትና፣ ኦብነግ ዋና መሥሪያ ቤታቸውን ኤርትራ(አስመራ) ማድረጋቸውም ብዙ ጥያቄ አስነስቶአል፡፡ “የኢትዮጵያን አንድነት እናከብራለን፣ ኢትዮጵያን ለማፈራረስ ወይንም ለመገነጣጠል ከሚዋጉ ሀይሎች ጋር አንተባበርም” እያሉ እነዚሁን ድርጅቶች ማስተናገድ የኤርትራን መንግሥት የዚህ እኩይ ዓላማ ተባባሪ ያደርገዋል፡፡
ዛሬ የሶማሌ መንግሥት ከኦጋዴን ነፃ አውጪ ድርጅት ጋር ስምምነት የለውም፡፡ ድርጅቱ ከአልሻባብ ጋር ግንኙነት አለው ተብሎ ስለሚጠረጠር፣ በፕሮግራሙ ላይም የሚንፀባረቀው የመገንጠል አላማ ከኢትዮጵያ ጋር ያጋጨናል ብሎ ስለሚያስብ የዲፕሎማቲክ አቋም ይዞአል፡፡ ሆኖም ይህ አቋም በኦጋዴን ያለውን አቋም አያጠፋውም፡፡ ቀድሞውንም የሶማሌን የመስፋፋት ፖሊሲና የኦጋዴንን መገንጠል የሚደግፉት ISIS ኢስላሚክ ኮርት (Islamic court) ሥልጣን ቢይዙ የኦጋዴንን መገንጠል በይፋ ደግፈው ኢትዮጵያ ላይ ውጊያ እንደሚከፍቱ ጥርጥር አይኖርም፡፡ ይህ የሶማሌ መንግሥትም አሁን ካለበት ሁኔታ ወጥቶ ፀጥታ የሰፊነበት ጠንካራ መንግሥት ቢቋቋም ኦብነግን በቀጥታ ሊደግፍ ይችላል፡፡ በእዚህም ምክንያት ነው የዚያድ ባሬ መንግሥት እንዲፈርስ ተቀዋሚ ድርጅቶች ተጠናክረው እንዲታገሉ የኢትዮጵያ መንግሥት የታገለው፡፡
የ1969 ዓ.ም. ጦርነት ካለቀ በሁዋላ በመንግሥት በኩል የተወሰነው ውሳኔ የሶማሌ መንግሥት ኢትዮጵያ ላይ ሌላ ጦርነት ማወጅ የማይችል ደካማ መንግስት ማድረግ ተቀዳሚ የኢትዮጵያ የሶማሌ ፖሊሲ ሆኖ በተግባር ዋለ፡፡በዚሁም መሠረት የተወሳሰበና ረቂቅ የሆነ ፕሮጀክት ተጀምሮ የሶማሌ ብሔራዊ ንቅናቄ(SNM) የሚለውን የተቃዋሚ ድርጅት በማስታጠቅና በማደራጀት ዚያድ ባሬን ከሥልጣን ማስወገድ ተቻለ፡፡ የሶማሌንም ብሔርተኝነትና የታላቋን ሶማሊያን ሕልም መግታትም ስኬታማ ሆነ፡፡ ሶማሊያ ነፃነት ከወጣች በኋላ ኢትዮጵያ በምሥራቅ ግንባር ሰላም አግኝታ አታውቅም፡፡ ዚያድ ባሬ ከወጣ በኋላ በጐሣ የተከፋፈለ ሕዝብ እርስ በእርሱ እንደሚጋጭ የተጠበቀ ነበር፡፡ ከ1969 ዓ.ም. እስከ 1983 ዓ.ም. ድረስ ኢትዮጵያ በሶማሊያ ያላት ፖሊሲ ከመቻቻል (Continment) ወደ መንግሥትን ማናጋት(Destablization) ተለወጠ፡፡ ተቃዋሚው ድርጅት(SNM) አባላት አብዛኛው ከይሳቅ ጐሣ የተመለመሉ ሲሆን የዚያድ ባሬ መንግሥት ግን ከመሪሀን ነበር፡፡ ዚያድ ባሬ በአባቱ ከመሪሀን ይሁን እንጂ በእናቱ ኦጋዴን ነው፡፡ የሶማሌ ብሔራዊ ንቅናቄ (SNM) እየጠነከረ ሲሄድ የዚያድ ባሬም ሥልጣን እየተዳከመ ሄደ፡፡ ወደ መጨረሻው በጐሣው ጥላ ሥር ገብቶ የጐሣ ጦርነት አስጀመረ፡፡ የኢትዮጵያ የውጭ ፖሊሲም ይህንን አፋፋመው፡፡ በአንድ ቋንቋ፣ በአንድ ሀይማኖት፣ በአንድ ባህል የተመሠረተችዉ ሶማሊያ በጐሣ ጦርነት ውስጥ ተነከረች፡፡ ዚያድ ባሬ በለኮሰው እሳት ተለበለበ፡፡ አገሪቱም እስከዛሬ ድረስ ሰላም አጥታ ትኖራለች፡፡ ኢትየጵያን ማሸበሩ ግን አላቋረጠም፡፡ ምንም እንኳን ቀጥታ የመንግሥት ድጋፍ ባይኖረውም ከሕዝቡ በሚያገኘው ድጋፍ ሌሎችም የኢትዮጵያን መዳከም ከሚሹ ድጋፍ እያገኘ ኦብነግ ሽብሩን ቀጥሎአል፡፡
በዚያም ሆነ በዚህ ኦብነግ በኢትዮጵያዊነቱ የማያምን በደቡብ ሱዳንና በኤርትራ እንደታየው ኢትየጵያን የሚያደማ፣ የሚያዳክም ረዥም ትግል አካሂደን መጨረሻ ላይ ነፃነት እንጐናፀፋለን ብለው ያምናሉ፡፡ በሁለተኛም ደረጃ ከሱማሊያ ጋር እንቀላቀላለን ብሎ የተነሳ ስለሆነ ከዚህ ድርጅት ጋር መሥራት፣ መተባበር ወይንም ድርጅቱ ሀሳቡን ለውጦአል ብሎ ማመን ራስን ማታለል ነው፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ጽሑፋቸው፣ መግለጫቸው የሚያሳየው የተነሱበትን ያልለወጡ መሆናቸውን ነው፡፡ አንደ ቀድሞው ኢሀፓ የትሮይ ፊረስ በመሆን ያልተጠበቀ ችግር ውስጥ ገብቶ የኦብነግ ጉዳይ ፈፃሚ ላለመሆን መጠንቀቅ ያሻል፡፡ በኦጋዴን መሬት በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ አባቶቻች፣ እናቶቻችንና ወገኖቻችን ደም የተለወሰ የከበረ መሬት ነው፡፡ ከእንግዲህ ወዲያ አባቶቻችን፣ እናቶቻችን፣ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን በደማቸው በአጥንታቸው በሕይወታቸው በከፈሉት መስዋዕትነት አንዳችም እፍኝ አፈር ለሌላ አትሰጥም፡፡
ኢብራሂም አብደላ የተባለ የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጪ ግንባር ተጠሪ በአንድ ወቅት ሲናገር የሚከተለውን አለ፡፡
“ድርጅታችን የሚከተሉት አላማዎች አሉት ኦጋዴንን ከኢትዮጵያ ቅኝ አገዛዝ ነፃ ማውጣት ነፃ መንግሥት መመሥረትና የሕዝቡን ፍላጐትና ምኞት ዕውን ማድረግ ከሶማሊያ ሕዝብ ጋር ያለውን የወንድማማችነትና የትግል አንድነት እንዲጠናከር በሌላ በኩል ደግሞ ከአረቡ ዓለም ጋር ያለንን ግንኙነት በጋራ ጥቅሞች ላይ ተመርኩዞ የሚያድግበትን መንገድ መሻት ነው፡፡” (የአፍሪካ ቀንድ የመጀመሪያው ዓመት ቁጥር 7-1985).
ከፍተኛ የኦብነግ ጦር መኮንን ደግሞ አብዲራሺድ ሀልጋም እንዲህ ይላል
“The ONLF objectives are to attain full independence from Ethiopian government and to have a country with no interference from other nations. We are fighters fighting for independence”
ሌላው ደግሞ ራሱን አድሚራል የሚለው የኦማር ኦስማን የኦብነግ ጦር መሪ እንዲህ ይላል
“Ogaden are Arab Muslim people, we have common enemy with Alshabab”
“የኦጋዴን ህዝብ አረብና እስላም ህዝብ ነው:: እኛና አልሻባብ የጋራ ጠላት አለን”
ደግሞ የኦብነግ መሥራችና የውጭ ጉዳይ ኃላፊ እንዲህ ይላል;
“When you are fighting for your rights time is not an issue. My father was fighting for our rights and my children will fight for our rights. We want right to self determination including even leaving the country Free choice is not secession”.
“ስለመብታችን ስንታገል ጊዜ ዋና ነገር አይደለም:: አባቴ ስለ መብታችን ይዋጋ ነበር:፡ ልጆቼ ደግሞ ለዚሁ መብታቸው ይዋጋሉ፣ የራሳችንን እድል ራሳችን መወሰን አለብን:: መገንጠልንም ጨምሮ፣ ይህ መገንጠል አይደለም፣ ነጻ ምርጫ ነው”
የኤርትራን የነፃነት ቀን በዓል ምክንያት በማድረግ ኦብነግ ለኤርትራ መንግሥት የላከው መልዕክት እንዲህ ይላል:
“From the trenches of battle fileds of Ogaden, where we struggle for our day of independence from Ethiopia, Convey the best wishes for a prosperous and peacefull future (ONLF 2002)”.
“አንድ ቀን ከኢትዮጵያ አገዛዝ ነፃ ለመውጣት ከሚታገልባቸው የኦጋዴን የጦር ምሽጐች የድርጅታችንን የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጪ ግንባር የነፃነት ተዋጊዎች የበለፀገና ሰላማዊ የወደፊት ጊዜ ይመኝላችሁዋል” ኦብነግ 2002).
ኦብነግ ለዜና ማሠራጫ በ June 2015, ባወጣው መግለጫ:
“We killed many colonial troops following heavey fighting”
“ብዙ የቀኝ ገዢ ወታደሮችን በጦርነቱ ላይ ገድለናል”.
ይህ እስከ ቅርብ ጊዜ ሲነገር ሲፃፍ የቆየ የኦብነግ አቋም ሕዝብ ሳያውቀው ተለውጦ እንደሆነ ሚስጢሩን የምታውቁ አስተምሩን፡፡ “ኦጋዴን ዛሬም በታሪክ የኢትዮጵያ አካልነች፡፡ የኦጋዴን ህዝባዊ የነፃነት ግንባር በኦጋዴን ህዝብ ኢትዮትያዊነት ያምናል፡፡ የኦጋዴን ህዝቡም አገሩም አረብ አይደለም፡፡ የኦብነግ የትግል ዓላማ እንደማናቸው ኢትዮጵያዊ ተቃዋሚ ሀይሎች ወያኔን አስወግዶ የሚሞክራሲያዊ የሁሉም ህዝብ መብት በእኩልነት የሚጠበቅበት ሥርዓት እንዲፈጠር ነው” የሚል የቀድሞውን አቋም የሚሽር መግለጫ ካወጣ ሁላችንንም ያስደስተናል፡፡ የኦሮሞ ነፃ አውጪ ድርጅትም(OLF) ከዚሁ አካል ጋር ተባባሪ ሆኖ የሚሠራ የመገንጠል አቋሙን ያለወጠ እስከሆነ ድረስ ከማናቸውም ኢትዮጵያዊ ከሆነ ተሳትፎ ተገልሎ መወገዝ ያለበት ድርጅት ነው፡፡
ኦብነግን በተመለከተ ተጨማሪ ንባብ ከእዚህ የሚከተሉትን ተመልከቱ፡፡
http://unpo.org/article/20258
http://www.aljazeera.com/programmes/talktojazeera/2016/05/ethnic-somali-abdirahman-mahdi-onlf-ethiopia-boiling-160507083254836.htm
https://www.voanews.com/a/somalia-onlf-member-transferred-ethiopia-terrorist-threat/4017898.html
http://www.aberfoylesecurity.com/?p=2469
http://hornaffairs.com/2014/10/22/un-report-eritrea-onlf-shabaab-terror-nexus/
They are giving their own blood for the sake of their Independence so that they can hold their next or future celebrations in their homeland to honour all who have fallen in fight for the return of the Republic of Ogaden without fear of execution, arrest or humiliation. Ogaden, which is politically and economically marginalized was handed over to Ethiopia in 1954 by the Great Britain.
Sep 08, 2015
Ogaden: ONLF’s 31st Anniversary
http://unpo.org/article/18537
5) The ONLF adopts the long-term popular war and independent frontal resistance, supported by the mobilization of the people and their initiatives as the foundation of it’s struggle. 6) The program of the ONLF shall be carried out by a combatant cadre carefully selected among its ranks with special emphasis on their political …
Ogaden National Liberation Front (ONLF ) – Political Objectives
http://onlf.org/?page_id=14
Declaration Forming The ONLF. We the people of Ogaden. Recognizing that our country has been colonized against our will and without our consent by Ethiopia. Noting the misrepresentation of our struggle as a border conflict between Somalia and Ethiopia. Having witnessed the indiscriminate murder of our families and …
POLITICAL PROGRAMME – ONLF
http://onlf.org/?page_id=16

ጉዳያችን GUDAYACHN
 www.gudayachn.com

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።