ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages

Tuesday, February 19, 2019

በፈድራሊዝም ስርዓት የኢትዮጵያ ሕዝብም አይደራደርም።የኢትዮጵያ ሕዝብም ለተጨማሪ ድል ይሰራል።ፈድራሊዝም ግን የጎሳ ፈድራሊዝም ብቻ አይደለም።

ጉዳያችን / Gudayachn
የካቲት 12/2011 ዓም (ፈብሯሪ 19/2019 ዓም)
===================
አቶ ለማ በሊቀመንበርነት የሚመሩት የኦዲፓ (የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ) ባወጣው መግለጫ ''
‘’በፌዴራሊዝም ስርዓት አንደራደርም፤ለተጨማሪ ድል እንሰራለን’’ በሚል ርዕስ ባወጣው መግለጫ ዙርያ በርካታ አስተያየቶች እየተሰጡ ነው።እዚህ ላይ ላለፉት ዘጠኝ ወራት በዶ/ር ዓብይ እና አቶ ለማ የተንፀባረቀው ኢትዮጵያዊነት ቀዳሚ አጀንዳ ጋር በተቃርኖ የሚያነሱት ወገኖች መሰረታዊ የመረዳት ችግር የሚመስለኝ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ከገባበት ጣምራ ተግዳሮት አንፃር ካለመመልከት የሚመነጭ ነው።

ኦዲፓ  በአንድ በኩል በህወሓት በሌላ በኩል በፅንፈኛ የኦሮሞ ብሄርተኛ ፖለቲከኞች በራሱ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ የሚነዛ ፕሮፓጋንዳ አለ።ይሄውም ኦዲፓ ወደ ኢትዮጵያዊ ፖለቲካ (ኢትዮጵያዊ ፖለቲካ ፈድራልዝምን ይቃረናል የሚል የተሳሳተ አስተሳሰብ እንዳለ ሆኖ) አዘንብሎ የነበረውን የፈድራሊዝም ስርዓት ሊያናጋ ነው በእዚህም የኦሮሞ ሕዝብ የነበረ መብቱን ሊያስወስድ ነው የሚል ፕሮፓጋንዳ ነው።ይህ ፕሮፓጋንዳ ጠለቅ ብሎ ለማያውቀው የከተማ ወጣት እና የገጠር ሕዝብ ደግሞ ይብሱን ተጣሞ ይቀርባል።እነ ለማ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ባለፈው ሳምንት በወለጋ ጉብኝት ወቅትም ይህንን ፕሮፓጋንዳ ምን ያህል እንደሄደ ተረድተውታል።ስለሆነም ከሁለቱም አካላት የሚነሳውን ፕሮፓጋንዳ ለመመከት በፈድራሊዝም አንደራደርም የሚል መግለጫ ማውጣት አለባቸው። ስለሆነም የዛሬው ‘’በፌዴራሊዝም ስርዓት አንደራደርም፤ለተጨማሪ ድል እንሰራለን’’ የሚል መግለጫ አውጥቷል። ይህ የማብረጃ ፕሮፓጋንዳ ካልሆነ በቀር ለራሱ ለኦዲፓ የጎሳ ፈድራሊዝም የትም ያህል እንደማያስኬደው በግልጥ የሚያውቀው ጉዳይ ነው።ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ኢትዮጵያዊነትን ባያነሱ ኖሮ ዘጠኝ ወሮች በስልጣን ላይ ባገኙት አመኔታ ደረጃ ስልጣን ላይ ሊቆዩ አይችሉም ነበር።

ይህ ማለት ግን ኦዲፓ ውስጥ ፅንፍ የያዙ አስተሳሰቦች በኦዲፓ ላይ የሉም ማለት አይቻልም።በሁሉም መስክ ኦዲፓን ለመውረር የማይደረግ እንቅስቃሴ የለም።ይህ ፅንፍ የያዘ አካሄድ ግን ወደ ጠብ የሚያመራ መሆኑን የማይረዳ የፖለቲካው ዓለም ተዋናይ የለም።ሆኖ ግን ካለው ተቃርኖ ብዛት አንፃር ጉዳዮችን እያረገቡ መሄድ እንደወቅታዊ ስልት የመያዝ አዝማምያ ይታያል።

መጪዋ ኢትዮጵያ አሃዳዊ መንግስት ይኖራታል ብሎ የሚያስብ ኢትዮጵያዊ ብዙ አይመስለኝም።የፈድራል አስተዳደር አስፈላጊ መሆኑን ከሳይንሱም ከሕዝቡ ነባራዊ እና ወቅታዊ ሁኔታም መረዳት ይቻላል።ይህ ማለት ግን የጎሳ ፈድራሊዝም ብቸኛ አማራጭ ነው ብሎ መሄድ ከግንብ ጋር መልሶ የመላተም ያህል አደጋ ነው። ላለፉት 28 ዓመታት የደረሰው የአንድ ጎሳ አስተዳደር በሌላ ጎሳ አስተዳደር የመተካት ያህል ፌዝ ነው የሚሆነው። 

ኦዲፓ ‘’በፌዴራሊዝም ስርዓት አንደራደርም፤ለተጨማሪ ድል እንሰራለን’’ እንዳለው ሁሉ የኢትዮጵያ ህዝብም በፌድራል ስርዓት አይደራደርም! ለተጨማሪ ድልም ይሰራል።ሕዝብ ፈድራሊዝም ሲል ግን በጎሳ ፌድራሊዝም ብቻ ቆርቧል ማለት አይደለም።የጎሳ ፌድራሊዝም ኢትዮጵያን ሊበታትናት ደርሶ ኢትዮጵያዊነት ሱሴ ነው በሚል አጭር ቃል  ነው ሕዝብ መልሶ የተሰባሰበው። የጎሳ ፌድራሊዝም አደገኛ መርዝ ነው። ሳይንስም የጎሳ ፈድራሊዝም የበታኝነት ሚናውን ያረጋገጠው ነው።በመሰረቱ የፈድራሊዝም መሰረታዊ ፅንሰ ሐሳብ የማዕከላዊ መንግስት ፈላጭ ቆራጭነት ሚና ተገድቦ ሕዝብ በዜግነቱ ኮርቶ እና መብቱ ተከብሮለት አካባቢውን እራሱ እንዲያስተዳድር የሚያደርግ የአስተዳደር ስርዓት ነው። 

''Federalism, essentially a defense mechanism against a central government that is too powerful and oppressive, is based on common interests.'' The Dangers of Ethnic Federalism,Berouk Mesfin,Institute for Security Study, Addis Ababa, 2008.

''ፌድራሊዝም በመሰረቱ የማዕከላዊ መንግስትን ከልክ ያለፈ ኃይል እና የመጨቆን አሰራር ተከላክሎ በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ አስተዳደር ነው'' 

ስለሆነም አንዳንዶች የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፀረ ፈድራሊዝም አለመሆኑን ማስረዳት ከሁሉም ወገን ይጠበቃል።ፈድራሊዝም ግን የጎሳ ፈድራሊዝም መሆን እንደሌለበት ማስመር ደግሞ ተገቢ ነው።የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ መንግስት በተግባር ላለፉት ዘጠኝ ወራት የኢትዮጵያዊ አጀንዳ ቀዳሚ መሆን እንዳለበት በወሰዳቸው እርምጃዎችም ሆነ  በሄደባቸው መንገዶች ሁሉ መረዳት ይቻላል።የመንግስት ድርጅቶች ላይ እየታዩ ያሉት የአደረጃጀት ለውጦች እና የምክር ቤቱ የመሰረታቸው የወሰን ጉዳይ የሚመልከተው ኮሚሽንም ሆነ ለማኅበራዊ አካላት የሚሰጠው ትኩረት አበረታች ናቸው።በተግባር ኢትዮጵያዊ መንገዶች ያየንበት አስተዳደር በሁለት አጣብቂኝ ውስጥ ገብቶ ያወጣው መግለጫ ፕሮፓጋንዳ ተግባር ቢሆንም ፌድራሊዝም ስትል ምን አይነት ፈድራሊዝም? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው።መግለጫው የወጣው ከፅንፈኛ አካላት ለተሰነዘረ ፕሮፓጋንዳ የተሰጠ ምላሽ ለመሆኑ ማስረጃው ደግሞ የመግለጫውን ቃል በቃል ማንበብ ይጠቅማል። እንዲህ ይነበባል - 
''አሁን ያለው መንግስት የፌዴራል ስርዓቱን ለማፍረስ እንሚሰራ በማስመሰል ህዝቡ ሌላ ድል ማግኘቱ ቀርቶ ቀድሞ ያገኘውንም ሊያጣ እንደሆነ በመናገር ህዝቦች ለውጡንና የለውጡን መሪዎች እንዲጠራጠሩ ሰፊ ፕሮፓጋንዳ እየተነዛ ነው።'' ይላል የኦዲፓ መግለጫ።

ሮፓጋንዳ እየነዙ ስለሆነ እኔ ፈድራሊዝም ላፈርስ አልመጣሁም  ነው የመልእክቱ ጭብጥ። ከእዚህ በተለየ የኦዲፓ መግለጫ የተለየ መስመር የያዘ አድርጎ መተርጎም ምንም ፋይዳ የለውም።ከእዚህ የተለየ የኦሮሞ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ እንዲል አይጠበቅም።ፈድራሊዝም ሲል ጎሳን መሰረት ያደረገ አለመሆኑን ተመራምሮ እንደደረሰበትም ቆየት ብሎ እንዲነግረን አባላቱን እንዲያስረዳ ግን የሁሉም ምኞት ነው።ከእዚህ ውጭ  በአንድ አዳር አቶ ለማ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የተቀየሩ አስመስሎ ማውራት አይጠቅም።ስልጣን ሕዝብ እጅ እንዳለ ለማሳየት ዛሬም መደራጀት ሃሳብን በነፃ መግለጥ እና ፅንፈኛ አስተሳሰቦችን ማጋለጥ ላይ ማተኮር ይገባል።

ስለሆነም ለፌድራሊዝም ዘብ የሚቆመው የኢትዮጵያ ህዝብም ነው።ለጎሳ ፌድራሊዝም ሳይሆን ለሕዝቡ አመቺ የሆነ መልክዓ ምድራዊ፣ታሪካዊ እና  ለሕዝቡ አስተዳደራዊ መንገድ አመቺነትን ያገናዘበ ፌድራሊዝም  ሕዝብ ዘብ ይቆማል። 


ጉዳያችን GUDAYACHN 
 www.gudayachn.com

No comments:

ሐያ ገዳማት የሚገኙበት በግሪክ የሚገኘው የአቶስ ተራራ ገዳማውያን አኗኗር (ቪድዮ)

ገዳሙ ከሰርብያ፣ሮማንያ፣ቡልጋርያና ሩስያ የመጡ ዓለምን የናቁ መነኮሳት ገድመውበታል።